ኦብነግ የኢትዮጵያን መንግሥት በጭፍጨፋ ከሰሰ

በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ውስጥ የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይል ጥቃት አድርሰው ሃምሣ አንድ ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ስሞታ አሰምቷል፡፡

ONLF_logo3

ሶማሌ ክልል ውስጥ ጃማ ዱባድ በሚባል መንደር ሰሞኑን የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይሎች በመንደርተኞች ላይ ጥቃት አድርሰው 51 ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር – ኦብነግ ከስሷል፡፡

“የመንግሥቱ የፀጥታ ኃይሎች በሌሎች አካባቢዎችም በተለያዩ የቅርብ ጊዜያት ከሦስት መቶ በላይ ሰላማዊ ሰዎችን ገድለዋል” ያሉት የኦብነግ ቃል አቀባይ አቶ ሃሰን አብዱላሂ ድርጅታቸው ጉዳዩን ለዓለምአቀፍ ተቋማት ለማድረስ ማስረጃዎችን እያጠናቀረ መሆኑን ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ የቪኦኤ የሶማሊኛ ዝግጅት ክፍል ወደ አካባቢው ደውሎ ያነጋገራቸው የጎሣ መሪ ወታደሮቹ ስድስት ሕፃናትና ሴቶችንም ጨምሮ ሃያ አራት ሰዎችን መግደላቸውን አመልክተዋል፡፡ ሌሎች ምንጮች ደግሞ ወታደሮቹ መንደሪቱን ማቃጠላቸውንና አሥር ሰዎች የገበቡበት እንደማይታወቅ ጠቁመዋል፡፡ ስለጉዳዩ ከክልሉም ሆነ ከፌደራል መንግሥቱ የተሰጠ መግለጫ የለም፡፡

ምንጭ፡- VOA Amharic service

Leave a comment