Daily Archives: October 23rd, 2016

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ የሰላማዊ ዜጎች እስር ቢኖርም፤ በአንዳንድ ቦታዎች አሁንም ተቃውሞች እንደቀጠሉ ናቸው

(አዲስ ሚዲያ) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓም ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በጅምላ እየታሰሩ ነው፡፡ በተለይ በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እስሩ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ሳምንት ከአዲስ አበባ በደቡብ ምዕራብ በቅርብ ርቀት የምትገኘው ሰበታ ከተማ ብቻ ከ አንድ ሺህ በላይ ተጠርጣሪ ናቸው ያላቸውን ነዋሪዎችን ማሰሩን ራሱ መንግሥት ያስታወቀ ሲሆን፤ በሌሎችም የኦሮሚያ እና አማራ ክልል ከተሞችና ወረዳዎችም በተመሳሳይ መልኩ እስሩ መቀጠሉን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

በአማራ ክልል ሰሜን እና ጎንደር ዞን መንግሥት የነዋሪዎቹን ትጥቅ ለማስፈታት ወደ ወረዳዎች እና ገጠር ቀበሌዎች የፀጥታ ኃይሉን ቢያሰማራም ከህዝቡ የአፀፋ ርምጃ በመወሰዱ በርካታ ወታደሮችና ሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ተገድለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ህዝባዊ ተቃውሞው ከተጀመረበት ቀን አንስቶ የመንግሥት የፀረ አገዛዝና ጭቆና ተቃውሞ እንደቀጠለ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

በአፋር ክልልም እንዲሁ የሰላማዊ ዜጎች እስሩ የቀጠለ ሲሆን፤ ባለፈው ሳምንት ጥቅምት 6 ቀን 2009 ዓ.ም. በአፋርኛ በማዜም የምትታወቀው ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌን ጨምሮ አስር ሰላማዊ ዜጎች በአሳይታ ከተማ መታሰራቸው ታውቋል፡፡

ethiopian-singer-mefera-mohmmed

ድምፃዊት መፈራ መሐመድ ላሌ

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ትግበራ ላይ መንግሥት እንደ ኢሳት፣ ኦ.ኤም.ኤን. የመሳሰሉ መገናኛ ብዙኃን መከታተልና መረጃ መለዋወ ላይ መመሪያው እገዳ ጥሏል፡፡ በተጨማሪ ያልተፈቀደ ሰልፍና የአደባባይ ስብሰባ፣ ለህዝብ አገልግሎት አለመስጠት፣ በትምህርትና በስፖርት ማዘውተሪያ አድማ ማድረግ በክልከላው ተካተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ትግበራባለመቀበል በድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ከቤት ያለመውጣት አድማ ማድረጋቸውን ቀጥለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከመውጣቱ አስቀድሞ በኢትዮጵያ የመንግሥትን በደልና ብልሹ አሰራር ለመቃወምና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ  ቀድሞም ቢሆን ለዓመታት ፈፅሞ የተከለከሉ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለአንድ ዓመት ያህል ያለማቋረጥ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የቀጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማርገብ በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ የሆነ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማውጣት ኢንተርኔትን በተለይም ማኀበራዊ ሚዲያ፣ በውጭ ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ተዘጋጅተው ለህዝቡ አማራጭ የመረጃ ምንጭ በመሆን እያገለገሉ ያሉ እንደ ኢሳት፣ ኦ ኤም ኤን ያሉ መገናኛ ብዙኃን እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ሚዲያ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዳይሰራጩ ከማፈን በተጨማሪ ህዝቡም መረጃ መለዋወጥና መስማትም እንደሌለበት በአዋጁ መከልከሉ ይታወሳል፡፡

አዋጁን ተከትሎ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተለይ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ ክልል ኮንሶ ፣ ጋሞ ጎዳ ዞን፣ በአፋርና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል (ኦጋዴን) የተለያዩ ከተሞችና ወረዳዎች በመዘዋወር ድንገት ቤት ለቤት ፍተሻ በማድረግ የተለያዩ የወርቅ ጌጣጌጦችን፣ ገንዘብ፣ ተንቀሳቃሽ ስልክ ከመወስድ በተጨማሪ ጠርጥረንሃል ያሉትን ሰው ያለምንም ፍርድ ቤት ማዘዣ እየደበደቡ በመውሰድ ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሚያስሯቸው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ምክንያት ከወትሮ በተለየ መልኩ በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢ ነዋሪው በፍርሃት ድባብ ውስጥ እንደሚገኙ በመጠቆም በማኀበራዊና ንግድ እንቅስቃሴዎች ላይም አለመረጋጋቶች እንደሚስተዋሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

መንግሥትበአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መሰረት አፈና እና ቁጥጥሩን አጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ዋነኞቹ የህዝባዊ ተቃውሞ አስተባባሪዎች መካከል የአማራ ተጋድሎና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች ከመንግሥት ርምጃ ጋር ተመጣጣኝ ሊሆን የሚችል አዳዲስ የትግል ስልቶችንም በቅርቡ ሊጀምሩ እንደሚችሉ ተነግሯል፡፡ በተለይ በውጭ የሚኖሩ የመንግሥትን አገዛዝ የሚቃወሙ ኢትዮጵያውያን በስልጣን ላይ ካለው ገዥው ስርዓት ለውጥ በኋላ በኢትዮጵያ ሊመሰረት ስለሚገባው ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ትግበራ በቪዥን ኢትዮጵያ እና በኦሮሞ ማኀበረሰብዓለም አቀፍ የህግ ባለሙያዎች ማኀበር አስተባባሪነት ከወዲሁ በሰሜን አሜሪካ ዋሸንግተን ዲሲ  እበእንግሊዝ ለንደን ምክክር መጀመራቸው ታውቋል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዜጎቹ የጉዞ ክልከላ አወጣ

የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለይ በአማራና ኦሮምያ ክልሎች ሁከቱ አሁንም ቀጥሎ በመቶዎች ለሚቆጠሩ መሞት፥ በሺዎች ለሚገመቱ ሌሎች መታሠር፥ መጎዳትና በንብረት ላይ ከፍተኛ ውድመት እየደረሰ ባለበት ሁኔታ፥ ዜጎቹ አስፈላጊ ካልሆነ በቀር ወደ ኢትዮጵያ እንዳይሄዱ አስጠንቅቋል።

usa

የኢትዮጵያ መንግሥት ከመስከረም 28 ቀን 2009 ዓም ጀምሮ ተግባራዊ የሆነውን የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ ደንግጓል። ጥቅምት 4 በወጣ መመሪያም ግለሰቦች መገናኛ ብዙሃን ሲከታተሉ፥ በስበሰባዎች ሲካፈሉ፥ ከባዕዳን መንግሥታት ወይም ድርጅቶች ጋር ሲገናኙ እንዲሁም የሰዓት እላፊውን ሲተላለፉ ቢገኙ ያለፍርድ ቤት ማዘዣ ተይዘው ሊታሠሩ እንደሚችሉ ያብራራል። መመሪያው በተጨማሪም፥ የዩናይትድ ስቴትስና የሌሎች ባዕዳን ሃገሮች ዲፕሎማቶች፥ ከኢትዮጵያ መንግሥት አስቀድመው ፈቃድ ሳያገኙ ከአዲስ አበባ ከተማ 40 ኪሎ ሜትር ውጪ እንዳይጓዙ ይከለክላል። ይህም ኤምባሲው ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ዜጎችን የመርዳት አቅሙን ክፉኛ ይጎዳል ብሏል።

የኢንተርኔትና የቴሌፎን አገልግሎቶች አልፎ አልፎ በመላ ሀገሪቱ ውስጥ ውሱን በመደረጋቸው ወይም ሙሉ በሙሉ ስለሚቋረጡ፥ አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ዜጎቹን የመርዳት አቅሙን ያግዳል ሲልም አብራርቷል።

በኢትዮጵያ የሚገኙ አሜሪካውያን አማራጭ የመገናኛ ዘዴ እቅዶችን እንዲያዘጋጁ፥ ቤተሰቦቻቸውና ወዳጆቻቸውም አሁን በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ ይህን እንደሚመስል እንዲያሳውቁም የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው በዚሁ ማስጠንቀቂያው ጠይቋል።

አሜሪካውያን ሰልፎች ከሚካሄዱባቸውና ሕዝብ በብዛት ከሚሰበሰብባቸው አካባቢዎች ራሣቸውን እንዲያርቁ፥ የሚሄዱባቸውን አካባቢዎች በደንብ እንዲቃኙና ደህንነታቸው የሚጠበቅበት መሆኑን እንዲያረጋግጡም መክሯል። መንግሥት ሰልፎቹ ሰላማዊ ቢሆኑ እንኳ ምላሹ በኃይል ሊሰጥና ጥይት ሊተኩስ እንደሚችልም አስታውሱ ብሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የዩናይትድ ስቴትስ ዜጎች ስለ ደህንነታቸው በንቃት እንዲከታተሉና አመጻ ሊፈጠርባቸው ከሚችሉ አካባቢዎች መውጣት በሚፈልጉበት ጊዜ ካደገኛ ሥፍራ ፈጥኖ መውጪያ ዘዴዎቻቸውን አስቀድመው ማዘጋጀት እንዳለባቸውም አሳስቧል።

የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመጨረሻም፥ የአሜሪካ መንግሥት ሠራተኞች ኢትዮጵያ ውስጥ ኦሮሚያን፥ አማራን፥ ሱማሌን፥ ጋምቤላን፥ ኢትዮጵያና ኬንያ የሚዋሰኑበትን ድንበር አካባቢ ማለትም ደቡብ ግዛቱን እንዲሁም ኢትዮጵያና ኤርትራ የሚዋሰኑበትን ሰሜኑን ግዛት ጨምሮ ወደ በርካታ አካባቢዎች እንዳይሄዱ አስጠንቅቋል። ወደተጠቀሱት አካባቢዎች ከሥራ ጋር የተያያዙ ጉዞዎች ፍቃድ የሚያገኙትም በሁኔታዎች መሠረት ይሆናል ብሏል። ወደ አዲስ አበባ በሚደረጉ ጉዞዎችና ከተማ ውስጥ በሚካሄዱ እንቅስቃሴዎች ላይ ግን ምንም እገዳ የለም ካለ በኋላ፥ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የመገናኛ ሁኔታ አስተማማኝ ባለመሆኑ ግን፥ አሜሪካውያን ዜጎች በጉዞ መርሃ-ግብሩ ማለትም በ STEP አማካይነት መመዝገብን ጨምሮ፥ የሞባይል ቴሌፎን ቁጥሮቻቸውን፥ አዲስ አበባ በሚገኘው ኤምባሲ በማስመዝገብ የደህንነት መረጃዎችን በጹሑፍ መልዕክት ሊያገኙ ይችላሉ ብሏል ሲል የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡

በተመሳሳይም የእስራኤል መንግሥትም ዜጎቿ ወደ ኢትዮጵያ የሚያደረጉት ጉዞ ላይ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማስጠንቀቋ ታውቋል፡፡

%d bloggers like this: