Monthly Archives: September, 2016

የኮንሶ ብሔረሰብ የዞን ምሥረታ ጥያቄ ከሕግ አንጻር ሲፈተሸ

woubeshet-mulat

ውብሸት ሙላት

ኮንሶ፣ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል በሰገን ሕዝቦች ዞን ውስጥ የምትገኝ ወረዳ ናት፡፡ ቀደም ሲል ግን ልዩ ወረዳ ነበረች፡፡ ኮንሶ አስተዳደር እርከን ብቻ ብቻ አይደለችም፤ብሔረሰብም ጭምር እንጂ! የሰገን ሕዝቦች ዞን ደግሞ በፊት የኮንሶ፣ የደራሼ፣ የአማሮ እና የቡርጂ ልዮ ወረዳዎች የነበሩትን በማጠቃለል የተመሠረተ ነው፡፡

በደቡብ ክልል ሕገ-መንግሥት መሠረት ልዩ ወረዳ ከዞን ጋር አቻ ሥልጣን አለው፡፡ ተጠሪነቱም ቀጥታ ለክልሉ ነው፡፡ ልዩ ወረዳ፣ ብዙ ጊዜ በአንድ ብሔር ብቻ ስለሚመሠረት የአንድ ብሔር ብቻ አባላት ያሉበት የወረዳ ምክር ቤት ይኖረዋል፡፡ የራሱ የልዩ ወረዳው የሥራ ቋንቋ እንዲኖረው መወሰን ይችላል፡፡ በዞን ደረጃ የሚኖሩትን መንግሥታዊ መዋቅሮችን በወረዳው በማቋቋም በርካታ የብሔረሰቡ ተወላጆች የሥራ ዕድል እንዲኖራቸው ያስችላል፡፡

መደበኛ ዞኖች ሕግ አውጪ የላቸውም፡፡ የዞን ሥራ አስፈጻሚዎችም የሚሾሙት በቀጥታ በክልሉ ሥራ አስፈጻሚ በመሆኑ የክልል ውክልና እንጂ በምርጫ የተገኘ ሥልጣን አይደለም፡፡ ወረዳዎችም ቢሆኑ ለአስተዳደር ቅልጥፍና፣ ድጋፍና ክትትል ሲባል በተጨማሪነት ለዞን ተጠሪነት ያለባቸው ቢሆንም ይህ ሁኔታ የመነጨው የክልሉ አስፈጻሚ አካላት በሚሰጠው ውክልና ላይ ተመሥርቶ እንጂ ሕገ-መንግሥታዊ መነሻ የለውም፡፡ ለዚያም ነው የወረዳ አስተዳዳሪዎችና ከንቲባዎች በዞን አስተዳዳሪዎች የማይሾሙትም ሆነ የማይወርዱት፡፡

በልዩ ዞኖች ግን የብሔረሰብ ምክር ቤት ስላላቸው፣ የዳኝነት መዋቅርና ሹመት በክልል ደረጃ ቢከናወንም እንኳን ከዞኑ የሚጠቆሙትና የሚሾሙት ዳኞች ላይ አስተያየት የመስጠት መብት አላቸው፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ፣ የዞንነት ጥያቄ በማንሳት ተቃውሞ ከጀመረ አንድ ዓመት አለፈው፡፡ ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ ቀላል የማይባል የሰው ሕይወት ጠፍቷል፡፡ የክልሉ የኮሚኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ሓላፊ ለአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ በቅርቡ በተናገሩት መረጃ እንኳን ከ1500 ቤቶች በላይ ተቃጥለዋል፡፡ ከአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን እንደሚሰማው የዞንነት ጥያቄው ካልተሳካ ወደ ኦሮሚያ ክልል የመካለል ጥያቄንም በአማራጭነት ሕዝቡ እያነሳ ነው፡፡

ይህ ጽሑፍ ዞን የሚመሠረትበትን ሕጋዊ አሠራር ይፈትሻል፡፡ የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን መብት ጋር የሚኖረውን ግንኙት በማየት የኮንሶ ብሔረሰብ ጥያቄ ከክልሉ እና ከፌደራሉ ሕገ-መንግሥት እንዲሁም ከሌሎች አግባብነት ካላቸው ሕጎች አንጻር ዳሰሳ ያደርጋል፡፡ እግረ-መንገዱንም አንድ ወረዳ ወይንም ሌላ አስተዳደረዊ መዋቅር ከአንድ ክልል ወደ ሌላ ክልል መጠቃለል የሚችልበትን ሕገ መንግሥታዊ ሁኔታም ካለ ምጥን ፍተሻ ያደርጋል፡፡

ኮንሶ ከሌሎች ዞኖች ጋር በሕዝብ ብዛት ስትነጻጸር፤

የኮንሶን የዞን ምሥረታ ጥያቄን በአግባቡ ለመረዳት በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት ዞኖች ጋር፣ በ1999 ዓ.ም. የተደረገውን የሕዝብና ቤት ቆጠራን መሠረት በማድረግ እናነጻጽራለን፡፡ በዚህ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት መሠረት የኮንሶ ልዩ ወረዳ ወደ 235 ሺህ የሚጠጋ ሕዝብ ነበረው፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የነበረው የወረዳው ሕዝብ ብዛት ማለት ነው፡፡ ከወረዳው ውጭም የሚኖሩትን ጨምሮ፣ የኮንሶ ብሔረሰብ ብዛት ከ250 ሺህ በላይ ነው፡፡ ዞን ለመመሥረት በአንድ አካባቢ መኖርን ስለሚጠይቅ፣ ለዞን ምሥረታ ጥያቄው ተገቢው ቁጥር መኖር ቅድመ-ሁኔታ ነው ማለት ይቻላል፡፡

የኮንሶ ወረዳ ሕዝብ፣ ከሀረሪ ክልል ሕዝብ ይበልጣል፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የክልሉ ሕዝብ ብዛት፣ ገና 200 ሺህ እንኳን አልሞላም ነበር፡፡ የኮንሶ ወረዳ በሕዝብ ብዛት፣ ከትግራይ ክልል የመቀሌ ልዩ ዞንን፣ ከአፋር ክልል የዞን ሦስት እና አምስትን፣ ከአማራ እና ከኦሮሚያ ክልሎች ከዞኖች ጋር አቻ ከሆኑት የባሕር ዳር፣ የደሴ፣ የጎንደር፣ የአዳማ እና የጅማ ከተሞችን፣ ከቤኒሻንጉል-ጉሙዝ፣ የካማሼ ዞንን፣ የጋምቤላ የሁሉንም ዞኖችን፣ እንዲሁም ከራሱ ከደቡብ ክልል ደግሞ የሸካ ዞንን በሕዝብ ብዛት ይበልጣል፡፡ የጋምቤላ ክልል ከኮንሶ ሕዝብ ወደ 80 ሺህ በሚጠጋ ቁጥር ብቻ ነው የሚበልጠው፡፡

konso-karat-town

ራስን በራስ የማስተዳደር መብት፤

የኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 89(1)፣ መንግሥት በዴሞክራሲያዊ መርሆች ላይ በመመሥረት ሕዝቡ በሁሉም ደረጃዎች ራሱን በራሱ የሚያስተዳደርበትን ሁኔታ ማመቻቸት ያለበትን ስለመሆኑ የፖለቲካዊ ፖሊሲው በጥቅሉ አስቀምጦታል ፡፡ ማንኛውም የብሔርነት፣ የብሔረሰብነት ወይንም ደግሞ የሕዝብነት ዕውቅና ያገኘ ማኅበረሰብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱን ተግባራዊ የሚያደርግበትን አስተዳደራዊ መዋቅር የመመሥረት ገደብ የሌለው ሕገ-መንግሥታዊ መብት እንዳለው የፌደራሉም የክልሎችም ሕገ መንግሥት አንቀጽ 39 (3) ላይ ተደንግጓል፡፡

ራስን የማስተዳደር ሙሉ መብት በክልል ላይ ብቻ የተንጠለጠለ አይደለም፡፡ ይህ መብት ውጤታማ እንዲሆን ያልተማከለ አስተዳደር ተግባራዊ መሆን አለበት፡፡ ያልተማከለ አስተዳደርን እንደ አንድ ፕሮግራም ብናየው ብዙ የሚያካትታቸው ነጥቦች አሉት፡፡ ከሚያካትታቸው ነጥቦች ውስጥ በባሕርያቸው የአካባቢው መንግሥት ሥልጣንና ሥራ የሆኑትን ለአካባቢው መተው፣ እንዲሁም ባሕርያቸው አካባቢያዊ ባይሆኑም እንኳን እነሱ ቢፈጽሟቸው የሚሻል ከሆነም ለአካባቢው መንግሥት መተው አለባቸው፡፡

እንዲህ መሆኑ ከታመነበት ግጭትን ለመቀነስም ሆነ በልበ-ሙሉነት ለመሥራት ሲባል ሥልጣንና ተግባራቸው በግልጽ ተለይቶ መቀመጥን ይፈልጋል፡፡
የአካባቢ መንግሥታት (Local Government) የራሳቸውን ጉዳይ በራሳቸው የመጨረስ፣ ፖሊሲ የመንደፍ፣ ለፖሊሲያቸው የሕግ ማዕቀፍ የመስጠት የመጨረሻ የሥልጣን ባልተቤት መሆን ያሻቸዋል፡፡

አካባቢያዊ መንግሥታት፣ አስተዳደራዊ ተቋሞችን የማቋቋምና ለሥራ ምቹ በሚሆን መንገድ በነጻነት የማዋቀርና የሰው ሃይል የመቅጠርም የማባረርም ሥልጣንን ይይዛል፡፡ ስለሆነም አካባቢያዊ መንግሥታት ፖለቲካዊ፣ የገቢና ወጭ፣ እንዲሁም አስተዳደራዊ ሥልጣንን ያካትታል ማለት ነው፡፡ ይህ አሠራር የማእከላዊ መንግሥት ድጋፍና ቁጥጥር እንዲሁም በይነመንግሥታዊ ትብብርንም አያስቀርም፡፡

ፖለቲካዊ ራስ ገዝነት ባልተማከለ አስተዳደርም ይሁን ራስን በራስ በሚያስተዳድሩ ብሔሮች ዘንድ ቁልፍ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ ማእከላዊም ይሁን የክልል መንግሥታት ባሰኛቸው ጊዜ የሚያፈርሷቸው ሲመቻቸው ደግሞ የሚያቋቁሟቸው ልዩ ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ቀበሌዎች ሊኖሩ አይገባም፡፡ ቀጣይ መሆን አለባቸው፡፡ በመኖርና በመፍረስ በስጋት እየወላወሉ የሚኖሩ ተቋማት ሊሆኑ አይገባቸውም፡፡ ወይንም ደግሞ እንዴት እንደሚቋቋሙም ይሁን እንደሚፈርሱ ግልጽ ሕግ፣ሁሉም የተስማሙበት ኖሮ በዚያው መሠረት መፈጸም አለበት፡፡ የኮንሶ ነገርም፣ በአንድ ወቅት ልዩ ዞን የነበረች ሲሆን አሁን ግን መደበኛ ወረዳ ብቻ በመሆን በሰገን ሕዝቦች ሥር ትገኛለች፡፡

በሕገ-መንግሥቱ በአንቀጽ 50(4) ከተገለጸው አንጻር ቋሚነት አላቸው ማለት ቢቻልም በተግባር እንደታየው ግን፣ ከ1994 ዓ.ም. በፊት ይህ ዓይነት ሥልጣን የሌላቸው ሲሆን፣ በኋላ ደግሞ መለወጡ ብሎም በአንዳንድ ክልሎች ሥልጣናቸው በሕገ-መንግሥት ሳይሆን በአዋጅ መገለጹ ወይንም በግልጽ አለመቀመጡ አጠራጣሪ አስመስሎታል፡፡

በተጨማሪም እንዴት ወረዳዎች እንደሚመሠረቱና እንደሚታጠፉ፣ ድንበራቸው እንደሚካለልና እንደሚደካ አለመገለጹ፤ መሥፈርቶቹን አንዳንድ ክልሎች በአዋጅ (ለምሳሌ ደቡብና ኦሮሚያ) ሌሎቹ ደግሞ ለአስፈጻሚው አካል መተው (ለምሳሌ ቤኒሻንጉል ጉሙዝና አማራ) ጉራማይሌ አድርገውታል፡፡ በመሆኑም ለልዩ ዞኖችም ይሁን ወረዳዎች የተሻለ ዋስትና መስጠት ያስፈልጋል፡፡ የዚህ ዋስትና አለመኖር ነው ኮንሶን በአንድ ወቅት ልዩ ወረዳ፣ በሌላ ጊዜ መደበኛ ወረዳ በመሆን ምንአልባትም ለተለያዩ ተቃውሞዎች መነሻ የሆነው፡፡

የልዩ ዞንና ወረዳ ምሥረታ ሂደት፤

በሽግግሩ ዘመን ሥራ ላይ በነበረው አዋጅ ቁጥር 7/1984 መሠረት ወረዳን ጨምሮ ወደ ላይ ያሉ መስተዳድሮችን ማቋቋም የማይችሉት በግልጽ ተዘርዝረው ነበር፡፡ በሕገ-መንግሥቱ ይህ ገደብ ተነስቷል፡፡ በተጨማሪም ክልል መመሥረት እንደመገንጠል ሁሉ ገደብ የለውም፡፡ ለነገሩ ክልል መመሥረትም ጉዳዩ ከክልል መሆኑ ነው እንጂ ያው መገንጠል ነው፡፡ ገደብ አለመኖሩን ለማመልከት “በማናቸውም ጊዜ” የሚል ቃል ተጠቅሟል፡፡

በሕገ-መንግሥቱ እንዲህ ዓይነቱ “መድልኦ” ተወግዷል ብንልም እንኳን በጋምቤላ አኙዋ፣ ኑዌርና መዠንግር ልዩ ዞን ሊያቋቁሙ እንደሚችሉ ሲገለጽ ኡፖና ኮሞ አይችሉም በማለት የክልሉ ሕገ-መንግሥት ገልጿል፡፡ በዚህም ከብሔረሰቦች መርጦ ለዞንና ለወረዳ አለ ማለት ነው፡፡ ቁጥራቸው አናሳ (በ1999ኙ ዓ.ም. በተደረገው ቆጠራ በክልሉ ውስጥ የሚኖሩት ማኦ 64፣ ኡፖ ደግሞ 990) መሆናቸው አንድ ነገር ሆኖ በሕገ-መንግሥት መከልከል ደግሞ ሌላ ነገር ነው፡፡

የአሁኑ ደቡብ ክልል ከመመሥረቱ በፊት አራት ክልሎች ነበሩ፡፡ አንድ ክልል ከሆኑ በኋላ ዞኖችና ወረዳዎች በተለያዩ ጊዜያት እንደገና ተዋቅረዋል፡፡ ለምሳሌ ሰሜን ኦሞ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ፣ዳውሮ) ወደ ሦስት ብሔረሰብ ዞኖች ተከፋፈለ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ እና ዳውሮ ) ተብለው፡፡ እንዲሁም ሁለት ልዩ ወረዳዎች ተጨመሩ ባስኬቶና ኮንታ፡፡ ሌላ ካፋ-ሸካ የሚል እንደ አንድ ልዩ ዞን ቢቋቋሙም ውሎ አድሮ ካፋ እና ሸካ ልዮ ዞኖች ተብለው ራሳቸውን ቻሉ፡፡ ቤንችና ማጂ ይባሉ የነበሩት ሁለት ዞኖች፣ ኋላ ላይ ቤንች-ማጂ ተብለው አንድ ዞን ሆኑ፡፡ ስልጤ ዞንም ከጉራጌ ተነጥሎ ራሱን ቻለ፡፡ ቀደም ሲል ስምንት ልዩ ወረዳዎች የነበሩ ሲሆን አሁን አራቱ (ኮንሶ፣ደራሼ፣ ቡርጂ እና አማሮ) በአንድነት ሰገን ዞንን መሥርተዋል፡፡

ቋንቋ፣ማንነት፣ የአሰፋፈር ሁኔታና ፍቃደኝነት ላይ መሠረት በማድረግ የሚቋቋሙ አካባቢያዊ መስተዳድሮች (local territorial autonomy) ጉዳትም እንዳላቸው የሚገልጹ አሉ፡፡ ከእነዚህም ጉዳቶች መካከል ክፍፍልን ያባብሳል፣ ክልሎች በአብዝኃኛው ወጥ የሆነ አንድ ብሔር ስለማይኖርባቸው አሁንም ቢሆን በኢትዮጵያ የአናሳና የብዙኃንን ግንኙነት ማስቆም አያስችልም፤ በተጨማሪም አሁን ባለው ሁኔታ ዞኖችና ወረዳዎች ሲዋቀሩም ይሁን ሲዋሃዱ ወጥ የሆነ የታወቀ ሕገ-መንግሥታዊ መርሕ የለውም፤ እንደገዥው ፓርቲ የፖለቲካ ግምገማና ድምዳሜ የሚወሰን ነው፤ ዘፈቀዳዊም ነው የሚሉ ክሶች ይቀርባሉ፡፡

የዞንና ምሥረታ በደቡብ፤

ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ማንነታቸው ከታወቀ እንደቡድን ማንኛውንም አስተዳደራዊ እርከን የመመሥረት መብት አላቸው ብለናል፡፡ ከደቡብ ውጭ ያሉት ክልሎች፣ በውስጣቸው የሚገኙት ነባር ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ዝቅተኛ ስለሆነ፣ ወይ መሥርተዋል፤ አሊያም ትተዋቸዋል፡፡ መመሥረት ቢፈልጉ ደግሞ እንዴት ጥያቄያቸውን እንደሚያቀርቡ፣ ለማን እንደሚያቀርቡ፣ ምን ምን ሁኔታዎችን ማሟልት እንዳለባቸው ወዘተ የሚያሳይ ሕግ የላቸውም፡፡ ደቡብ ግን አለው፡፡

የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ስላለው፣ የዞንም ይሁን የወረዳ አመሠራረት ጥያቄ እንዴት መስተናገድ እንዳለበት፣ ይህንን ምክር ቤት ለማጠናከርና ሥልጣንና ተግባሩን ለመወሰን በወጣው አዋጅ ላይ ተገልጿል፡፡ ሥነ-ሥርዓቱ ከክልል ምስረታ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ልዩነቱ ጥያቄውን ያቀረበው በአስተዳደራዊ መዋቅር ተደግፎ ከሆነ (ለምሳሌ ልዩ ወረዳ የነበረው ልዩ ዞን መሆን ቢፈልግና ጥያቄው የቀረበው የወረዳው መስተዳደር ቢሆን) የመስተዳድሩ ምክር ቤት በሁለት ሦስተኛ ድምፅ ከደገፈው ወይንም ጥያቄውን ያቀረበው፤ ሕዝቡ ከሆነ (5% የሚሆነው ስምና ፊርማ አስፍሮ) ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ሲደግፈው እና የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ሲወስን ተፈጻሚ ይሆናል፡፡

በዚህ ሕግ መሠረት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ወስኖ እንኳን ምክር ቤቱ ተጨማሪ ማስረጃ የማሰባሰብ ሥልጣን ስላለው አሰባስቦ ከመረመረ በኋላ ነው ውሳኔውን የሚያሳውቀው፡፡ ውሳኔውን ያሳውቃል ማለት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ የወሰነውንም ሊሽረው ይችላል ማለት ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ አሠራር ወለፈንድ ይመስላል፡፡ ድምፅ ሳይሰጡ ቢሆን እንኳን ይሻላል፤ ድምፅ ሰጥተው ከጨረሱ በኋላ የሌሎች ብሔረሰቦች ተወካዮች የሕዝብን ውሳኔ ካላከበሩ የት ላይ ነው ታዲያ የራስን ዕድል በራስ መወሰኑ? ይሔው ሕግ ይሔንኑ ጉዳይ በሚደነግግበት ክፍሉ ስለየራስን ዕድል በራስ መወሰን ነው የሚያወራው፡፡ በራሳቸው የወሰኑት ከተሻረ የትኛው ዕድላቸው ላይ ወሰኑ?

ሌላው ይህ ሕግ በዝርዝር ባያብራራውም በውሳኔው መሠረት ለብቻቸው ተለይተው ራሳቸውን ማስተዳደር የሚጀምሩት ብሔረሰቦች ቀድሞ ከነበሩበት ዞን ወይንም ወረዳ ፍትሐዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል ሊያደርጉ እንደሚችሉ አስቀምጧል፡፡ ክልል ሲመሠርቱ ያልተቀመጠውን፣ በደቡብ ክልል ውስጥ ዞንና ወረዳ (ልዩም ይሁን አይሁን) ሲመሠርቱ የንብረት ክፍፍል እንዲደረግ ያስቀምጥና ስለተግባራዊነቱም የብሔረሰቦች ምክር ቤት እንደሚከታተል ገልጿል፡፡ ፌደሬሽን ምክር ቤት አዋጅ ወይንም የፌደራሉ ሕገ-መንግሥት ስለ ክልል ምሥረታ ያላስቀመጠውን በሥሩ ለሚገኙ መስተዳድሮች ማስቀመጡ ለፌደራሉም መንግሥት ትምህርት ነው፡፡

የክልሉ ብሔረሰቦች እና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች ሚና ሲገመገም፤

ከላይ በጥቅሉ ባስቀመጥነው መሠረት የኮንሶን ጉዳይ እንመልከተው፡፡ የኮንሶ ሕዝብ ከጠቅላላው አምስት ፐርሰንት ድጋፍ ካገኘ በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አማካይነት ሕዝበ-ውሳኔ ይካሄዳል፡፡ የልዩ ዞንነቱን ጥያቄ አብዝኃኛው ድምጽ ሰጪ ከደገፈው ውጤቱ ለክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ቀርቦ ከጸደቀ በኋላ የዞን ምሥረታው ተግባራዊ ይሆናል፡፡ ምክር ቤቱ፣ ስለ ድምጽ አሰጣጡ እና በአጠቃላይ ስለ ነበረው ሁኔታ እና ሂደት ካጣራ በኋላ ሊያጸድቅም ሊሽረውም ይችላል፡፡

ጥያቄው አዲስ ክልል የመመሥረት ቢሆን ኖሮ ግን፣ ጥያቄውን ያቀረበው ብሔረሰብ ምክር ቤት፣ለምሳሌ ሲዳማ ቢሆን የሲዳማ ምክር ቤት፣ በሁለት ሦስተኛ ድምጽ ድጋፍ ካገኘ ይሄንኑ ውሳኔ በጽሑፍ ለክልል ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ጥያቄው የቀረበለት የክልል ምክር ቤት ሕዝበ-ውሳኔ ከማዘጋጀት የዘለለ በሕግ የተቀመጠ የመከልከል ወይንም ሌላ ሥልጣን የለውም፡፡ ጥያቄውን ለማብረድ ፖለቲካዊ ሥራ ሊሰራ ይችል ይሆናል፡፡ ጥያቄው በደረሰው በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ድምፀ-ውሳኔ ማዘጋጀት አለበት፡፡

የኮንሶን በተመለከተ፣ የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድም ሙሉ በሙሉ ጥያቄውን ካልተቀበለ አሊያም ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ካላዘጋጀ ወይንም ደግሞ የሕዝበ-ውሳኔውን ውጤት ከሻረው ጉዳዩን በይግባኝ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ማምጣት ይቻላል፡፡ምክር ቤቱ ጥያቄውን በአወንታ ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ሊያዘጋጅ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች መኖራቸውን ስለማይታወቅ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ሊመጣ ይችላል ማለት ነው፡፡

የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አወቃቀሩ ልክ እንደ ፌደሬሽን ምክር ቤት በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ከእያንዳንዱ ብሔር አንድ አባል ያለበት፣ ነገር ግን ከአንድ ሚሊዮን በላይ ቁጥር ካለው ለእያንዳንዱ አንድ ሚሊዮን ሌላ ተጨማሪ አንድ አባል ለምክር ቤቱ ይጨመርለታል፡፡

አባላቱ የሚመረጡት የብሔረሰቡ ዞኖች ወይንም ወረዳዎች ምክር ቤት መካከል ሆኖ መሥተዳድር ከሌላቸው ግን በቀጥታ ከብሔረሰቡ ተመርጠው ይወከሉበታል፡፡ የፌደሬሽን ምክር ቤት ደግሞ ለክልል ምክር ቤት ከተመረጡ ተወካዮች ውስጥ በክልሉ አሸናፊ የሆነው የፖለቲካ ፓርቲ የፈለገውን ሰው ከምክር ቤቱ አባላት መርጦ ይልካል፡፡ ስለሆነም፣ የደቡብ ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት የሚኖረው የአባላት ብዛት እና ክልሉ በፌደሬሽን ምክር ቤት የሚኖረው ውክልና እኩል ነው፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ፣ ቢያንስ 65 አባላት በሚኖሩት የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድ ወኪል ይኖረዋል፡፡ በፌደሬሽን ምክር ቤትም እንዲሁ፡፡ ከሕገ መንግሥታዊነት እና ሕጋዊነት ይልቅ፣ ከሕገ መንግሥቱ ጋር አብሮ በማይሄደው ፓርቲያዊ የሆነው ዴሞክራሴያዊ ማእከላዊነት ላይ በመመርኮዝ ውሳኔዎች እንደሚሰጡ ስለሚታወቅ፣የብሔረሰቦቹ ምክር ቤት አባላትም ለተመረጡበት ፓርቲ መታመን ስለሚጠበቅባቸው በክልል እና በፌደሬሽን ምክር ቤቶች መካከል የተለያዩ ውሳኔዎችን መጠበቅ አይቻልም፡፡

የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ላይ የሚኖራቸው ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የበለጠ የሚከፋው ደግሞ እነዚህ የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልሎቹን ርዕሰ መስተዳደር ጨምሮ፣የፌደሬሽን ምክር ቤት አባል መሆናቸው ነው፡፡ ክልል ላይ ላደረሱት በደል አቤቱታ ሲቀርብባቸው፣ በፌደሬሽን ምክር ቤት በዳኝነት ይሰየማሉ፡፡

የፌደሬሽን ምክር ቤት ካሉት 153 አባላት ውስጥ፣ ከ65 የማያንሱ ከደቡብ ክልል የተወከሉ ናቸው፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የክልሉ አቋም ለኮንሶ የዞን ጥያቄን አለመቀበል ከሆነ፣ የፓርቲውን ጫና እና የተማከለ ውሳኔውን እንኳን ብንተወው፣ የፌደሬሽን ምክር ቤት ላይ አብላጫ ድምጽ ለማግኘት በጣት የሚቆጠሩ ደጋፊዎችን ማፍራት ብቻ ነው የሚጠበቅበት፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ ወደ ኦሮሚያ ክልል ለመጠቃለል …..

የፌደራሉ ሕገ መንግሥት እንዴት መገንጠል እንደሚቻል እንጂ ሌሎች አገራት ከኢትዮጵያ ጋር መዋሃድ ቢፈልጉ እንዴት ሊቀላቀሉ እንደሚችሉ የሚገልጽ ሥነ-ሥርዓት አላስቀመጠም፡፡ አንድ ክልል ከሌላ ክልል ጋር መዋሐድ ቢፈልግ ወይንም አንድ ብሔር ከአንድ ክልል ወጥቶ ወደ ሌላ ክልል መካለል ቢፈልግ፣ ይሄንን ማስተናገድ የሚችል ግልጽ የሆነ ሕግ የለንም፡፡ እንደ አዲስ ክልል መመሥረት ለሚፈልግ ሥርዓት አለው፡፡ ግንኙነቱም በተገንጣዩ እና በቀሪው ክልል መካከል ይሆናል፡፡ ወደሌላ ክልል መጠቃለል ከሆነ ግን የሌላ ክልል ተሳትፎን ይጠይቃል፡፡

የኮንሶ ሕዝብ በኦሮሚያ ክልል ከቦረና፣ሊበን ከሚባለው አካባቢ መጣን ብለው ስለሚያምኑ፣ የቋንቋው ቤተሰብም ኩሽቲክ በመሆኑ፣ ከኦሮሞ ሕዝብ ባህል ጋር የሚመሳሰሉ ልምዶች ስላላቸው ይመስላል ይህ ዓይነት አማራጭ ሊነሳ የቻለው፡፡ የሁለቱ ክልሎች ቅንነት እስካለ ድረስ የድንበር ግጭት ሊፈታ በሚችልበት መንገድ በስምምነት መጨረስ ይቻላል፡፡ በተጨማሪም፣ የድንበር ማካለል ጥያቄ በማንሳት በሕዝበ ውሳኔ መፍታት ይቻላል፡፡

ይህን ለማድረግ ግን፣በኮንሶ ጉዳይ፣የኦሮሚያ ክልል የድንበር ጥያቄ ማንሳት ወይንም የሕዝቡን ጥያቄ መቀበል አለበት፡፡ ከወልቃይት ጉዳይ የሚለየው የኮንሶ ሕዝብ የኦሮሞነት ጥያቄ አለማንሳቱ ነው፡፡ ሁለቱም ቢሆኑ የድንበር ማካለል ብቻ አይደሉም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄዎችም ሕጋዊ አሠራር የሚያስፈልጋቸው ይመስላል፡፡

ሲጠቃለል፣ ሁሉም ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በማናቸውም ጊዜ ክልል የመመሥረት ሕገ-መንግሥታዊ የሆነ መብት አላቸው፡፡ ነገር ግን ከሰማኒያ በላይ ክልል የማቋቋም አቅም አለን ወይ? እንኳን ክልልና ወረዳና ዞን መቋቋምም ከወጭ አንጻር ከባድ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ከ50 በላይ የሚሆኑት ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ከ100,000 በታች ሲሆኑ ሃያ አንዱ ደግሞ ከ10,000 በታች ናቸው፡፡ ለቀበሌና ለወረዳ የመሳሰሉት አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትንስ መቋቋም ይቻላልን? የበጀት፣ የሰው ኃይል እና የመሳሰሉትን ፍላጎቶች መሸፈን መቻሉ አጠራጣሪ ነው፡፡ይሁን እንጂ፣ መተግበር የማይቻል መብት ውሎ አድሮ ቅያሜ ማምጣቱ አይቀርም፡፡ የኮንሶም ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ እናም የአሰፋ አባተን ግጥም ልዋስና ልደምደም፡፡

“የማትበላ ወፍ ተይዛ በጭራ፣
ልቤን አደማችው ሞጭራ ሞጫጭራ፤”

እንዳለው የማይተገበር መብት አስቀምጦ የሰው ሕይወት እና ንብረት እንዲጠፋ ምክንያት ከመሆን እንደ አዋጅ ቁጥር 7/1984 በግልጽ የትኞቹ ብሔረሰቦች ምን ዓይነት መስተዳደር ማቋቋም እንደሚችሉ አስቀድሞ ሕገ መንግሥቱን በማሻሻል ማስቀመጥ፣ ወይንም ደግሞ መብቶቹን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ አንድ ጊዜ ልዩ ወረዳ፣ ሌላ ጊዜ እንደ ኮንሶ፣ ከሌሎች ጋር በመቀላቀል ዞን ማድረግ ግጭትን መጥራት ነው፡፡ ተመጣጣኝ የሕዝብ ቁጥር እያላቸው፣ አንዱን መርጦ ዞን እንዲኖረው ማድረግ ፍትሐዊ አይደለም፡፡

አልወድቅም ያለው ደመራ

 

Abel-Wabella

አቤል ዋበላ

ሁለት ተከታታይ ደመራዎችን ያበራኹት ቂሊንጦ ዞን አንድ ነበር፡፡ በእስር ቤት ሀይማኖታዊ እና ብሔራዊ በዓላት እንደሁኔታው እንደአቅሚቲ ይከበራሉ፡፡ ዛሬ በዚህች አጭር ማስታወሻ ላጫውታችኹ የወደድኩት በዚያ ካሳለፍኳቸው በዓላት አንዱ የሆነውን የ2007 ዓ.ም. የደመራ በዓል ነው፡፡

ቂሊንጦ ያለው እስረኛ በሙሉ ያልተፈረደበት የቀጠሮ እስረኛ ነው፡፡ ያው ሁሉም እንደሚያውቀው ፍርድ ቤቱ ማስረጃዎችን መርምሮ ውሳኔ እስኪሰጥ አመታት መፍጀቱ የተለመደ ነው፡፡ ስለዚህ በእስር ቤቱ አመታትን ያሳለፉ ሲኒየር የቀጠሮ እስረኞችን ማግኘት የተለመደ ነው፡፡ አምና ለበዓል የተደረገው ዘንዶሮ እንዳይቀርባቸው እስረኞቹ ኮሚቴ አቋቁመው ተፍ ተፍ ይላሉ፡፡ በመዋጮም በጨረታም ብር ይሰበስባሉ፡፡ ከውጭ ተገዝተው የሚመጡ ዕቃዎችን እንዲያስገቡ የማረሚያ ቤቱን ኃላፊዎች እንዲማልዱ ትልልቅ ሰዎች ተመልምለው ይላካሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ በሙስና የተከሰሱ ሰዎች በማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ዘንድ ተሰሚነት ስለሚኖራቸው የሚላኩት እነርሱ ናችው፡፡ እነርሱም ተስማምተው ደጅ ከጠኑ፣ ከቦጨቁትም በጥቂቱ ዘግነው ስለሚሰጡ በስኬት ይመለሳሉ፡፡

በዚያ አመት ማረሚያ ቤቱ ለደመራ ታስበው የተገዙ ችቦዎችን አላስገባም በማለቱ እስረኛው ሲያጉረመርም ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዱ እስረኛ እስር ቤት መሆኑን ይዘነጋዋል፡፡ እስኪ አላስገባም ይበሉና እንተያያለን በማለት ሲዝቱ ሳይ ግርም አለኝ፡፡ ጸብ ቢነሳ ወዴት መሮጥ እንዳለብኝ ማሰቤ አልቀረም፡፡ በዚያን ወቅት ከማዕከላዊ ከመጣኹ ገና ሁለት ወሬ ስለነበር የእስረኛውን ስነ ልቦና ስላልተረዳው አንድ ግርግር እንዳይፈጠር መስጋቴ አልቀረም፡፡ እየቆየው ስሄድ ባዶ ጉራ እንደሆነች ገባኝ፡፡

በኋላ ምልጃው ከውጭ የመጣውን ባያሰገባም የማረሚያ ቤቱ ውጨኛው ግቢው ውስጥ ከሚገኙ ዛፎች የሚነድ ነገር ተሰብስቦ ደመራው እንዲዘጋጅ የሚፈቅድ ይሁንታን አስገኘ፡፡ የተወሰኑ ልጆች ተመርጠው ከኛ ዞን ወጥተው የሚነድ ነገር ለመልቀም ከአጃቢ ፖሊስ ጋር ወደዋናው ጊቢ ወጡ፡፡

መስከረም ከክረምቱ ብዙም ያልተለየ ስለሆነ ብዙም ያልደረቀውን ማገዶ ይዘው መጡ፡፡ ከዚያ ወፈር ያለውን ስር የሌለው ልጅ-እግር ዛፍ መኸል አቁመው ደመራ የሚስል ነገር ሠሩልን፡፡ ቆፍረው ቢቀብሩትም አመሻሽ ደርሶ ሳንሎክሰው እንዳይወድቅ ስጋት ውስጥ ገባን፡፡

በአይነ ቁራኛ ሲጠበቅ ሰዓቱ ደረሰ፡፡ ከእስረኛው መካከል ካህናት እና ዲያቆናት አልታጡም፡፡ ለስርዓተ ጸሎቱም ደመራውንም ለመሎከስ ተዘጋጁ፡፡ ጸሎቱ አብቅቶ ደመራው ጋዝ ተርክፍክፎበት መንደድ ጀመረ፡፡ ወፍራሙም ዲያቆን ከበሮውን አንስቶ ይደቃው ጀመር፡፡

በደመራ ትውፊት ደመራው መሀል ከላይ የአደይ አበባ በመስቀል ቅርጽ የሚታሰርበት ያለው አውራ ነዶ ወዴት እንደሚወድቅ በጉጉት ይጠበቃል፡፡ ታዳሚው ወዴት እንደሚወድቅ ሳይመለከት አይበተንም፡፡ ከልጅነት ጀምሮ እንዳስተዋልኩት ደመራው ወዴትም ይውደቅ ወዴት አመቱ የደስታ ነው፤ አመቱ የሰላም እና የብልጽግና ነው፤ የሚል በጎ በጎ ምኞት ይሰነዘራል እንጂ ወደሰሜን ከወደቀ ሀዘን ወደደቡብ ከወደቀ ደስታ የሚል የተደነገገ አሉታዊ ትርጓሜውም፡፡ የኛም ደመራ ለዚህ ወግ በቅታ ወዴት እንደምትወድቅ መጠበቅ ጀመርን፡፡ እስረኛውም ወደመውጫው በር ወድቆለት አመቱ የፍቺ ዓመት ነው እያለ ለማሳለፍ ተዘጋጅቷል፡፡ የማረሚያ ቤቱ ፖሊሶችም ወዴት ይወደቅ ብቻ ቶሎ ይውደቅና ቆጥረውና ቆልፈውብን ለመሄድ ጓግተዋል፡፡

ቢጠበቅ ቢጠበቅ ወደታች በጥልቀት ይቅበሩት አልያም እንጨቱ እርጥብ ስለሆነ ብቻ ባልታወቀ ምክንያት ሳይወድቅ ቆየ፡፡ በዙሪያው ያለው ርብራብ ተቃጥሎ ወደአመድነት ተለውጧል፡፡ ከመሬት ትንሽ ከፍያለው ወደባቱ አከባቢ እሳት እንደበላው ያስታውቃል፡፡ ዲያቆኑም ደክሞት መዝሙር መምራቱን አቁሟል፤ ፖሊሶቹ እየተቁነጠነጡ ነው፤ ደመራው አልወደቀም፡፡ ሁሉም ሰው ግራ ገብቶት ትውፊቱን ላለመተው በግርምት ይተያያል፡፡

አንድ መላኩ የሚባል በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥሮ የገባ እስረኛ አለ፡፡ ፍርድ ቤቱ መታመሙን እርግጠኛ ባይሆንም የአእምሮ ህመምተኛ ሆኗል፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ኦብሰሲቭ ኮምፐልሲቭ ዲሶርደር እንዳለበት በግልጽ ያስታውቃል፡፡ ዝርዝሩን ለባለሙያዎች እንተወው፡፡ ቆሻሻ ሲያነሳ እና ሲጥል ነው የሚውለው፡፡ ሰው ሰለማይተናኮል እስረኛው ሁሉ ወዳጁ ነው፡፡ የተደራጀ ነገር ባያወራም ከመታሰሩ በፊት ኮሚክ ነገር እንደነበር ያስታውቃል፡፡ አንዳንዴ ሲለው እንግሊዘኛ ይሞካክራል ይሄን ጊዜ እስረኛው “ፓ! መሌ እኮ የተማረ ነው” ብሎ ያደንቀዋል:: ብቻ ምን አለፋቹኽ መሌ ራሱ ተረኩ ብዙ ነው፡፡

የመሌን ታሪክ መጥቀሴ አለነገር አይደለም፡፡ በዚያ ቀን እስረኛው እና ፖሊሱ ተፋጥጦ ትውፊት ላለማፍረስ የደመራውን በራሱ መውደቅ ሲጠባበቅ የመሌን ትኩረት ይስባል፡፡ መዝሙር የለ፤ እንቅስቃሴ የለ ፡፡ የሚስቅ የሚጫወት ሰውም አይታይም፡፡ ሰው ሁሉ ያን በእሳት የተበላ እንጨት በጉጉት ይመለከታል፡፡ መሌ ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው? ቀጥ ብሎ ሄደና ደመራውን አንዴ በእርግጫ ሲለው በአፍጢሙ ድፍት አለ፡፡ መጻኢውን ጊዜ ለመተንበይ የፈለጉ ጥቂት የማይባሉ ሰዎች ቢናደዱም አብዛኛው እስረኛ ፖሊሶቹን ጨምሮ በሳቅ እያውካካ የበዐሉ ፍጻሜ ሆነ፡፡

ዛሬ እቤቴ ቁጭ ብዬ ሳስብ ያ በእሳት ተበልቶ ሳይወድቅ ለተወሰኑ ደቂቃዎች የቆየ እንጨት የወያኔ መንግስት ይመስለኛል፡፡ (At least metaphorically) እንደመሌ ያለ በካልቾ ብሎ እስኪያደባያው ድረስ የሚጠብቅ ይመስለኛል፡፡ የመሌን ድርሻ የሚወስድ ማን ይሆን?

ኦሕዴድ ሊቀመናብርቱን አነሳ

ዮሐንስ አንበርብር

workineh-gebeyehu-and-muktar-kedir

– የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ እየተካሄደ ነው

የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ሰሞኑን ባካሄደው የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባው፣ የድርጀቱን ሊቀመንበር አቶ ሙክታር ከድርንና ምክትል ሊቀመንበሯን ወ/ሮ አስቴር ማሞን ከኃላፊነት ማንሳቱን አስታወቀ፡፡

ማዕከላዊ ኮሚቴው ማክሰኞ መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም. ምሽት ላይ በፌስቡክ ገጹ እንዳሳወቀው፣ ሁለቱ አመራሮች ያቀረቡትን ጥያቄ በመቀበል ከድርጅቱ ኃላፊነት እንዲነሱ በሙሉ ድምፅ ወስኗል፡፡ በምትካቸውም የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባዔ የሆኑን አቶ ለማ መገርሳን የኦሕዴድ ሊቀመንበር አድርጎ ሲመርጥ፣ በፌዴራል መንግሥት የትራንስፖርት ሚኒስትር የሆኑት ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁን ደግሞ የኦሕዴድ ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል፡፡

ማዕከላዊ ኮሚቴው ባወጣው መግለጫ ሁለቱ የድርጅቱ ሊቀመናብርት ከኃላፊነት የተነሱት ባቀረቡት ጥያቄ መሆኑን ቢገልጽም፣ የሪፖርተር ምንጮች ግን ሁለቱ ሊቀመናብርት በማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባው በኦሮሚያ ተስፋፍተው ዓመቱን ሙሉ ለዘለቁ ግጭቶችና የኅብረተሰቡ ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት ያልቻሉ ናቸው በማለት ሲወቅሳቸው እንደነበርና ሁለቱም አመራሮች ራሳቸውን መከላከል አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

አቶ ለማ መገርሳ ወጣት ከሚባሉት የኦሕዴድ አመራሮች ውስጥ አንዱ ሲሆኑ፣ ኦሕዴድን የተቀላቀሉት በ1983 ዓ.ም. እንደሆነና የትውልድ ቦታቸውም ወለጋ መሆኑን ምንጮች አክለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅትም የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባዔና በፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ መንግሥት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እንደሆኑም ይታወቃል፡፡

የኦሕዴድ ምክትል ሊቀመንበር ሆነው በወ/ሮ አስቴር ማሞ ምትክ የተሾሙት ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ የፌዴራል ትራንስፖርት ሚኒስትር ሲሆኑ የትውልድ ቦታቸው ሻሸመኔ ነው፡፡

አቶ ሙክታርና ወ/ሮ አስቴር ከድርጅቱ ኃላፊነት ቢነሱም፣ አቶ ሙክታር የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ሆነው ጨፌ ኦሮሚያ በጥቅምት ወር መጀመርያ ላይ እስከሚሰበሰብ ይቀጥላሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በኦሕዴድ የቆየ የአሠራር ልማድ መሠረት የድርጀቱ ሊቀመንበር የክልሉ ፕሬዚዳንትነት ሥልጣን ያገኛል፡፡ በዚህ አሠራር የሚቀጥል ከሆነ ጨፌው በጥቅምት ወር መጀመርያ ላይ ሲሰበሰብ አቶ ለማ መገርሳን የክልሉ ፕሬዚዳንት አድርጎ ይመርጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ወ/ሮ አስቴር ማሞ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ ክላስተር አስተባባሪና የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስትርነታቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በጥቅምት ወር መጀመርያ ሳምንት ላይ አዲስ ካቢኔ እስኪያዋቅሩ ድረስ ይቀጥላሉ፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ እየተካሄደ መሆኑን የድርጅቱ መግለጫ ያመለክታል፡፡ በዚህ ስብሰባም ሹም ሽሮች እንደሚኖሩ እየተነገረ ነው፡፡ የደኢሕዴን ምክትል ሊቀመንበርና የትምህርት ሚኒትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በበኩላቸው ከፌዴራል ተቋማት የተወጣጡ የኢሕአዴግ መካከለኛ አመራሮችን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በማወያያት ላይ ናቸው፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና አቶ አንዱዓለም አራጌ 5 ዓመት እስር እንደዋዛ

ጋዜጠኛና ጦማሪ እስክንድር ነጋ እና የሰላማዊ ትግል አቀንቃኝ ፖለቲከኛ አቶ አንዱአለም አራጌ በሽብር እና በሃገር ክህደት ወንጀል ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው እስር ቤት ከገቡ መስከረም 3 ቀን 2009 ዓ.ም ድፍን አምስት ዓመት ሆናቸው፡

እስክንድር “ንፁህ ስለሆንኩኝ፣ የቀረበብኝ ማስረጃ የሌለ በመሆኑ እንዲሁም ፍርድቤቶችን የሚያህሉ የተከበሩ ተቋማት የበቀል የአፈናና የጭቆና መድረክ መሆን ስለሌለባቸው በነፃ እንድለቀቅ የተከበረውን ፍርድቤት እጠይቃለሁ” ብሎ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድቤት ይግባኙን በነሐሴ 2004 ዓ.ም ያቀረበ ቢሆንም የከፍተኛው ፍርድቤት የፈረደበትን የአስራ ስምንት ዓመት ፅኑ እስራት እና አምስት አመታት ህዝባዊ መብቶች እግድ ጠቅላይ ፍርድቤቱም አፅንቶበት የፍርዱን ሩብ አመታት በእስራት አሳልፏል፡፡

በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር አዲስ አበባ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት አምስት አመታትን በእስር ሲያሳልፍ ዘንድሮ የ48 አመት ጎልማሳ የሚሆነው ጦማሪው እስክንድር ነጋ በየኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ መንግስት ለሰባተኛ ጊዜ ሲታሰር በበርካታ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብተ ተሟጋች ድርጅቶች እስራቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሆን ደምፃቸውን ከፍ አድርገው አምስቱንም አመታት ለኢትዮጵያ መንግስት ውትወታቸውን አስምተዋል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፍርድቤት የችሎት ሂደቱን በመከታተል ላይ እያለ በግንቦት ወር 2004ዓ.ም ፔን አሜሪካ ከተባለ አለማቀፍ ድርጅት በአደገኛ የመገናኛ ብዙሐን ድባብ ውስጥ ሆኖ በመፃፍ ላደረገው አስታዋፅኦዖ “የመፃፍ ነፃነት ሽልማትን” አግኝቷል፡፡ በዚሁ አመት አለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተማጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል እስክንድር ነጋ የህሊና እስረኛ ስለመሆኑ አውጇል፡፡

ለሰባተኛ ጊዜ ለእስር በተዳረገ በአንድ አመት ከአራት ወራት ጊዜ ውስጥ በታህሳስ 2005ዓ.ም ደግሞ የሂውማን ራይትስ ዎች የነፃ ንግግር ሽልማት አሸናፊ ከመሆኑ በተጨማሪ በ36ተኛው አለማቀፍ የፀሃፊዎች ፌስቲቫል ላይ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ “የአንድ ስብዓዊነት ሽልማት” አሸናፊ ሆኗል፡፡

በጋዜጠኝነት ሙያው በሚሰራው ስራ የኢትዮጵያ የፀረ ሽብር አዋጅ ቀደምት ሰለባ የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር በ1997 ዓ.ም የተደረገውን አገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ መንግስት በአገር ክህደት፣ አመፅ በመቀስቀስ፣ህገ መንግስት እና ህግ መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል በመናድ ወንጀል ተከሶ ፍርድ ቤት የፈረደበት ቢሆንም አንድ አመት ከአምስት ወራት እሰራት በኃላ ክሱ ተቋርጦ መለቀቁ ይታወሳል፡፡

የኢንተርናሽናል ወመንስ ሚዲያ አሶሴሽን “የብርቱ ጋዜጠኛ” ሽልማት አሸናፊ የጋዜጠኛ እስክንድር ባለቤት ጋዜጠኛ ሰርክዓለም ፋሲልም የ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ ከባለቤቷ ጋር በተመሳሳይ ክስ በአንድነት ታስራ በቃሊቲ እስር ቤት ሳለች የመጀመሪያ እና ብቸኛ ልጃቸውን ናፍቆት እስክንድርን ተገላገላለች፡፡

የያኔው ስድስተ አመት ህፃን ልጁን ከትምህርትቤት ወደ ቤት እያመጣ ሳለ በድንገት ያለምንም ማስጠንቀቂያ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው እስክንድር ነጋ እነሆ ዛሬ አብረውት ከተከሰሱት 23 አባሪዎቹ ጋር አምስት አመትን ሲደፍን የቀደሞ የአንድነት ፓርቲ ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበርና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አንዷለም አራጌም የእድሜ ልክ እስራቱን በቃሊቲ ማረሚቤት እየገፋ ይገኛል፡፡

‹ምርጫ 97ን›› ተከትሎ ወህኒ ከወረደው የቅንጅት አመራር አንዱ የነበረው የያኔው ወጣት የአሁኑ ጎልማሳ፣ በብዙዋች ዘንድ የሰላማዊ ትግል አርበኛ ተበሎ የሚወደሰውአንዷለም አራጌ የቅጥት ማቅለያ እንዲያቀርብ በፍርድቤት ሲጠየቅ አንዷለም አራጌ እንዲህ ብሎ ነበር ማቅለያውን ያቀረበው፡፡ “እኔም ለልጆቼ፣ ለወገኖቼ፣ ለአገሬ እና ለራሴ በመረጥኩት ሰላማዊ ትግል ስታገል ቆይቻለሁ፡፡ የበደልኩት ህዝብ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ወንጀል ሰርቻለሁ ብዬ አላሰብም፡፡ ውስጤ ፍፁም ሠላማዊ ነው ከሳሾቼ የሚስጡኝን የግፍ ፅዋ ለመጠጣት ዝግጁ ነኝ፡፡”

አቶ አንዷለም አራጌ “ያልተሄደበት መንገድ” የሚል የመጀመሪያ መጸሐፉን በእስር ላይ ሆኖ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለአንባቢያን አደርሷል፡፡ በ2007 ዓ.ም ሰኔ ወር ደግሞ “የሀገር ፍቅር እዳ” የተሰኘው ሁለተኛ መጽሐፋ ዳግም ለህትመት በቅቷል፡፡

እስካሁንም ድረስ በእስር ላይ የሚገኙት እነዚህ የሰላማዊ ትግል አርበኞ አዲሱን አመት 2009 ዓ.ም የተቀበሉት አምስተኛ አመታቸውን በማሰብ ነው፡፡

እስክንድር ነጋ እና አንዷዓለም አራጌ በፍትህ እጦት አመታትን በእስር እንዲያሳልፉ ሲገደዱ እስራቸው አገሪቷ በዓለም አቀፍ ህግ መደረክ ተገዢ እሆናለሁ ብላ ቃል የገባችባቸውን የቃልኪዳን ሰነዶች ሁሉ የናደ ሰለመሆኑ የሰበዓዊ መብት ተሟጋቾች በተደጋጋሚ ሲሞግቱ አምስት አመታት አልፈዋል፡፡

ዛሬም አስራቸው ህገ መንግስቱን የጣሰ፣ አላግባብ፣ ኢፍታዊ እና የሰብዓዊ መብቶቻቸውን ያላከበረ ነው ፡፡ አንዱአለም በተለምዶው ቅጣት ቤት ተብሎ የሚጠራው ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግበት ክፍል ውስጥ ታስሮ ሲገኝ እስክንድር በቃሊቲ የተለያዩ ዞኖች ታስሯል፡፡ ሁለቱም እስረኞች ከቅርብ ቤተሰብ ውጪ ማንም እንዳይጠይቃቸው የተከለከሉ ሲሆን ከእስራቸው እስከ አያያዛቸው ኢሰብአዊነትን እያስተናገዱ አምስት አመት አስቆጥረዋል፡፡
ምንጭ፡- EHRP

በደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ

በባህር ዳር በአበባ እርሻዎችና በሌሎች ንብረቶች ውድመት ደርሷል

– የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ አሳስቦኛል አለ

በአማራ ክልል በደቡብ ጎንደር ዞን ዋና ከተማ ደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት በደረሰ ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ፡፡ የመከላከያ ሠራዊት እስረኞች እንዳያመልጡ ዙሪያውን ከቦ እንደነበርና ሊያመልጡ የነበሩ በርካታ እስረኞች መሞታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የእሳት አደጋው የተከሰተው ሐሙስ ነሐሴ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ እስረኞቹ ከአደጋው ለማምለጥ መሞከራቸውን አስረድተዋል፡፡ ይሁን እንጂ አካባቢውን በፍጥነት የከበበው የመከላከያ ሠራዊት እስረኞቹ እንዳያመልጡ ሲተኩስ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

debre-tabor-prison-fire

በእሳት አደጋው ሳቢያ ከፍተኛ ጉዳት በማረሚያ ቤቱ ላይ መድረሱንና ሊያመልጡ በነበሩ እስረኞች ላይም ጉዳት እንደደረሰ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የደቡብ ጎንደር ማረሚያ ቤቶች መምርያ ኃላፊ ምክትል ኮማንደር መንጌ ከበደ ቃጠሎው የተነሳው በኤሌክትሪክ መስመሮች መገናኘት መሆኑን ገልጸው፣ ሊያመልጡ የነበሩ ሁለት እስረኞች መገደላቸውንና ከእስረኞች ደግሞ ሁለት መቁሰላቸውን አስረድተዋል፡፡
በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተስፋፋ የሚገኘው አመፅ፣ ከመንግሥት ጋር ቁርኝት አላቸው በተባሉ የግል ባለሀብቶች ንብረቶችና የሕዝብ አገልግሎት መስጫ ተቋማት ላይ ያነጣጠረ ጉዳት እያደረሰ መሆኑም ተገልጿል፡፡

ኢስመራልዳ (Esmeralda Farms) የተባለው በባህር ዳር የሚገኘው የኔዘርላንድ ባለሀብቶች የአበባ እርሻ በእሳት ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡
መቀመጫውን በኔዘርላንድ ያደረገው የአበባ ኩባንያው ዋና ቢሮ ባወጣው መግለጫ፣ በፖለቲካ ተቃውሞው ምክንያት በባህር ዳር የሚገኘው የአበባ እርሻ (ኮንዶር ፋርም) በእሳት ሙሉ በሙሉ መውደሙንና የኩባንያው አጠቃላይ ኢንቨስትመንት አሥር ሚሊዮን ዩሮ እንደሆነም አስታውሷል፡፡

በኢትዮጵያ ከሚገኘው ቢሮ ጋር መገናኘት አለመቻሉን የሚገልጸው መግለጫው፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጃችን በቀውሱ ምክንያት ከአካባቢው በመልቀቃቸው መረጃዎችን ማግኘት አልተቻለም፤›› ብሏል፡፡

በመንግሥት ላይ የተነሳው ተቃውሞ በአካባቢው በሚገኙ የአበባ እርሻዎች ላይ ጉዳት ማድረስ መቀጠሉንና አሥር ያህል የአበባ እርሻዎች መቃጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ኮንዶር ፋርም የተባለው የአበባ እርሻ ሲቃጠል በአካባቢው የመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች የነበሩ ቢሆንም፣ ጉዳቱን ያደረሱት ከፀጥታ ኃይሎች ቁጥር በብዛት የሚበልጡ በመሆናቸው ማዳን አለመቻሉን ኩባንያው ገልጿል፡፡
መጋዘኖች፣ የማቀዝቀዣ ክፍሎች፣ ትራክተሮች፣ የጭነት ተሽከርካሪዎች፣ ኮንቴይነሮችና ማሸጊያዎች በሙሉ በእሳት መውደማቸውን አስታውቋል፡፡

‹‹ሁሉም ጠፍቷል፡፡ የአሥር ሚሊዮን ዩሮ ኢንቨስትመንትና የረጅም ዓመታት ጥረት በአንድ ቀን ወድሟል፤›› ሲል በመግለጫው የደረሰውን ጉዳት አመልክቷል፡፡

ሌላው በየመኑ ባለሀብት መሐመድ አልካሚን የተቋቋመውና ከ500 በላይ ሠራተኞች የነበረው የአበባ እርሻ ይገኝበታል፡፡
ለባህር ዳር ከተማ የውኃ አቅርቦት ምንጭ የሆነው እንፍራንዝ ከተማ አካባቢ የሚገኘው የጥቁር ውኃ የውኃ ማጠራቀሚያ ጋንም ቃጠሎ ደርሶበታል፡፡ ይህም በከተማዋና በአካባቢዋ የውኃ አቅርቦት ላይ እጥረት እንደሚያስከትል እየተነገረ ነው፡፡
በተያያዘ ዜና በክልሉ ውስጥ ያለው ተቃውሞ እየተባባሰና በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ የሚደርሰው ጉዳት እየጨመረ መምጣቱን መረጃዎች እያሳዩ ነው፡፡

በተለይም ማክሰኞ ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትሩ በክልሉ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ ለማስቆም የፀጥታ ኃይሉ ሕግ እንዲያስከብር ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን ከገለጹ ጀምሮ ሰዎች መሞታቸውን፣ የዘር ጥቃት ተፈጸመባቸው የተባሉ ደግሞ ወደ ጎረቤት አገር እየተሰደዱ መሆናቸው እየተገለጸ ነው፡፡

በተለይ በአምባ ጊዮርጊስ፣ በደብረ ታቦር፣ በመተማ ዮሐንስና በአጎራባች አካባቢዎች የሰው ሕይወት መጥፋቱን የሚገልጹ ቁጥሮችም እየጨመሩ ስለመውጣታቸው መረጃዎች እየጠቆሙ ይገኛል፡፡ ነገር ግን በመንግሥት በኩል እስካሁን ምንም ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልተሰጠም፡፡

ሪፖርተር ከምንጮች ማረጋገጥ እንደቻለው በክልሉ የተለያዩ ከተሞች የመከላከያ ሠራዊት እየገባ ሲሆን፣ የከባድ መሣሪያ ተሽከርካሪዎች መታየታቸውን ለማወቅ ችሏል፡፡

የአማራ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን፣ በክልሉ ምዕራባዊ አካባቢዎች ሁከት መከሰቱን ተናግረዋል፡፡ በአንዳንድ ፀረ ሰላም ኃይሎች የተነዛ መረጃ ሕዝቡን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ መምራቱንና በተፈጠረው ሁከትም በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ እየተከሰተ ያለው ግጭት እያሳሰበው መምጣቱን ጠቁሞ፣ ሁሉም ወገኖች ከማንኛውም ግጭት እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡

የኮሚሽኑ ዋና ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ ዓርብ ነሐሴ 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ ‹‹በአገሪቱ የማኅበራዊ ፖለቲካው የሰው ሕይወት ማጥፋት፣ በንብረቶች ላይ ውድመት ማስከተል፣ እንዲሁም የቴሌኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት እስከማቋረጥ ደረጃ መድረሱ አሳሳቢ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ሊቀመንበሯ አክለው ሁሉም ወገኖች ወደ ሰላማዊ ሁኔታ በማመዘን ለሕግ መከበር እንዲተጉ፣ ሰላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብትና የዴሞክራሲ ባህልና መርሆችን እንዲያከብሩ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

%d bloggers like this: