Monthly Archives: January, 2018

የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ: በወልድያ የበዓለ ጥምቀት ግጭትና ግድያ የጸጥታ ኃይሉን ወቀሱ፤“የእነርሱ መዘዝ ነው፤ወጣቱ አበላሸ የምንለው ነገር የለም”

“መከላከያዎቹ እንዳይመጡ ቀድመን አሳስበናል፤ከዞኑም ጋር ተናበን እየሠራን ነበር፤”
“በሰላም ሊጠናቀቅ ባለበት ሰዓት መጥተው ግጥም አሉ፤ ይኸው ወጣቱን አሳበዱት፤”
“ወጣቱን ሌላ የፖሊቲካ አካል ቀሰቀሰው አሉ፤ ወታደሮቹን ማን ነው የቀሰቀሳቸው?”
“የበቀል ነው የሚመስለው፤እንደው ከራሳቸው መካከልም የሚያጠፋ ያለ ይመስለኛል፤”
“ታቦቱን ያከበሩት ካህናት፣በጎናቸው ባሉት ካህናት ተገድፈው ነው እንጅ ወድቀዋል፤”
“ተዉ ብሎ ይህን ማስተካከል እና መሥመር ማስያዝ ያለበት መንፈሳዊ አባት ነው፤”
“ቤተ ክርስቲያኗን ወጣቱ ሰምቶልናል፤ታቦቱ ከገባ በኋላ ሁሉም እንሙት እያለ ነበረ፤”
†††

“ተረጋግቶ እያለ ድኻ የሚረዳ ልጅ ገድለው ዳግም በእነርሱ ስሕተት ግጭቱ ቀጠለ፤”
“ሕንፃ እግዚአብሔር እያፈረሳችሁ ፎቅ ትጠብቃላችሁ፤”ብሎ ሕዝቡ በጣም ተቆጨ፤
“ስንቱስ ንብረት ወደመ? የእነርሱ መዘዝ ነው፤ ወጣቱ አበላሸ የምንለው ነገር የለም፤”
“መከላከያ ይውጣ፤ ወጣቱ ከከተማው ፖሊስ ጋር ይጠብቀዋል፤” በሚል ተስማማን፤
ርእሰ መስተዳድሩም፣ “ሠራዊቱን አስወጣለሁ፤ አጣሪ እልካለሁ፤ አጥፊው ለሕግ ይቀርባል፤ ይፋም አደርጋለሁ፤” ብለዋል፤ ልቅሶ ቤትም ገብተው አብረው እያለቀሱ አጽናንተዋል፤
“ከኹለት ዙር ውይይት በኋላ፣ ወጣቱን በየአቅጣጫው የሚመሩ ካህናት መድበን ወደየቤቱ እንዲገባ አድርገናል፤ በሰላም እየዘመረም ወደየቤቱ ተመልሷል፤”
“እኛም በየሐዘን ቤቱ እየዞርን ስናጽናና ውለናል፤ ርእሰ መስተዳድሩ ከተመለሱ በኋላ ከላኳቸው ልኡካን ጋራ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ተካትተን እየመከርን ነው፤”
†††

his-grace-abune-ermias-speaks-on-the-woldias-massacre-e1516905706194
ፎቶ፡ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ፤ የሰሜን ወሎ እና ከሚሴ ዞን ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ

በሰሜን ወሎ ዞን ወልዲያ ከተማ፣ በጥምቀት እና በቃና ዘገሊላ በዓል አከባበር ወቅት የተቀሰቀሰው ግጭትና የተፈጸመው ግድያ፣ በጸጥታ ኃይሉ ስሕተት የደረሰ ነው፤ ያሉት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ረዳት፣ ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ፣ ለጠፋው የዜጎች ሕይወት እና ለወደመው ንብረት ወቀሱት፡፡

የቃና ዘገሊላ በዓል፣ እንደ በዓለ ጥምቀት ኹሉ በሥርዐቱ እየተከበረ በሰላም ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ሰዓት የመጣው የጸጥታ ኃይል “ያልተጠራ” እንደነበር የጠቀሱት ብፁዕነታቸው፣ ከመጣ ችግር እንደሚፈጠር ስለታመነ እንዳይመጣ ሊቀ ጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ቀድመው አሳስበው እንደነበር አውስተዋል፡፡

his-grace-abune-qerlos
ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፤ የሰሜን ወሎ እና ዋግ ኽምራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

ለበዓሉ አከባበር፣ ሀገረ ስብከቱ ከዞኑ ሓላፊዎች ጋራ እየተናበበ በመሥራቱ የተጠየቀ ተጨማሪ ኃይል እንዳልነበርና “እነርሱ አይምጡ፤ እኛው በእኛው ፕሮግራማችንን እንመራለን፤” በማለት ቀድሞ እንዳሳወቀ ብፁዕነታቸው ጠቁመዋል፡፡

ይኹንና በመምጣታቸው ወጣቱን ለተቃውሞ እንዳነሣሡ ተናግረዋል፤ “ወጣቱን አሳበዱት፤ የተሳደበም ይመስለኛል፤ ድንጋይም ሳይወረውር አይቀርም፤ በጥይት ለቀሙት፤” በማለት የርምጃውን ኢፍትሐዊነት አስረድተዋል፡፡ በማግሥቱም ቀጥሎ የነበረው ግጭትና የንብረት ውድመት መንሥኤ የጸጥታ ኃይሉ እንደኾነ የተናገሩት ብፁዕነታቸው፣ “የእነርሱ መዘዝ ነው፤ እኛ ወጣቱ አበላሸ የምንለው ምንም ነገር የለም፤” ሲሉ ድርጊቱን ኮንነዋል፡፡

በሞትና መቁሰል ስለደረሰው ጉዳትም፣ “ብዙ ሰው ነው የተጎዳብን፤ ያላወቅነውም ይኖራል፤” ብለዋል ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ፡፡ ግጭቱ በተከሠተበት ወቅት ከመርሳ ከተማ ወደ ወልዲያ ተመልሰው በዚያው አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ለማስተማር በዝግጅት ላይ እንደነበሩ ገልጸው፣ የጸጥታ ኃይሎቹ ለብተና በተጠቀሙበት አስለቃሽ ጢስ ታቦቱን ያከበሩት ካህናት፣ “በጎናቸው ባሉ ካህናት ተገድፈው ነው እንጅ ወድቀዋል፤” ብለዋል ጥልቅ ቅሬታ በሚደመጥበት አነጋገር፡፡

የጸጥታ ኃይሉን ለምን ማሠማራት እንዳስፈለገ እንደማያውቁ ብፁዕነታቸው ጠቅሰው፣ ኾነ ተብሎ የታቀደ እንደሚመስላቸው ሳይገልጹ አላለፉም – “ለምን እንደመጡ አናውቅም፤ ኾን ብለው ለመምታት ይመስላል፤ ከራሳቸው መካከልም የሚያጠፋ ያለ ይመስለኛል፤” ብለዋል፡፡ አያይዘውም፣ “ወጣቱን ሌላ የፖሊቲካ አካል ቀሰቀሰው ይባል፤ እነርሱን ወታደሮቹን ማን ነው የቀሰቀሳቸው? ሰላም እንዳይኾን!” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ከክልሉ ርእሰ መስተዳድር ጋራ በኹለት ዙሮች በተካሔደው ውይይት፣ ወጣቱ በአጠፌታ ተሠማርቶበት ከነበረው የንብረት ማቃጠልና ማውደም አረጋግተው ወደ አዳራሽ እንዲገባ በማድረግ ከሌሎች የሃይማኖት አባቶች እና የአገር ሽማግሌዎች ጋራ የተሳካ ሥራ እንደሠሩ ብፁዕነታቸው ይገልጻሉ፡፡ ቀደም ሲል ከእግር ኳስ ጨዋታ ጋራ ተያይዞ ተከሥቶ በነበረው የከተማዋ ግጭት በተለይ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን የማረጋጋት አባታዊ ሚና እንደነበራቸው በማውሳት፣ “ቤተ ክርስቲያኗን ወጣቱ ሰምቶልናል፤” ሲሉ አመስግነዋል፡፡

ባለፈው ሰኞ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር በተገኙበት በተደረገው ውይይት፣ የመንግሥት ጥፋት በግልጽና በዝርዝር መቅረቡን፤ ለከተማው ሰላምና ጸጥታ በሚረዱ አጠቃላይ መፍትሔዎች ላይም ስምምነት እንደተደረሰ አስታውቀዋል፡፡ ሠራዊቱን ከከተማው እንደሚያስወጡ ርእሰ መስተዳድሩ የገለጹ ሲኾን፣ ለሰላሙና ጸጥታው ወጣቱ ከፖሊስ ተባብሮ እንደሚሠራም አረጋግጧል፡፡ ርእሰ መስተዳድሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ “ስለተፈጸመው ነገር የሚያጣራ አካል እልካለሁ፤ አጥፊው ለሕግ ይቀርባል፤ ለእናንተም ይፋ አደርጋለሁ፤” ማለታቸው ታውቋል፡፡

ከውይይቱ በኋላ አቶ ገዱ፣ ሐዘንተኞችን በየቤታቸው ተገኝተው በማጽናናታቸው ያመሰገኑት ብፁዕነታቸው፣ በቤተ ክርስቲያንም በኩል ካህናትን መድቦ ወጣቱ በሰላም ወደየቤቱ እንዲገባ ከማድረግ ባሻገር፣ እስከ ትላንት ድረስ ሐዘንተኞችን ሲያጽናኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡ በአኹኑ ወቅትም በክልሉ መንግሥት ተሠይሞ ከተላከው ልኡካን ቡድን ጋራ፣ እርሳቸውን ጨምሮ የከተማው የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች የተካተቱበት ምክክር እየተካሔደ እንዳለ አስታውቀዋል፡፡

እየተከሠተ ያለው የግፍና የጥፋት ድርጊት፣ ሕዝብን ከሕዝብ እያለያየ መኾኑ በእጅጉ እንደሚያሳዝናቸው ብፁዕነታቸው ተናግረዋል፡፡ “ተዉ ማለት ያለበት፣ ይህን ማስተካከልና መሥመር ማስያዝ ያለበት መንፈሳዊ አባት ነው፤” ሲሉ ቤተ ክርስቲያን ጥፋትን የመከላከል፣ አጥፊውን የማውገዝና የመገሠጽ፣ የተበደለው እንዲካስና እንዲጽናና የማድረግ በአጠቃላይ የአገርን ሰላምና የሕዝብን አንድነት የማስጠበቅ ከባድ መንፈሳዊና ታሪካዊ ሓላፊነት እንዳለባት አመልክተዋል፡፡

አባቶችና መንበረ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ክብር በመዳፈርና ሥርዐቷን በመጣስ ጭምር ስለተፈጸመው የወልዲያው ግፍ፣ አቋማቸውን እንዲያሳውቁና ኖላዊነታቸውን እንዲያረጋግጡ በብዙኃን መገናኛዎችና በመግለጫዎች የሚሰነዘሩት ጥያቄዎችና ወቀሳዎች እንደቀጠሉ ናቸው፡፡

መኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች፣ ከትላንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የጥምቀት እና የቃና ዘገሊላ በዓልን ለማክበር በወጡ የወልዲያ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የተፈጸመውን ግድያ የተመለከተችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ድርጊቱን አለማውገዟ ያስተዛዝበናል፤ ብለዋል፡፡

ለተነሣው ግጭትና ለተወሰደው የግድያ ርምጃ የቀረበው ምክንያት፣ “መንግሥትን የሚቃወም ዜማ አሰማችሁ፤” የሚል እንደኾነ በመግለጫቸው የጠቀሱት ፓርቲዎቹ፣ “ይህ ደግሞ መብት መጣስ ነው፤” ብለዋል፡፡

አክለውም፣ “የጸጥታ ኃይሎች ቅዱስ ታቦትን ባከበሩ ቀሳውስት ላይ አስለቃሽ ጭስ መተኮሳቸው ሃይማኖቱን መዳፈር በመኾኑ መንግሥት ድርጊቱን በማውገዝ የእምነቱን ተከታዮች በዐደባባይ ይቅርታ ይጠይቅ፤ ለሟች ቤተ ሰዎች የደም ካሳ እንዲከፍል፤ ግድያው እንዲፈጸም ትእዛዝ የሰጡም ኾነ ጉዳዩን በቸልተኝነት የተመለከቱ የዞኑ ባለሥልጣናት በሕግ እንዲጠየቁ፤ ግድያውን የፈጸሙ የመንግሥት ታጣቂዎች ለሕግ እንዲቀርቡ እንጠይቃለን፤” ሲሉ አቋማቸውን አስታውቀዋል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤን በመወከል በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ርእሰ መንበርነት አመራር የሚሰጠው ቋሚ ሲኖዶስ፣ ከልደት ጀምሮ በነበሩት ዐበይት ክብረ በዓላት ሳቢያ የተመደቡት ተለዋጭ አባላቱ ብፁዓን አባቶች በየአህጉረ ስብከታቸው በመኾናቸው አለመሰብሰቡ ተጠቁሟል፡፡ ሰሞኑን እስከ ግንቦቱ የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ድረስ በተለዋጭነት በተመደቡት አራት ብፁዓን አባቶች አባላቱ በሚቀጥለው ሳምንታዊ መደበኛ ስብሰባው፣ ጉዳዩን ይመለከተው እንደኾነም ለማረጋገጥ አልተቻለም፡፡

ምንጭ፦ ሐራ ዘተዋሕዶ

7 die at Ethiopia’s Epiphany in clashes with security forces

By ELIAS MESERET

January 21, 2018, ADDIS ABABA, Ethiopia (AP) — An Ethiopian police official in the restive Amhara region in the north confirmed Sunday evening that seven people were killed when worshippers celebrating the Epiphany holiday clashed with security forces.

The killings on Saturday, January 20,2018 in the town of Woldiya, some 500 kilometers (310 miles) north of the capital Addis Ababa, happened on the second day of the colorful Epiphany celebrations in this East African nation.
Amare Goshu, a police official in the region, told the state-owned Ethiopian Broadcasting Corporation that seven people died, including one security officer, during the confrontation. He said that the security forces responded with force when youths in the town tried to attack officers who were patrolling the holiday procession areas. “More than 15 citizens and 2 police officers were also injured and are now receiving treatment,” he said.

Two Woldiya residents, who spoke to The Associated Press on condition of anonymity for fear of reprisal, said the measures taken by the security forces were excessive and feared the death toll was higher. One claimed police fired on demonstrators who were throwing stones. The other said the death toll could rise further as gunshots could be heard until midday Sunday. Both added that a number of hotels, restaurants and shops were burned down by angry protesters.

Ethiopia’s Amhara and Oromia regions have seen violent anti- government protests since November, 2015, when people took to the streets demanding political freedom and the release of political prisoners. Hundreds have been killed and more than 11,000 arrested, although most have since been released.

Ethiopia is an ally of the U.S. but it is often accused by rights groups of stifling dissent and arresting opposition figures and journalists critical of the government. A prominent opposition politician, Merera Gudina, was released on Wednesday as part of a pledge by the government to open up the political space and create a national consensus.

Source: AP.

ታዳሚን እንባ ያራጨው የችሎት ውሎ

በጌታቸው ሺፈራው

ጥር 7 ቀን 2010 ዓ.ም. በጠዋት ሰብሰብ ብለን የገባነው ወደ 4ኛ ወንጀል ችሎት ነበር። ከ4ኛ ወንጀልችሎት ስወጣ 19ኛ ወንጀል ችሎት ታዳሚውን ያስለቀሰ፣ ዳኞቹን ሳይቀር ያሳዘነ ትዕይን እንደነበር ሰማሁ። 19ኛ ወንጀል ችሎት የነበረ አንድ ጓደኛዬን ማስታወሻውን እንዳየው ጠየኩት። የተጀመሩ ዐረፍተ ነገሮች፣ ያልተቋጩ ሀረጎችን አነበብኩ። በእርግጥ እንባ በሚያራጭ ትዕይንት ውስጥ መፃፍ ከባድ ነው። እኔንም ብዙ ቀን አጋጥሞኛል።የጓደኛዬ ማስታወሻ ላይ የሰፈሩ የተቆራረጡትን ዐረፍተ ነገሮች መዝግቤ፣ ጓደኛዬ በችሎት ያየውን እንዲያብራራልኝ ጠየኩት። በአማራ ክልል በነበረው ህዝባዊ ንቅናቄ ሰበብ የታሰሩትና በእነ ታደሰ መሸሻ አሰጌ ክስ መዝገብ ከተከሰሱት መካከል 3ኛ ተከሳሽ የሆነው ዮናስ ጋሻው ደመቀ በሌሎች የአማራ ወጣቶች የሚፈፀመው ጭካኔ ተፈፅሞበታል። አስቻለው ደሴና ሌሎች አማራ ወጣቶች እንዳደረጉት ሱሪውን በችሎት አውልቆ “ህዝብ ይፍረደኝ” ብሏል። ሃይላንድ ያንጠለጠሉበትን ብልቱን አሳይቷል።በዚህ ወቅት ታዳሚው አልቅሷል። ጓደኛዬ ይህን ሰቆቃ እያየ በደንብ መፃፍ አልቻለም። ዳኞች እንኳ አንገት ደፍተዋል። በጠዋቱ ችሎት በተከሳሹ ሰቆቃ ያለቀሱትን ታዳሚዎችም አነጋግሬያቸው ነበር። ከሰዓትም ሀዘኑ ሳይለቃቸው ስለ ሰቆቃው ነግረውኛል።

Yonas_Human rights violation victim.jpg
ፎቶ፡ ዮናስ ጋሻው (ከጌታቸው ሺፈራው ገፅ የተወሰደ)

ዮናስ ማዕከላዊ በነበረበት ወቅት ሀይላንድ አንጠልጥለውበታል። በፒብሳ ከታትፈውታል። እግሩ ተጎድቷል። ማዕከላዊ በተፈፀመበት ሰቆቃ የነርቭ በሽተኛ ሆኗል። ይህን ሲናገር ሰቆቃውን ያደረሱበት ሁለት የማዕከላዊ ገራፊዎች ችሎት ውስጥ ተቀምጠው ነበር።

የጓደኛዬ ማስታወሻ አገላበጥኩ። ዮናስ የተበደለው ማዕከላዊ ብቻ አይደለም። ከመታሰሩ በፊትም በቤተሰቡ ላይ በደል ደርሶበታል። ” ወንድሜን ሆን ብለው በኦራል(መኪና) ገጭተው ገደሉት፣ እናቴንም በተመሳሳይ መልኩ ገድለውብኛል። በማዕከላዊ አማራና ኦሮሞ ዘር እንዳይተካ ለምን ይደረጋል? የተማርነው ጥላቻ ነው። የእኛ ትውልድ ከእኛ ምን ይማራል? ሀይላንድ ተንጠልጥሎብኛል። በፒንሳ…… ሁላችንም ጉዳት ደርሶብናል” ብሎ በችሎት ምሬቱን ተናግሯል።

የዮናስ ስቃይ ከማዕከላዊ በኋላም አላበቃም። በማዕከላዊ የደረሰበትን ጉዳት ለመታከም ወደ ዘውዲቱ ሆስፒታል ተወስዶ፣ ከአቅማችን በላይ ነው ብለውታል። ጳውሎስ ሄዶ የአጥንት ስብራት እንዳለበት ማረጋገጫ ቢሰጠውም ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ውጤቱን አጥፍቶበታል። በድብደባው ምክንያት የቀኝ እግሩ ሽባ ወደመሆን ደርሷል። ለዚህም ሽፍን ጫማ ያስፈልጋል። ሆኖም ሽፍን ጫማውን ገብረእግዚ የተባለ የገዥዎች ወገን ቀዶ ጥሎበታል። “ሽፍን ጫማ ለማድረግ እንኳ ብሔር መቀየር አለብን” ሲልም ገዥዎቹ እያደረሱበት ያለው በደልና ጭካኔ ቅጥ ጠይቋል።

ጠዋት ቀጠሮ የነበራቸው ተከሳሾች ጉዳይ ከሰዓትም ይቀጥላል ስለተባልን ከማህሌት ፋንታሁን ጋር ከሰዓት ወደ 19ኛ ወንጀል ችሎት አቀናን።ተከሳሾቹ ወደ ቂሊንጦ ሄደው ስለነበር ችሎት ስራ ይጀምራል ከተባለው ሰዓት ዘግይተው ደረሱ። ከሌሎች ተከሳሾች ቀደም ብሎ አንድ ተከሳሽ እያዘገመ ነው። በቀኝ ጎኑ በኩል ሌላ ተከሳሽ ደግፎታል። ወዲያውኑ ከኋላው የነበሩት ተከሳሾች አለፉትና ተደግፎ ከኋላ ማዝገም ጀመረ። በጠዋቱ የችሎት ጊዜ ሱሪውን አውልቆ የተፈፀመበትን በደል የተናገረው ተከሳሽ እንደሆነ መገመት ችያለሁ። ተከሳሾች ወደ ችሎት ከገቡ በኋላ እኛም ለመታደም ገባን። ተደግፎ ፍርድ ቤቱ ግቢ ውስጥ ወዳለው ጊዜያዊ ማቆያ ያቀናው ተከሳሽ ፊት ወንበር ላይ ተቀምጧል። የቀኝ እግሩ ለሚያየውና የደረሰበትን በደል ለሚገምት በሚሰቀጥጥ መልኩ ይንቀጠቀጣል። ተቀምጦ እንኳን በቀኝ እግሩ አይረግጥበትም። የቀኝ የሰውነት ክፍሉ እስከ ትክሻው ድረስ ይንዘፈዘፋል።ችሎቱ ስራ ላይ በነበረበት ሰዓት ለሽንት ተደግፎ ሲወጣ የቀኝ እግሩን በደንብ አይረግጥበትም። ይጎትተዋል ማለት ይቀላል።

የማዕከላዊ ምስክሮች

ከሰዓት በነበረው የፍርድ ቤቱ ሰዓት ሁለት የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ተሰምተዋል። በቀዳሚነት የተመሰከረበት ደግሞ ሰቆቃ የተፈፀመበት ዮናስ ነው። ምስክሩ ባህርዳር ከተማ ይኖር የነበር ደላላ እና የሆቴል ባለቤት ነኝ አለ። አሁን ተፈትቼ ባህርዳር እገኛለሁ ብሎ ቃሉን ሰጠ። እውነታው ግን ሌላ ነው። ዮናስ ጋሻው ወደ ግንቦት 7 እንድልከው ጠይቆኝ ነበር ብሎ መሰከረ። ቆይቶ ደግሞ የአማራ ሕዝብ ነፃነት ንቅናቄ (አሕነን) የተባለ፣ የግንቦት 7 ቅርንጫፍ ነው ያሉት ቡድን እንዲቀላቀል በአንድ ስብሰባ እንደተነገረው፣ ከምሽቱ 12 ሰዓት ተሰብስው ማታው መንግስትን ለመገልበጥ ጦርነት ሊያደርጉ፣ ምስክሩም አባል እንዲሆን በተነገረው በነጋታው በተነገረው ጦር አደራጅቶ አባይን ሊያስዘጋ ተልዕኮ እንደተሰጠው መሰከረ። ምስክሩ መረጋጋት አይስተዋልበትም። የሚሰጠው መልስ ይበቃል እየተባለ እንኳን ማብራሪያውን ይቀጥላል። ዐቃቤ ሕግ፣ ፍርድ ቤቱም፣ የተከሳሾች ጠበቃም “በቃ” እያሉት አይበቃውም።

ፍርድ ቤቱ በመሃል እየገባ “ወደ ግንቦት 7 ለመሄድ የሚጠየቁት ምን ሰለሆኑ ነው? ወደ ግንቦት 7 እንዲልኩት ሲጠይቅ የነበረ ሰው እንዴት የግንቦት 7 ቅርንጫፍ ነው የተባለ ቡድን መስርቶ እንዲቀላቀሉ ይጠይቅዎታል? በአንድ ቀን ዝግጅት እንዴት ጦርነት ይደረጋል? አንድ ቀን ተነግሮዎት ያለ ዝግጅት እንዴት አባይን ያስዘጋሉ? ማን ጋር ሆነው አገኙት?……” ብዙ ብዙ ጥያቄ አነሳ። 19ኛ ወንጀል ችሎት ዳኞች አንድ ቀን በማጣሪያ ጥያቄ ምስክርን አጥብቀው ሲጠይቁ አይቻለሁ። ዶ/ር መረራ ጉዲና ሲመሰከርባቸው። እንደዛሬው ምስክርነት ግን ግራ ሲጋቡ፣ ግራ የተጋቡበትን የምስክርነት ቃል ለተከሳሽ የሚጠቅም በሚመስል መልኩ ሲጠይቁ አይቼ አላውቅም። ምን አልባት፣ ጠዋቱ የፍርድ ቤቱ ሰዓት የተነገረው ተፅዕኖ ፈጥሮ ይሆናል።

ተከሳሾች በጠበቃ አለልኝ ምህረቱ በኩል ምስክሮቹ ማዕከላዊ ታስረው እንደነበር፣ ተገደው እንደመሰከሩ፣ በድብደባ ብዛት “ልንመሰክርባችሁ ነው” ብለው ለተከሳሾች እንደነገሯቸው ጠየቁ፣ ዳኞችም አጣሩ። አንደኛው ምስክር “ሁላችንም ከምንታሰር የተወሰንነው ለቤተሰብ እንድረስ ብያቸዋለሁ” ብሎ አመነ።

በጠበቃና በዳኞች ጥያቄ ብዛት ሌላኛው ምስክርም “መንግስት ምህረት ያደረገልኝ በእነሱ ላይ እመሰክራለሁ ስላልኩ ነው” ብሎ የማዕከላዊ ምስክር መሆኑን ተናገረ። ስልክ ስለመደዋወል ሲመሰክር የነበረው አንድ ምስክር “አሁን ስልክ የት አለ?” ሲባል “አልጋ የያዝኩበት ሆቴል አስቀምጨቃለሁ” ብሎ ተናገረ። ስልክ ቁጥሩን ሲጠየቅም “092 352 9019” ብሎ ተናገረ። ከችሎት እንደወጣሁ በዚህ ቁጥር ላይ ደወልኩ። ከቴሌ የድምፅ መልዕክት “ይህ ቁጥር አይታወቅም……” የሚል መልስ አገኘሁ። እኔ ስታሰር የተወሰደብኝ ስልክ ቁጥር አልተመለሰልኝም። በእኔ ቁጥር ላይም ስደውል የሚሰጠኝ መልስ ተመሳሳይ ስለሆነ ይህ ምስክር አሁን እጠቀምበታለሁ ያለው ስልክ ሲታሰር ተወስዶበት ቴሌ ቁጥሩን እንዳልለመለሰለት ግልፅ ሆነልኝ። እሱ ግን እጠቀምበታለሁ ብሎ መስክሯል። የማዕከላዊ ምስክር ከዚህ ውጭ ይላል ተብሎ አይጠበቅም።

ምስክሮቹ በዳኞችና በጠበቃ አለልኝ ምህረቱ ሲጠየቁ ” በምህረት ተፈትተናል” ብለዋል። የተፈቱበትን ቀን፣ ወርም ሲጠየቁ መልሳቸው “አናስታውስም” ነው። አልተፈቱምና የተፈቱበትን ቀን ሊያስታውሱ አይችሉም!
ተከሳሾቹም ምስክሮቹ ማዕከላዊ ታስረው እንደሚገኙ፣በእነሱ ላይ በሀሰት መስክረው እንደሚለቀቁ ቃል ተገብቶላቸው በሀሰት እንደሚመሰክሩባቸው ተናግረዋል። ሰቆቃ ደርሶበት ሱሪውን በችሎት አውልቆ ሀይላንድ የተንጠለጠለበትን ብልቱን ያሳየው ዮናስም በጠዋቱ ችሎት ምስክሮቹ ማዕከላዊ ታስረው፣ በግድ መስክሩ እየተባሉ እንደሆነ ተናግሮ ነበር። እውነታውም ይሄው ነው!

ሁለቱ ምስክሮች መስክረው ችሎት ተጠናቅቆ ስንወጣ የገቡት ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ መኪና ነበር። እስረኞች ወደሚመላለሱበት፣ እኔም በአንድ ወቅት የማዕከላዊ እስረኛ ሆኜ ወደተመላለስኩበት መኩና እንጅ አልጋ ወደያዙበት ሆቴል የሚያደርሳቸው መኪና ውስጥ አልገቡም። ጉዟቸው ጓደኞቻቸው ወደተሰቃዩበት፣ እነሱም ተሰቃይተው በሀሰት እንዲመሰክሩ ወደተገደዱበት ወደ ማዕከላዊ ነው።
ዮናስ አካሉን ወዳጣበት፣ ብልቱ ላይ ውሃ ወደተንጠለጠለበት፣ ኢህአዴግ ደርግ ሲጠቀምበት ነበር ብሎ 26 አመት ሙሉ አማራ እና ኦሮሞ ወጣቶችን ወደሚያሰቃይበት ማዕከላዊ! ምስክሮች የሄዱት ተፈትተን እንኖርበታለን ወዳሉት አማራ ክልል ሳይሆን ትህነግ/ህወሓት የአማራ ወጣቶችን ብልት ወደሚሰልብበት፣ የትህነግ የጥላቻ ጥግ ወደሚታይበት ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ!

የተከሳሾች እና ከሳሾች ወግ ትዝብት

በጌታቸው ሺፈራው

“ቶርች ሲያስደርጉን የነበሩት ጌታቸው አምባዬ ናቸው። እግርና እጃችን በካቴና አሳስረውናል።” 36ኛ ተከሳሽ ካሳ መሃመድ
~”አማራ፣ ጉራጌ፣ ኦሮሞ፣ ሙስሊም በመሆናችን ብቻ ተከሰናል። እኔ የተከሰስኩት ጉራጌ ስለሆንኩ ነው። የዶ/ር ብርሃኑ ነጋ፣ የዶ/ር ታደሰ ብሩ ዘመድ ነህ እየተባልኩ ነው የተመረመርኩት። “22ኛ ተከሳሽ ሚስባህ ከድር
~”እኔ ከዚህ ፍርድ ቤትም፣ ከአምባገነኑ መንግስትም ፍትህ አልጠብቅም። ለታሪክ ነው የምከራከረው። ” 1ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ
~”የሰውን ልጅ እንደሰው አለመቁጠር፣ ህሊና ቢስነት ነው።” 13ኛ ተከሳሽ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ
~”እኛ የተከሰስነው ለምን ከእሳትና ከጥይት ተረፋችሁ ተብለን ነው።” 31ኛ ተከሳሽ ጌታቸር እሸቴ
~”ማረሚያ ቤት አንድ ቀን ባደርኩ ቁጥር ለህይወቴ እሰጋለሁ” 5ኛ ተከሳሽ አግባው ሰጠኝ
~”በሌላ ሀገር ከእግዚያብሔር ቀጥሎ ፍትሕ የሚሰጥ ፍርድ ቤት ነው። በእኛ ሀገር ግን በደሕንነት ብጣሽ ውቀትና ስልክ ትዕዛዝ ነው የሚሰራው።” 3ኛ ተከሳሽ አሸናፊ አካሉ
~”እነዚህን ዐቃቤ ሕግ ብሎ መጥራት አይቻልም። ዐቃቤ ሕግ ማለት በጥላቻ ግለሰብን የሚያጠቃ፣ ህሊና ቢስ አይደለም።” 25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ
~”ከአሁን በኋላ ወደ ፍርድ ቤት መመላለስ አልፈልግም። ፍርድ ቤት በሌለሁበት የሚወስነውን ውሳኔ በማረሚያ ቤት ሆኜ እቀበላለሁ” 18ኛ ተከሳሽ አንጋው ተገኘ
~”እኔ ለህሊናዬ የምኖር ሰው ነኝ። ስሜ መጥፋት የለበትም። እኔ እንደዛ ባደርግ እንኳ ተቋሙ ነው የሚከራከረው።” መኩሪያ አለሙ (ዐቃቤ ሕግ)
~”በሚዲያ የሚነገር ነገር አለ።ተፅዕኖ ያመጣል። ምስክሮችም ላይመጡ ይችላሉ። ከሳሽ የለሁበትም ሲል ወዲያውኑ ማንሳት አለበት። …” ፍርድ ቤቱ

ዐቃቤ ሕግ በቂሊንጦ ቃጠሎ ሰበብ በታሰሩት፣ በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ክስ መዝገብ (38) ተከሳሾች ላይ 85 ምስክር አስቆጥሯል። ዐቃቤ ሕግ ተደጋጋሚ ቀጠሮዎች ተሰጥተውት ምስክሮችን አሰምቷል። ከነሃሴ 1 እስከ ነሃሴ 12/2009 በነበረው ተከታታይ ቀጠሮ የተወሰኑ ካሰማ በኋላ፣ የ5 ወር ቀጠሮ ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010 ዓም በተሰጠው ቀጠሮ ጥቂት ምስክሮችን አሰምቷል። በዚህ ቀጠሮ ለተከታታይ 5ቀን ምስክር ሳያቀርብ ተከሳሾች ተመላልሰዋል። በ5ቱ ተከታታይ ቀናት ጉዳዩን የማያውቁ ዐቃቤ ሕጎች ተመላልሰዋል።ዛሬ ጉዳዩን የሚያውቁት ሶስት ዐቃቤ ሕጎች ተሰይመው ቀሪ 28 ምስክር ስላላቸው ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። አንድ ዐቃቤ ሕግ ቀጠሮው እስከ ጥር 7/2010 ስለመሰላቸው፣ በዚህ ጊዜ ለማቅረብ ሀሳብ እንደነበራቸው ገልፀዋል። ዐቃቤ ሕጎች ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጥያቄ ካቀረቡ በኋላ ጠበቆችና ተከሳሾች ተቃውሞ አቅርበዋል። በተለይ ተከሳሾች ምሬታቸውን ጭምር ገልፀዋል። ዐቃቤ ሕግ ተዘለፍኩ ብሏል። ፍርድ ቤቱ በመሃል ገብቷል። የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የነበረው ክርክር ከሞላ ጎደል እንደሚከተለው ቀርቧል።

~3ኛ ተከሳሽ አሸናፊ አካሉ:_ “በዚህ ችሎት 5አመት ተመላልሻለሁ። ዐቃቤሕግ ይጀምራል። ዐቃቤ ሕግ ይጨርሳል። ዐቃቤ ሕጉ መኩሪያ አለሙ ቀጠሮው እስከ ጥር 7/2010ዓም ስለመሰለኝ ነው ብሏል። በጣም ያሳዝናል። አምስት አመት በሙሉ ምንም ፍትሕ ሳላገኝ ተጨማሪ ቀጠሮ ይሰጠኝ የሚለው ሌላ ስድስተኛ አመት እንድታሰር ነው። እንደአለመታል ሆኖ እንጅ በሌላ ሀገር ከእግዚያብሔር ቀጥሎ ፍትሕ የሚሰጥ ፍርድ ቤት ነው። በእኛ ሀገር ግን በደሕንነት ብጣሽ ውቀትና ስልክ ትዕዛዝ ነው የሚሰራው። እስኪ ስልጣናችሁን ተጠቀሙበት! በጣም ያሳዝናል።”

~18ኛ ተከሳሽ አንጋው ተገኘ:_”(ዐቃቤ ሕጎች) ባህሪያቸው እንደዚህ ነው። ነሃሴ ላይ በነበረው ቀጠሮው ምስክር ሳያቀርቡ ብዙ ቀን አሳልፈዋል። እኛ ትግስት ያደረግነው እውነቱ እንዲወጣ ነው። 5ወር ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ምስክር ማቅረብ አልቻሉም። እነሱ በ5ውስጥ የወር ደሞዛቸውን ይወስዳሉ።……ምስክር የተባሉት ሰዎች አንመሰክርም ብለዋል። የመሰከሩትም “ቶርች”ተደርገው የመሰከሩ ናቸው። ከአሁን በኋላ ወደ ፍርድ ቤት መመላለስ አልፈልግም። ፍርድ ቤት በሌለሁበት የሚወስነውን ውሳኔ በማረሚያ ቤት ሆኜ እቀበላለሁ”
~13ኛ ተከሳሽ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ:_ “ሁሉ ነገር በፅሑፍ የለም። ዳኝነትም በህሊና ነው። ዐቃቤ ሕግ ቤተሰብ የምናስተዳድር፣ ህይወት የምንመራ ሰዎችን አስሮ በህይወታችን ላይ ቀልድ ነው የያዘው። በመጀምርያው 10 ቀን እንድታቀርብ ተብሎ በራሱ ቁጥጥር ስር ያሉትን ማቅረብ አልቻለም። ባለፈው ቀጠሮ ፖሊስ ምስክር ስላላመጣ ዐቃቤ ሕጉ ፖሊስ ያላቀረበው ቀጠሮው ለአንድ ቀን ብቻ ስለመሰለው ነው ብሎ ነበር። ላለፉት 5 ቀናት አላመጣም። በ5 ቀን ያላመጣውን በመላ ኢትዮጵያ ተፈላልገው ይምጡልኝ ማለት የሰውን ልጅ እንደሰው አለመቁጠር፣ ህሊና ቢስነት ነው።”

~1ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ:_ “ዐቃቤ ሕግን እንደተቋም ነው የምናየው። እነሱም ይላሉ። ከሆነ በየቀኑ የሚመጡት ዐቃቤ ሕጎች ተመሳሳይ ነገር መናገር ነበረባቸው። የሚሰጡት ማስተባበያ አሳፋሪ ነው። ለህግ እውቀት ላላቸው ደግሞ ይበልጥ ያሳፍራል። እኔ ከዚህ ፍርድ ቤትም፣ ከአምባገነኑ መንግስትም ፍትህ አልጠብቅም። ለታሪክ ነው የምከራከረው። የተገደሉት ወንድሞቻችን እንደኛ በማንነታቸው ተከሰው እስር ቤት የገቡ ናቸው። ከዐቃቤ ሕግ ለእኛ ይቀርባሉ። እኛም ሞት ተፈርዶብን ነበር። እንደ እድል ሆኖ በህይወት አለን።……… የተገረፍነውን ግርፋት ረስተን፣ ችለን ከዐቃቤ ሕግ ጋር እየተከራከርን ነው። እኛ ሞትን ተጋፍጠን ነው እየተከራከርን ያለነው። የታፈነው የነሃሴ 28/2010 (የቂሊንጦ ቃጠሎ) ታሪክ ትተነው የምናልፈው አይደለም። በዚህ ችሎት በተደጋጋሚ ቀርቤያለሁ። በዚህ ችሎት ምንም አይነት እምነት የለኝም። እናንተ ለእኛ መልካም ስትሆኑ በሙስና ትከሰሳላችሁ፣ለእኛ ክፉ ስትሆኑ ደግሞ ሹመት ይሰጣችኋል። ከዚህ አምባገነን መንግስት ጋር ተከራክሬ ፍትህ አገኛለሁ ብየ አልጠብቅም።

ውሃ እንኳን በህግ አምላክ ሲባል ይቆማል የሚል ማህበረሰብ ነው ያሳደገኝ።……እኔ በሙያዬ ስለ አየር ኃይል ልከራከር እችላለሁ። ስለ ፍትህ መከራከር ያለባችሁ እናንተ ናችሁ።”
~5ኛ ተከሳሽ አግባው ሰጠኝ:_” እኛ ያለነው በማረሚያ ቤት ነው። አንድ ቀን ባደርኩ ቁጥር ለህይወቴ እሰጋለሁ። እናንተ እስረኞችን በአደራ በማረሚያ ቤት አስቀምጣችኋቸው ሲሞቱ ለምን ሞቱ ብላችሁ አልጠየቃችሁም። እኔም በማረሚያ ቤት አንድ ቀንም እንድቆይ የሚያደርግ ቀጠሮ እንዲቀጠርብኝ አልፈልግም።”

~31ኛ ተከሳሽ ጌታቸር እሸቴ:_”እኛ የተከሰስነው ለምን ከእሳትና ከጥይት ተረፋችሁ ተብለን ነው። ክራውን ፍርድ ቤት ስንቀርብ መኩሪያ (ዐቃቤ ሕግ) አዎ ቀርጬሃለሁ ብሎኛል። የቀረፀኝ ለእኔም ለፍርድ ቤቱም ስለሚጠቅም እንዲያቀርብልኝ እፈልጋለሁ።30ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር ከመቀሌ ይመጣሉ ተብሏል። በእርግጥ ከመቀሌ ካልሆነ ከየትም ሊመጡ አይችሉም።……በድሉ በላይ የተባለ ምስክር በነፍስ የገባ፣ ሲገባ እኔ የተቀበልኩት ሰው ነው። ነፍስ አጥፍቶ የታሰረ ሰው መስክሮ ተፈትቷል። ምስክሮች ወንጀላቸው እየተነሳላቸው ከእስር በተፈቱበት ሁኔታ አላገኘናቸውም ማለት በእኛ ላይ ቁማር መጫወት ነው። ”
~38ኛ ተከሳሽ ከድር ታደለ:_ “……ከዐቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግራችሁ ነው የምትሰሩት? መስክሩ የሚባሉት ተገደው ነው። የተፈቱት መመስከር ስለማይፈልጉ ይጠፋሉ። ማረሚያ ቤት ውስጥ ያሉት መስክሩና ትፈታላችሁ ስለሚባሉ ይመሰክራሉ። መስክሩ ከእስር ትለቀቃላችሁ እየተባሉ ነው። ዛሬ ዐቃቤ ሕጎች እንደሰርግ አጃቢ ተሰብስበው የመጡት ቀጠሮ ለማስቀጠር ነው። እስከዛሬ ጉዳዩን የማያውቅ ዐቃቤ ሕግ ነበር የሚልኩት ። ፍርድ ቤቱ በዐቃቤ ሕግ ጥያቄ መሰረት ቀጠሮ የሚፈቅድ ከሆነ ከዐቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግሮ እንደሚሰራ 100 % ማረጋገጫ ይሆናል።

25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ:_ ምስክሮች ተለይተው አንድ ቦታ ነበር የተቀመጡት። እየመከሯቸው ይሆናል።…ዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን በጥንቃቄ መያዝ ነበረበት።…ከጫፍ እስከጫፍ መብቱን የጠየቀውን ስንት ሰው የሚያስር መንግስት ምስክሮችን ማምጣት አይከብደውም ነበር።……እነዚህን ዐቃቤ ሕግ ብሎ መጥራት አይቻልም። ዐቃቤ ሕግ በጥላቻ ግለሰብን የሚያጠቃ፣ ህሊና ቢስ አይደለም። መኩሪያ ሸዋሮቢት እስር ቤት መጥቶ “የመንግስት ስም ከሚጠፋ እናንተ ብትጠፉ ይሻላል” ብሎናል።……
~አንተነህ አያሌው (ዐቃቤ ሕግ):_ እኛ እዚህ የምንቀርበው ህጋዊ ክርክር ለማድረግ እንጅ ማንም እንዲሰድበን አይደለም። እስካሁን ባደረግነው ክርክር የማንንም ተከሳሽ፣ ወይም ጠበቃ ስም አንስተን አልዘለፍንም። ማንም እየተነሳ ህሊና ቢስ እያለ እያደበን ፍርድ ቤቱ ዝም እያለ ቆመን ቆመን መከራከር አንችልም። ተከራካሪ ወገኖችን ለማሸማቀቅ እየተሰራ ነው። እኛ፣ ፍርድቤቱ እና ህብረተሰቡ እየተዘለፈ ነው።
~መኩሪያ አለሙ(ዐቃቤ ሕግ):_ የህግ ባለሙያ ነኝ ተቋሙ በላከኝ ቦታ ሄጄ እሰራለሁ።ሸዋሮቢት የተከሳሾችን አያያዝ አጣራ ተብሎ ሄጃለሁ። እንደ ባለሙያ ሁለት ተከሳሾችን አነጋግሬያለሁ። እዛ ቦታ ላይ የተነገረውን ብናወራው ተከሳሾችን ይጎዳል። እኔ ለህሊናዬ የምኖር ሰው ነኝ። ስሜ መጥፋት የለበትም። እኔ እንደዛ ባደርግ እንኳ ተቋሙ ነው የሚከራከረው። የተማርኩትም ያሳደገኝ ማህበረሰብም እንዲህ ነገር አላስተማረኝም።

~ካሳሁን አውራሪስ (ዐቃቤ ሕግ):_ በዚህ አይነት ክርክር የግለሰብ ስም በመጥራት መከራከር ጉዳዩን አቅጣጫ የሚያስቀይር ነው። ችሎት ተደፈረ የሚባለው ችሎቱ ሲዘለፍ ብቻ አይደለም። ህሊና ቢስ እየተባልን እየተዘለፍን ነው።……
~ፍርድ ቤቱ (መሃል ዳኛው):_ ሰው መብቱን ለመጠቀም ተብሎ የሚናገረውን ቃል ከወጣ በኋላ መመለስ አይቻልም። ነገር ግን የችሎቱን ክብር በሚጠብቅ መልኩ ማነገር ይገባል። … ዐቃቤ ሕግ ያቀረቡትም ይህን ነው። የዳኛ ስራ ከትምህርት ቤት የተለየ ነው። የተከሰሰ፣ ከሳሽ፣ የተጎዳውም ሀሳቡን የሚያቀርበው ፍርድ ቤት ነው። ሀሳቡን ሲገልፅ ግን ለዳኞች ፈተና ነው። እንደትምህርት ቤት አይደለም። ጎጅውም ተጎጅውም በአካል ነው የሚመጡት።ዳኞች ፈተና ውስጥ ይገባሉ። ፈተናውን ለመቋቋም የችሎቱ ሂደት ሰላማዊ መሆን አለበት።…… ትርፍ ነገር ይነገራል። ይህን ስንገድብ ሌላ ይቀራል በሚል እንታገሳለን። መታገሱ ለህግ የበላይነት ይጠቅማል። ኮሽ ባለ ቁጥር አይተኮስም እንደተባለው ነው። በተናገራችሁ ቁጥር 1 አመት ብንቀጣ 25 አመት ይደርሳል። መሳደብ አይጠቅምም። አፍ መያዝ ግን አንችልም።…… በሚዲያ የሚነገር ነገር አለ።ተፅዕኖ ያመጣል። ምስክሮችም ላይመጡ ይችላሉ። ከሳሽ የለሁበትም ሲል ወዲያውኑ ማንሳት አለበት። ……የፍርድ ቤት ክብር የእኔ አይደለም። በክብር የተቀመጠው ሰው ጭምር ነው።…”
~25ኛ ተከሳሽ ደረጀ መርጋ:_ የፍትህ አካሉንም እውነቱ እንዲወጣ እንከራከራለን። የተገደሉት ወንድሞቻችን ናቸው። ሲገደሉ በአይናችን አይተናል። ያም ሆኖ ገድላችኋቸዋል ተብለን ተከሰናል። ይህ ሁሉ ስሜታዊ ያደርገናል።…… ዐቃቤ ሕግ የሚያቀርባቸው ምክንያቶች ምክንያታዊ የሚያደርጉ አይደሉም። ፍርድ ቤቱ ይህን አይቶ ውሳኔ እንዲሰጥ ነው።

~22ኛ ተከሳህ ሚፍታህ ከደር:_ በዚህ ሀገር የዐቃቤ ሕግ ስልጣን ገደብ ሊኖረው ይገባል። ከታሰርኩ አራት አመት ሊሞላኝ ነው። ባልተጣራ ክስ ከሶኝ ነፃ ተብያለሁ። አሁን ደግሞ ሌላ ክስ አቅርቦብኛል። የተከሰስኩት በማንነቴ ነው። በፈለገው ወንጀል እየከሰሰ የፈለገውን ያህል ያስራል። ይህን በማድረጉ አይጠየቅም። እኛ ደግሞ አንካስም። የተወሰኑ ሰዎች እንዳይከሰሱ ሲባል ዐቃቤ ሕግ ሸዋሮቢት ሄጀ አነጋግሬያቸዋለሁ ብሏል። ስለተፈፀመብን ነገር ግን አልገለፀም። ሰብአዊ መብት ግን ጥፍራችን መነቀሉን፣ ጣታችን መሰበሩን…መገረፋችን ገልፆአል። የትኛው ነው እውነቱ? ገዳይ ነው እየመሰከረብን ያለው። ኦፊሰር ገ/ማርያመው ሲገድል እያየን ነው መጥቶ የመሰከረብን። ክሱ ላይ ያልተጠቀሰ 24ኛ ሰው መሞቱን መስክሮ ሄዷል። ቴዎድሮስ የሚባለው ሟች በክሱ አልተጠቀሰም።…… በማናውቀው ጉዳይ ነው የተከሰስነው። ከፍተኛ በደልና ስቃይ እየደረሰብን ነው። አንድ ፍራሽ ላይ ለሁለት ነው የምንተኛው።

~34ኛ ተከሳሽ ፍፁም ጌታቸው:_ ለሞቱት ነው የምንከራከረው ብለዋል። የሞተውኮ ከ150 ሰው በላይ ነው። ዞን 5 አርማዬ ዋቄ ተደብስቦ ነው የተገደለው። እነዚህ ገዳዮች አይጠየቁም? ……ከዚህ ችሎት ከሚከታተለው መካከል የሟች ቤተሰብ አለ? በመኪና አደጋ የሞተ ሰው ቤተሰብ እንኳ ችሎት ይታደማልኮ!
~36ኛ ተከሳሽ ካሳ መሃመድ:_ፍርድ ቤቱ ማረሚያ ቤት ውስጥ ያለውን ችግር ይወቅልን። ዞን 5 ያለን እስረኞች ኦፊሰር ገብረማርያም መስክሮ ከሄደ በኋላ ማስፈራሪያ እየደረሰብን ነው። ኦፊሰር ጉኡሽ መለስ ምስክርነቱ ይለቅና እንተያያለን እያለ እየዛተብን ነው። በህይወት እንድንቆይ ካስፈለገ ማረሚያ ቤቱ ጉዳይ መስተካከል አለበት።አሁንም እኛን ገድለው ሌላ የአማራና የኦሮሞ ልጆችን እኛን ገደላችሁ ብለው ይከሷቸዋል። እዚህ ወንበር ላይ የመሰከረው ገብረማርያም በጥይት እደፋሃለሁ ብሎኛል። እነ ካሳ መሃመድ፣ ተመስገን ማርቆስ፣አሸናፊ መለስ፣ ሚስባህ ከድር፣ አጥናፉ አበራ ቀይ መስመር አልፈዋል ዋጋቸውን ያገኛሉ ተብለናል። እኔ የድንግል ማርያም ልጅ ነኝ፣ በእናቴ ፀሎት እወጣለሁ። የእኛ አልበቃ ብሎ ሀገራቸውን ለማገልገል የመጡ ምሁራን ከእኛ ጋር ተከሰው እየተሰቃዩ ነው። ……ከእነ አግባው ጋር ዝዋይ ተወስደን፣ ራቁታችን በፓንት ብቻ ሆነን ተደብድበናል።……ይህ የለበስኩት ልብስ የተገደለው ጓደኛዬ የአርማዬ ዋቄ ልብስ ነው። ጫማውም የእሱ ነው። ከዝዋይ ስንመለስ ገድለውታል። እነ ገብረማርያም የህወሓትን ተልዕኮ ለማስከበር ነው። እኛ ደግሞ መብታችን ለማስከበር ፍርድ ቤት እንናገራለን። ቶርች ሲያስደርጉን የነበሩት ጌታቸው አምባዬ ናቸው። እግርና እጃችን በካቴና አሳስረውናል።… በሀገራችን ተገልብጥን ተገርፈናል። ኩላሊት በሽተኛ ሆነን ነው ተገልብጠን የተገረፍነው። ኧረ ስለመድሃኒያለም! እነሱ የተጨመቀ ቡና ሲጠጡ እኛ እየተጨነቅን ነው። እነሱ ዝልዝልና ቁርጥ ሲበሉ እኛ እየተዘለዘልን ነው።

(ፍርድ ቤት ዐቃቤ ሕግ ቀሪ 28 ምስክሮችን ለማቅረብ ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው ያነሳውን ጥያቄ፣ የተከሳሽ ጠበቆችና ተከሳሾች የዐቃቤ ሕግን ጥያቄ በመቃወም ምስክርነቱ ታልፎ ብይን እንዲሰጥ ያቀረቡትን ተቃውሞ ለመበየን ለነገ ጥር 4/2010ዓም ቀጠሮ ይዟል። በሌላ በኩል የቂሊንጦ ጥበቃና ደህንነት ኃላፊ ምስክርነት ከሰጡ በኋላ ኃላፊውን በችሎት ተናግራችኋል በሚል በማረሚያ ቤት ዛቻ እየደረሰብን ነው ያለው ካሳ መሃመድ አቤቱታውን በፅሁፍ አቅርቦ እንዲጣራ ፍርድ ቤቱ ገልፆለታል። ጉዳዩ ከምስክር አሰማም ጋር የተገናኘና ዝም ተብሎ መታለፍ ስለሌለበት ይጣራል ብሏል።)

አራት የኦፌኮ አመራሮች ተፈረደባቸው

~የኦፌኮ አመራሮችን ደግፈው ያጨበጨቡ የግንቦት 7 ተከሳሾች ተፈርዶባቸዋል
ጌታቸው ሺፈራው
Bekele Gerba et al.
ፎቶ፡ እነ በቀለ ገርባ (ከማኅበራዊ ገፅ የተወሰደ)

ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ንቅናቄ የተከሰሱት አራት የኦፌኮ አመራሮች ዛሬ ጥር 3/2010 በችሎት መድፈር ቅጣት ተወስኖባቸዋል። በእነ ጉርሜሳ አያኖ ክስ መዝገብ የተከሰሱት ጉርሜሳ አያኖ፣ ደጀኔ ጣፋ፣ አዲሱ ቡላላ እና በቀለ ገርባ በመከላከያ ምስክርነት የጠቀሷቸው እነ ለማ መገርሳ እንዲሁም በእስር ላይ የሚገኘው አንደየዓለም በምስክርነት እንዳይቀርቡ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ብይን በሰጠበት ወቅት ተቃውሞ በማሰማታቸው ችሎት ደፍራችኋል በሚል እያንዳንዳቸው 6 ወር ተፈርዶባቸዋል።

ፍርድ ቤቱ ” በሚረባና በማይረባ ጉዳይ የመንግስት ባለስልጣናት ለምስክርነት መቅረብ የለባቸውም” በሚል ባለስልጣናቱ በምስክርነት እንዳይቀርቡ ውድቅ ያደረገ ሲሆን አቶ በቀለ ገርባ “በሚረባና በማይረባ እያላችሁ የምትጠቀሙት ቃል ከእናንተ የሚጠበቅ አይደለም” ማለታቸውን ችሎቱ የታዘቡ ገልፀዋል። አቶ ደጀኔ ጣፋ በበኩላቸው “አቃቤ ህግ አመራሮችን ጠርቶ አስመስክሮብናል። እኛ አመራሮችን በምስክርነት ስንጠራም መመስከር የለባቸውም ሊባል አይገባውም” ሲሉ በችሎቱ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።
ተከሳሾቹ “ደም ደም ትሸታላችሁ፣ 26 አመት ሙሉ የኦሮሞን ህዝበ ገድላችኋል፣ 26 አመት ሙሉ በኢትዮጵያ ህዝብ ደም ተጨማልቃችኋል፣ ሞት በእኛ ይብቃ ” ሲሉ እንደተናገሩና እንደዘመሩም ታውቋል። አመራሮቹ በፍርድ ቤቱ ውሳኔ ተቃውሞ በማሰማታቸው በችሎት መድፈር በተፈረደባቸው ወቅት ፍርድ ቤቱ ሲያነብ አንሰማም ብለዋል።

በእነ በለጠ ክስ መዝገብ በግንቦት 7 የተከሰሱት 3 ተከሳሾችም፣ እነ ጉርሜሳ ሲፈረድባቸው አጨብጭባችኋል በሚል በችሎት መድፈር 3 ወር ተፈርዶባቸዋል። 3 ተከሳሾች “ለምን አጨበጨባችሁ?” ተብለው በፍርድ ቤት ሲጠየቁ “ወንድሞቻችን ስለሆኑ ነው” ብለው መልስ መስጠታቸው ታውቋል። ከችሎት ወጥተው የእስረኞች ጊዜያዊ ማቆያ የነበሩ እስረኞችም በኦሮምኛ ሲዘምሩ ተደምጠዋል። በአማርኛም “ሞት በእኛ ይብቃ! ደም ደም ይሸታል ቤቱ፣ የፍርድ ቤቱ! ” እያሉ ሲዘምሩ ተሰምተዋል።

በተያያዘ ዜና መንግስት የፖለቲካ እስረኞችን እፈታለሁ ብሎ መግለጫ ከሰጠ በኋላም የፖለቲካ እስረኞች እየተፈረደባቸው ነው። ትናንት ጥር 1/2010 ዓ•ም የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በግንቦት 7 ክስ የተመሰረተባቸው በእነ ትንሳኤ በሪሶ ክስ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ ግሩም አስቀናው ላይ የ4 አመት ፍርድ ውሳኔ አስተላልፏል።

ፍርድ ቤቱ የ”ወንጀሉን” ደረጃ በመከካለኛ በመያዝ መነሻ ቅጣቱን 7አመት አድርጎ፣ በአራት ማቅለያዎች 4 አመት ፅኑ እስራት ፈርዶበታል። አቶ ግሩም አስቀናው የሰው ምስክር እና ቃል ማስረጃ የሌለበት ሲሆን በሰነድነት የተያያዘበት የስልክ ማስረጃም ከእሱ ስልክ ያልገኘ እንደሆነ ሲከራከር ቆይቷል።
መንግስት በቅርቡ በሰጠው መግለጫ የፖለቲካ እስረኞችን እፈታለሁ ቢልም እስረኞች ይፈታሉ ተብሎ በሚጠበቅበት ወቅት እንደ ግሩም ቅጣት የተላለፈባቸው፣ እንዲከላከሉ የተበየነባቸውም የፖለቲካ እስረኞች ይገኙበታል።

%d bloggers like this: