የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋች እና ጦማሪ ስዩም ተሾመ በማዕከላዊ እስር ቤት የመብት ጥሰት ተፈፀመበት
(ዳጉ ሚዲያ) የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋች፥ የኢትዮ ቲንክታንክ እና ማኀበራዊ ገፅ ጦማሪ ስዩም ተሾመ ከሚኖርበትና ይሰራበት ከነበረው ወሊሶ ከትማ በፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እስር ቤት ከፍተኛ ስቃይና እንግልት እንደተፈፀመበት ተጠቆመ።
ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ. ም. ጀምሮ በድጋሚ ለ6 ወራት የሚቆይ የአቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ በተደረገ ሳምንት ሳይሞላው ስዩም ተሾመ ከመኖሪያ ቤቱ ታፍኖ ማዕከላዊ በሚባለው የፌደራል ወንጀል ምርመራ ማዕከል ከፍተኛ ምርመራ እየተደረገበት ሲሆን፤ የአገዛዙ መርማሪዎች አካላዊ ጥቃት በመፈፀምና በማስገደድ የሚጠቀማቸውን የኮምፒዩተርና የኢንተርኔት አገልግሎት የይለፍ ቃሎች(ፓስ ወርድ) መወሰዱም ታውቋል። መርማሪ ፖሊሶችም የፍርድ ቤት ክስ በመመስረት ተጨማሪ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ በጠየቁት መሰረት እንደተፈቀደላቸውም ለማወቅ ተችሏል። ስዩም ተሾመን ማዕከላዊ ምርመራ በመሄድ ለመጎብኘት የሞከሩ ወዳጆቹ፥ የመብት ተሟጋቾችና የስራ ባልደረቦቹ እንዳይጎበኙት መከልከላቸውም ታውቋል።
ስዩም ባለፍው ለ10 ወራት ተግባራዊ ተደርጎ በነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተመሳሳይ መልኩ ከመኖሪያ ቤቱ በገዥው ስርዓት የፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በምርመራ ወቅት ከፍተኛ የአካል ጥቃት ተፈፅሞበት እንደነበርና ከተወሰኑ ወራት እስር በኋላ መለቀቁ ይታወሳል።
በሞያሌ 10 ያህል ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተገደሉ
(ዳጉ ሚዲያ)ትናንት ቅዳሜ መጋቢት 1 ቀን 2010 ዓ.ም በደቡብ ኢትዮጵያ፥ቦረና ዞን የሞያሌ ከተማ በገዥው መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት የፀጥታ አባላት 10 ሰላማዊ ዜጎች ሲገደሉ 11 ያህሉ መቁሰላቸውን የዓይን እማኞችን እና የከተማውን ከንቲባ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል።
ግድያውን በተመለከተ በአስቸኳይ አዋጁ መሰረት የመላ ሀገሪቱን አጠቃላይ የጠጥታ እና የተፈጥሮ ሃብትን በበላይነት እየተቆጣጠረ ያለው የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያት በበኩሉ በተፈጠረ የመረጃ ስህተት ምክንያት 9 ሰላማዊ ዜጎች በስሩ ባሉ የፀጥታ ኃይሎች 9 ሰላምዊ ዜጎች መገደላቸውን እና 12 ያህል መቁሰላቸውን አስታውቋል።
ግድያው የተፈፀመው በከተማው በተለምዶ ሸዋበር በሚባል ሰፈር ሲሆን፤ በወቅቱ በአካባቢው ምንም ዓይነት ህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ባልነበረበትና ዜጎች በተለመደ ሰላማዊ መደበኛ ዕለታዊ እንቅስቃሴ እያሉ ግድያው በጅምላ መፈፀሙን የከተማው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በተለይ ጥቃቱ በሚፈፀምበት ወቅት በመዝናኛ ስፍራ የነበሩ፥ በምግብ ቤትና በሱቅ ግብይት ላይ የነበሩና መንገድ ላይ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል።
በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ ም የታወጀው እና ለ6 ወራት የሚቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ክልል ባሉ የተለያዩ ከተሞች በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በኮማንድ ፖስቱ የፀጥታ አባላት መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ የሞያሌው የጅምላ ግድያ ተጨማሪ ጥቃት መሆኑ ታውቋል። የጅምላ ጥቃቱን ተከትሎም በርካታ የከተማው ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሀገር ኬንያ ተሰደዋል።
ቀደም ሲል የመብት ተሟጋች ኢትዮጵያውያን፥ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፥ ዓለም አቀፍ ይሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት፥ የአሜሪካ መንግሥትና የአውሮፓ ህብረት አባላት እና የገዥው መንግሥት አካል የሆኑ በርካታ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተግባራዊ እንዳይደረግ ተቃውመውት እንደነበር አይዘነጋም። ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየተፈፀመ ያለው ግድያ እና እስር ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል።