Daily Archives: March 29th, 2018

በአዲስ አበባ እና በባህርዳር ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች እና ፖለቲከኞች ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለቀናት በአደራ እስር ላይ ይገኛሉ

(ዳጉ ሚዲያ) በቅርቡ የተደረገውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ከዓመታት እስር በኋላ የተለቀቁ ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች፥ ፖለቲከኞችን ጨምሮ ሌሎች የመብት ተሟጋቾችን ጨምሮ ያለ በቂ ምክንያት ከመጋቢት 16 ቀን 2010 ዓ.ም.ጀምሮ በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ከነበሩበት የምሳ እና የ “እናመሰግናለን” ግብዣ ላይ በነበሩበት ወቅት በድጋሚ ታስረዋል።

በድጋሚ ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፥ አቶ አንዷለም አራጌ፥ ጦማሪ ዘላላም ወርቃገኘው፥ ወ/ት ወይንሸት ሞላ፥ ጦማሪ ማህሌት ፍንታሁን፥ ጦማሪና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ሀይሉ፥ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፥ አቶ ይድነቃቸው አዲስ፥ አቶ አዲሱ ጌታነህ፥ አቶ ተፈራ ተስፋዬ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ልዩ ስሙ ጎተራ ፖሊስ በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከመደበኛ ሥራቸው ተይዘው ከታሰሩት መካከል የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋችና ጦማሪ ስዩም ተሾመ እንዲሁም የመብት ተሟጋች እና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የፍትህ ቢሮ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደዓ በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ወህኒ ቤት ታስረው ይገናሉ።

Ethiopian re-arrested political Prisoners
በቅርቡ ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች መካከል በከፊል

በተያያዘ ዜና የአማራ ህዝብን ከአገዛዙ ጥቃት ለመከላከል በሚል በህጋዊ መንገድ የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅት ለመመስረት በይፋ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ የአካባቢ አስተባባሪዎች መካከል ከሌሎች ወዳጆቻቸው ጋር በመሆን በጋራ በመሆን ሰኞ መጋቢት 17 ቀን 2010 ዓ ም ባህርዳር ከተማ ተሰብስበው እራት ሲመገቡ በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው ከታሰሩ በኋላ ድብደባ እንድተፈፀመባቸው ተጠቆመ። ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በበእስር ላይ የሚገኙት ምሁራን፥ ፖለቲከኞች እና በዕለቱ በጓደኝነት እራት ግብዣው ላይ የተገኙ ጋዜጠኞች በባህርዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ይገኛሉ።

በባህር ዳር ከተማ ተይዘው ከታሰሩት መካከል ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ (ባህርዳር ዩንቨርሲቲ መምህርና የጣና ደህንነትና የአካባቢ ጥበቃ ማህበር ፕሬዚደንት እና ተመራማሪ፣ ረዳት ፕሮፊሰር)፥ ጋሻው መርሻ (የአንጸባቂው ኮከብ መጽኃፍ ከታቢ፤ አዲስ አበባ በማስተማር ሙያ ላይ ይገኛል)፥ የሱፍ ኢብራሂም (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበረና በአሁንኑ ወቅት ጠበቃ)፥ ተመስገን ተሰማ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር፤የወሎ ዩኒቨርስቲ የህግ ትምህርት ቤት መስራች፣ ረዳት ፕሮፊሰር እና አማራ ነን የሚለው መዝሙርም ገጣሚ)፥ በለጠ ሞላ ( ተባባሪ ፕሮፊሰር ፡አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ ጋዜጠኛ ንጋቱ አስረስ (የአማራ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ(አርታኢ)፤ከ1997 እስከ 1999 የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአማራ ተማሪዎች ማህበር ፕሬዜዳት፤)፥ ጋዜጠኛ በለጠ ካሳ (የቀለም ቀንድ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረ)፥ አቶ ሲሳይ አልታሰብ( ሲቪል ኢንጅነር)፥ አቶ ዳንኤል አበባው፥ አቶ መንግስቴ ተገኔ፥ አቶ ቦጋለ አራጌ፥ አቶ ካሱ ኃይሉ (የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ መምህር፡የማህበረሰብ ሳይንስ ተመራማሪ)፥ አቶ ተሰማ ካሳሁን፥ አቶ ድርሳን ብርሃኔ፥ አቶ በሪሁን አሰፋ፥ አቶ ፍቅሩ ካሳው፥ አዲሱ መለሰ (የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ መምህር)፥ አቶ ተመስገን ብርሃኑን ጨምሮ አንድ ስማቸው ያልተጠቀሰ ግለሰብም በእስር ላይ ይገኛሉ።

በአዲስ አበባ እና በባህርዳ ይታሰሩት ሁሉም ተከሳሾች ክስ እንዳልቀረበባቸውና የታሰሩበትም ምክንያት እንዳልታወቀ የተገኘው መረጃ አመልክታል። ይህንንም ተከትሎ ሐሙስ ምሽት መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ ም የተለያዩ ማኀበራዊ ሚዲያን በመጠቀም #ሁሉም_የፖለቲካ_እስረኞች_ይፈቱ የሚል ዘመቻ የተደረገ ሲሆን፤ ከአሰራቸው የመንግሥት አካል ግን የተሰጠ ምላሽ የለም።

አዲሱ የኢህአዴግ ሊቀመንበር ዶ/ር አብይ አህመድ በመጪው ሰኞ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን ሥራቸውን በይፋ እንደሚጀምሩ ይጠበቃል

(ዳጉ ሚዲያ)የአራት ፓርቲዎች ግንባር አባል የሆነው የኦህዴድ ሊቀመንበር ዶ/ር አብይ አህመድ መጋቢት 18 ቀን 2010 ዓ.ም. የኢህአዴግ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡ ሲሆን፤ የብአዴን ተወካይና ሊቀመንበር አቶ ደመቀ መኮንን በፊት በነበሩበት ምክትል ሊቀመንበር ሆነው እንዲቀጥሉ ተወስኗል። በተለመደው የኢህአዴግ አሰራ መሰረት አዲሱ የኢህአዴግ ሊቀመንበር ዶ/ር አብይ አህመድ በመጪው ሰኞ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመገኘት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን ቃለ መሃላ በመፈፀም በይፋ ሥራ ይጀምራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

Dr Abiy Ahmed

ዶ/ር አብይ አህመድ (ፎቶ፡ ወልስትሬት ጆርናል)

ገዥው ኢህአዴግ መጋቢት 18 ቀን 2010 ዓ.ም. የድርጅቱ ሊቀመንበር አድርጎ የመረጣቸው ዶ/ር አብይ አህምድ አሊ የተለያየ የሥራ ልምድና የትምህርት ዝግጅት እንዳላቸው መረጃዎች ይጠቁሟሉ። ዶ/ር አብይ በጅማ ዞን አጋሮ ከተማ የተወለዱ ሲሆን፤ በመንግሥት የሥራ ድርሻ በመከላከያ ሚኒስቴር የወታደራዊ ደህንነት እና መገናኛ ኃላፊ በመሆን የሌተናል ኮሎኔል ማዕረግ አላቸው። ከውትድርና ዓለም ከተሰናበቱ በኋላ የፌደራሉ የሳይንስና ቴክኖሎጂ የልቀት ማዕከል ዋና ዳይሬክተር፥ የሀገሪቱ የስለላ ተቋም የሆነው የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ መስራችና ምክትል ዳይሬክተር፥ የፌደራሉ የሳይንስና ቴኬኖሎጂ ሚኒስትር፥ የኦሮሚያ ክልል የከተማ ልማት እና ቤቶች ቢሮ ኃላፊ፥ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዘዳንት እና የኦህዴድ ዋና ጸሐፊ በመሆን ማገልገላቸው ታውቋል።

የ42 ዓመቱ ዶ/ር አብይ በትምህርት ዝግጅታቸው በኮምፒዩተር ሳይንስ ምህንድስና አዲስ አበባ ከሚገኘው ማይክሮሊንክ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኮሌጅ የመጀመሪያ ድግሪ፥ ድህረ ምረቃ በክሪፕቶግራፊ ከደቡብ አፍሪካው ማኪሄ ዳይናሚክስ ተቋም፥ ድህረ ምረቃ በለውጥ አመራ ከግሪንዊች ዩኒቨርሲ፥ ድህረ ምረቃ በንግድ አስተዳደር ከአሽላን ዩኒቨርሲ እንዲሁም ዶክተሬት ድግሪ በሰላም እና ደህንነት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲ አግኝተዋል።

አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ከፖለቲካ ህይወትና ከመደበኛ ሥራቸው በተጨማሪ በብዕር ስማቸው “እርካብ እና መንበር” የሚል መፅሐፍ ለንባብ አብቅተዋል። ዶ/ር አብይ አህመድ ከወ/ሮ ዝናሽ ታያቸው ጋር ትዳር በመመስረት የ3 ሴቶች ልጆች አባት ሲሆኑ፤ በመጪው ሰኞ ሥልጣናቸው የሚያስረክቡት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝን በመተካት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ቃለ መሃላ እንደሚፈፅሙ ይጠበቃል።

ዶ/ር አብይ በኦሮሚያ ክልል በቅርቡ ወደ አመራር ከመጡትና በህዝቡ ዘንድ ከፍተና ተቀባይነት ካገኙት የአቶ ለማ መገርሳ ቡድን አባል ሲሆኑ፤ ከአገዛዙ መሪዎች ባልተለመደ መልኩ ንባብ፥ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት፥ መማርና ማወቅ እንዲሁም ብሄራዊ የሀገር አንድነትና ውይይቶችን እንደሚያብረታቱ በተለያዩ መድረኮች ሲገልፁ ተስተውሏል። ይሁን እንጂ አሁን በሚመሩት የኢህአድግ አገዛዜ በሀገሪቱ ያለውን የነፃ ፕሬስ፥ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ፥ በሙያ የመደራጀት፥ የመሰብሰብ፥ የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበርና መተግበር በተፃፈና ባልተፃፈ የድርጅታቸው ሕግ ገደብ የተጣለባቸው በመሆኑ፤ ሲናገሩ የነበሩትን ለመተግበር ከወዲሁ ብርቱ ፈተና ይጠብቃቸዋል። በተጨማሪም የድርጅቱ ሊቀመንበር ሆነው በተመረጡበት ወቅት በድጋሚ የታሰሩት ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾችና የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በአስቸኳይ አዋጅ ስም ለእስር ተዳርገዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ዶ/ር አብይ መሪ ሆነው በተመረጡበት ወቅት ሀገሪቱ ከፍተኛ የፖለቲካ፥ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያ ቀውስ ውስጥ ባለችበት ወቅት ወደመሪነት የመጡ ሲሆን፤ በተለይ በኦሮሚያ፥ በአማራ እና በከፊል በደቡብ ክልል ተከታታይ የሆነ ከፍተኛ የሆነ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ እንደነበር ይታወሳል። 180 አባላት ባአሉት እና በዕለቱ 170 ብቻ በተገኙበት የኢህአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ በርካታ ቀናት በፈጀ አለመግባባትና ውጥረት በኋላ በተደረገው ውድድር የድርጅቱ ሊቀመንበር ውድድር የኦህዴድ ተወካይና ሊቀመንበር ዶ/ር አብይ አህመድ 108 ድምፅ፥ የደኢህዴን ተወካይና ሊቀመንበር አቶ ሺፈራው ሽጉጤ 59 ድምፅ ሲያገኙ የህወሓት ተወካይና ሊቀመንበር ዶ/ር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል 2 ድምፅ በማግኘት አሸናፊው ታውቋል። በወቅቱ የብአዴን ተወካይና ሊቀመንበር የነበሩት አቶ ደመቀ መኮንን ምርጫው ሊጀምር ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩ ከውድድሩ ራሳቸውን ማግለላቸውም ተሰምቷል።

ምንም እንኳ ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዳንድ የተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ የመልካም ምኞች የገለፁላቸው በርካታ ዜጎች ቢኖሩም፤ በተለይ የመብት ተሟጋቾች፥ ጋዜጠኞችና የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትና አመራሮች በእስር የሚገኙ የፖለቲካ እስረኞች መፈታት፥ የአፋኝ ህጎች መሻሻል እንዲሁም የዴሞክራሲያዊ ተቋማት ለውጥ መደረግ በቅድሚያ ተግባራዊ መደረግ እንዳለባቸው ሳይገልፁ አላለፉም። በተለይ የተለመደው የአገዛዙ አፋኝ ህጎች እና አምባገነናዊነት ካልተሻሻለ እንዲሁም በህግ የተሰጣቸው ሥልጣን ተጠቅመው የራሳቸውን አዳዲስ ካቢኔ አባላትን በራሳቸው አቋቁመው ሥራ ካልጀመሩ የእርሳቸው መምጣት ብቻውን ለውጥ አያመጣም የሚል ጥርጣሬ ያላቸው ዜጎች በርካታ ናቸው።

በሀገሪቱ ካለው አፈና በተጨማሪ የሥራ አጦች ብዛት እየጨመር መሄድ፥ ሙስና፥ አድሏዊ አሰራር፥የፍትህ መጓደል፥ የዜጎች ነፃነት ማጣት እርምት የሚያሻቸው አንገብጋሚ ጉዳዮች ቢሆኑም የትኞቹን ቅድሚያ ሰጥው ሊተገብሩ እንደሚችሉ ሰኞ ከሚሰጡት መግለጫ እና እቅድ በተጨማሪ በተግባር የሚታይ ይሆናል።

%d bloggers like this: