Category Archives: Human Rights

በጋምቤላ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰማ

ባለፈው ሳምንት ጥር 19 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል በተከሰተው የብሔር ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰምቷል፡፡ የግጭቱ መንስኤ እስካሁን በገለልተኛ አካል ባይታወቅም ግጭቱ በክልሉ ነዋሪ በሆኑ አኝዋክና ኑዌር ማኀበረሰብ መካከል በተፈጠረ ግጭት እንደሆነ ይነገራል፡፡

Gambella Public Counsel

የማዕከላዊ መንግሥት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩሉ የሟቾች ቁጥር 14 ነው ግጭቱም በቁጥጥር ስር ውሏል ቢሉም፤ የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ኢታንግ ወረዳ አስተዳደር አቶ ኦኬሎ ኦባንግ በበኩላቸው ብዙ ሰዎች እንደሞት እንደሚነገርና በአሁን ወቅት የሟቾችን ቁጥር በርግጠኝነት መግለፅ እንደማይቻል ለብሉንበርግ ተናግረዋል፡፡

ለግጭቱ ምክንያት ሊሆን ይችላል ተብሎ የተገመተው በአካባቢው የደደቡብ ሱዳን አማፂ መሪ ሬክ ማቻር ደጋፊ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ከ264 ሺህ በላይ የኑዌር ጎሳዎች በክልሉ ኢታንግ ወረዳ መስፈራቸውና በአካባቢው ማኀበራዊ መስተጋብር ላይ ተፅዕኖው እየበረታ ነው በሚል እንደሆነም ቢነገርም ከመንግሥትም ሆነ ከዓለም አቀፉ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹ አሳድረዋል ስለተባለው ተፅዕኖ የተገለፀ ነገር የለም፡፡
የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ በአካባቢው የፀጥታ ኃይሎች እና በማኀበረሰቡ መካከልም አለመግባባቶች እንደተፈጠሩ በዚህም በርካታ ሰዎች መጎዳታቸውን እና የመኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

ከግጭቱ ጋ በተያያዘም በርካታ ሰዎች በክልሉ ዋና ከተማ ጋምቤላ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውንና ጉዳት የደረሰባቸው የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡

የመሬት ቅርምት እና ውጤቱ

ብስራት ወልደሚካኤል

በኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ ባለ ሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ ዕድገት አስመዝግቢያለሁ ሲል ይሰማል፡፡ በተለይ 11 በመቶ በተደጋጋሚ ዓመታዊ የኢኮኖሚ ዕድገት አስመዝግቢያለሁ ፣የምግብ ዋስትናን አረጋግጫለሁ ካለ ሰነባብቷል፡፡ ነገር ግን ተጨባጭ እውነታዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ የተባለ ባለሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ ዕድገት በመን እና እንዴት እንደመጣ፣ የት ማን ተጠቃሚ ሆነ የሚሉ ጥያቄወች ግን መልስ አይሰጥባቸውም፡፡

በዚህ ሁኔታ ዛሬ ላይ አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ የሚፈልጉ ዜጎች ቁጥር ከ15 ሚሊዮን ወደ 18 ሚሊዮን ማሻቀቡን ዓለም አቀፍ መረጃዎች እያመለከቱ ነው፡፡ በተለይ የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት በኢትዮጵያ የተከሰተው ርሃብ ሀገሪቱ በታሪኳ አይታው በማታውቀው መልኩ ከፍተኛ ህዝብ መራቡን እና አፋጣኝ ምላሽ ከዓለም አቀፍ ለጋሽ ሀገሮችና ተቋማት ካልተሰጠ ችግሩ ከዚህም ሊከፋ እንደሚችል በተደጋጋሚ የተማፅኖ እና ማስጠንቀቂያ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ይህም በተከታታይ ዓመታት ባለ ሁለት አሀዝ የኢኮሚ ዕድገት አስመዝግባለች በተባለችው ሀገር ባለሁለት አሀዝ 15 ሚሊዮን ህዝብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ አስፈላጊ መሆኑ አለ6 የተባለውን የቁጥር ዕድገት ገቢራዊ ሳይሆን ምናባዊ ያደርገዋል፡፡

በተለይ ሟቹ አቶ መለስ በስልጣን ላይ በነበሩበት እስከ 2002 ዓ.ም. ድረስ ከፍተኛ የሆነ የሀገሪቱን ለም መሬት በሊዝ/በኪራይ ሒሳብ ለውጭ ባለሃብቶች እንዲተላለፍ አድርገዋል፡፡ ከተላለፈው መሬት በተጨማሪ ለግብር እና ኢንዱስትሪ አገልግሎት በሚል ሰፋፊ መሬቶች ከዜጎች ተነጥቀው በመንግሥት የመሬት ባንክ ስር እንዲሆኑ ተደርገው ነበር፡፡

ለሽያጭ የተዘጋጀውና የተሸጠው መሬት መጠን

የማኀበራዊና ተፈጥሮ ሃብት ተመራማሪ ደሳለኝ ራህመቶ 2003 ዓ.ም. (እ.አ.አ. 2011)ጥናት፤ ከ1996 ዓ.ም. እስከ 2002 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ አጠቃላይ ለባለሃብቶች የተዘጋጀው ሰፋፊ ለም መሬት 3, 870, 280 ሄክታር መሬት ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ለባለሃብቶች የተላለፈው/የተሰጠው መሬት በከፊል 1, 342, 370 ሄክታር መሬት ነው፡፡ ይህም በሄክታር በየዓመቱ ከ14 ብር እስከ 135 ብር ዋጋ ከ30-50 ዓመት በሚፈጅ ኪራይ ውል የተላለፈ መሬት ነው፡፡ በመንግሥት እጅ ለሽያጭ/ኪራይ የተዘጋጀው መሬትና ተላልፎ የተሰጠውን መሬት በክልሎች ምን ያህል እንደነበር ያለውን በከፊል እንመልከት፤

ትግራይ ክልል 51, 544 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ30-40 ብር ዋጋ በመንግሥት ቢተመንም፤ በሊዝ የመሬት ኪራይ ለባለሃብት የተላለፈ መሬት የለም፡፡
አፋር ክልል 409, 678 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ እስካሁን ዋጋው ባልታወቀ ሒሳብ ለባለሃብት በሊዝ የተላለፈው መሬት 54, 000 ሄክታር መሬት ነው፡፡

አማራ ክልል 420, 000 ሄክታር መሬት ለባለሃብት በሚል ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ14-79 ብር ዋጋ ተተምኖ ከተዘጋጀው መሬት ላይ ለባለሃብት የተላለፈው 121, 370 ሄክታር መሬት ነው፡፡

ኦሮሚያ ክልል 1, 057, 866 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ70-135 ብር ዋጋ ተተምኖ ከተዘጋጀው መሬት ላይ 380 000 ሄክታር መሬት በሊዝ ተላልፏል፡፡

ደቡብ ክልል 348, 009 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር በዓመት በሄክታር ከ30-117 ብር ዋጋ ተተምኖ 60, 500 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡

ጋምቤላ ክልል 829, 199 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ20-30 ብር ዋጋ ተመን 535, 000 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡

በቤኒሻንጉል ክልል 691, 984 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ15-25 ብር ዋጋ ተመን 191, 500 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡

ኦጋዴን (ሶማሌ) ክልል 26, 000 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ16-65 ብር ቢተመንም በሊዝ ለባለሃብት የተላለፈ መሬት የለም፡፡

*ከላይ የተጠቀሰው መረጃ የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች (አብዛኞቹ የህወሓት ሰዎች ናቸው) ከ2,000 ሄክታር መሬት በታች በእያንዳንዱ ባለሃብት የተወሰደውን ፣ ለአበባ እርሻ ልማት በየከተሞች አቅራቢያና ገጠር ከገበሬዎች ተነጥቆ የተሰጠውን መሬት ፣ መንግሥት ለስኳር ፕሮጀክት በሚል የወሰደውን 335, 000 ሄክታር መሬት አያጠቃልልም፡፡ መሬቱን ከወሰዱ ባለሃብቶች/ኩባንያዎች መካከል በአፋር ክልል የተሰጠው የግብፅ ብሔራዊ ባንክ እና በኦሮሚያ ክልል ለጥራጥሬ ምርት ከተሰጠው የጅቡቲ መንግሥት በስተቀር እስካሁን ምርታማና ውጤታማ የሆኑ የሉም፡፡ የግብፅ መንግሥት በብሔራዊ ባንኩ አማካኝነት እና የጅቡቲ መንግሥት በቀጥታ የሀገሮቻቸውን የምግብ ፍጆታ ለመደጎም የሚጠቀሙበት እርሻ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ግን የዜጎቹን የምግብ ፍጆታ ለመሸፈን እና የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በመንግሥት ተቋማትም ሆነ በባለሃብቶች በኩል አንዳችም የግብርና መሬት ጥቅም ላይ አላዋለም፡፡ ሰፋፊ ለም መሬት ለሀገር ውስጥና ለውጭ ባለሃብቶች የተሰጡትም ቢሆኑ ዋጋቸው እጅግ እርካሽ ከመሆኑ የተነሳ ከውጭ ምግብ ነክ ምርቶችን ወደሀገር ውስጥ ለማስገባት እንኳ የሚበቁ አይደለም፡፡

የአካባቢና ማኀበራዊ ተፅዕኖው

ሁሉም ባለሃብቶች ማለት ይቻላል መሬቶቹን በወሰዱበት አካባቢ የነበሩ ነዋሪዎችን ያለ በቂ ካሳና ምክክር ከማፈናቀላቸው በተጨማሪ ለዘመናት ሲንከባከቡት የነበሩ የተፈጥሮ ደኖች ሙሉ ለሙሉ ተመንጥረው ከጥቅም ውጭ ሆነዋል፡፡ ይሄም ምናልባት በ10 እና 20 ዓመታት ውስጥ ከማኀበራዊ ተፅዕኖ በተጨማሪ ተፈጥሮን በማዛባት የሀገሪቱ የአየር ንብረትና አካባቢ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ እንደሚኖረው ይታመናል፡፡ የአካባቢና አየር ንብረት መዛባት ተፅዕኖ ደግሞ እንደ ድርቅ ያሉ ሌላ ተጨማሪ ችግር ይዘው ከመምጣታቸው በተጨማሪ፣ ድርቅን ተከትሎ ምናልባትም ከአሁኑ መላ ካልተዘየደ ሀገሪቱ በታሪኳ አይታ ማታውቀው ርሃብ ሊከሰት እንደሚችል ይጠበቃል፡፡

Ethiopian land grab Impact

አስገራሚው ነገር የሀገር ውስጥ ባለሃብቶችም ሆኑ ከውጭ የመጡ ባለሃብቶች ፕሮጀክታቸውን ለማሳካት ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ እና ንግድ ባንክ ከፍተኛ ብድር ወስደው ያልመለሱና በዛው የጠፉ በርካቶች ሲሆኑ፤ ምንም ሳይሰሩበት/ላይሰሩበት የተፈጥሮ ደኖችን (በተለይ በሰሜን ምዕራብ፣ በምዕራብ እና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢ) መንጥረው ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ከጥቅም ውጭ አድርገው መሄዳቸው ነው፡፡ ከዚህ ጋ በተያያዘ ሻምፖርጂየተባለ የህንድ ኩባንያ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 50 ሺህ ሄክታር ለም መሬት ለግብርና ልማት በሚል ወስዶ የነበረውን ደን መንጥሮና አቃጥሎ እስከ አዲስ አበባ ድረስ ከሰል ይሸጥ እንደነበርና ከዛም ጥሎ ወደሀገሩ ጠቅልሎ እንደሄደ ይነገራል፡፡ በአካባቢውም ከሰል ነጋዴ ባለሃብቶች በሚል ይተቻሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ተጨማሪ ሌላ ጉዳት ነው፡፡ ይህ ምንግሥት እሰራዋለሁ ላለው ስኳር ፕሮጀክት (ከሰም፣ ደቡብ ኦሞ እና ወልቃይት ) እና ኢሉባቦር ለማዳበሪያ ፋብሪካ ለማቋቋም በሚል ሙሉ ለሙሉ ከጥቅም ውጭ ያደረጋቸውን ደኖች ሳይካትት ነው፡፡ የስኳር ፕሮጀክቶቹም ሆኑ የማዳበሪያ ፋብሪካዎቹ የተፈጥሮ ደኖችን ከማውደም እና የአካባቢውን ነዋሪዎቸ ከማፈናቀል ባለፈ እስካሁን የታየ ምንም አዎንታዊ ውጤት የለም፡፡

ከላይ የተጠቀሱ እና ለባለሃብቶች በሊዝ መልክ የተላለፉ መሬቶች ውጤታማ ሆነው ቢታዩ ኖሮ የመንግሥት ዓላማና ግብ የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ላይ ሳይሆን የውጭ ምንዛሪ ላይ ትኩረት ያደረገ ነበር፡፡ ይህ የሚያሳየው ሀገሪቱ ላይ እየተተገበረ ያለው የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም እና የኢኮኖሚ ፖሊሲው ምን ያህል የተሳሳተ እንደሆነ እና መንግሥት እስካሁንም የዜጎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በስሩ ካሉ የመገናኛ ብዙኃን ከሚነገረው ወሬ በስተቀር በተግባር ይሄ ነው የሚባል ጅማሮም ሆነ ውጤት የለም፡፡
በተለይ ከመሬት ቅርምቱ ጋ በተያያዘ ሶስት ተጨማሪ ጉዳዮችን እናንሳ፡፡

መንግሥት ሰፋፊና ለም የሆኑ የሀገሪቱን መሬት እጅግ ዝቅተኛ በሆኑ ዋጋ ለግማሽ ምዕተ ዓመት ድረስ ለመስጠቱ በዋናነት የሚሰጠው ምክንያት ፤
– ለዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር/የስራ አጥ ቁጥር ለመቀነስ
– በግብርናው ዘርፍ የቴክኖሎጂ ሽግግር ለማምጣት
– የግብርና ምርትን በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪን ማስገኘት የሚል ነበር፡፡

ነገር ግን ከተጠቀሱት ምክንያቶች ስኬታማ የሆኑ የሉም፡፡ በአንፃሩ በማኀበረሰቡ እና በአካባቢው ላያ ያደረሱት ጉዳት ግን አለ፡፡ በመሬት ቅርምቱ ከደረሱ ጉዳቶች መካከል ጥቂቶቹ፡
ነዋሪዎችን ያለበቂ ካሳና ምክር አገልግሎት ማፈናቀል ይገኝበታል፡፡ ከዚህ ጋ በተያያዘ በዋነኛነት በጋምቤላና ደቡብ ኦሞ ከፍተኛውን ቁጥር ይይዛሉ፡፡

በጋምቤላ ወደ 225, 000 የአካባቢው ነዋሪዎች ያለበቂ ካሳና፣ ምክክርና ስምምነት ተፈናቅለዋል፡፡ ይህንም ተከትሎ ከ 8 ሺህ እስከ 10 ሺህ ተፈናቃዮች ሀገር ለቀው ወደ ጎረቤት ሀገሮች በተለይም ወደ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ኬንያ ተሰደዋል፡፡ የመሬት መፈናቀሉን ከተቃወሙ ከክልሉ ነዋሪዎች መካከል ፤ ከመንግሥት በተለይም ከወቅቱ ጠቅላ ሚኒስትር በነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝ በተወሰደ ወታደራዊ የኃይል እርምጃ 424 የአኝዋክ ማኀበረሰብ አባላት በተመሳሳይ ቀን በጅምላ ተገድለዋል፡፡ በርካታ ሰዎችም በጋምቤላና አዲስ አበባ በሚገኙ ወህኒ ቤቶች ታስረዋል፡፡ ይህ ድርጊት የተፈፀመው በአብዛኛው በዛው በጋምቤላ ክልል አኝዋክ ዞን ነዋሪዎች ነበሩ፡፡

በትውልድ ኢትዮጵ በዜግነት ሳውዲ ዓረቢያዊ የሆኑት መሐመድ አሊ አላሙዲ ንብረት የሆነው ሳውዲ ስታር ኩባንያ ከዚሁ ከጋምቤላ ብቻ 139 ሺህ ሄክታር መሬት ሩዝ እና አኩሪ አተር አምርተው የሰውዲ ዓረቢዎችን የምግብ ፍጆታ ለመሸፈን ታቅዶ ቢከናወንም ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ የህንዱ ካራቱሪ ኩባንያ 10 ሺህ ሄክታር መሬት ጠይቆ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በነበሩት በሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዛና ፈቃድ ያለ ኩባንያው ፍላጎት 300 ሺህ ሄክታር መሬት ቢሰጣቸውም ውጤታማ አልሆኑም፡፡ ይህ ኩባንያ በቅርቡ 100 ሺህ ሄክታር መሬት መነጠቁን ተከትሎ በኩባንያው ባለቤት ካራቱሪና በመንግሥት በኩል አለመግባባት ተፈጥሯል፡፡ ሁለቱም ኩባንያዎች በርካታ ነዋሪዎችን አፈናቅለዋል፣ የተፈጥሮ ደኖችን ከጥቅም ውጭ አድርገዋል፡፡

በደቡብ ኦሞ ሸለቆ በተለይ በደቡብ ኦሞ ዞን ልክ እንደጋምቤላው ያለበቂ ካሳና ምክክር ከ200, 000 በላይ የአካባቢው ነዋሪዎች ተፈናቅለዋል፡፡ ማፈናቀሉን ከተቃወሙት መካከል በተለይ ኩራዝ የስኳር ፕሮጀክት ግንባታ አካባቢ የነበሩ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ነዋሪዎች በተመሳሳይ ወታደራዊ እርምጃ ተገድለዋል፡፡ የመሬት ቅርምቱን የተቃወሙ ተፈናቃዮች መካከል በደቡብ ኦሞ እና ሐዋሳ በሚገኙ ወህኒ ቤቶች በርካቶች ሲታሰሩ፣ ከእስርና ግድያ ያመለጡ ደግሞ ወደጎረቤት ኬንያ ተሰደዋል፡፡

ሰፋፊ ለም መሬቶቹ ለባለሃብቶች ተሰጥተው፣ በመሬቱ ስም ከሀገሪቱ ከፍተኛ የባንክ ብድር እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ እስካሁን ባሉ መረጃዎች ከጅቡቲ መንግሥት እና ከግብፁ ብሔራዊ ባንክ መሬቶች በስተቀር በሌሎቹ መሬቶች ከባንክ ብድር ተወስዶባቸው በርካቶቹ ብድሮች አልተመለሱም፡፡ የባንክ ብድርንም ሆነ የመሬት ኪራይ ክፍያን ባለመፈፀም መሬት የተሰጣቸው የተለያዩ የህንድ ኩባንያዎችና የህወሓት ሰዎች ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛሉ፡፡ ከዚሁ ሰፋፊ የመሬት ቅርምት ጋር በተያያዘ ዜጎች በግፍ ተፈናቅለዋል፣እየተፈናቀሉም ይገኛሉ፡፡ የባለሃብቶችን ድምፅ የሚሰማ አካል ቢኖርም የዜጎችን ድምፅና አቤቱታ እንዲሁም መብትና ጥቅም የሚያስጠብቅ አካል ግን አልተገኘም፡፡ የዚህ ሁሉ ችግር አብይ ምክንያት ከ”ህገ መንግሥት” እስከ ኢህአዴግ ፖሊሲ መሬት “የመንግሥትና የህዝብ ነው፣ መሬት አይሸጥም አይለወጥም” በሚል ፈሊጥ እያንዳንዱ ዜጋ የመሬቱ ባለቤትነቱ በአዋጅ እንዲነጠቅ መደረጉ ነው፡፡

በህወሓት/ኢህአዴግ ቋንቋ መሬት የመንግሥትና የህዝብ ነው፤ መንግሥትና ህዝብ ደግሞ ህወሓት ነው፡፡ ዜጋው እየኖረበት ያለበት መሬት ባለቤትነቱ በመነጠቁና በሱስ ስም “መንግሥት” እና “ህዝብ” የሚል ምናባዊ ተቋም አማካኝነት በላዩ ላይ ቤቱ ከነንብረቱ ያለማንም ከልካይ ይሸጣል፣ ይለወጣል፣ ይሄንን ተቃውሞ ጥያቄ የሚያቀርብ ደግሞ ይገደላል፣ አሊያም ይታሰራል፣ በለስ ቀንቶት ከነኚህ ርምጃዎች ካመለጠ ወደጎረቤት ሀገር ጥገኝነት ፍለጋ ይሰደዳል፡፡

ዜጎች ለምን የመሬታቸው ባለቤት አልሆኑም?

ዜጎች የመሬታቸው ባለቤቶች አለመሆናቸውና በመሬታቸው ላይ ማዘዝና መወሰን አለመቻላቸው ራሳቸውን እንደ ዜጋ የሚያዩበት አሊያም የሀገሪቱ ሉዓላዊ ግዛት ባለቤት ስለመሆናቸው የሚያስችል መብት ሙሉ ለሙሉ በህገ መንግሥቱ አዋጅ ተነጥቋል፡፡ በዚህም ከስነ ልቡና በተጨማሪ የገበሬዎች መሬት ምርታማነት ላይ ጥያቄን ያስነሳል፡፡ ምክንያቱም መሬቱን የራሱ አድርጎ መወሰንና ማዘዝ እንዲሁም ከባንክ ብድር ማግኘትም ሆነ መሸጥ የሚያስችል መብት በመነፈጉ ከእለት ጉርስ ባለፈ ስለ ምርታማነት የመጨነቅ ስሜት አይስተዋልበትም፡፡ ከባለፈው ህዳር ወር 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅ መነሻው የአዲስ አበባ እና የኦሮሚል ክልል ልዩ ዞን የተቀናጀ መስተር ፕላን ይደረግ እንጂ ዋናው ምክንያት ዜጎች የመሬት ባለቤትነታቸው ተነጥቆ በተደጋጋሚ በግፍ መፈናቀላቸው ነው፡፡ ይሄ ዛሬ በአንድ ክልል ተጀመረ እንጂ ብሶቱ ከልክ እያለፈ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ነገ መከሰቱ የማይቀር ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ መፍትሄ ማስት ፕላኑን ማቆም ወይም የስርዓቱን ሰዎች ሰብስቦ የፕሮፖጋንዳ ድጋፍ ዜና እወጃ ሳይሆን መሰረታዊ የህገ መንግሥትና የፖሊሲ መሻሻል ነው፡፡

በኢትዮጵያ መሬት የእያንዳንዱ ባለ ይዞታ/ባለቤት ንብረት መሆኑን፣መሬትን የሚሸጥም ሆነ የሚሰጥ ራሱ ባለቡቱ እንደሆነ፣ መንግሥት ለከተማ መኖሪያና ማኀበራዊ አገልግሎት ተቋማት መገንባት ቢፈልግ ከባለይዞታቸው ተደራድሮ በገበያ ዋጋ እንዲገዛ ቢደረግ፣ ተቋማቱን ለመገንባት ዜጎች ተገቢውን ግብር እየከፈሉ ስለሆነ፣ በመሬታቸው ላይ የመወሰንና የማዘዝ ሙሉ ስልጣን ለእያንዳንዱ ዜጋ መሰጠት አለበት፡፡ አሁን ባለወ ነባራዊ ሁኔታ የሀገሪቱ መሬት ከፊውዳላዊ ስርዓት እጅግ የከፋ እንጂ የተሻለ ነገር የለውም፡፡ ምክንያቱም በፊውዳሉ ስርኣት ዜጎች የመሬታቸው ባለቤቶች አልነበሩም፣ ዛሬም አይደሉም፡፡ ይሄ ተለወጦ በደርግ ዘመን የካቲት 25 ቀን 1967 ዓ.ም. የታወጀው የመሬት ላራሹ አዋጅ እንደገና ተግባራዊ መደረግ አለበት፡፡ በግለሰቦችና በማኀበረሰቦች(ለግብርና እና ማኀበራዊ አገልግሎት) ያልተያዙ ቦታዎችን መንግሥት ለማኀበራዊ አግልግሎት ለማዋል ቢወስን ግልፅነትና ተጠያቂነት ባለበት መልኩ እንዲከናወን ግልፅ የሆነ ህጋዊ ማዕቀፍ ሊኖረው ይገባል፡፡ አሁን ያለው የጠባብ ፖለቲካዊ ቤተሰብ ግንኙነት ውርስ አሰራር መቆምና በግፍ የተወሰደው መሬት ለተፈናቃዮችና ባለቤቶች መመለስ እና አሰራሩ መከለስ ይኖርበታል፡፡

በሌላ በኩል የተለያዩ የሀገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች በግብርና ሙያ በርካታ ተማሪዎችን እያስተማሩ ቢያስመርቁም፤ ባለሙያዎቹ የቀሰሙትን እውቀት አሟጠው እንዲጠቀሙ፣ ሀገሪቱንም እንዲጠቅሙ፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ የተሻለ ውጤት እንዲያመጡ የመሬት አቅርቦትም ሆነ የባንክ ብድር በመንግሥት አልተመቻቸም ሳይሆን አልተፈቀደላቸውም፡፡ በሌላ በኩል ከግብርናው ጋርም ሆነ ከንግድ ጋ ምንም እውቀት የሌላቸው የህወሃት ሰዎች በፈለጉት ሰዓት የፈለጉትን መሬት ለሚፈልጉት ዓላማ በፈለጉት ቦታ ሲያገኙ፣ የባንክ ብድርም በፈለጉት ሰዓት ያገኛሉ፤ በተመሳሳይ የውጭ ባለሃብቶችም እንዲሁ፡፡ ነገር ግን ጊዜያቸውን እና ገንዘባቸውን መስዋዕት አድርገው ከ16 ዓመታት ያላነሰ በእውቀት ማዕድ ላይ የነበሩና ያሉ ዜጎች አብዛኞቹ ስራ አጥ ሆነው ስራ ለማግኘት መንግሥት እንዲጠብቁ ሲፈረድባቸው፣ በለስ የቀናቸውም ቢሆኑ አውቀታቸው በአግባቡ ስራ ላይ ለማዋዕል የሚያስችል መንግሥታዊ አገልግሎት ባለመኖሩ ቢሮ ገብቶ ወርሃዊ ደመወዝ በመጠበቅ ሙሉ ለሙሉ መንግሥት ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ ይገደዳሉ፡፡

በሀገሪቱ የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ፣ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም፣ ኢኮኖሚውን በተመለከተ የዜጎችን መብትና ጥቅም ሊያስጠብቅ የሚያስችል ፖሊሲ ባለመኖሩ ከሌሎች ሀገረች ሲነፃፀር እንደ ኢትዮጵያ በእውቀትና በትምህርት ኪሳራ የደረሰባትም ሆነ የሚደርስባት ሀገር ስለመኖሯ አጠራጣሪ ነው፡፡ ቢያንስ በግብርና ሙያ የሚመረቁ ባለሙያዎች በየመስካቸው በቂ የመሬት አቅርቦት እና የባንክ ብድር ቢመቻችላቸው ከራሳቸው አልፈው ሀገሪቱን በብዙ መልኩ መጥቀም በቻሉ ነበር፡፡ ምናልባት የተሻለ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ሽግግር ቢያስፈልግ እንኳ እዛው በሚማሩበት የትምህርት ተቋም ማመቻቸት አሊያም ለተጨማሪ አጫጭር የሙያ ስልጠናዎቹን ሊሰጡ የሚችሉ በዘርፉ ውጤታማና ከእኛ ልቀው ካሉ ሀገሮች ባለሙያዎችን አምጥቶ አሰልጥኖ ወደስራ እንዲገቡ ቢደረግ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ የስራ አጥ ቁጥርን ለመቀነስ፣ የዜጎችን መብትና ጥቀምን ለማስጠበቅና ለመጠበቅ እጅግ የተሸሉ ቢሆኑ እንጂ የሚያንሱ አይደሉም፡፡ የአካባቢና የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ላይም ቢሆን በተገቢው መንገድ እንዲከናወን በማድረግም ሆነ ጥራት ያለው ምርት አምርቶ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ለማስገኘትም ቢሆኑ ከውጭ ባለሃብቶችም ሆነ በፖለቲካ ወገንተኝነት ከሚደረግ የጥቅም ትስስር በእጅግ የዘርፉ ተማሪዎች ውጤታማ ስለመሆናቸው ጥርጥር የለውም፡፡

በርግጥ ዜጎች ሁሉ በፖለቲካው፣ በኢኪኖሚውም ሆነ በማኀበራዊ አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ ስርዓቱ ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ ከሚሰራ እና ራሱን የአናሳ ብሔር ተወካይ አድርጎ በዘረኝነት ፖለቲካዊ ወገንተኝነት በተጠመደ ህወሓት/ኢህአዴግ ቡድን ከላይ የተጠቀሰውን ቀና አስተሰሰብ መጠበቅ የዋህነት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ነገር ግን ጥቅሙ ለባለሙያዎቹ፣ ለሀገሪቱም፣ ለህዝቡም ሆነ ለራሳቸው የተሻለ ጥቅም ያለውና አዋጭ መፍትሄ ነው፡፡ መፍትሄዎቹ ላለፉት 25 ዓመታት ባለመወሰዳቸው የመሬት ቅርምቱ በሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት፣ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማኀበራዊ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ ችግር አስከትሏል፣ የተለመደው የኪሳራ አካሄድ አሁንም በተጠናከረ መንገድ ቀጥሏል፡፡ የዚህ ሁሉ መዘዝ ግን አንዱን አካባቢ ብቻ ነጥሎ ጉዳት የሚያደርስ ሳይሆን አጠቃላይ በሀገሪቱ ኢኮኖሚና ፖለቲካ ማኀበራዊ ጉዳይ ላይ የራሱን አሉታዊ ጫና ማሳረፉ አልቀረም፡፡ የመሬት ባለቤትነት የህግ ማሻሻያ እና የፖሊሲ ለውጥ ካልተደረገ ዜጎች ከመሬታቸው በግፍ የመፈናቀል እና የመሬት ቅርምቱ ተጠናክሮ መቀጠሉ የሚያጠያይቅ አይደለም፡፡

እነ ጌታቸው ሽፈራው ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

*”ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ ተደርገናል” ተጠርጣሪዎች
*”6 ቀን ደንበኛየን ለማግኘት ተመላልሼ ተከልክያለሁ” የጋዜጠኛ ጌታቸው ጠበቃ አምሃ መኮንን

Getachew Shiferaw

በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከታህሳስ 15/2008 ዓ.ም ጀምሮ በማዕካለዊ ወንጀል ምርመራ በእስር ላይ የሚገኙት እነ ጌታቸው ሺፈራው ፍርድ ቤት ቀርበው ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
በእነ ዳንኤል ተስፋየ ስም በተከፈተው የምርመራ መዝገብ ስር የተካተቱት ሦስት ተጠርጣሪዎች አቶ ዳንኤል ተስፋየ፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል እና ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ሲሆኑ፣ ተጠርጣሪዎች ዛሬ ጥር 14/2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ቀርበው ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ጠይቆ የ27 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋ፡፡

ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ የጠየቀበትን ምክንያት ለፍርድ ቤት ያስረዳ ሲሆን ‹‹የቴክኒክ ማስረጃዎችን ከብሄራዊ ደህንነትና መረጃ ኤጀንሲ ጠይቀን ማስመጣትና ተጨማሪ ግብረ አበሮችን መያዝ ይቀረናል›› ብሏል፡፡

ተጠርጣሪዎች ከተያዙበት ቀን ጀምሮ በማንም እንዳይጎበኙ መከልከላቸውን በማስረዳት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ‹‹ከተያዝኩ ጀምሮ ቤተሰቦቼን አይቼ አላውቅም፡፡ እስር ላይ ሆኜ በቀን ለ10 ወይም 15 ደቂቃዎች ነው የጸሐይ ብርሃን የማገኘው፤ ይሄ እንዲስተካከልልኝ ፍርድ ቤቱን እጠይቃለሁ›› ሲል ያመለከተ ሲሆን፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል በበኩሉ፣ ‹‹ቤተሰቦቼን ያየኋቸው ዛሬ ችሎት ስመጣ ከርቀት ነው፤ ቤተሰቦቼን እንዳይ ይፈቀድልኝ›› በማለት እያነባ ጠይቋል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ደግሞ በጠበቃው በኩል ያለውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ አሰምቷል፡፡ ጠበቃው አቶ አምሃ መኮንን ለስድስት ቀናት ማዕከላዊ ደንበኛቸውን ለማነጋገር ቢመላለሱም ከበር ላይ እንዲመለሱ በመደረጋቸው ከደንበኛቸው ጋር ሳይነጋገሩ ፍርድ ቤት መቅረባቸው አግባብ አለመሆኑንና ድርጊቱ ህገ-መንግስቱን የሚጣረስ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹‹ደንበኛየን ያገኘሁት አሁን ነው፡፡ ደንበኛየ የምንፈልገውን ነገር ሳናገኝ ከጠበቃህ ጋር አናገናኝህም ተብሏል፡፡ ይህ በህገ-መንግስቱ የተሰጠውን መብት የጣሰ ተግባር ነው፡፡ አሁንም ደንበኛየ፣ ከዚህ በኋላ እኔን ሳያነጋግር ቃሉን ለመስጠት ፈቃደኛ እንዳልሆነ ፍርድ ቤቱ እንዲመዘግብልኝ እፈልጋለሁ›› ሲሉ ጠበቃ አምሃ መኮንን ለፍርድ ቤቱ ገልጸዋል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እስካሁን በቤተሰብም ሆነ በጓደኞቹም እንዳይጠየቅ መከልከሉ የህግ አግባብ የሌለው የመብት ጥሰት ነው ብለዋል ጠበቃ አምሃ፡፡

ጠበቃ አምሃ ፖሊስ ተጨማሪ ጊዜ የጠየቀበት ምክንያት ደንበኛቸው የዋስትና መብቱ ተከብሮለት ሊከናወን እንደሚችል በማስረዳት የዋስትና መብት እንዲከበርለት ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን በሁሉም ላይ ፖሊስ የጠየቀውን የጊዜ ቀጠሮ በመፍቀድ ለየካቲት 11/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በተመሳሳይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከሦስት ወራት በላይ በማዕከላዊ በእስር ላይ የሚገኙት በጋሞ ጎፋ አርባምንጭ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች እነ ሉሉ መሰለ እና አየለች አበበ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበው ‹የመጨረሻ› ነው የተባለለትን ተጨማሪ የ28 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ

እነ ሀብታሙ አያሌው ለጥር 10 ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል

አቃቤ ህግ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብርተኝነት ክስ መስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ተበይኖላቸው አቃቤ ህግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠይቆባቸው ጉዳያቸውን በእስር ላይ ሆነው እየተከታተሉ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች በድጋሜ ለጥር 10 ቀን 2008 ዓ.ም ተቀጥረዋል፡፡

Political prisoners

ዛሬ ታህሳስ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በእነ ሀብታሙ አያሌው ላይ የተጠየቀው ይግባኝ ላይ ብይን ይሰጣል ተብሎ ቢጠበቅም ዳኛ ዳኜ መላኩ ‹‹የምንመረምረው ነገር አለ›› በሚል ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥተዋል፡፡
ይግባኝ የተጠየቀባቸው ተከሳሾች ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሺ እና አብርሃም ሰለሞን ሲሆን፣ ሁሉም ተከሳሾች ነሀሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በስር ፍርድ ቤት ነፃ ቢባሉም እስካሁን በእስር ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ

ዮናታን ተስፋዬ እና ጌታቸው ሺፈራው ከጠበቆቻቸው ጋር እንዳይገናኙ ተደረጉ

በማዕከላዊ ፌደራል ወንጀል ምርመራ በእስር ላይ የሚገኙት ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እና የሰማያዊ ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ ከጠበቆቻቸው ጋር እንዳይገናኙ መደረጋቸውን ሊያነጋግሯቸው ወደ ማዕከላዊ አምርተው የነበሩት ጠበቆቻቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

Yonatan Tesfaye

የሁለቱ ወጣቶች ጠበቆች የሆኑት ጠበቃ አምሃ መኮንን እና ሽብሩ በለጠ ታህሳስ 27 ቀን 2008 ዓ.ም ደንበኞቻቸውን ለማግኘት ወደ ማዕከላዊ ሄደው የነበር ቢሆንም ‹‹ሰራተኞች ስብሰባ ላይ በመሆናቸው መግባት አትችሉም›› በሚል ከበር መልሰዋቸዋል፡፡

Getachew Shiferaw_Addismedia
በማዕከላዊ በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎችን ጠበቆች ማግኘት የሚችሉት በሳምንት ሁለት ቀናት፣ ማለትም ዕሮብ እና አርብ መሆኑን ያስታወሱት ጠበቃ አምሃ፣ በእነዚህ ቀናትም እንኳ ደንበኞቻችንን ማግኘት መከልከላችን ግልጽ የህገ-መንግስት ጥሰት ነው ብለዋል፡፡
‹‹ህገ-መንግስቱ በእስር ላይ ስለሚገኙ ሰዎች መብት በግልጽ የሚናገረው በየትኛውም ቀን ከጠበቆቻቸው፣ ከወዳጆቻቸው፣ ከሀይማኖት አባቶቻቸው እና ከወላጆቻቸው ጋር መገናኘት እንደሚችሉ ነው፡፡ ይህ ሆኖ እያለ በሳምንት ሁለት ቀናት ብቻ ደንበኞቻችንን ለማግኘት መገደቡ ሳያንስ ዛሬ ከበር ላይ መከልከላችን የሚያሳየው በግልጽ ህገ-መንግስቱን ለማክበር ቁርጠኝነት እንደሌለ ነው›› ብለዋል ጠበቆቹ፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እና ዮናታን ተስፋዬ ከታሰሩ ከሳምንት በላይ ቢሆናቸውም እስካሁን በአንድም ሰው እንዲጎበኙ አልተፈቀደም፤ በወቅቱ በተመሳሳይ ለእስር የተዳረጉ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትም በቤተሰብ እንዳይጎበኙ ተደርገዋል፡፡ በዚህም ታሳሪዎቹ በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ባለመቻሉ ቤተሰቦቻቸውንና ወዳጆቻቸውን እንዳሳሰባቸው በመጥቀስ ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡