Category Archives: Human Rights

ብሎገሮቹ እና ጋዜጠኞቹ ተጨማሪ 20 ቀናት ቀነ ቀጠሮ ተሰጣቸው

∙ተሻሻለ በተባለው ክስ ላይ አስተያየት ተሰጥቶበታል

z9በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የዞን 9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ተጨማሪ 20 ቀናት ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

ዛሬ ታህሳስ 7 ቀን 2007 ዓ.ም ለ13ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ጦማርያኑና ጋዜጠኞች በጠበቆቻቸው አማካኝነት ቀደም ብሎ ተሻሽሎ በቀረበባቸው ክስ ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

የተከሳሽ ጠበቆችም ተሻሻለ በተባለው ክስ ላይ አስተያየታቸውን በጽሑፍ አቅርበዋል፡፡ ጠበቆቹ አስተያየታቸውን በጽሑፍ ከማቅረባቸው በተጨማሪ በቃል ለችሎቱ ለማስረዳት ጠይቀው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ፣ ‹‹በጽሑፍ ካቀረባችሁ በቃል መድገም አያስፈልግም›› በሚል ሳይፈቅድላቸው ቀርቷል፡፡

ጠበቆቹ ‹‹ተሻሻለ የተባለው ክስ ምንም መሻሻል የለውም›› በማለት ለፍርድ ቤቱ ለማስረዳት ቢሞክሩም፣ ችሎቱ ንግግራቸውን አቋርጦ ‹‹ክሱ በታዘዘው መሰረት መሻሻል አለመሻሻሉን መርምሮ የሚወስነው ፍርድ ቤቱ ነው›› ሲል አስረድቷል፡፡

በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ በተከሳሽ ጠቦቆች የቀረበውን አስተያየትና ቀደም ብሎ ለአቃቤ ህግ ክሱን እንዲያሻሽል የሰጠውን ትዕዛዝ በማገናዘብ ጉዳዩን መርምሮ ክሱ በምን አግባብ እንደተሻሻለ አይቶ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 27 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል ሲል የነገረ- ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

(ከዝዋይ እስር ቤት)

temesgen_desalegn መሐሙድ የሱፍ የተወለደው በ1980ዓ.ም ከሶማሌ ክልል ርእሰ-መዲና ጅጅጋ 500 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በምትገኘውዶሀን ከተማ ነው፡፡ ለቤተሰቡ ሰባተኛ ልጅ ሲሆን፤ አምስት እህቶችእና ሦስት ወንድሞች አሉት፡፡ በጅጅጋ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት እስከ አስረኛ ክፍል ድረስ መዝለቁቢሳካለትም፤ ከዚህ በላይ ግን ሊቀጥል አልተቻለውም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የኢትዮጵያመንግስት የደህንነት ሠራተኞች የ1999ዓ.ም የግንቦት ሃያ በዓል በጅጅጋ ከተማ ስታዲዬም በተከበረበት ዕለት፣ የኦጋዴን ነፃአውጪ ግንባር (ኦብነግ) በሰነዘረው የቦንብ ጥቃት ተሳትፈሃል በሚል ለእስር በመዳረጉነው፡፡ ይህንን ተከትሎምከምድራችን አስከፊ ማሰቃያዎች መካከል ግንባር ቀደም በሆነውና የክልሉ ነዋሪ “ጄል-አዳብ” (የገሃነም እስር ቤት) እያለ በሚጠራው ማጎሪያ ውስጥ እጅግ በጣም የከፋ ምድራዊ መከራ እንደተቀበለሀዘን በተጫነው ድምፅ ይናገራል፡፡ በሠውነቱ የተለያዩ ክፍሎች ላይ እንደ ፍም ቀልተው የሚታዩት ጠባሳዎቹም ያሳለፈውንሥቃይ አፍ አውጥተው ይመሰክራሉ፡፡

ለአራት ወራት ያህል አንድ ክፍል ውስጥ ለብቻው ተቆልፎበት፤ ሃያ አራት ሠዓታትሙሉ እጆቹ በካቴና ተቀፍድደው፣በቀን ከአምስት ጊዜ በላይ ለምርመራ እየተጠራ ያለዕረፍት ከባድ ስቅየት (ቶርቸር)ሲፈፀምበት ቆይቷል:፡ በመጨረሻም ለአንዲትም ቀን የፍርድ ቤት ደጅ ሳይረግጥ፣ ለኦብነግ አባላት አንድ ፓኬት ሲጋራሲያቀብል እጀ-ከፈንጅ ተይዟል በሚል ክስ የጅጅጋ ዞን ፍርድ ቤት በሞት እንዲቀጣ መወሰኑን እዛው እስር ቤት ሆኖከኢትዮጵያ ሬዲዮ የዜና እወጃ እና ከቪኦኤ ሶማሊኛ ፕሮግራም ሠምቷል፡፡

ከፍርዱ በኋላም በተመሳሳይ ወንጀል ከተከሰሰ አንድ እስረኛ ጋር በካቴና ተጠፍሮ በቀን አንድ እንጀራ ለሁለት ተካፍሎእንዲበላ እንደ ውሻ እየተወረወረለት 60 ቀናትን አሳልፏል፡፡ መሐሙድ በተለይም በእንቅልፍ ወቅት እርሱ ወይምየሰንሰለት ደባሉ የተገላበጠ እንደሆነ ካቴናው የሚያደርስበትን የመለብለብ ቃጠሎ ሲያስታውስ ዓይኖቹ በእንባ ይሞላሉ፡፡በአሁኑ ወቅት በዝዋይ ማጎሪያ ከባድ ጥበቃ ለሚደረግባቸው ብቻ በተመደበ ‹‹ዘጠነኛ ቤት›› ውስጥ አስራ አንድ ሶማሊኛተናጋሪዎችን ጨምሮ በድምሩ ሰላሳ አራት ሰዎች ጋር ከዛሬ ነገ የግፍ ፍርዱ ተፈጻሚ ሊሆንብኝ ይችላል በሚል ሰቀቀንእየባነነ በስጋት ተጠፍንጎ መኖር ከጀመረ እነሆ ሰባት ዓመት ሊደፍን ሦስት ወራት ብቻ ቀርተውታል፡፡

 የተዋረደው የፍትሕ ሥርዓት!. . .

ርግጥ ነው ይህ በጨረፍታ ያቀረብኩት አሳዛኝ ታሪክ የመሐሙድ የሱፍ ብቻ አይደለም፡፡ ሌሎች ሰባት ‹‹አባሪዎቹ››ስቃዩንም ሆነ የሞት ፍርዱን ይጋሩታል (በነገራችን ላይ በአንድ መዝገብ የተወነጀሉት እነዚህ ስምንት የሞት ፍርደኞች፡-መሐድ ኢብራሂም፣ አረብ ሰዋኔ ዱልባንቲ፣ ሐሰን መሐመድ ዑስማን፣ ሐሰን መሐመድ ዓሊ፣ ሙክታር መሐመድ ዓብዱላሂ፣ከድር ሽኩር ሙሳ እና ካሚል ዓብዱልናስር እንኳን በጋራ መንግሥት ላይ ሊያሴሩ ቀርቶ እርስ በርስም የተዋወቁት እስር ቤትውስጥ ነው፡፡ ከጅጅጋ ወደ ዝዋይ ‹‹ዘጠነኛ ቤት›› ተዘዋውረው በርካታ ዓመታትን ያሳለፉትም በጭካኔው ወደርእንደማይገኝለት የሚነገረው የክልሉ ፕሬዚዳንት አብዲ በአደራ እንዲቀመጡ በመተላለፋቸው መሆኑን ነግረውኛል፡፡) እንደ መሐሙድ ሁሉ እነርሱም ፍርድ ቤት ቀርበውአያውቁም፤ ምንም ዓይነት የሰውም ሆነ የሰነድ ማስረጃ አልተቆጠረባቸውም፡፡ እዚህ ጋ የማነሳው አሳዛኝ ገጠመኝከመካከላቸው አንዳቸውም ራዲዮ ስላልነበራቸው የተጣለባቸውን የሞት ፍርድ ውሳኔ የሠሙት፣ ዜናው ከተላለፈ ከበርካታቀናት በኋላ ሬዲዮ ካላቸው እስረኞች መሆኑ ነው፡፡

ይህ እጅግ አሳፋሪና አስደንጋጭ መንግሥታዊ ውንብድና በደንብ ይብራራ ዘንድ ለተከሳሶቹ ከተሰጣቸው ባለ አንድገፅ የክስ ቻርጅ የሁለቱን ብቻ በአዲስ መስመር እጠቅሳለሁ፡-‹‹በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ሕግና ፍትሕቢሮ በሶማሌ ክልላዊ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት ጅጅጋ የዐ/ሕግ/መ/ቁ 90/2000

ከሳሽ፡- ዐ/ሕግ

ተከሳሽ፡- ሐሰን መሐመድ ዑስማን (ሐንን መድቤ)

ዕድሜ፡- 21 ሥራ፡- ተማሪ አድራሻ፡- ጅጅጋ ከተማ፡- 06 ቀበሌ ወንጀል በ1996ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ.መ.ሥ.ሥ.ህ.ቁ. 240(3) እና 251(መ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀል ዝርዝር

ተከሳሽ ከመስከረም 1999 ዓ.ም. ጀምሮ እራሱን ኦ.ብ.ነ.ግ. እያለ ከሚጠራው ተቃዋሚና አሸባሪ ድርጅት ጋር በራሱፈቃድ በዚሁ በጅጅጋ ከተማ ከላይ በተጠቀሰው ዓመተ-ምህረት አባል በመሆን በጫካ በዚሁ አካባቢ ከሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች ጋርበከተማም

ሆነ በጫካ በመገናኘት በኢኮኖሚ ረገድ የሚያስፈልጋቸውን፡- ጫማ፣ ልብስ የመሳሰለውን እዚያው ድረስ ሄዶ በማቀበልአብሮ ሲንቀሳቀስ በመቆየቱ ተከሶ ቀርቧል፡፡››

ሁለተኛው የክስ ቻርጅ ደግሞ እንዲህ ይነበባል፡-

‹‹በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ሕግና ፍትሕ ቢሮ

በሶ/ክ/መ/ ጅጅጋ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት

ጅጅጋ

የዐ/ሕ/መ/ቁ 90/2000

ከሳሽ፡- ዐ/ሕግ

ተከሳሽ፡- መሐድ ሼክ ኢብራሂም

ዕድሜ፡- 28፣ሥራ፡- የለውም አድራሻ፡- ጅጅጋ ከተማ፡- ቀበሌ 05

1ኛ ክስ፣ወንጀሉ፡-

በ1996 ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ/መ/ህ/ ቁ. 241 እና 251(መ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀሉ ዝርዝር

ተከሳሹ በ1998 ዓ.ም. ወራትና ቀኑ በውል ካልታወቀ ጊዜ ጀምሮ እራሱን ኦ.ብ.ነ.ግ. እያለ ከሚጠራው ተቃዋሚ የፖለቲካ

ድርጅትና አሸባሪ ጋር በራሱ ፈቃድ አባል በመሆን ከዚህ ሕገ-መንግሥቱን ከሚፃረር ድርጅት በቀጥታ ፌዴሬሽኑእንዲከፋፈል፣ ክልሉን

የመገንጠል ዓላማ ለማሳካት ይህንኑ ድርጅት ከዚሁ በጅጅጋ ከተማ ለጊዜው ካልተያዘ ግብረ-አበሩ ጋር በመሆን ይህንኑአሸባሪ ድርጅት

በሚያስፈልገው ማቴሪያል ሁሉ፡- ጫማ፣ የፖሊስ የደንብ ልብስ፣ መድሃኒት. . . የመሳሰለውን በማቀበሉ፡፡

2ኛ ክስ፣ወንጀሉ፡-

በ1996ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ/መ/ህ/ ቁ. 36 (ለ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀሉ ዝርዝር

ተከሳሹ ከ1996 ዓ.ም. ጀምሮ የተለያዩ መ/ቤቶች ማለትም፡- የክልሉ ት/ቢሮን፣ የቀብሪ-ደሐር ት/ቢሮን፣ እንዲሁም የMSF እና የተለያዩ መሥሪያ ቤቶችን እና የትምህርት ተቋማትን ማህተም በማስመሰል አትሞ እና የኃላፊዎችን ፊርማ ዓይነትአስመስሎ በማስፈር ሐሰተኛ ሰነድ አዘጋጅቶ በመገኘቱ ተከሶ ቀርቧል፡፡›› (ሁሉም የክስ ቻርጆች ማኅተም እና አንጋው አፈወርቅ ምንተስኖት የተባለ የክልሉ ዐቃቤ ሕግ ፊርማ አላቸው) እነሆም ያለአንድ ምስክር፣ ያለምንም የሰነድ ማሰረጃ፣ አንድም ቀን ችሎት ቀርበው የእምነት ክህደት ቃል ሳይጠየቁ እና ሳይከራከሩ (ያውም የዞን ፍርድ ቤት) በነዚህ በስም በጠቀስኳቸው በስምንቱ ኢትዮጵያውን ላይ የሞት ቅጣትን የመሰለየመጨረሻ ውሳኔ እንደቀልድ አስተላልፎባቸዋል፡፡ (በነገራችን ላይ ሌሎች 13 የኢትዮጵያ-ሶማሌ ተወላጆችም በተመሳሳይ የሐሰትውንጀላ የዕድሜ ልክ እስር ተፈርዶባቸው ዝዋይ ይገኛሉ፡፡ የሚገርመው ጉዳይ ደግሞ ም ቢሆኑ መጀመሪያ ተጠርጥረው በተያዙበት ወንጀልአይደለምየተጠየቁት፡፡ ጉዳዩ ጭራሽኑ በምርመራም ወቅት አልተነሳም) መቼም በዚህ መልኩ በተቀናበረ የውሸት ክስ ከ20-27 ዓመት የሚገኙ ወጣቶችን በሲኦላዊ እሳተ-ነበልባል ስቅየት ውስጥ እንዲያልፉ ከማድረግም በዘለለ፣ ብሩህ ቀናቸውን አጨልሞ ላይመለሱወደመቃብር የሚሸኝ ቅጣት ሲጣል ከመመልከት የበለጠ የትኛውንም ዜጋ የሕሊና ስቃይ ውስጥ ከትቶ፣ አንገት አስደፍቶ፣ በቁጣ ቀስቅሶ ወደአደባባይ የሚያወጣ ገፊ-ምክንያት አለ ብዬ አላምንም፡፡

ማነው ተጠያቂው?

በእነዚህ ንፁሃን ኢትዮጵያውያን ላይ ‹በጄል-አደብ› የደረሰባቸው በነውረኝነት የታጀለ ኢ-ፍትሐዊ ፍርድ እና ስቅየት፣ የሥርዓቱን እውነተኛ ማንነት ገሃድ የሚያወጣ ተጨባጭ ተግባር መሆኑ ባይካድም፡ ይህንን አረሜናዊ ድርጊት በፊት-አውራሪነት የመሩት፡- ኮሎኔል ሞኒ መንገሻ በጊዜው የክልሉ የፀረ-ሽብር ግብረ-ኃይል ዋና ኃላፊ የነበረ አሁን ወደአዲስ አበባ ተቀይሮ‹ሕገ-ወጥ የሠው ዝውውር ወንጀል መከላከል› ኃላፊ፣ ቢኒያም የተባለ የክልሉ የደህንነት ኃላፊ፣ ሻለቃ ዘገየ በክልሉ የፌዴራል ፖሊስኃላፊ፣

ወልደአራዌ የክልሉ ፖሊስ ም/ኮሚሽነር፤ እንዲሁም ሻለቃ ወንድሜ፣ ሻለቃ በለጠ እና ታሰረ የተባሉ ኃላፊነታቸውንለይተው የማያስታውሷቸው ግለሰቦች መሆናቸውን ግፉአኖቹ በተሰበረ ልብ፣ ምሬት በሞላው ድምፅ፣ ተስፋ በቆረጠ ስሜትሲተርኩልኝ ዓይኖቼ ላይ የተቋጠረው የእንባ ከረጢት ገንፍሎ እንዳይፈስ ብርቱ ትግል ማድረጌን አልሸሽግም፡፡

የሆነው ሆኖ እነዚህ የሥርዓቱ ሹማምንት የፍርድ ቤት ደጅ ሳይረግጡ፣ የሞት ቅጣት እንዲተላለፍባቸው ባደረጓቸው ምስኪኖች ላይ የማሰቃያ ጥበቦቻቸውን በሙሉ ከሞከሩባቸው በኋላ፡- ‹‹ሞት እንፈርድባችኋለን!!›› እያሉ ያስፈራሯቸውናይዝቱባቸው ነበር፤ እነርሱም፡- ‹‹እናንተ ፍርድ ቤት ናችሁ እንዴ?›› ብለው በግርምትና ባለማመን ሲጠይቋቸው፣ ማናአህሎኝነትያሳበጣቸው የፀጥታ

ኃላፊዎች እንዲህ በማለት አስረግጠው መልስ መስጠታቸውን ሰምቻለሁ፡-

‹‹አዎን! ፍርድ ቤት ማለት እኛ ነን!!››

በርግጥ ከዚህ ሁሉ መከራ በኋላ የተላለፈባቸው ውሳኔ፣ ያውም በሞት እንዲቀጡ የሚል መሆኑን ስናስተውል የዛቻውን መነሾ መረዳቱ አዳጋች አይሆንብንም፡፡ በአናቱም በምርመራ ወቅት ዕድል ፊቷን ያዞረችበትን ተጠርጣሪ እዛው እስረኛ ፊትበሽጉጥ ግንባሩን በርቅሰው እንደ መናኛ ነገር ሜዳ ላይ ይዘረጉት እንደነበረ የዓይን እማኞች ይመሰክራሉ፡፡

በጥቅሉ ይህ ሁነት በሀገሪቱ አለቅጥ የተንሰራፋውን የፍትሕ እጦት፣ የሠብአዊ መብት ጥሰት፣ ዳኞች ከሕግ ይልቅ ከቤተ- መንግሥት በሚላክላቸው የፍርድ ውሳኔ ንፁሃኑን ለምድራዊ ስቃይ ከመዳረግም አልፈው ተርፈው በጭካኔሕይወታቸውንም እንደሚነጠቁ በቂ ማስረጃ ይመስለኛል፡፡

‹‹ጄል-አዳብ››

የክልሉ ኗሪዎች ‹‹ጄል-አዳብ›› (የገሃነም እስር ቤት) እያሉ የሚጠሩት የጅጅጋው ማሰቃያ ቤት ክፍሎች የተሠሩት አራትመቶ ታሳሪዎችን እንዲይዙ ታስቦ ቢሆንም፣ አብዛኛውን ጊዜ ከአራት ሺህ በላይ ታሳሪዎች እንደሚታጎሩበት አረጋግጫለሁ፡፡ይህም አንድ ሰው ከአንድ ሰዓት በላይ በእንቅልፍ ማሳለፍ እንዳይችል አድርጎታል፡፡ ምክንያቱም ቦታውን ለተረኛው የመልቀቅ ግዴታአለበትና፡፡

ምናልባት እንቅልፍ ቢጥለው እንኳ ተረኞቹ ቀስቅሰው (ጎትተው) ያስነሱታል፡፡

ከ‹‹ጄል-አዳብ›› በሕይወት ተርፎ የሚወጣ ሰው ዕድለኛ ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ በዚህ ቦታ ከቤተሰብ ጋር መገናኘት ጭራሽ አይሞከርም፡፡ ማሰቡ እንኳ እንደ ቅንጦት ነው የሚታየው፡፡ በእስር ቤቱ አጥር ሦስት መቶ ሜትር ክልል ርቀት ዙርያ ውስጥመገኘትም ለከባድ ስቃይ (አንዳንዴም ለሞት ቅጣት) ይዳርጋል፡፡ በሃያ አራት ሰዓት አንዴ፣ አንድ እንጀራ ለሦስት እየተቃመሱለአምስት ዓመት በዛ እስር ቤት ያሳለፈ ምስኪን አጋጥሞኛል፡፡ ይህ ወጣት በ2004ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ሦስት ዓይነት ተላላፊ  በሽታ (ተቅማጥ፣ ሰውነትን የሚያሳክክና ጉሮሮን አሳብጦ ለአዕምሮ መቃወስ የሚዳርግ) ተከስቶ በቀን እስከ አስራ አራት ሰው ድረስ ይሞትእንደነበር ያስታውሳል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ሕክምና ብሎ ነገር አልነበረም፡፡

እንዲያውም በግልባጩ የክልሉ አስተዳዳሪዎችጭካኔያቸውን (ኢ-ሠብአዊነታቸውን) ወለል አድርገው የሚያሳብቁ ድርጊቶች መፈፀማቸውን አላቋረጡም፡፡ ለማሳያ ያህልም እስረኛው ከሌሊቱስድስት

ሰዓት ላይ በአንድ ድምፅ እንዲህ የሚል መፈክር እንዲያሰማ መገደዱን እዚህ ጋ መጥቀስ ይቻላል፡-

‹‹መለስ ዜናዊ ሐኖላዶ!›› (መለስ ዜናዊ ለዘላለም ይኑር!)

‹‹አብዲ ሑመድ ዑመር ሐኖላዶ!››

‹‹ኢትዮጵያ ሐኖላዶ!››

ኦብነግ ሐዳኦዶ!›› (ኦብነግ ይውደም!)ሌላው አስገራሚ ጉዳይ ቤተሰብ ታሳሪ ልጁ በሕይወት ይኑር ይሙት የሚያውቀውከማጎሪያው በስንት ጊዜ አንዴ የሚፈታ ሰው ሲገኝ ብቻ የመሆኑ እውነታ ነው፡፡ እናም ድንገት በአንዲት ‹ዕድለኛ› ቀን አንድ ታሳሪ ከ‹‹ጄል-አዳብ›› የተለቀቀእንደሆነ ወሬው ከመቅጽበት ይዛመትና ለሳምንታት አሊያም ለወራት የእስረኛው ቤት በእንግዶች እስከ አፍ-ገደፉ ጢም ብሎ ይውላል፡፡የተለመደ ነውና እሱም ያለመታከት የቀረበለትን ጥያቄ በሚከተለው መልኩ ሲመልስ ይከርማል፡- ‹‹ኦ!… እገሌ ከሞተ እኮ ሁለት ዓመት አለፈው›› ፤ “እገሌማ ሲያሳዝን! ካረፈ ገና አንድ ወሩ ነው”፤ “ኦ! እገሌ ለወደፊቱ እግዜር ይጠብቀው እንጂ እስካሁን በሕይወት ይገኛል…” ወዘተ ወዘተ. . .

አመክሮና በቀለ ገርባ

Zelalem Kibret

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) ምክትል ሊቀመንበርና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ መድረክ ስራ አስፈፃሚ የነበሩት “ህጋዊ የፖለቲካ ፓርቲን ሽፋን በማድረግ  የአሸባሪ ቡድን የሆነው ኦነግ አባል ሆነዋል” በሚል ክስ ተመስርቶባቸው የ8 ዓመት እሥር የተበየነባቸው ሲሆን፤ ይግባኝ ጠይቀው እስሩ ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ተደርጎላቸዋል፡፡

bekele-gerbaከ3 ዓመት ከ7 ወር የእስር ጊዜ ውስጥም 3ቱን ዓመት በመጨረሳቸው በአመክሮ ይፈቱ ዘንድ ለማረሚያ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ማረሚያ ቤቱም ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው›  በማለት እስከአሁን ሊፈታቸው አልቻለም፡፡ ይህም ብዙ ጥያቄዎችን አስነስቷል፡፡

አንዳንድ ህጋዊ ሁኔታዎች ስለጉዳዩ፡

አመክሮ ምንደር ነው?
ሌላውን ትርጉም ትተን የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ‹በተወሰነ ጊዜ በአመክሮ መፈታት› በሚለው ክፍል በተለይም በአንቀፅ 202 እንደደነገገው፡
“ተቀጭው ከተወሰነበት የእስራት ጊዜ ከሶስት እጅ ሁለቱን እጅ ወይም ፍርዱ የእድሜ ልክ እስራት ሲሆን ሀያ ዓመት በፈፀመ ጊዜ አግባብ ባለው አካል ወይም በጥፋተኛው አሳሳቢነት ጥፋተኛውን ከቅጣቱ ነፃ ያወጣዋል፡፡” ይህም ማለት አመክሮ 2/3ኛውን የቅጣት ጊዜውን የጨረሰ ታራሚ ከእስር የሚፈታበት አሰራር ነው፡፡

አመክሮ ለማግኝት ምን መስፈርት ማሟላት ያስፈልጋል?

የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ከላይ በጠቀስነው አንቀፅ 202 ላይ አመክሮ ለማግኝት አንድ እስረኛ ማሟላት የሚያስፈልገውን መስፈርቶች ይዘረዝራል፡፡ ይህም፡

– ‹ታራሚው በስራ ጠባዩ የተረጋገጠ መሻሻል አሳይቶ እንደሆነ…›

– ‹ካሳ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበት ከነበረና ካሳውን መክፈሉ የተረጋገጠ እንደሆነ…›

– ‹አመሉና ጠባዩ መልካም አኗኗር ለመኖር የሚያስችለውና በአመክሮ መፈታቱ መልካም ውጤት ሊያስገኝ ይችላል ተብሎ የታመነ እንደሆነ..›

ነው ብሎ ይደነግጋል፡፡

ማረሚያ ቤት ወይስ ፍርድ ቤት?

ታራሚን በአመክሮ የመልቀቅ የመጨረሻው ስልጣን የፍርድ ቤት፡፡ ነገር ግን ጉዳዩን ማረሚያ ቤቱ በራሱ ተነሳሽነት ወይም በታራሚው አሳሳቢነት ለፍርድ ቤት ሲያቀርብ ነው ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጠው፡፡ እዚህ ላይ ማረሚያ ቤቱ ትልቁን ስልጣን ይዞ እናገኛለን፡፡ ማረሚያ ቤቱ ለፍርድ ቤት ማቅረብ ካልፈለገ ሊተወው የሚችልበት አግባብ አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ማረሚያ ቤቱ በሕግ ስር ያለ አካል እንደመሆኑ መጠን በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 202 ላይ የተቀመጡ መስፈርቶችን ላሟላ ታራሚ አመክሮ ሊከለክል አይችልም – የታራሚው መብት ነውና!

በቀለ ገርባስ?

አቶ በቀለ ገርባ ከተፈረደባቸው የአምስት ዓመት እስር ውስጥ 2/3ኛውን ወይም 3 ዓመት የሚሆነውን ጨርሰው የአመክሮ ጥያቄያቸው በማረሚያ ቤቱ በኩል ለፍርድ ቤት እንዲቀርብላቸው ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ  ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የሚል መልስ እንደሰጣቸው ተሰምቷል፡፡
1ኛ. አመክሮ መስጠት የማረሚያ ቤት መብት ሳይሆን ግዴታም ጭምር ነው፡፡ መስፈርቱን ያሟላ ታራሚ አመክሮ የማግኝት መብት ያለው መሆኑ በሌላ በኩል አመክሮ ሰጭውን አካል ላይ ግዴታ ይጥላልና፡፡
2ኛ ሌላው አቶ በቀለ ገርባ መስፈርቱን አሟልተዋል ወይስ አላሟሉም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ 2/3ኛውን የእስር ጊዜ መጨረስ የሚለውን Objective መስፈርት እንዳሟሉ ግልፅ ሲሆን፡፡ ችግሩ የተፈጠረው Subjective መስፈርቱ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ይህም ማለት በእስር ወቅት መልካም ፀባይ አሳይተዋል ወይስ አላሳዩም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ አንድ ታራሚ በእስር ወቅት ለመልካም ፀባይ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮችን ካሳየ የቅጣት ማስጠንቀቂያ ከመፃፍ እስከ ብቻውን ማሰር (Solitary Confinement) ድረስ ያሉ እርምጃዎች በማረሚያ ቤቱ ሊወሰዱበት ይችላሉ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ ከፀባያቸው ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ቅጣት ያልተወሰደባቸው ከመሆኑም ሌላ መልካም ፀባይ እንዳሳዩ ከማረሚያ ቤቱ እንደተነገራቸው ራሳቸው ገልፀዋል፡፡ በቀለ ገርባ ምም መስፈር አሟልተዋል ማለት ነው፡፡ ታዲያ ምን ይሆን አቶ በቀለን በአመክሮ ከመፈታት ያገዳቸው?

አንዳንድ ነገሮች

ባለው አካሄድ አብዛኛው ታራሚዎች በአመክሮ ይፈታል፡፡ ከሌባ እስከ ሙሰኛ፡፡ High Profile በሆኑ ክሶች የተከሰሱ ሰዎች ሳይቀሩ በአመክሮ ሲፈቱ እንደነበር እናስታውሳለን ለምሳሌ ቴዲ አፍሮ 24 ወራት ተፈርዶበት 16 ወራትን ጨርሶ በአመክሮ ተፈቷል፡፡ አቶ አሰፋ አብርሃ 9 ዓመት ተፈርዶባቸው ሰባት ዓመታት ታስረው ከብዙ ውዝግብ በኋላ በአመክሮ ተፈተዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅንጅት ክስ ስር ተከሰው የነበሩት አቶ ዳንኤል በቀለና አቶ ነፃነት ደምሴ 30 ወራት የተፈረደባቸው ሲሆን 20 ወራትን በእስር አሳልፈው አመክሮ ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ ‹ፍርዳችሁን ጨርሳችሁ ውጡ› በሚል ምክንያት አመክሮ ከልክሏቸው ነበር፡፡

እንግዲህ አቶ በቀለ ገርባ በሕጉ የተቀመጠውን መስፈርት አሟልተው እያለ በአመክሮ የመፈታት መብታቸው አልተከበረም ወይም ማረሚያ ቤቱ ግዴታውን ሊወጣ አልፈለገም!

ምክንያት: በጉልበተኞች የምትተዳደር ሀገር ዜጋ ስለሆኑ!

ልዩ ማስታወሻ፡-ይህ ባለፈው ጥር  16 ቀን 2006 ዓ.ም. የዞን 9 ብሎገርና የአምቦ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ዘለዓለም ክብረት ከመታሰሩ በፊት የፃፈው ቢሆንም፤በአሁን ሰዓት እሱ ራሱ በግፍ እስር አቃቂ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ይገኛል፡፡

#‎FreeBekeleGerba

ይድረስ ለአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና ለኢህአዴግ አመራሮች!

ብስራት ወልደሚካኤል

afrosonb@gmail.com

 Image

በቅድሚያ የከበረ ሰላምታዬ በያላችሁበት ይድረሳችሁ፤ ምንም እንኳ እናንተ ብዙውን ሰላም እየነሳችሁ ብታስቸግሩም፡፡ ዛሬ ግን እስኪ በእናንተ እና በቤተሰባችሁ ላይ እንዳይፈፀም የምትፈልጉትን በሌላው ላይ ስላደረጋችሁት ከብዙው አንዲት እውነት ብቻ አንስቼ ልጠይቃችሁ ወደድሁ፡፡ የጥያቄው መልስ ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለህሊናችሁ፣ እናንተ በምትመሩት አስከፊ፣ አፋኝ እና ጨቋኝ ስርዓት ሰለባ ለሆኑ እንዲሁም አሁንም በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የተለመደውን እኩይ ተግባር ለምትፈፅሙባቸውና ለቤተሰቦቻችሁ ይሆን ዘንድም አበክሬ እጠይቃለሁ፡፡

ክቡር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እርስዎ ተወልደው ባደጉበት የደቡብ ክልል ወላይታ ዞን ቦለሶ ሶሬ ወረዳ መዲና በሆነችው አረካ ከተማን መቼም የሚረሷት አይመስለኝም፡፡ እርስዎ አሁን የደረሱበት የይምሰልም ይሁን ተግባር የጠቅላይሚኒስትርነት በትረ ስልጣን ከመጨበጦ በፊት እዛው አረካ ከተማ አካባቢ እንደ አብዛኛው የሀገራችን ህዝብ በግብርና እርሻ ሙያ ዕየተዳደሩ ነው እንበል፡፡ ታዲያ በዚህ ሙያ ሳሉ ልክ አሁን እንዳሉት ባለትዳር እና የ3 ልጆች አባት ሆነው፤ እርስዎ በሚመሩት ኢህአዴግም ይሁን 24 ሰዓት በምትኮንኑት ደርግ ስርዓት አርዓያ “ሞዴል” አርሶ አደር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ተብለው የትውልደ ቀዬዎትን ወክለው በደቡብ ክልል መንግስት ቢሸለሙ ምን ይሰማዎታል? ያው ደስታ እንደሚሉኝ አልጠራጠርም፡፡

አለበለዚያም ገበሬ ሆኜ አላውቅም ካሉም፤ ያኔ አርባምንጭ የውሃ ቴክኖሎጂ ተቋም (የአሁኑ አርባምንጭ ዩኒቨርስቲ) ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በተመረቁበት ሲቪል ምህንድስና(Civil Engineering) አሊያም ከፊንላንድ በተመረቁበት የአካባቢ ንፅህና ምህንድስና(Sanitory Enegineering) እስተማሩና እያስተዳደሩ ሞዴል መምህር ተብለው በወቅቱ ገዥ ስርዓት ቁንጮዎች ቢሸለሙ ምን ይሰማዎታል? አሁንም ያው ደስታ ነው እንጂ ሀዘን ሊሉኝ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ማንም ሰው በሙያው ጥሮ ግሮ ላበረከተው አስተዋፅዖ እና ለሌሎች መልካም አርዓያ በመሆኑ የሚጠላ አይኖርምና፡፡ ይሄንን ምሳሌ ለራስዎ መቀበል ካልቻሉም ከቤተሰብዎ እጅግ መልካም ነው ብለው አብልጠው የሚወዱት ወንድምዎ ካሉም በእርስዎ ምትክ እርሳቸውን ተክተው እርስዎን በታዛቢነት ያስቀምጡ፤ ስሜቶንም ያሰላሱ፣ ይግለፁ፡፡

በሙያዎ  ለብዙ ዓመታት ሰርተው ለሌሎች አርዓያ ተብለው ሽልማት፣ እውቅና እና ሙገሳ ከተሽጎደጎደልዎ 3 ወር ሳይሞላ፤ ከትዳር አጋርዎ ወ/ሮ ሮማን ተስፋዬ እና የበኩር ልጅዎን ተማሪ ዮሐና ኃይለማርያምን ጨምረው ከሌሎች ልጆቾ ጋር አምላኬ በሰላም አሳድረኝ ብለው ተቃቅፈው ተኝተው በሸለሞት አካል አሸባሪ ተብለው ሌሊት በቤትዎና በቤተሰብዎ ላይ በ 16 “የፀረ-ሽብር” ግብረ ኃይል የጥይት እሩመታ ሲሰሙስ ምን ይሰማዎታል? አሁን ልክ እንደቅድሙ ደስታ ሊሉኝ አይችሉም፡፡ በዚህ ብቻ ሳያበቃ እርስዎን በቤተሰብዎ ፊት በሸለሞት አካል በ 16 ግብረ ኃይል ሽፍታ ነው ተብለው በክብር አርፈው ከተኙበት ቤት በሚተኮሱ የጥይት ናዳዎች በቤተሰብዎ ፊት ህይወትዎ እስከወዲያኛው ቢያልፍ እና እንደው ግማሽ ነብስ የለም እንጂ በከፊል ድርጊቱን ቢታዘቡት ምን ይላሉ; ከእርስዎ በተጨማሪ ለፍተው ጥረው ግረው ያቆሟት ቤት፣ ያፈሯቸው ላሞች ፣በጎችና በሬዎች በማያውቁት ነገር የጥይት ናዳ ሲያርፍባቸውስ;

ከላይ በተጠቀሱት ሳያበቃ ግብረ ኃይሉ አሁን የሰው ህክምና ሳይንስ የምታጠናው የበኩር ልጅዎ ተማሪ ዮሐና ሌሊቱን ገና በ8 ዓመቷ ከእቅፎ ተኝታ እርስዎ ሲገደሉ እርሷ የምትፅፍበት፣ አሊያም በትርፍ ጊዜዋ ከብቶች የምታግድበት ወይንም እንደሌሎች ህፃናት ከአቻዎቿ ጋር ለመጫወት የምትጠቀምበት የቀኝ እጇ ሙሉ ለሙሉ በጥይት ቢቆረጥስ ምን ይሰማዎታል? በዚህም ደስታ እንደማይሉኝ ግልፅ ነው፡፡ ልክ በውጊያ አውድማ እንዳለ ወታደር ከወላጆቿ እቅፍ ሳለች ቀኝ እጇ የተቆረጠችው ልጅ ስታድግስ ምን ይሰማት ይሆን? ፍርዱን ህሊና ላለው ሁሉ ልተወው፡፡

 ልክ እንደ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በሌሎች የኢህአዴግ አመራሮች እና አባላት ላይ ተመሳሳይ ድርጊት ቢፈፀም ምን ይሰማችኋል; እናንተም ደስታ እንደማትሉኝ አልጠራጠርም፡፡ ይህንን ሁሉ የጠቀስኩት በማንም የሰው ሰብኣዊ የሰው ልጅ ላይ እንዲህ ዓይነት ዘግናኝ ድርጊት እንዲፈፀም ፈልጌ አይደለም፤ ይሄንንም አቶ ኃይለማርያምም ሆኑ ሌሎች ግብር አበሮእዎ በቅን ልቦና እንድትረዱልኝ እሻለሁ፡፡

ክቡርነትዎ፤ ከላይ ብእርስዎ የጠቀስኩት ምሳሌ በሌላ ኢትዮጵያዊ ላይ በእናንተ ስርዓት አመራር የተፈፀመ እውነተኛ ድርጊት መሆኑንን ከዚህ እንደሚከተለው በአጭሩ ልነግሮት እወዳለሁ፡፡Image

ጥቅምት 15 ቀን 2006 ዓ.ም. በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ዳባት ወረዳ አረቦር ቀበሌ ልዩ ቦታው ደቀፉቀር በሚባል ስፍራ  ከሌሊቱ 12 ሰዓት ከነ መላው ቤተሰቦቻቸው አምላኬ በሰላም አሳድረኝ ብለው የተኙ፤በእነ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስርዓት ሞዴል አርሶ አድር ተብለው የተሸለሙ ታታሪ ገበሬ አቶ ማስረሻ ጥላሁን  በ 16 የፀረ ሽብር ግብረኃይል በተተኮሱ የጥይት ናዳዎች እዛው እቤታቸው ህይወታቸው አልፏል፡፡ የሚያሳዝነው ለግድያ የተላከው ግብረ ኃይል አቶ ማስረሻን ከገደሉ በኋላም በመኖሪያ ቤታቸው ላይ ተከታታይ የጥይት ናዳ በማውረድ ቤታቸውን የጥይት ጌጥ ሲያደርጉት ጥረው ግረው ያፈሯቸው ከብቶችንም ከመግደል እና ከማቁሰል አልቦዘኑም ነበር፡፡ የሚገርመው እንዴት የአንድ ሰው መኖሪያ ቤት የቀድሞ የአድዋ ወይም ባድመ፣…የውጊያ ስፍራ ሊመስል እንደቻለ ግልፅ አይደለም፡፡

ከላይ ከተጠቀሰው በተጨማሪ እጅግ የሚዘገንነው እና የሚያሳዝነው በተመሳሳይ ሰዓት የአቶ ማስረሻ ጥላሁን የ 8 ዓመት ልጅ ስለእናት ማስረሻ እዛው በሞት ከተነጠቀው ወላጅ አባቷ እና በፀረ ሽብር ግብረኃይል ከተሸበሩ ምስኪን ቤተሰቦቿ እቅፍ ሆና ሲነጋ ጥቅምት 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ከአቻዎቿ ጋር ትምህርት ቤት ስለመሄድ እና ስለመጫወት ስታልም ብዙ ስራዎችን የምትሰራበት ቀኝ እጇ በግብረ ኃይሉ ጥይት ሙሉ ለሙሉ ተቆርጧል፡፡

አቶ ኃይለማርያም በእርስዎ እና በግብር አበርዎ የሚመራው ኢህአዴግ ሞዴል አርሶ አደር ያላችኋቸውን አቶ ማስረሻ ጥላሁንን በ 16 “የፀረ ሽብር” ግብረ ኃይል ለማስገደል በወረዳውና በዞኑ አመራሮች ሽፍታ ነው የሚል ለባለቤታቸውና በህይወት ለተረፉ ልጆቻቸው መልስ ተሰጥቶ ፍትህ እንጦርጦስ ገብቷል፤ ቀድሞም ቢሆን ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአዴግ እስካለ ፍትህ እና ርትዕ ከማግኘት ሰማይ ቤት ደርሶ መመለስ የቀለለ ይመስል ሰው ተስፋ ቢቆርጥም፤ ለወጉም ቢሆን ፍርድ ቤት መኳተኑ አልቀረም፡፡ ነገር ግን እሮጣ ያልጠገበች፣ክፉና ደጉን የማታውቅና ቂም በቀል የሌለባት፣ ዓለማችንንም ይሁን ሀገራችንን ኸረ እንደውም አካባቢዋን በቅጡ ለይታ የማታውቅ የ 8 ዓመቷ ህፃን ስለእናት ማስረሻ ጥላሁንን ምን ብላችሁ ይን እጇ እንዲቆረጥ የተደረገው? ነው ወይስ ይህቺን ህፃንም ሽፍታ ነች ልትሉን ነው? ኸ…ረ…ረ..የፍትህ ያለህ፣…የህፃን ልጅ ያለህ፣…ቢያንስ ሰብዓዊነት እንኳ እንዴት ይሳናችኋል?

እስኪ አቶ ኃይለማርያም ስለእናት ማስረሻ ላይ የተፈፀመው በእርስዎ የበኩር ልጅ ዮሐና ኃይለማርያም ላይ ቢፈፀም ምን ይሰማዎታል; ስለ እናንተ ልጆች እንደምታስቡ ሁሉ ስለሌሎች ህፃናት ያላችሁ አስተሳሰብና አመለካከት ወይም ግንዛቤ የት ድረስ ነው? ዛሬ በዚህ ግፈኛ ስርዓት ቀኝ እጇ የተቆረጠው ስለእናት ማስረሻ ነገ እንደማንኛውም ልጅ አራሷን፣ ቤተሰቧን፣ ሀገሯን ብሎም የዓለምን ማኀበረሰብ ልታገለግል ምትችል፣ ብዙ ተስፋ የሰነቀች ነች፡፡

አሁን ግን ገና የ !ኛ ክፍል ትምህርቷን  በጀመረች አንድ ወር ከአስር ቀን የመመህሮቿን የፊደል አጣጣል ትዕዛዝ የምትቀበልበት ቀኝ እጇ ገና ከጅምሩ ተቆርጧል፡፡ በዚህም ምክንያት ሰኞ ማክሰኞ እያለች ትምህርቷን መከታተል ሲገባት ፍትህ አጥታ ከምትኖርበት ዳባት ወረዳ፣ ሰሜን ጎንደር ዞን ከዚያም የአማራ ክልል ፍትህ ፅፈት ቤት እስከ ህፃናት ጉዳይ በጥይት ናዳዎች ከተረፉ ቤተሰቦቿ ጋር ፍትህን ፍለጋ እየተንከራተተች ትገኛለች፡፡

በአንፃሩ ደግሞ የአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ልጅ ዮሐና ኃይለማርያም በተደላደለ ሰላም፣ ጤናና እና ሁኔታ የህክምና ትምህርት ትከታተላለች፣ የብአዴኑ ሊቀመንበር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ልጆችም የተሸለ ትምህርት ቤት ከዚሁ ደህ ህዝብ በሚገኝ ገንዘብ ይማራሉ፣ የአቶ በረከት ስምዖንን ፣ የዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል፣ የአቶ ሙክታር ከድር፣ የነ ሀሰን ሽፋ፣ የነ ጌታቸው አሰፋ ፣ የነ አያሌው ጎበዜ፣ የነ ገዱ አንዳርጋቸው፣ የነ ግዛቱ አብዩ እና የሌሎች የኢህአዴግ ሹማምንት ልጆች በህዝብ ሃብት ተንደላቀው በተመቻቸ ሁኔታ ይማራሉ፡፡  የዳባት ወረዳ ነዋሪዋ ህፃን ስለ እናት ማስረሻ ደግሞ ለትምህርት ባልተመቻቸ ሁኑታ እንኳ የጀመረችውን ትምህርት እንዳትማር ቀወላጅ አባቷን በግፍ ከማጣቷ በተጨማሪ ቀኝ እጇን ተቆርጣ ፍትህን ፍለጋ ትኳትናለች፡፡

ታዲያ ክቡር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እና ሌሎች የኢህአዴግ ሹማምንት ሆይ፤ የምትመሩት ስርዓት በህፃናት ስም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ረብጣ ዶላሮችን እንደሚያገኝ የምትዘነጉት አይመስለኝም፡፡ ይሁን እንጂ በህፃናቱ ስም የሚመጣው እርዳታ ቢያንስ በአግባቡ ጥቅም ላይ መዋል ባይችል እንኳ ለምን አንዲትን ህፃን በፀረ-ሽብር ግብረኃይል በጥይት ለማስመታት ዋለ? በዚህች ህፃን ልጅ እና ወላጅ አባቷን ጨምሮ በቤተሰቦቿ ላይ የተፈፀመው ግፍ የት ድረስ ያስኬዳችኋል? ይህችን ደብዳቤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ አቶ ኃለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ ይህቺ ደብዳቤ ደረሳችሁ ሌሎች የኢህአዴግ አመራሮች ፤ ስለ ህፃናት ልጆቻችሁ፣ ስለ እናቶቻችሁ ፣ ስለሚስቶቻችሁ እና ስለራሳችሁ ብላችሁ የዚህቺን ህፃን እና ቤተሰቦች ጊዜ ሳትሰጡ ፍትህን ፍለጋ እየደከሙ ነውና ፍትህን ይሻሉ፡፡

እነ አቶ ኃለማርም ደሳለኝ የእውነት ከልብ አዝናችሁና እና ተሰነምቷችሁ ፍትህን መስጠት ከቻላችሁ የድርጊቱ ፈፃሚዎች  ብዙ በምታወሩበት ኢቴቪና  በሌሎች መድረኮች ሌሎች አመራሮችም ሆኑ ህዝብ እንዲማሩበት ጭምሩ ተገቢው ፍርድ በግልፅ በአደባባይ ሊሰጥ ይገባል፡፡ እዚህ ላይ የሴቶች እና ህፃነት ጉዳይ ቢሮዎች፣ አቃቤ ህግ፣ ጠበቆች ፣የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና ሌሎች የሚመለከታችሁ አካላት የድርሻችሁን ትወጡ ዘንድ ተግባሩ የት አለ? ስል መልሳችሁን በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡

ታህሣሥ 2006 ዓ.ም.  ተፃፈ

አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ

ሰበር ሰሚ ችሎት የነ አቶ በቀለ ገርባን ይግባኝን እንደማያይ አስታወቀ -እነ አንዱዓለም አራጌም የፊታችን ሰኞ ሰበር ሰሚ ችሎት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የኦፌኮ-መድረክ ምክትል ሊቀመንበር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ላይ እና የኦፌኮ ሌላው አመመራር ወጣት ኦልባና ሌሊሳ የጠየቁትን ይግባኝ ዛሬ ጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በዋለው ችሎት የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የህግ ስህተት የለውም በሚል ሰበር ሰሚ ችሎቱ ይግባኙን ውድቅ አድርጎታል፡፡ አቶ በቀለ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት በፌደራሉ አቃቤ ህግ በተከሰሱበት የሽብር ወንጀል 8 ዓመት ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን ፤ ይህን በመቃወምፈደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠይቀው ነበር፡፡

ጠቅላይ ፍርድ ቤቱም በከፍተኛው ፍርድ ቤት የተወሰነውን የ8 ዓመት እስራት ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ማድረጉይታወቃል፡፡ አቶ ኦልባና ሌሊሳም በከፍተኛው ፍርድ ቤት 13 ዓመት ፅኑ እስራት የተፈረደባቸውን በይግባኝ ጠቅላይፍርድ ቤቱ ወደ 11 ዝቅ እንዲል አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ እነ አቶ በቀለ ገርባ የተከሰስነው በሐሰት የፈጠራወንጀል እንጂ ምንም የፈፀምነው ወንጀል ስለሌለ፤ አቃቤ ህግም በከሰሰን ወንጀል ያቀረበው ማስረጃ እርስ በርሱየሚጣረስ በመሆኑ ሰበር ሰሚ ችሎቱ በነፃ ሊያሰናብተን ይገባል ሲሉ ይግባኝ ቢሉም ፤ሰበር ሰሚ ችሎቱ በዛሬውጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ውሎው የይግባኝ ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጎታል፡፡

በተያያዘ ዜና የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ አንዱዓለም አራጌ ፣ሌላው የፓርቲው ምክር ቤት አባል አቶ ናትናኤል መኮንን፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ፣ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ እናሌሎች የአንድነት ፓርቲ አመራርና አባላት በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እና ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተወሰነባቸውንየጥፋተኝነት ውሳኔ በመቃወም ለሰበር ሰሚ ችሎት ይግባኝ ብለዋል፡፡ በዚሁ መሰረት የፊታችን ሰኞ ጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ 8 ሰዓት 6 ኪሎ በሚገኘው ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ቀነ ቀጠሮ መሰጠቱንጠበቃው አቶ አበበ ጉታ አስታውቀዋል፡፡

ይህም ለነ አቶ አንዱዓለም ቀጠሮ የመጀመሪያው የሰበር ሰሚ ችሎት ቀነ ቀጠሮ መሆኑ ታውቋል፡፡ አቶ አንዱዓለምአራጌ በከፍተኛው እና በጠቅላይ ፍርድ ቤት ዕድሜ ልከል ፅኑ እስራት ሲፈረድበት ጋዜጠና እስክንድ ነጋ ደግሞ 18 ፅኑ እስራት ፍርድ በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ መፅናቱ ሲታወቅ የሌሎችም እንዲሁ መሆኑም አይዘነጋም፡፡