Category Archives: Politics

የጀርመኗ መራሒተ መንግሥት አንገላ መርከል መንግሥት ለተቃዋሚዎችና ለሲቪክ ማኅበራት ሰፊ የፖለቲካ ዕድል እንዲሰጥ ጠየቁ

ብርሃኑ ፈቃደ
– ፖለቲካዊ አለመግባባቶች በምክክር እንዲፈቱና ለወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር የመንግሥት የቤት ሥራ መሆኑን አሳሰቡ

– ከተቃዋሚ ፓርቲዎችና ከሲቪክ ማኅበራት ጋር በአገሪቱ ጉዳይ ተነጋገሩ

angela-merkel-and-hailemariam-in-ethiopia

ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ሰኞ መስከረም 30 ቀን 2009 ዓ.ም. አዲስ አበባ የገቡት የጀርመኗ መራሒተ መንግሥት አንገላ መርከል፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በፖለቲካ መስክ ለተቃዋሚዎችም ሆነ ለሲቪክ ማኅበራት ሰፊ ዕድል እንዲሰጥ ጠየቁ፡፡ የፖለቲካ አለመግባባቶች በውይይትና በምክክር እንዲፈቱም አሳሰቡ፡፡
መርከል ማክሰኞ ጥቅምት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ጋር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት እንደተናገሩት፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎች መደመጥ አለባቸው፡፡ ሲቻልም በተወካዮች ምክር ቤት ጭምር እንዲሳተፉ በማድረግ ድምፃቸው እንዲሰማ፣ ውይይትና ክርክር እንዲያደርጉ መንገዱን ማመቻቸት ይገባል፡፡

‹‹መነጋገር በጣም ጠቃሚ እንደሆነ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ጋር በተነጋገርንበት ወቅት ገልጫለሁ፡፡ የሲቪክ ተቋማትን ማሳተፍና በጠረጴዛው ዙሪያ እንዲገኙ መጋበዝ ይገባል፡፡ ጥሩ ትምህርት ቤቶች ሠርታችኋል፡፡ ከጎበኘኋቸው የአፍሪካ አገሮች ይልቅ እዚህ ብዙ ጥሩ ነገሮች ተሠርተዋል፡፡ ነገር ግን ለወጣቶች ሥራ መፍጠር ካልቻላችሁ የተሠራው ሁሉ ምንም ትርጉም አይኖረውም፤›› ያሉት መራሒተ መንግሥት መርከል፣ ‹‹ከአገሪቱ ግማሽ ያህሉ ሕዝብ በወጣቶች የተገነባ ነው፡፡ ወጣቶች ደግሞ ስሜታቸውን ባገኙት መንገድ መግለጽ ይፈልጋሉ፡፡ በማኅበራዊ ሚዲያዎችና በሌሎችም የሚሰማቸውን ለመግለጽ ይፈልጋሉ፡፡ ቅሬታውቸውን ሲገልጹም ትዕግሥት ላይኖራቸው ይችላል፤›› ብለዋል፡፡ በውይይትና በመነጋገር ጥሩ የመፍትሔ ሐሳቦች እንደሚመነጩ ሲመክሩም፣ በአገራቸው የፖለቲካ ሥርዓት በውይይትና በመነጋገር አብዛኞቹ ለውጦች እንደሚመነጩ አብራርተዋል፡፡ በዚህም አገር የቱንም ያህል አስቸጋሪና ከባድ ቢሆን በመነጋገር ችግሮችን መፍታት ይገባል ብለዋል፡፡

መንግሥት እንዲህ ያሉ አሳሳቢ ችግሮችን ለመፍታት ወጣቶችን በኢኮኖሚ መስክ በተገቢው መንገድ ተጠቃሚ እንደሆኑ ከማድረግ ባሻገር፣ ነፃ ሚዲያም ለአገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ህልውና ወሳኝ እንደሆነ በመግለጽ መንግሥት ትኩረትም ቦታም እንዲሰጠው ጠይቀዋል፡፡

‹‹ዴሞክራሲያችን እንጭጭና ያልጠነከረ በመሆኑ በርካታ ችግሮች አሉበት፡፡ በየፈርጁ ያሉብንን ችግሮች ከማመን ተቆጥበን አናውቅም፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ በአገሪቱ ይበልጥ የፖለቲካ ምኅዳሩን የሚያሰፉ ዕርምጃዎች እንደሚወሰዱ ከመራሒተ መንግሥት መርከል ጋር በመሆን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት አስታውቀዋል፡፡ አሳታፊና ለበርካቶች ዕድል የሚፈጥሩ፣ ለሲቪክ ማኅበራትም ቦታ የሚሰጡ ፖለቲካዊ ዕርምጃዎች እንደሚወሰዱ ጠቁመዋል፡፡ በምርጫ ሥርዓቱ ላይ ያሉትን ችግሮች ለመቅረፍ ማሻሻያዎች እንደሚደረጉም አስታውቀዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ የመርከል ማብራሪያዎች በአብዛኛው በፓርላማው በፕሬዚዳንቱ ከቀረበው የመንግሥት የሥራ ዕቅድ ጋር ተመሳሳይነት ያላቸው ነበሩ፡፡

ወጣቶች ሥራ በማጣት በዚህም ሳቢያ በተፈጠረባቸው መከፋትና ተስፋ መቁረጥ መንግሥት ላይ ተቃውሞ ማሰማታቸው ተገቢ እንደሆነ ያመኑት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መንግሥት የተነሳበትን ተቃውሞ ትክክለኛ መሆኑን እንደሚቀበልም አስታውቀዋል፡፡ ከ15 ሚሊዮን ያላነሱ ወጣቶች በሥራ ፍለጋና በትምህርት ላይ እንደሚገኙ የጠቀሱት አቶ ኃይለ ማርያም፣ መንግሥት የሥራ ዕድሎችን በሚፈለገው መጠን ማሟላት እንዳልቻለ አምነዋል፡፡

ይሁንና ተቀባይነት ያላቸውን ተቃውሞች ተገን በማድረግ የተከሰቱት ብጥብጦችና ንብረት የማውደም ዕርምጃዎች ተቀባይነት የላቸውም ብለዋል፡፡ በርካታ ፋብሪካዎች፣ የውጭና የአገር ውስጥ ባለሀብቶች የገነቧቸው ኢንዱስትሪዎችና ሀብቶች መቃጠላቸውን በመግለጽ፣ እንዲህ ያሉትን ብጥብጦች ጉዳት ያስከተሉት ‹‹ከውጭ ጠላቶች›› ጋር የሚያብሩና ‹‹መሣሪያ የታጠቁ›› አካላት ናቸው በማለት በአገሪቱ የተቀጣጠለውን ፖለቲካዊ ቀውስ ለማብረድ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መደንገጉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መደንገግ በኋላም በአገሪቱ አንድም ብጥብጥ እንዳልተከሰተ ጠቁመዋ፡፡

የተከሰቱትን ግጭቶችና ብጥብጦች ለመቆጣጠር የፀጥታ ኃይሎች የወሰዱት ዕርምጃ ተመጣጣኝነትን በሚመለከት ተጠይቀውም፣ ‹‹መሣሪያ ካነገቱ ታጣቂዎች ጋር መነጋገር የሚቻለው በመሣሪያ ብቻ ነው፤›› ያሉት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ይሁንና የፀጥታ ኃይሎች የወሰዱት ዕርምጃ ተመጣጣኝ ስለመሆኑና ከሚፈቀድላቸው በላይ ኃይል ስለመጠቀማቸው ምርመራ እንደሚካሄድ አስታውቀዋል፡፡

በተከሰተው ቀውስ ምክንያት የሟቾች ቁጥር ከ500 በላይ ስለመድረሱ የተጠየቁት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ግጭቶቹን የሚያባብሱት የታጠቁ ሰዎች የሚያደርጉት እንቅስቃሴ የሟቾችን ቁጥር ከዚህም በላይ ሊያሻቅበው እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ ጉዳዩንም የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እያጣራ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተከሰቱ ግጭቶች የሟቾች ቁጥር 190 ያህል እንደደረሰ፣ ከዚህም ቀደም በተከሰተው ግጭት በኦሮሚያ 178 ሰዎች፣ በአማራ ክልል ደግሞ 120 ሰዎች መሞታቸውን ኮሚሽኑ ይፋ እንዳደረገ በመጥቀስ ከጀርመን ጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

የተቀሰቀሱ ግጭቶችን በቁጥጥር ሥር ለማዋል የመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች የሚወስዷቸው ዕርምጃዎች ተመጣጣኝነት ላይ የሚነሱትን ክሶች መነሻ በማድረግም፣ መንግሥታቸው የጀርመንን ድጋፍ እንደሚሻና ሥልጠና እንዲሰጥም ጠይቀዋል፡፡ ብጥብጥን ለመቆጣጠርና ግጭቶች ደም አፋሳሽ ከመሆናቸው በፊት በሠለጠነ መንገድ ለመቆጣጠር የፀጥታ ኃይላቸውን ጀርመን እንድታሠለጥንላቸው ያቀረቡትን ጥያቄ የተቀበሉት መርከል፣ ድጋፍ እንደሚሰጡ አስታውቀዋል፡፡

በሁለቱ መሪዎች በተሰጠው መግለጫ ወቅት መራሒተ መንግሥት መርከል ከተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ጋር ስለሚያደርጉት ውይይት አጀንዳ ምንም ዓይነት ማብራሪያ ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ሁለቱ መሪዎች በፀጥታና በደኅንነት ጉዳዮች፣ ስደተኞችን በተመለከቱ ተግባራትና በሌሎችም ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ በሁለትዮሽ ውይይታቸው ወቅት መነጋገራቸው ታውቋል፡፡

ጀርመን በኢትዮጵያ መንግሥት አሸባሪ ተብለው ከተፈረጁ የተቃዋሚ ቡድኖች መካከል እንደ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ያሉት የሚገኙባት እንደመሆኗ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ሁለቱ መሪዎች ተነጋግረው እንደሆነ ሪፖርተር ጥያቄ ያቀረበላቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ፣ መሪዎቹ እንዲህ ባሉ ነጥቦች ላይ በተናጠል እንዳልተነጋገሩ ገልጸዋል፡፡

መራሒተ መንግሥት መርከል ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ያደረጉትን ውይይት አጠናቀው፣ በጀርመን ድጋፍ በአፍሪካ ኅብረት ቅጥር ግቢ ውስጥ የተገነባውንና በቀድሞው የታንዛኒያ መሪ ጁሊየስ ኔሬሬ ስም የተሰየመውን የፀጥታና የደኅንነት መሥሪያ ቤት መርቀዋል፡፡ ስድስት ያህል የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችን አነጋግረው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበርና የውጭ ግንኙነት ኃላፊ ዶ/ር መረራ ጉዲና ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከመራሒተ መንግሥት መርከል ጋር በአገሪቱ በተካሄዱ ተቃውሞዎችና የመንግሥት ምላሽ፣ በነፃና ፍትሐዊ ምርጫ ጉዳዮች ላይ ተነጋግረዋል፡፡
አገሪቱ በወሳኝና አሳሳቢ ጊዜ ላይ እንዳምትገኝ የገለጹት ዶ/ር መረራ መንግሥት እንደወትሮው ‹‹የተቀባባና የተሽሞነሞነ መግለጫውን›› ትቶ ትክክለኛ ለውጥ በአፋጣኝ እንዲያመጣ፣ የሚደረጉ ለውጦችም ወደፊት በታሳቢነት ሳይሆን አሁኑኑ ሊደረጉ እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ አንገላ መርከል የአገሪቱ ተቃዋሚዎች፣ ሲቪክ ማኅበራትና ሌሎችም የሚገኙበትን ሁኔታ እንደሚገነዘቡና በሚደርስባቸው ጫናም ሐዘኔታ እንዳደረባቸው ዶ/ር መረራ ገልጸዋል፡፡

አንገላ መርከል ወደ አገራቸው ከተመለሱ በኋላ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ወደፊት እንደሚጠብቁ የገለጹት ዶ/ር መረራ፣ እሳቸውን ጨምሮ ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፣ የዞን ዘጠኝ ጦማሪያን፣ የሴቶች ማኅበራት ተወካዮች በተገኙበት ከመራሒተ መንግሥት መርከል ጋር መነጋገራቸው በማውሳት ሪፖረተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሰብዓዊ መብት ጥሰቱን ሊያባብሰው ይችላል ተባለ

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተለያዩ ቦታዎች ይሰፍራል ተብሎ የሚጠበቀው የመከላከያ ሰራዊት ከዚህ በፊት ይወስድ የነበረውን የሃይል ዕርምጃ በማጠናከር ተጨማሪ አፈናን አግባራዊ እንደሚያደርግ የስብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ገልጸዋል።

በሃገሪቱ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መንግስት ከዜጎቹ የተነሱ ጥያቄዎችን በሰላማዊ መንገድ ከመፍታት ይልቅ በሃይል ለመቆጣጠር ፍላጎት እንዳለው ማሳያ ነው ሲሉ በድርጅቱ የአፍሪካ ቀንድ ተመራማሪ የሆኑት ፊሊክስ ሆርን ገልጿል።

በኦሮሚያ ክልል ለወራት የዘለቀው ህዝባዊ ተቃውሞ በመቶዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ሞት ምክንያት መሆኑን ያወሳው ሂውማን ራይትስ ዎች ጥያቄ ያላቸው አካላት ምላሽን ካላገኙ ተቃውሞ ቀጣይ ሊሆን እንደሚችል አሳስቧል።

ለአለም አቀፉ ማህበረሰ ስጋት እየሆነ የመጣው የጸጥታ ሃይሎች እርምጃና ተቃውሞ ቀጣይ የሚሆን ከሆነም ሃገሪቱ ሊቀለበስ ወደ ማይችል የሰብዓዊ መብት ቀውስ ውስጥ ልትገባ እንደምትችል ሂውማን ራይትስ ዎች በወቅታዊ የኢትዮጵያ ጉዳዮች ዙሪያ ባወጣው ሪፖርት አመልክቷል።
በርካታ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የሰብዓዊ መብት ረገጣን ሊያባብስ ይችላል ሲሉ ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ለስድስት ወር የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጊዜው ከመጠናቀቁ በፊት ሊነሳ እንደሚችል የመንግስት ባለስልጣናት መግለጻቸውን ብሉምበርግ ማክሰኞ ዘግቧል።
“የስድስት ወሩ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሙሉ ለሙሉ ላያስፈልገን ይችላል ሲሉ ለዜና አውታሩ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ ከተቀመጠው ጊዜ በፊት ችግሮቹን ልንቆጣጠር እንችላለን ብለዋል።
ምንጭ፡-ኢሳት

በዲላ ከተማ በተቀሰቀሰ ደም አፍሳሽ ግጭት የበርካታ ሰዎች ሕይወት አለፈ

ዮናስ ዓብይ እና ውድነህ ዘነበ

ባለፈው ሳምንት ዓርብ መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በደቡብ ክልል ጌዲዮ ዞን የተቀሰቀሰው ደም አፍሳሽ ግጭት፣ ለበርካታ ሰዎች ሕይወት መጥፋትና ንብረት ውድመት ምክንያት ሆነ፡፡

ከጌድዮ ዞን እየወጡ ያሉ መረጃዎች ባለፈው ዓርብ ከቀኑ 4፡30 ሰዓት ተጀምሮ እስከ ቅዳሜ ድረስ በቀጠለው ደም አፍሳሽ ግጭት የ63 ሰዎች ሕይወት ማለፉን ይጠቁማሉ፡፡ ከጌዲዮ ብሔረሰብ አባላት 52 ሰዎች፣ ከሌሎች ክልሎች መጥተው በዲላ ከተማ ከሚኖሩ ውስጥ ደግሞ 11 የሚደርሱ ግለሰቦች ሕይወት ማለፉን ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በዚህ ግጭት መኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ተቋማት፣ የሕዝብና የጭነት ተሽከርካሪዎችና የቤት መኪኖች በእሳት ጋይተዋል፡፡ የክልሉ መንግሥት ግን ቁጥሩ የተጋነነ ነው ይላል፡፡

የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አህመድላዲን ጀማል በተቀሰቀሰው ግጭት የሰው ሕይወት ማለፉንና ንብረት መውደሙን ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡
ነገር ግን ምክትል ኮሚሽነሩ እንደገለጹት፣ የሟቾችን ቁጥርና የደረሰውን የንብረት ውድመት የሚያጣራ ግብረ ኃይል ወደ ሥፍራው በመላኩና ሪፖርቱን ባለማጠናቀቁ፣ የሟቾችንም ሆነ የደረሰውን የንብረት ውድመት በቁጥር ማስደገፍ አይቻልም፡፡

መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከረፋዱ 4፡30 ሰዓት ላይ የጌዲዮ ተወላጅ የሆኑ ሰዎች በተለይ ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የመጡ የዲላ ከተማ ነዋሪዎች ላይ መጠነ ሰፊ ጥፋት መፈጸማቸውን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ምንጮች እንደገለጹት የጥቃቱ ማጠንጠኛ ከሌሎች አካባቢዎች የመጡ ሰዎች በዞኑ ውስጥ ሀብትና ንብረት ማፍራታቸው፣ በአንፃሩ ደግሞ የጌዲዮ ብሔረሰብ አባላት በድህነት ውስጥ ነን በሚል ምክንያት ለዓመታት በአካባቢው የሚኖሩ የሌሎች ክልል ተወላጆች ከአገር እንደሚወጡ መጠየቃቸው ነው፡፡
በዚህ ሳቢያ የከተማው ነዋሪዎች ቤቶቻቸውና ንብረቶቻቸው ከመውደማቸውም በተጨማሪ ግድያ ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ከከተማ እንዲወጡ የተደረጉም አሉ፡፡

ለዚህ ግጭት መነሻ የሆነው በዲላ ከተማ ‘ታይዋን’ ተብሎ በሚጠራው የገበያ ሥፍራ አካባቢ በጌዲዮ የገበሬዎች ኅብረት ሥራ ዩኒየንና በከተማው ነጋዴዎች መካከል የመሬት ይገባኛል ጥያቄ በፍርድ ቤት እልባት ማግኘቱ ነው፡፡

በሁለቱ አካላት መካከል ሲካሄድ የቆየው የፍርድ ቤት ክርክር ለከተማው ነጋዴዎች መወሰኑ ቁጣ ቀስቅሷል፡፡ በውሳኔው የተነሳም የአካባቢው ነዋሪዎች ቁጣ ወደ ደም አፍሳሽ ግጭት ተቀይሯል፡፡
የእዚህ ግጭት ሰለባ የሆኑ የዲላ ከተማ ነጋዴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በከተማ ከሚኖሩ ሌሎች ብሔሮች አባላት መካከል 11 የሚሆኑ ሞተዋል፡፡ እንዲሁም ከጌዲዮ ወገኖች 52 ያህል መገደላቸውን አስረድተዋል፡፡
የደቡብ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሂክማ ኬይረዲን ለሪፖርተር እንገደለጹት ግን አጠቃላይ የሟቾች ቁጥር 23 ሲሆን፣ ግጭቱም ብሔር ተኮር አይደለም፡፡

በዚህ ግጭት የዲላ ከተማን ሲሶ ያህሉን እሳት በልቶታል፡፡ ‹‹ፌዴራል ፖሊስ ቅዳሜ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ባይደርስ ሁላችንም እናልቅ ነበር፤›› በማለት የግጭቱን አስከፊነት ነጋዴው ገልጸዋል፡፡
የጌዲዮ ዞን መቀመጫ የሆነችው ዲላ ከአዲስ አበባ ከተማ 369 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡ ዞኑ በአጠቃላይ 1,347.04 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት አለው፡፡
ዞኑ የኢትዮጵያ ስፔሻሊቲ ቡና (ይርጋ ጨፌ) ይመረትበታል፡፡ በዞኑ ዲላ፣ ጨለልቅቱ፣ ይርጋ ጨፌና ወናጎ አጎራባች አካባቢዎች ግጭቱ ተንሰራፍቶ ነበር፡፡

የፖሊስ ምክትል ኮሚሽነሩ እንዳሉት፣ በአሁኑ ወቅት የክልሉ ሰላም ወደነበረበት ተመልሷል፡፡ ችግሩንም የፈጠሩ አካላትም በቁጥጥር ሥር እየዋሉ ነው፡፡ እስከ ማክሰኞ ጥቅምት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ሰላም ቢሰፍንም በከተማው የንግድ እንቅስቃሴ አለመጀመሩ ታውቋል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

በኢትዮጵያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታወጀ፤ ህዝባዊ ተቃውሞውም አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል

(አዲስ ሚዲያ)በኢትዮጵያ ለተከታታይ አስር ወራት የፈጀው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከትናንት ቅዳሜ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለ6 ወር ተግባራዊ የሆነ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማውጣቱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ዝርዝር ጉዳይን በተመለከተ ወደፊት ይገለፃል ከማለት በስተቀር አጠቃላይ ይዘቱን በተመለከተ ያሉት ነገር የለም፡፡

በሌላ በኩል በጠቅላይ ሚኒስተሩ በሚመራ ኮማንድ ፖስት ስር የህግ አስከባሪዎችም መከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የፌደራል የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል፣ የአካባ ሚሊሻዎች እና ንብረት ጠባቂ የፀጥታ ኃይሎች የሚያካትት መሆኑን ደግሞ ጠቅላይ አቃቤ ህጉ አቶ ጌታቸው አምባዬ አብራርተዋል፡፡ አስቸኳይ አዋጁ በአጠቃላይ ሀገሪቱ ላይ ተግባራዊ መደረጉንም ጠቅላይ አቃቤ ህጉ አስታውቀዋል፡፡

halemariam-desalegn

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አተገባበር መሰረት የተጠረጠረ ማንኛቸውም ሰው ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሊታሰር እንደሚችል፣ ቤቶችና አካባቢዎችም ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ብርበራ ሊካሄድባቸው እንደሚችልም እና ማንኛውም ዓይነት መገናኛ ብዙኃን ሊዘጋ እንደሚችልም ጠቅላይ አቃቤ ህጉ ይፋ አድርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ተቃውሞን ሊገልፁ የሚችሉ ምልክቶችን መጠቀምንም አዋጁ እንደሚከለክል፣ አዋጁን ተላልፎ የተገኘም ቅጣት እንደሚጠብቀው አስታውቀዋል፡፡

በተለይ ከህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እንዲሁም ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል የተነሱ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞች መንግሥት በወታደራዊ ኃይል ግድና፣ እስርና አፈና ለማስቆም መሞከሩን ተከትሎ ያለማቋረጥ ተቃውሞዎቹ ተጠናክረው መቀጠላቸው ስርዓቱን ስጋት ላይ ጥሎታል፡፡ በተለይ እንደ ማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ መረጃ ከሆነ ከሀገሪቱን አጠቃላይ ህዝብና የቆዳ ስፋት 62% የሚሸፍነው የሀገሪቱ ህዝብ በአደባባይ የስርዓት ለውጥ እንደሚፈልግና በስልጣን ላይ ባለው ስርዓት መገዛት ለከፍተኛ ግድያ፣ እስር፣ በደልና ጭቆና እንደዳረገው በአደባባይ እየገለፀ ይገኛል፡፡ ለህዝቡ ጥያቄ የመንግሥት ምላሽ ግድያ፣ እስርና ማሰቃየት መሆኑ ደግሞ ህዝቡን የበለጠ እንዲቆጣና የተቃውሞ አድማሱን እንዲያሰፋ እንዳስገደደው ይነገራል፡፡

በተለይ ባለፈው እሁድ መስከረም 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሞ ማኀበረሰብ ዘንድ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠውና በርካታ ኢትዮጵያውያን የሚታደሙበት የኢሬቻ በዓል በደብረዘይት/ቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ እየተከበረ ባለበት ወቅት ህዝቡ በሰላማዊ መንገድ አገዛዙ ላይ ተቃውሞውን ማሰማቱን ተከትሎ በተወሰደው ርምጃ አጠቃላይ ከ678 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው በመላው ኢትዮጵያ የበለጠ ቅሬታን ፈጥሯል፡፡ በዚህም በኦሮሚያ ክልል የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደ ህዝባዊ አብዮት መሸጋገሩንም የኦሮሞ መብት አራማጆች ይፋ ማድረጋቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ የአገዛዙ ሰዎች፣ ደጋፊዎችና ተባባሪዎች ናቸው የተባሉ ንበረቶች እና አገዛዙ የሚጠቀምባቸው የተለያዩ መንግሥታዊ ተቋማት ላይ ርምጃ መውሰዳቸው ታውቋል፡፡ የኦሮሞ ህዝባዊ ተቃውሞ አሁንም ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ የመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጃም ተጠናክሮ በመቀጠል የበርካታ ሰላማዊ ዜጎች ህይወት ጠፍቷል፡፡

በተመሳሳይ በአማራ ክልል ባለው ህዝባዊ ተጋድሎ የቀጠለ ሲሆን፤ የመንግሥት ወታደራዊ እርምጃ በርካታ ሰላማዊ ዜጎችን ህይወት ቀጥፏል፡፡ በኦሮሚያ እና አማራ ክልል በተጨማሪ በደቡብ ክልል ኮንሶ ወረዳም ተመሳሳይ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ እና የመንግሥት የኃይል ርምጃ የቀጠለ ሲሆን፤ በዚህም በርካታ ሰላማዊ ዜጎች ተገድለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛው ደቡብ ክልል ጌዲዮ ዞን ባሉ ወረዳዎችና ከተሞች ከፍተኛ ተቃውሞና ግጭቶች ተቀስቅሰዋል፡፡ በዚህም የሰው ህይወት መጥፋትን ጨምሮ የበርካታ ሰላማዊ ዜጎች የንግድ ሱቆችና መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ የተለያዩ የኃይማኖት ተቋማትም ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ አጠቃላይ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል እንዲሁም በደቡብ ክልል ኮንሶ ወረዳ ባሉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቁጥር ከ 1,420 በላይ መድረሳቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግሥት በበኩሉ ህዝባዊ ተቃውሞቹ በውጭ ኃይል የተቀነባበሩ ናቸው በማለት ለመሸፋፈን ቢሞክርም ከህዝቡ፣ ከመብት አራማጆችም ሆነ ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ተቀባይነት አላገኘም፡፡

የኦሮሞ ቻርተር ጉዳይ ወዴት ያደርሰናል?

semahegn-gashu

ሰማሀኝ ጋሹ (ዶ/ር)

የኦሮሞ ቻርተርና ወታደራዊ ክንፍ መቋቋምን በተመለከተ የሚመክር በአትላንታ የሚካሄድ ስብሰባ ዜና እና ሰነድ ይፋ ከተደረገ በሗላ በተለያዩ ወገኖች ዘንድ ጥርጣሬና ጥያቄ አስነስቷል። ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ አቶ ጃዋርንና ፕ/ር ህዝቄልን የኦሮሞ ቻርተርን በተመለከተ ውይይትም አካሂዷል። በውይይቱ ወቅት የመገንጠል ጥያቄዉን በተመለከተ ጥሩ ማብራርያ የተሰጠ ቢሆንም አሁንም በርካታ መልስ የሚሹ ጉዳዮች አሉ። በተለይ አትላንታ ይካሄዳል ተብሎ የታሰበዉን ስብሰባ በተመለከተ የወጣዉ መግለጫ በብዙዎች ዘንድ ያልተጠበቀ ነገር ነዉ። በጎንደር በተካሄዳዉ የተቃዉሞ ሰልፍ ወቅት ህዝቡ ‘ የኦሮሞ ደም የኛ ደም ነዉ’ ፥ ‘ በቀለ ገርባ መሪያችን ነዉ’ በማለት ለኦሮሞ ህዝብ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ ያለዉን አጋርነት ከገለፀ በሗላ በህዝቦች መካከል የነበረዉንና በህወሓት ለዘመናት የሚዘወረዉን የከፈፍልህ ግዛ (divide and conquer) ፖለቲካ በማዳከም ከፍተኛ የትግል አንድነት ያመጣ መሆኑ ይታወቃል። ህዝቡ ይህንን የተፈጠረዉን አንድነት የሚያጠናክር የፖለቲካ ሀይሎች የጋራ መድርክ ሲጠብቅ የተናጥል ስብሰባ መጠራቱ በብዙዎች ዘንድ ጥርጣሬ መጫሩ የሚጠበቅ ነዉ። ከዚህ አኳያ የተፈጠረዉን የህዝብ አንድነት ሊያጠናክር የሚችል ስራ ላይ ማተኮር ሲገባ የተናጠል የስብሰባ ጥሪ መጠራቱ በጋራ ትግሉ ላይ የራሱን ተፅእኖ ማሳደሩ የማይቀር ነዉ።

ከዚህ የከፋዉ ደግሞ የቀረበዉ ሰነድ ስለ ህዝቡ የጋራ ትግልና የደረሰበትን ደረጃ ጨርሶ አያነሳም። ሰነዱ ወደፊት የኦሮሞ ህዝብ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርአት ዉስጥ የሚኖረዉን ሚና በተመለከተም ምንም አይነት ፍንጭ ያልሰጠ ሲሆን የኦሮሞን ህዝብ በደሴትነት ተነጥሎ የተቀመጠ ያስመስለዋል። እንደዉም ሰነዱ የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት አድርጎ ያቀርበዋል። የቅኝ ግዛት ትንታኔዉን (colonial thesis) በርካታ የኦሮሞ ምሁራንና ፖለቲከኞች እንደማይደግፉት እየታወቀ ሁሉንም የኦሮሞ መሪዎች ላማሰባሰብ ያለመ ሰነድ ለምን ያአንድ ወገን አቋም ብቻ ለማንፀባርቅ እንደፈለገ ግልፅ አይደለም። የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት ጥያቅ እንዳልሆነ የሚያምኑትን የኦሮሞ ፖለትከኞችና ምሁራን የሚያገል ያሰመስለዋል። የኦሮሞን ህዝብ ቅኝ እንደተገዛ አድርጎ ማቅረቡ የኦሮሞ ህዝብ ከሌላዉ ህዝብ ጋር ያለዉን የባህልና የታሪክ ትስስርና የኦሮሞ ህዝብ ለኢትዮጵያ አንድነትና ህልዉና ያበረከተዉን አስተዋፅኦ የሚያሳንስ ነዉ። ከዚህም በተጨማሪ ይህን አይነቱ ትንታኔ አንዱን ማህበረሰብ ጨቋኝ ሌላዉን ተጨቋኝ በማድረግ የሚቀርበዉን የታሪክ ትንታኔ ህያዉ ሆኖ እንዲቆይ የሚፈልግ ያስመስለዋል። ይህም እስካሁን የሄድንበትን የጋራ አለመተማመን (mutual suspicion) በማስቀጠል ልንፈጥረዉ ለምናስበዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት እንቅፋት ይሆናል።

በተለይ በኢትዮጵያን አንድነትና በግለሰብ መብት ላይ የተመሰረተ የፖለቲካ ስርአት እንዲቋቋም የሚፈልጉ ዜጎችን የቀድሞዉ ስርአት ናፋቅዎችና ምኒልካዉያን እየተባለ መስደብ የተለመደ ነዉ። ያሁኑን ተዉልድ የፖለቲካ አስተሳሰብ መተቸት ካስፈለገ በራሱ በትዉልዱ አስተሳሰብ ላይ ተመስርቶ መተቸት ሲገባ ከቀደሙት ስርአቶች ጋር በማያያዝ አንገት ለማስደፋት የሚደረገዉ እንቅስቃሴ ያደባባይ ሚስጥር ነዉ። የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ከወራት በፊት ያደረገዉን የሬድዮ ዉይይት አስመልክቶ የቀድሞዉ ስርአት ናፋቂ የሚል ስድብና ዛቻ የኦሮሞ አክቲቪስቶች ነን ከሚሉ ወገኖች አስተናግዷል። ለዚህም ነዉ የአማራ ወጣቶች ሁሉም የብሄር ድርጅቶች አማራን በጠላትነት የሚፈርጁ በመሆኑ ተደራጅተን እራሳችንን እንከላከል እያሉ ያሉት። ምንም እንኳን ያለፈዉን ታሪካችንን በተመለከተ ብሄራዊ መግባባት ላይ መድረስ አስቸጋሪ ሊሆን ቢችልም እንዲህ አይነት የታሪክ ትንታኔዎችን ለፖለቲካ ፍጆታ ባለመጠቀም የተሻለ የፖለቲካ ድባብ ለመፍጠር ጥረት እንዳልተደረገ ግን ከቀረበዉ ሰነድ መረዳት ይቻላል።

ከዚህም በጠጨማሪ የቀረበዉ ሰነድ ባለፉት አስርተ አመታት የብሄረሰቦችን እኩልነት ለማምጣት የተሄደበትን መንገድ፥ ዉጤቱንና ችግሮቹን ሳያነሳ የኦሮሞ ህዝብ ከዛሬ አርባ አመት በፊት በነበረበት ሁኔታ እንዳለ አድርጎ ያቀርበዋል። ከሁሉም ብሄረሰቦች የተወጣጡ ወጣቶች በተማሪዎች እንቅስቅሴ ወቅት ያነሱት የመሬት ላራሹና የራስን እድል በራስ የመወሰን ጥያቄ በደቡብ ኢትዮጵያ የነበረዉን የጭሰኝነት ስርአት ያስወገደ ሲሆን ይህም ለኦሮሞ ህዝብ ታላቅ ለዉጥ አምጥቷል። ደርግም ሆነ ወያኔ ስታሊናዊ በሆነ መንገድ ችግሮቹን ለመፍታት የሄዱበት መንገድ ዉጤቱ አመርቂ ባይሆንም ሙከራዎች ግን ተደርገዋል። ይህ ሁሉ የፖለቲካ ለዉጦች በተካሄዱበት ሀገር አሁንም ቅኝ እንደተገዛን ነን የሚል እድምታ ያለዉ አቀራረብ በጣም ጨለምተኛና ካላፈዉ ስህተቶች ተምሮ የቀረዉን የእኩልነት ጥያቅ ለማሳካት በሚያስችል መልኩ አለመቀረፁ በኢትዮጵያ ያለዉን አስቸጋሪ የፖለቲካ ሁኔታ ለመፍታት ያለዉን ቁርጠኝነት ዉሱን ያስመስለዋል።

የኦሮሞ መሪዎች ስብሰባ ያስፈለገበትን ምክንያት አቶ ጃዋር ሲያስረዳ ወደፊት ለሚደረገዉ የሽግግር ወቅት እያንዳንዱ ማህበረሰብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ መምጣት ስላለበት የኦሮሞን ቻርተር ለማዘጋጀት በማስፈለጉ ነዉ ይላል። ለዚህም የደቡብ አፍሪካዉን ብሄራዊ ኮንግረስና የህንዱ ጃዋራላል ኔህሩ በትግል ወቅት እንዲህ አይነት ቻርተር አዘጋጀተዉ ነበር ሲል ያስረዳል አቶ ጃዋር። እያናንዳንዱ ማህብረስብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ ይምጣ ከተባለ ሁሉም ብሄረሰቦች አንዳንድ ቻርተር በማዘጋጀት ሲመጡ ቢያንስ ከ 80 ያላነሱ ቻርተሮች ተዝጋጅተዉ ሊቀርቡ ነዉ ማለት ነዉ( ያዉም እያንዳንዱ ማህበረሰብ በአንድ ድርጅት ይወከላል ብለን ካሰብን ነዉ።) እንዲህ ያለ ሁኔታን እንዲኖር መፈለግ አላማዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ወይስ የባቢሎንን ግንብ ለመገንባት ነዉ? ሁሉም ብሄር የራሱን መብት እንዲከበር በሚል በሚያደርገዉ ፍላጎት ሁሉንም የሚያረካ መፍትሄ ማግኘት የሚክብድ ከመሆኑም በተጨማሪ የፈለገዉን ያላገኘዉ ወገን ‘የራሴን እድል በራሴ’ እወስናለሁ ወደሚል ሌላ ዙር ግጭት ይገባል። በተለይ ወታደራዊ ክንፍ ያለዉ የብሄር ድርጅት የሚበረታታ ከሆነ በጉልበት የፈለገዉን ለማድረግ ማንገራገሩ የማይቀር ነዉ። ወያኔም በ1983 ዓም ባደረገዉ የሽግግር መንግስት ምስረታ ወቅት በብሄር የተደራጁትን ብቻ ተቀብሎ ህብረ ብሄር የሆኑትን ግን አልቀበልም ነበር ያለዉ። ለዚህም የተማመነዉ የነበረዉን ጉልበት ነዉ። ኦነግንም ከሽግግሩ መንግስት እንዲወጣ ያደረገዉ ይሄዉ የወያኔ እብሪተኝነት ነዉ። አሁንም በብሄር ተደራጅታችሁ የራሳችሁን ቻርተር አዘጋጅታችሁ ኑ ማለት ተመሳሳይ አካሄድ ያለዉ ነዉ። በርካታ ማህበረሰቦችም በተለያየ ምክንያት ተደራጅተዉ ቻርተር አዘጋጅተዉ ላይቀርቡ ይችላሉ። በዚህ ጊዜ የነዚህ ማህበረሰቦች እድል ቻርተር አዘጋጅተዉ በመጡት ሊወሰን ነዉ ማለት ነዉ? ይህስ አካሄድ ወያኔ በ1983 ካደረገዉ በምን ይለያል? ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የፖለቲካ ሃይሎች እኛ ባልነዉ ካለተስማማችሁ ዞር በሉ ቢሉ ዋስትናዉ ምንድን ነዉ? አልሸሽም ዞር አሉ እንደሚባለዉ ተመልሶ ወደ ግጭት አያስገባንም ወይ?

አቶ ጃዋር ያቀረባቸዉ የደቡብ አፍሪካ፤ ህንድና ቱኒዝያ ምሳሌዎች አሁን ከተጠራዉ የኦሮሞ የነፃነት (freedom) ቻርተር ጉዳይ በጣም የተለዩ ናቸዉ። በነዚህ ሃገሮች የቀረቡት የነፃነት (freedom) ቻርተሮች ሆነ ድርድሮች ሃገራዊና የሁሉንም ማህበረሰብ ፍላጎት የሚያንፅባርቁ እንጂ የአንድ ብሄርን ብቻ የሚመለከቱ አልነበሩም። እንዲሁም በህንድ የተካሄደዉ የፀረ ቅኝ ግዛት ትግልና በደቡብ አፍሪካ የተካሄደዉ የፀረ አፓርታይድ ትግል አሁን ኢትዮጵያ ዉስጥ ካለዉ የፖለቲካ ሁኔታ ጋር ያላቸው ዝምድናና እና ልዩነት በግልፅ አልቀረበም ። የምናቀርባቸዉ ምሳሌዎች ተገቢ ትርጉማቸዉን የያዙ ቢሆኑ የምናቀርበዉን ሃሳብ ተአማኒነት ያጠናክረዋል። አቶ ጃዋር ስለ ቱኒዝያ የተናገረዉም እኛ እየሄድንበት ካለው ጋር የሚገናኝ አይደለም። ከሌሎች አብዮት ከተካሄደባቸዉ የአረብ ሃገራት በተለየ የተሻለ የፖለቲካ ሽግግር በቱንዝያ የተፈጠረዉ እንደ ሊቢያና ሶርያ በሃይማኖትና በጎሳ ለመከፋፈል ባለመፍቀዳቸዉ ነዉ። ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የብሄር ድርጅቶችን የምናበረታታ ከሆነ ግን ለጊዜዉ በአንድ ጠላት ላይ ሲያተኩሩ ልዩነት የሌላቸዉ የሚመስሉ የፖለቲካ ህይሎች ያ ጠላት ከስፈራዉ ሲነሳ እርስ በርሳቸዉ መበላላታቸዉ የማይቀር ነዉ። ሊብያ ዉስጥ በተካሄደዉ አብዮት ወቅት ሁሉም ጎሳዎች ጋዳፊን ለመጣል ሰምና ወርቅ ሆነዉ ከሰሩ በሗላ አሁን ሁሉም በየፊናዉ ወታደራዊ ቀጠና አቋቁሞ እየተጋጨ ሲሆን ማዕከላዊ መንግስት በስምምነት ለመመስረት አልቻሉም።

በእዉነት የኢትዮጵያን የፖለቲካ ችግሮች ለመፍታት ቅንነቱና ቁርጠኝነቱ ካለ እንደ ኑክልየር ሳይንስ ዉስብስብ ስላልሆነ 80 ቻርተር ማዘጋጀት አያስፈልገዉም። የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሰረታዊ ችግሮች እንዴት ብሄራዊ አንድነትንና የብሄር መብትን፥ የግለሰብና የቡድን መብትን አጣጥመን እንቀጥል፥ እንዴት ብሄራዊ መግባባትን እንፍጠር፥ ዴሞክራሴያዊ ባህልና ተቋማት እንዴት እንገንባና ማህበራዊና ኤኮኖምያዊ ፍትህ እንዴት እናረጋግጥ የሚሉት ናቸዉ። እነዚህን የፖለቲካ ጥያቄዎች ለመመለስ ዋናዉ መነሻ የተናጥል አካሄድን በተቻለ መጠን በማስቀረት ሁሉም የፖለቲካ ሃይሎች በጋራ የሚመክሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነዉ። ነገር ግን አሁንም የሽግግር ሂደቱን በበላይነት ለመቆጣጠር የሚካሄደዉ ፉክክር ስር የሰደደዉን የፖለቲካ ሃይሎች አለመተማመን እንዲቀጥል የሚያደርገዉ ከመሆኑም በተጨማሪ የግጭትንና የእኔ አውቅልሃለሁን የቆየ የፖለቲካ ባህል ለመለወጥ የሚኖረዉን እድል ያደበዝዘዋል።