ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው
በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቃገኘው የክስ መዝገብ የተከሰሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በመያዝ የሕግ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው፡፡ ድብደባው የተፈፀመባቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ..ም. እነ አብርሃ ደስታ በነበራቸው የፍርደ ቤት ቀጠሮ ተገኝተው የሚጠበቅባቸውን የሕግ አገልግሎት ሰጥተው ከፍርደ ቤት ከወጡ በኋላ ብሔራዊ አረቄ ፋብሪካ አካባቢ ወደ አዋሳ ለሌላ የህግ አገልግሎት ለመስጠት እያመሩ በነበረበት ወቅት በማያውቁት ግለሰብ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክታል፡፡
ደብዳቢው ግለሰቡ ድብደባ ከፈፀመ በኋላ እሮጦ ለማምለጥ ሲሞክር በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ትብብር የተያዘ ሲሆን፤ በወቅቱም ደብዳቢው የአእምሮ ችግር እንዳለበት ለመምሰል ከሞከረ በኋላ የብአዴን-ኢህአዴግ አባል እንደሆነና 400 ብርም እንደተከፈለው መናገሩን እንዲሁም አዲስ አበባ ለቡ አካባቢ 105 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቶት ቤት እየሰራ እንደሆነ መግለፁን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ጠበቃ ተማም ነገ አዋሳ ላይ ሌላ የነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የፍርድ ቤት ጉዳይ ስላለ ዛሬ የግድ ሄደው ማደር ስለነበረባቸው ደብዳቢውን እንዲለቀቅ አድርገው ወደ አዋሳ ማምራታቸው ታውቋል፡፡
ጠበቃ ተማም ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በተጨማሪ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎችን፣ የተለያዩ ጋዜጠኞችን፣በሀገር ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን እና ሌሎች በርካታ የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ለማኀበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ከጥብቅና አገልግሎት በተጨማሪ በተለያዩ ጋዜጦች የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ይፅፉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ በዚህም ከመንግሥትና ከስርዓቱ ደጋፊዎች ከፍተኛ ጫና እየተደረገባቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ቅጣት ተላለፈባቸው
᎐ተጨማሪ ቅጣትም ይጠብቃቸዋል፡፡
• “እኛ የደፈርነው ችሎት አሻንጉሊት ችሎት ነው” አብርሃ ደስታ
• “ችሎቱ ላይ ያጨበጨብነው በማፌዝ ሳይሆን በምሬት ነው” የሺዋስ አሰፋ
• “ፍትህ ተጠምተናል፣ ፍትህ ለኢትዮጵያ ህዝብ!” ዳንኤል ሺበሽ
በዘለዓለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ከስምንት ወራት በላይ በእስር ላይ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነት እንዲሁም የዓረና ትግራይ ፓርቲዎች አመራሮች ‹ችሎት በመድፈር ወንጀል› ጥፋተኛ በመባላቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም በልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት በሦስቱ አመራሮች ላይ እያንዳንዳቸው በሰባት ወራት እስራት እንዲቀጡ ተወስኖባቸዋል፡፡
የካቲት 26 ቀን 2007 ዓ.ም ተከሳሾች በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸውና ንብረትም እንደተወሰደባቸው በመግለጽ አቅርበውት ለነበረው አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ሙሉ ለሙሉ በመቀበል አቤቱታቸውን ውድቅ ማድረጉን ተከትሎ 5ኛ ተከሳሽ አቶ የሺዋስ አሰፋ በማጨብጨቡና 3ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታና 4ኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል ሺበሽ ሳይፈቀድላቸው ‹‹ጥሩ ፍርድ፣ ጥሩ ብይን›› በማለት አቶ የሺዋስን በመደገፍ ችሎት ደፍረዋል ተብለው ጥፋተኛ መሰኘታቸው ይታወሳል፡፡ በዚህ መሰረት ፍርድ ቤቱ ለዛሬ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ተሰይሞ በአብርሃ ደስታ፣ በየሺዋስ አሰፋ እና ዳንኤል ሺበሽ ላይ የ7 ወራት እስራት በይኖባቸዋል፡፡ ሦስቱም ተከሳሾች ፍርድ ቤቱ የሰጠውን ውሳኔ በመቃወም ድጋሜ ችሎት ውስጥ አጨብጭበዋል፡፡ በዚህም ድጋሜ ጥፋተኛ ተብለዋል፤ ከሁለት ቀናት በኋላም የቅጣት ውሳኔ ይወሰንባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሦስቱ ተከሳሾች ‹‹እድል ስጡን እንናገር፣ አቤቱታም አለን ተቀበሉን›› ቢሉም ፍርድ ቤቱ ሊሰማቸው አልፈለገም፡፡
በተለይ ዳንኤል ሺበሺ ‹‹ሌላ አቤቱታ አለኝ፣ ፍርድ ቤቱ ያዳምጠኝ›› ብሏል፡፡ ፍርድ ቤቱ አሁንም ችሎቱ ላይ እያፌዛችሁ ነው በሚል ጥፋተኛ ሲላቸው ሦስቱም አመራሮች ፍርድ ቤቱን ማስፈቀድ ሳያስፈልጋቸው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ‹‹እኛ የደፈርነው ችሎት አሻንጉሊት ችሎት ነው፡፡ ‹Already› የተደፈረ ችሎት ነው›› ሲል አብርሃ ደስታ ተናግሯል፡፡ በዚህ ጊዜ ዳኞቹ ጣልቃ በመግባት፣ ‹‹የምትናገረው ነገር እንደገና ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ የሚወስድህ ጉዳይ ነው፤ ምርመራ ይደረግበታል›› ሲሉ አብርሃ በበኩሉ ‹‹አሁንስ ቢሆን የምናገረውን ፖሊስ እየሰማ አይደለምን?›› ሲል መልሷል፡፡ አቶ የሺዋስ አሰፋ በበኩሉ ‹‹ከስምንት ወር በላይ ታፍነናል፡፡ በህግ አይደለም የተያዝነው፡፡ ደግሞ ማጨብጨባችን በችሎቱ ከማፌዝ ሳይሆን ከምሬት በመነጨ ነው፡፡ ህገ-መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል፡፡ እኔ ለምሳሌ የሰማያዊ ፓርቲ አባል በመሆኔ ነው የታሰርኩት፡፡›› ብሏል፡፡
አቶ ዳንኤል ሺበሽ ድግሞ ‹‹አሁንም ችሎት ደፍራችኋል ካላችሁ ቅጣቱን ጨምሩብንና ሸኙን፡፡ በእርግጥ ዳኞች ላይ ያለውን ጫና እንረዳለን፡፡›› ሲል ችሎት ውስጥ ተናግሯል፡፡
በዚህ ሁኔታ በተከሳሾችና በችሎቱ መካከል ያለው አለመግባባት ሲጨምር ዳኞቹ መጋቢት 3/2007 ዓ.ም ለሁለተኛ ጊዜ የቅጣት ውሳኔ እንደሚሰጥ በመጥቀስ ሦስቱ ተከሳሾች ከችሎት በፖሊስ እንዲወጡ ተደርገዋል፡፡ ከችሎት እየወጡ እያሉም አቶ ዳንኤል ሺበሽ ‹‹ፍትህ ተጠምተናል፤ ፍትህ ለኢትዮጵያ ህዝብ!›› እያለ ችሎቱን ለቅቆ ወጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ሦስቱ ተከሳሾች ከችሎት መውጣታቸውን ተከትሎ፣ከዚህ ቀደም በማረሚያ ቤቱ ላይ በቀረበው አቤቱታ ዳኞች በሰጡት አስተያየት ላይ አቤቱታ አቅርቦ እንደነበር በማስታወስ አቤቱታው እንዲመዘገብለት የጠየቀው አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ ‹‹በበኩሌ ያሉኝን መረጃዎች እያቀረብኩ ስነ-ስርዓቱን አክብሬ ክርክሩን አቀጥላለሁ›› ሲል ተናግሯል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ- ኢትዮጵያ
የማለዳ ወግ…ለተሃድሶ ጀማሪዎች ለጅዳ ቆንሰል ተማጽኖየ !
* ፖለቲካውን እንደርስበታለን መብት በማስከበሩ ላይ በርቱ
ሰሞነኛ ወጋችን ፍተሻ ፣ አሰሳ ፣ ማጣራት ሆነና ልብን በሃዘን የሚሰብሩት ጩኸት እንዳይረሳ ሰጋሁ ። ለነገሩ የሳውዲ መገናኛ ብዙሃን በሚለቋቸው መረጃዎች ልክ መረጃ ተለዋውጠናል ባይባልም ፣ ያለፈውን አመትና የቆየውን ሁከት የሚያሳይ የቆየ ተንቀሳቃሽ ምስል እየለጠፉ የቆየነው አዲስ ነው ሳይሉና ሳያሳውቁን መረጃውን የሚለቁ የራሳቸን ሰዎች ተበራክተዋል። በዚህም ፍተሻ አለ የለም ወደሚለው አተካራ እየተዶልን ይመስላል። ተወደደም ተጠላ የሰው ሃገር የሰው ነው ፣ ሳውዲዎች በሃገራቸው ሰማይ ስር እንኳንስ በአደባባይ በተናገሩት ጊዜ ባሻቸው ጊዜ ህገ ወጥ ያሉትን ይዘው የማባረር መብት አላቸው ። አለመቀደም ነው እንጅ ሲላቸው ም የጠራረጉትን ጠራርገው ሲያበቁ ሁሉ ትተው የምህረት አዋጅ ሲሉ እናውቃለን ። ይህ ሲወርድ ሲዋረድ የምናውቀው አሰራራቸው ነው ። የዘንድሮውን ለየት የሚያፈርገው ” የምህረት አዋጅ የሚባል ነገር አይታሰብም “ማለቱ አይደለም ። ይልቁንም ስራቸውን በጣም በተረጋጋ ሁኔታ የመብት ጥሰት እንዳይኖርና ማህበራዊ ገጾች ጥሰቱን እየተቀባበሉ እንዳያወግዟቸው በጥንቃቄ እየተሰራ መሆኑን ልብ ብለን የግንባር ስጋ ከመሆን ካመለጥን መልካም ነው !
ከሰሞነኛው መረጃ ቅበላ ጎን ለጎን በተለያዪ አላባቢዎች ያሉ ወዳጆቸ ከሚያደርሱኝ መረጃዎች መካከል ሰሞነኛው የአፈሳ ፣ እስራት ፣ ማጣራቱ መረጃ ከአዕምሮየ አላዳፍን ያላቸውን የሚያሙ ግን ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባ ጉዳዮችን ማንሳት ወደድኩ ! ለዚህ የማለዳ ወግ መነሻ የሆነኝ ባሳለፍነው ሳምንት የዲያስፖራ ምክር ቤት የሚሉትን ለማቋቋም ከተሰበሰቡት የድርጅት ሰዎች አጠራርና የህዝብ ውክልና ጉዳይ ነው። ከአንድ አፍቃሬ ህወሃት ወዳጀ ጋር በዚህ ዙሪያ ስናወጋ ” ያን ሰሞን ተሃድሶ አድራጊውን ቆንስል እንዳላመሰገንክ ዛሬ በዲያስፖራው ጉዳይ ነካከህው! ” ነበር … ቀድሞውንም አሁንም በማይረባውና በማንግባባበትን የፖለቲካ ጉዳይ እንደርስበታለን መብት በማስከበሩ ላይ ግን ኢህአዴግ ምንቴስ ሳንል እንትጋ ፣ በርቱ እንበርታ ስል ባደረግነው ማሳረጊያ ተገወባባን … እናም ሰሞነኛ የመረጃ ግብአቱ ቦታውን ሳያጣብበው ለተገፋት የወገኖቻችን መብት እንደጋገፍ እንበርታ ስል የደረሰኝን መረጃ ተከትሎ በውስጤ ከሚጉላሉት ብዙ አሳዛኝ ታሪኮችን በጨረፍታ ዳስሸ መብት በማስከበሩ ረገድ መስማት የጀመሩት የጅዳ ቆንስል ተወካዮቻችንን ለመብታችን መከበር ጽኑልን ስለ መማጸን ፈለግኩ …
የሰሚራ ጉዳት …
ባሳለፍነው አንድ ቀር ገደማ በጥይት ተመታ በቢሻ ሆስፒታል በጥይት ተመታ ቆስላ በሆስፒታል ስለምትገኘው እህት ጉዳይ በማህበራዊ መረጃ መረቡ በኩል መረጃው ሲሰራጭ እኔም እጅ ገባ ። ብዙም ሳይቆይ በየድህረ ገጾች ተለቀቀ ። እኔም መረጃውን ለማጣራት ያፈረግኩት ሙከራ በተሳካ ማግስት በጅዳ የጅዳ ቆንስል መስሪያ ቤት ወደ ቦታው በማቅናት ተጎጅዋን ማግኘታቸውን፣ ማነጋገራቸውንና ጉዳዩን እየተከታተሉት የመሆኑን የምስራች አበሰሩን ፣ ደስም አለን! ምስጋናም አቀረብን !
ይህ ከሆነ ከሳምንት በኋላ የሰሚራን ጉዳይ ለመከታተል ስሞክር በመረጃ አሰባሰቡ ዙሪያ ያልጠበቅኩት ችግር መከሰቱን ሰማሁ ፣ ረፋዱ ላይ ወደ ጅዳ ቆብስል ጎራ በማለት ጉዳዩን ከያዙት ዲፕሎማት የደረሰኝን መረጃ መሰረት በማድረግ ለማጣራት ብሞክርም ሃላፊው ለስራ ስለወጡ ማግኘት አልቻልኩም ። ያም ሆኖ በቦታው ላገኘኋቸው መልዕክቴን አስተላልፊ ተመለስኩ ! ይህ በእንዲህ እንዳለ በጉዳዩ ዙሪያ ያናከርኩት አንድ ወዳጀ በደረሰኝ መረጃ ዙሪያ አንድ ወንድም ዘርዘር ያለ መረጃ ያለው መልዕክት ከነ ተንቀሳቃሽ ፊልም ጭምር የያዘ መረጃ ማስተላለፉን ጠቆመኝ ። መረጃውን ከያዘው ወንድም መረጃ ትመለከቱት ዘንድ ከዚህ ገሰር አያይዠዋለሁ !
ሩቅያ …
ከወራት በፊት እዚህ ጅዳ ውስጥ በአንድ ት/ቤት የቅርብ ርቀት በተከሰተ የመኪና አደጋ የአሰሪዎቿን ልጆች ለማዳን ስትል ለከባድ አደጋ የተጋለጠች ሩቅያ የተባከች እህት አሳዛኝ ታሪክ አውቃለሁ። የሩቅያ ታሪክ በአረብ መገናኛ ብዙሃን ሳይቀር ቀርቧል። ከአደጋው በኋላ ራሷን የማታውቀው ሩቅያ በአንድ ሆስፒታል ለወራት ስትታከም ቆይታ ” ከህመሟ አገግማለች !” ተብሎ ከሆስፒታል ወጥታለች ። ያለ ወገን ደገሰፊ አምስት እህት ወንድሞችዋን የምታስተምር ትጉህ ክጅ አግር ናት ሰሚራ። ለህክምና ብትወጣም እርዳታ በማድረግ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ነዋሪዎች ግን አልረሷትም ። አደጋ ያደረሰባት ደግሞ ከእስር ወጥቷል ። እንዴት ወጣ አይታወቅም ። በውል ቋሚ የሆነ የሚደግፍ የሚረዳት ግን የለም ። ጉዳዩን በፊት ገጼ ካቀረብኩት በኋላ ለጅዳ ቆንስል አሳውቄ ነበር ። በወቅቱ ሄደው ጠይቀዋታል።እየተመላለሱም ጉዳዩን የተከታተሉ መሆኑን የገለጹልኝ የጅዳ ቆንስል ባለደረባ የሩቅያን ጉዳይ እንዳልረሱት ከቀናት በፊት አጫውተውኛል ። ይሁን … ብዙዎች ግን የሩቅያ ጉዳይ ተድበስብሶ እንዳይቀር እንማጸናለን !
መሐመድ …
መሃመድ ይባላል ፣ በ3 አመት የብላቴና እድሜው ድክ ድክ እያለ ለቀላል ቀዶ ህክምና ወደ ሃኪም ቤት ገባ ፣ ከቀዶ ጥገናው ክፍል ከገባ ከሰአታት በኋላ ከቀዶ ህክምናው ቢወጣም አልነቃ አለ። ሰአታት ተቆጠሩ ፣ ቀኖች ሲከተሉ ጉዳይ አስደንጋጭ እየሆነ መጣ ! ወላጅና የቤተሰብ አባላት የሚይዙ የሚጨብጡት ጠፋባቸው። ህክምናውን ያከናወኑት የሚሰጡት የተስፋ መልስ ጭብጥ እውንት ጠፋበት … ቀናት በቀናት ተተክተው ሳምታት ወርን ሲወልዱ የብላቴናው አለመንቃት በሆስፒታሉ ሃኪሞች ስህተት እንደሆነ ይፋ ተነገረ ! ይህ ሲሆን ታዲያ ከሆስፒታሉ የተሰጠው ምላሽ አስደንጋጭ ነበር ። የሶስት አምት ልጃቸው መሃመድ በህክምና ስህተት ማደንዘዣ በዝቶበት እንዳልነቃነና ይህን ስህተት የፈጸመው ዶር ከስራው መባረሩ ተገልጾላቸው መሃመድ እስኪነቃ አስፈላጊ ህክምናና ክፍል ተሰጥቶት ህክምናውን በነጻ እንደሚቀጥል ለወላጆች መርዶ ተነገራቸው ! ይህንን በደል ለማሰማት ወላጆቹ ከጅዳ ቆንሰል ከፍ እስካሉ የመንግስት መ/ቤቶች ቢደርሱም ሰሚ አላገኙም። እንዲያ ሆኖ ብላቴናው ከሰመመንና ከተኛበት አልጋ ሳይነቃ 11 ኛ አመቱን ዘንድሮ ይዟል …
ጉዳዩ አሳዛኝ ነው ከማለት በላይ ነው … ይህ በደል ወደ ሳውዲ ከፍተኛ የመንግስት አካላት ስለመታወቁ ግን አሁንም እጠራጠራለሁ ፣ ይህንኑ ለማጣራት አምድ ወዳጀ ከቤተሰብ አባላቱ ጋር ሊያገናኘኝ ቃል ገብቶልኛል። ያ ሙሉ አሳዛኙን መረጃ በዝርዝር እናወጋዋለን ! .. ባሳለፋቸው የብላቴናውና የወላጆቹ አስከፊ የጨለማ የመከራ አመታት ብላቴናውን የአልጋ ቁራኛ ህክምና በሚሰጠው ክፍል ሄጀ ለማየት ካንድም ሁለት ሶስቴ በሩ ላይ ደረስ ደርሸ ህመሙን መቋቋም ሳልችል ቀርቸ ሳላየው ተመልሻለሁ ! መውለድ ከባድ መሆኑንም የተረዳሁት ያኔ ነበር … የመሃመድ ጉዳይ በአንባሳደር ተክለአብ በአንባሳደር መርዋን እና በቆንስል ጀኔራል ዘነበ እየታወቀ እልባት የሚሰጥ የሚከታተለው ጠፍቶ ጉዳዩ ተድበስብሶ እዚህ ደርሷል ። ይህም ያማል ! ዘንድሮ ግን በቆንስሉ ትጉህ የተሃድሶው መሪዎች መፍትሔ ያገኙለት ዘንድ እንማጸናለን !
ስላለፈው ወቃሹ ታሪክ እንጅ እኛ አይደለንም፣ አንወቃቀስም …
የጀዛኑን ካልድ ለሶስት አመታት የቀጠለ አበሳ ሰሞኑን እልባት ሊያገኝ መሆኑን ሰምቻለሁ ፣ በካልድም ጉዳይም ሆነ በስም አይጠሬውን የአንድ እህት ሬሳ ታሪክ የምናወራው ዛሬ አይደለም ፣ አልነካካውም ! ስላለፈው መብት ጥሰትና የመብት ጥበቃ ጉድለት መረጃዎችን ከመሰብሰብ አልፈን ፣ ያለፈውን ጉዳይ እያነሳን መወቃቀሱ አይጠቅምም !
ዛሬ ሌላ ቀን ነው ፣ ላለፉት 11 ዓመታት እልባት ካልተሰጠው ከመሃመድ ጉዳይ ጀምሮ እስከ ጀዛኑን ካልድ ፣ በአሰሪዋ የፈላ ውሃ የተደፋባትና ላለፉት አንድ አመት ጉዳዩዋን በጅዳ ቆንስል ሆና የምትከታተለው የሄለን ጉዳይ ፣ በቅርብ በጥይት ከተመታችው የሰሚራ ጉዳይ እና መኪና ተገጭታ አካሏ እስከ ጎደለው ሩቅያ የዜጎችን መብት ለማስከበር የመንግስት ተወካዮች የተከፈተው በር እንዳይዘጋ ስንማጸን ፣ መረጃዎችን በማሰባሰቡ ረገድ ግልጽ መረጃ በመለዋዎጥ የመንግስት ተወካዮች መብታችም ያስከብሩልን ዘንድ ደጋግሜ እማጸናችኋለሁ !
በኢትዮጵያ መንግሥት የሳይበር ጥቃት መፈፀሙ ይፋ ተደረገ
የኢትዮጵያ መንግስት የመረጃ ጠለፋ መፈጸሙን እንደገፋበት ሂዩማን ራይትስ ዎች ተናገረ፡፡ የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት ዛሬ ይፋ አንዳደረገው ከሆነ መንግስት ቀስ በቀስ ጋዜጠኞችን ጸጥ ያደርጋል እንዲሁም የዲጂታል ጥቃት ይፈጽማል ሲል ገልጿል፡፡
ባለፈው አመት “ዘይ ኖው ኤቭሪቲንግ ዊ ዱ፤የኢንተርኔትና የቴሌኮም ስለላ በኢትዮጵያ” ሲል ቡድኑ ባወጣው ዘገባ የኢትዮጲያ መንግስት በዜጎቹ ላይ የቴሌኮምና የመረጃ መረብ እያንዳንዱን ሚስጥራቸውን ይበረብራል ማለቱ አይዘነጋም፡፡
ዘንድሮም በተመሳሳይ መንግስት ይህን ድርጊት መፈጸሙን አጠናክሮ እንደቀጠለ የሚናገረው ቡድኑ በውጪ የሚኖሩ ነጻ ጋዜጠኞች ላይ ሳይቀር የሳይበር ጥቃት ይፈጽማል በማለት አትቷል፡፡
መሰረቱን በካናዳ ቶሮንቶ ያደረገ አንድ ገለልተኛ አጥኚ ቡድን ሰሞኑን በአንድ የሚዲያ ተቋም ላይ መንግስት የሳይበር ጥቃት መፈጸሙን ማረጋገጡን የሚገልጸው ሂዩማን ራይትስ ዎች ለኢትዮጵያ መንግስት የመረጃ መረብ መጥለፊያና ጥቃት መፈጸሚያ ምርቶችን የሚሸጡ አለም አቀፍ ኩባኒያዎች ድርጊቱን እንዲያጣሩ፤ድርጊቱን ፈጻሚው መንግስትም በአስቸኳይ ከድርጊቱ እንዲታቀብ አሳስቧል፡፡
ይህን የሂዩማን ራይትስዎች መረጃ ተከትሎ በርካታ አለም አቀፍ ሚዲያዎች ባወጡት ዘገባ የኢትዮጵያን መንግስት አውግዘዋል፡፡
ባለፈው አመት የኢትዮጵያ መንግስት ከአንድ የጣሊያን የደህንነት ተቋም በውጪ የሚኖሩ ጋዜጠኞችን ለመሰለል የሶውትዌር ምርት እንደገዛ በአንድ ገለልተኛ ቡድን ምርመራ መረጋገጡን በመጥቀስ ዘገባውን የሚጀምረው ማዘርቦርድ የተባለው የወሬ ምንጭ ይሁን እንጂ ዘንድሮም በተመሳሳይ መንግስት የሳይበር ጥቃቱን ቀጥሎበታል ሲል ያትታል፡፡ በዚህም ሰለባ ከሆኑት መካከል የኢትዮጵያ ሳተላይት ሬዲዮና ቴሌቪዥን(ኢሳት) እንዲሁም በውጭ የሚኖሩና በስራ ላይ ያሉ የኢትዮጵያውያን ነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች እንደሚገኙበት መዘገቡ አይዘነጋም፡፡
ይህን በሚመለከት ተመሳሳይ ዘገባ ይዞ የወጣው ዋሽንግተን ፖስት በበኩሉ የኢትዮጵያ መንግስት በውጪ ያሉ ነጻ ጋዜጠኞችን በሽብር ይከሳል አልፎ ተርፎም የሚያሰራጯቸውን የሚዲያ አገልግሎቶች ጃም በማድረግና በሳይበር ጥቃቶች ለማፈን ይሞክራል ማለቱን ድሬ ቲዩብ ዘግቧል፡፡
“ብሔር”ን ማን ፈጠረው?
የ”ብሔር”ን አፈጣጠር አስመልክቶ ሶስት ዋና ዋና አስተሳሰቦች የየራሳቸውን መልስ ይሰጣሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል ተፈጥሯዊ (Primordial)፣ በማህበራዊ ሂደቶች የተፈጠረ (constructed) እና ልሂቃን ለስልጣን መሳሪያነት የፈጠሩት (instrumental) የሚባሉ ናቸው፡፡ የመጨረሻዎቹ ሁለቱ ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር የተሳታፊ ሀይሎችንና ወቅት ላይ ልዩነት ያላቸው ቢሆንም ከመጀመሪያው በተቃራኒ ‹‹ብሄር›› የሠው ልጆች የፈጠሩት እንጂ ተፈጥሯዊ አይደለም ብለው ያምናሉ፡፡ በመሆኑም ክርክሩ ተፈጥሯዊ እና ሰዎች የፈጠሩት በሚል ሁለት ጎራ ጠበብ ብሎ መቅረብ ይቻላል፡፡
የመጀመሪያው አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› ድሮ ሰው ከተፈጠረበት ወቅት ጀምሮ የኖረና ሰዎች እርስ በእርሳቸው ጠንካራ ግንኙነት በመፍጠር ጥቅማቸውን ያስጠብቁበት የነበረ ተፈጥሯዊ (ሲወረድ ሲዋረድ የመጣ) ቡድናዊ መገለጫ ነው የሚል ነው፡፡ ሆኖም ይህ አስተሳሰብ ከጊዜ ወደጊዜ ከአንድ ‹‹ብሄር›› እየተሰነጠቁ ወይንም በሌላ ምክንያት የሚወጡ ‹‹ብሄሮች››ን ጥያቄ ሊመልስ አልቻለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአንዳንድ አገራት ጠንካራ የአገር ግንባታ ምክንያት የተለያዩ የነበሩ ህዝቦች አንድነት ስለማድረጋቸውም መለስ የለውም፡፡ ከምንም በላይ የዘመኑ ኢኮኖሚና አገራዊ ብሄርተኝነት ‹‹ብሄር›› የሚባልንም ሆነ ሌላ ማህበራዊ ስብስብን እያፈረሰ መገኘቱ ለዚህ አስተሳሰብ ድክመት ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
‹‹ብሄር›› በሂደት የተፈጠረ ነው የሚለው አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› የተፈጠረው በተለያዩ ምክንያቶች በጊዜ ሂደት በተለይም በማህበራዊ ግንኙነት የተፈጠረ እና ትርጉሙ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀየረ የመጣ ነው የሚል ነው፡፡ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው ከሚሉት በተቃራኒ ‹‹ብሄር›› ማህበራዊ ፈጠራ ነው የሚለው የባህል ለውጥ፣ ድንበር፣ ታሪካዊ ወቅት፣ የግለሰቦች ሚና፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ምክንያቶች ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር እንደ ምክንያትነት ይጠቅሳል፡፡
ሶስተኛው አስተሳሰብ ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ተጠያቂ የሚያደርጋቸው ልሂቃንን ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› የተፈጠረው ለልሂቃን መሳሪያነት (instrument) ነው ይላል፡፡ በዚህ አስተሳሰብ ስር የሚገኙ ምሁራን ‹‹ብሄር››ን የፈጠሩት በ‹‹ብሄር›› ስም የሚነግዱ ልሂቃን ወይንም ‹‹የብሄር ኢንተርፕርነሮች›› (ethnic entrepreneurs) ይሏቸዋል፡፡ ይህንም የሚያደርጉት በአንድ አገር መንግስት ውስጥ ይገባናል የሚሉትን ጥቅም ለማሳደግ፣ ለዚህምና ለሌሎቹ ለሚደረጉ ትግሎች በዚህ በፈጠሩት ማንነት ስም በርከት ያሉ ምልምሎችን ለማግኘትና ይህንንም ተጠቅመው የራሳቸውን ግለሰባዊ ስልጣን ለማጠናከር ነው፡፡
ሁለተኛውና ሶስተኛም አስተሳሰቦች ከልዩነታቸው ይልቅ ተመሳሳይነታቸው የጎላ ነው፡፡ ልዩነታቸው ‹‹ብሄር›› በሂደት የመጣ ነው የሚሉት ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር የፖለቲከኞቹን ሚና አጉልተው አለማሳየታቸው ሲሆን በአንጻሩ ‹‹ብሄር›› የልሂቃን ፈጠራ ነው የሚሉት ትልቅ ትኩረት የሚሰጡት ለልሂቃን ብቻ መሆኑ ነው፡፡ በእርግጥ ‹‹ብሄር›› ቀስ በቀስ የተፈጠረ ነው የሚሉትም ስለልሂቃን በስፋት ባያነሱም ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ጠባብ ብሄርተኝነትን እንደምሳሌ ሲጠቅሱ የሚነሳው ‹‹ብሄር›› ለልሂቃን መሳሪያ መሆኑ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአንድ ወቅት በልሂቃን የበላይነት የተፈጠረው ብሄርተኝነት ቀስ በቀስ በህዝብ ዘንድ ሲዘወተር ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ድርሻቸው ከፍተኛ ስለሚሆን ሁለቱ አስተሳሰቦችን የሚመሳሰሉባቸው ነጥቦች ይበዛሉ፡፡ ሁሉቱ አስተሳሰቦች በየራሳቸው ያለባቸው መጠነኛ ክፍተትም ሁለቱን አስተሳሰቦች በጥምረት በመጠቀም ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ሙሉ እይታ መፍጠር እንደሚቻል ብዙዎቹ ምሁራን ያምኑበታል፡፡ ሁለቱን የጋራ የሚያደርጋቸው ደግሞ የልሂቃን ሚና ነው፡፡
ኢትዮጵያና ‹‹ብሄር››
ኢትዮጵያ የተለያየ ባህል፣ ወግ፣ ታሪክና ቋንቋ ያላቸው ህዝቦች መኖሪያ ብትሆንም ‹‹ብሄር›› በፖለቲካ ቃናው ትኩረት እየተሰጠው የመጣው ከጣሊያን ወረራ በኋላ ነው፡፡ በእርግጥ ከዚያ በፊትም ቢሆን የኢትዮጵያ የተለያዩ ገዥዎች ህዝብን በቋንቋ፣ ከባቢና በመሳሰሉት አንቀሳቅሰው ከሌሎች ጋር ያላቸው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልዩነት ለማጠናከር አልጣሩም ለማለት አይቻልም፡፡ በተለይ ህዝቦች በመንገድና በመሳሰሉት መሰረተ ልማት ባለመገናኘታቸው ባህል፣ቋንቋና ሌሎችም ባህላዊ እሴቶቻቸው በመለያየታቸው በሂደት ከሌሎች ለሚለዩባቸው አጋጣሚዎች ክፍተት ይፈጠራሉ፡፡ ይህን ልሂቃን በመሳሪያነት ሲጠቀሙበት ደግሞ ‹‹ብሄር›› መፈጠሩ የግድ ነው፡፡
አንድ ተመሳሳይ ቋንቋ፣ ባህልና ሌሎች ማህበራዊ እሴቶችን ይከተላል የምንለው ህዝብ በውስጡ መጠነኛ ልዩነቶች ይኖሩታል፡፡ ህዝቦች በተለያዩ ምክንያች ግንኙነታቸው ከተዳከመ እያደር እነዚህ ልዩነቶች እየተጠናከሩም በእነዚህ ህዝቦች መካከል ሰፋ ያለ ልዩነት ይፈጠራል፡፡ በተለይ እነዚህን ልዩነቶች የሚያስታርቅና የበላይ የተባለ ገዥ ማህበራዊ እሴት ከሌለ ህዝቦቹ ቀስ በቀስ ልዩነታቸው ሊሰፋ ይችላል፡፡ በየትኛውም አንድ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝብ መካከል ዘየና ሌሎች ልዩነቶች በሂደት የቋንቋ መሰረታዊ ልዩነቶችን ይፈጥራሉ፡፡ ለአብነት ያህል አማርኛ እና ትግርኛ ከግዕዝ የመጡ መሆናቸው የሚነገርላቸው ቢሆንም የህዝቦች አሰፋፈር ልዩነት፣ መንገድና ሌሎችን የመሳሰሉ መሰረተ ልማት አውታሮች አለመኖር እንዲለያዩ አድርጓቸዋል፡፡ የልሂቃን ሚና ሲጨመርበት ደግሞ የአሁኑን ፖለቲካ ፈጥሯል፡፡
በአሁኑ ወቅት በትምህርት ደረጃ የሚሰጠው አማርኛ ሸዋ፣ ጎንደር፣ ጎጃምና ወሎ አካባቢ የሚነገሩ ዘየና ሌሎች የቋንቋው ልዩነቶችን ማስታረቅ ባይችል፣ በመሰረተ ልማት መገናኘት ባይችሉ እነዚህ ከጅኦግራፊያዊ አቀማመጥ ውጭ የማይለያዩ አማርኛ ተናጋሪ ህዝቦች ትግርኛ እና አማርኛ እንደተለያዩት የተለያዩ ቋንቋዎች መሆን ይችሉ እንደነበር አያጠራጥርም፡፡
ኢትዮጵያ አገውኛ ተናጋሪ ህዝቦች ይኖሩባት እንደነበር ታሪክ ያስረዳል፡፡ በሰሜን ኢትዮጵያ ይኖሩ የነበሩት ህዝቦች አገዎች እንደነበሩ በኢዛናና ካሌብ ዘመን የነበሩ ቅሬቶች ፍንጭ ሰጥተውል፡፡ እነዚህ ህዝቦች በአማርኛና ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ ተውጠው በአሁኑ ወቅት በተወሰኑ አካባቢዎች ብቻ ይገኛሉ፡፡ ለአብነት ያህል በወሎና ጎጃም አገው በሚል፣ በጎንደር ቅማንት፣ በባህር ዳር አካባቢ ወይጦ እና የመሳሰሉ ስሞች ተሰጥቷቸው ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ህዝቦች ትግራይና ኤርትራ ውስጥም ተበታትነው ይኖራሉ፡፡ ከከረን ጀምሮ በቋራ፣ ዳንግላ፣ ሰቆጣ፣ ጣና ዳር….ተበታትነው ከሚገኙት ውጭ ሌሎቹ በትግርኛ እና አማርኛ ተናጋሪ ሆነዋል፡፡ ይህኛው ክስተት የሚያሳየው ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ማንነት ሳይሆን የሚዋጥ፣ የሚቀየር መሆኑን ነው፡፡ እነዚህ በአንድ ወቅት ‹‹አገው›› ተብለው የነበሩ ህዝቦች በሂደት በመጣ ማግበራዊ፣ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ‹‹ኤርትራዊ››፣ ‹‹ትግሬ››ና ‹‹አማራ›› ተብለዋል፡፡ ልሂቃንም በተለያዩት እነዚህ ማንነቶች በአንድ ወቅት አንድ የነበሩትን ህዝቦች አንቀሳቅሰዋቸዋል፡፡ ሌላው ይቅርና ግዕዝ ከቤተክርስቲያን አልፎ በተወሰነ ህዝብ የሚነገር ቢሆኑ ኖሮ ኢህአዴግ አንድ ተጨማሪ ‹‹ብሄር›› ሊያቋቁም ነበር ማለት ነው፡፡
የአክሱም ስርወ መንግስት በተለያዩ ምክንያቶች ተዳክሞ የዛጉየ ስርወ መንግስት ሲተካ ከድልነአድ እስከ ይኩኑ አምላክ ያሉት 8 የአክሱም ስርወ መንግስት ነገስታት በሸዋ እየሸሹና ተደብቅው ኖረዋል፡፡ የአሁኑ ወቅት ልሂቅ መር የ‹‹ብሄር›› ፖለቲካ አክሱም ውስጥ የነበሩትን ነገስታት ‹‹የትግሬ ቅድመ አያቶች›› አድርገው ይወስዷቸዋል፡፡ ከአክሱም መጥተው ሸዋ ነገስትነትን የመሩትን ደግሞ ‹‹አማራ›› ይሏቸዋል፡፡ ታሪክ ደግሞ የአክሱም ስርወ መንግስት ወቅት በሰሜን ኢትዮጵያ ይነገር የነበረው ቋንቋ አገውኛ እንደነበር ያስረዳናል፡፡
‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ቢሆን ኖሮ አገውኛ የሚናገሩት አብዛኛዎቹ ኢትዮጰያ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ህዝቦች ሌሎች ቋንቋዎችን በሚናገሩ ህዝቦች ሳይዋጡ ‹‹አገው›› ሆነው በቆዩ ነበር፡፡ ትግሬ ከአክሱማውያን የመጣ ‹‹ብሄር›› ቢሆን ኖሮ መነሻቸው ከአክሱማውያን የሆኑት የሸዋ ነገስታትም እስከ አሁን ‹‹ትግሬ›› ሆነው በቀጠሉ ነበር፡፡ ይሁንና ‹‹ብሄር›› በሂደት በተለይም የልሂቃን ሚና ተጨምሮበት የሚፈጠር አዲስና የፈጠራ ማንነት በመሆኑ እነዚህ ህዝቦች የተለያዩ ማንነቶች እንዳላቸው እየተቆጠረ ነው፡፡
በአንድ ወቅት ኢህአዴግ አራት ያህል የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችን ‹‹ወጋጎዳ›› በሚል አዲስ የ‹‹ብሄር›› ማንነት ለመመስረጥ ጥረት አድርጎ ነበር፡፡ ይህ አዲስ ማንነት ቢሳካ ኖሮ ሀይለማሪያም ደሳለኝ የወላይታ ሳይሆን በልሂቃን መሳሪያነት ከሌሎች ሶስት (ጋሞ፣ ጎፋና ዳዋሮ) ጋር የተለነቀጠው ‹‹ወጋጎዳ ብሄር›› ተደርገው ሊወሰዱ ነበር፡፡ ምንም እንኳ በተለያዩ ምክንያቶች ባይሳካም ‹‹የወጋጎዳ›› ፕሮጀክት ብሄርን የሚፈጥሩት ልሂቃን መሆናቸውን ቁልጭ አድርጎ አሳይቷል፡፡
ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ በኋላ ‹‹ብሄር›› በግልጽ ተፈጥሯዊ እንደሆነ ተደርጎ ተግባራ ሊሆን ችሏል፡፡ ብሄር ተፈጥሯዊ ነው የሚለውን አስተሳሰብ የሚከተሉ አካላት አንድ ግለሰብ በ‹‹ብሄሩ›› እንጂ በግለሰባዊነቱ መቆም አይችልም የሚል አስተሳሰብ ያራምዳሉ፡፡ ይህም በእኛው ህገመንግስት ‹‹እኛ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች›› በሚል ተቀምጧል፡፡ በመሳሪያነት የሚጠቀሙ ፖለቲከኞች ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው የሚሉ አካላት አስተሳሰብ የሚጠቀሙ ናቸው፡፡ በመሆኑም በአስተሳሰብ ደረጃ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው የሚለውን በመጠቀም ኢህአዴግ የ‹‹ብሄር ኢንተርፕርነር›› ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ከሆነ የትኛውም ፖለቲከኛ ወይንም ፓርቲ ሊመሰርተው የሚችለው መንግስትም ሆነ ስርዓት ‹‹ብሄር›› ተመሳሳይ የ‹‹ብሄር›› ማንነት ላይ ያተኮረ መሆን አለበት፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ህዝቦች በአጼ ሀይለስላሴ፣ ደርግ፣ ኢህአዴግ ስር የያዙት የ‹‹ብሄር›› ማንነት በየ ስርዓቱ የተለያየና በየ ጊዜው እንደ ልሂቃኑ ጥበትና ኢትዮጵያዊ አላማ የሚወናበድ ነው፡፡
ወደ ኢህአዴግ ወረድ ብልን እንኳ በአቶ መለስና በሌሎቹ ገዥዎች ኢትዮጵያንም ሆነ በየ የኢትዮጵያን ‹‹ብሄሮች›› የሚያንቀሳቀሱበት አጋጣሚ የተለየ ነው፡፡ አንድ ህዝብ ሊከተለው የሚችለው በጊዜው በኢኮኖሚ፣ ሚዲያም ሆነ ወታደራዊ ሁኔታ ጊዜው ስልጣን የሰጠውን አካል ነው፡፡ ህወሓትና አረና የትግራይን ህዝብ የ‹‹ብሄር›› ማንነት የሚቀርጹበት ሁኔታ ተመሳሳይ አይሆንም፡፡ ብአዴንና የድሮው መአአድ፣ ኦነግና ኦህዴድ፣ የደቡብ ህብረትና ደኢህአዴን፣ ሶዴፓና ኦብነግ፣ ሻቢያና ጀብሃ እንወክለዋነን የሚሉትን ህዝብ ብሄራዊ ማንነት የሚመሩበትና የሚፈጥሩት በተለያየ መልኩ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከ20 አመት በፊት የነበሩትና አሁን ያሉት እነዚህ ፓርቲዎች ህዝብን የሚቀሰቅሱበት አጋጣሚ የተለያየ ነው፡፡ በቅርቡ ኦነግ የመገንጠል ጥያቄውን አንስቻለሁ ሲል ከ20 አመት በፊት ከነበረው የኦነግ የ‹‹ብሄር›› ማንነት መለየቱን ለመገንዘብ ይቻላል፡፡
‹‹ብሄር››ና ደም
‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ካልሆነ ከደም ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም ማለት ነው፡፡ ሳይንስ በራሱ ዘር፣ ብሄርና ሌሎችን የሰው ልጅ ማህበራዊ ትስስሮች ለማመሳሰል ቢሞክርም ሊሳካለት አልቻለም፡፡ በተለይ ምዕራባዊያን ከሌሎች የተለዩ መሆናቸውን ለማረጋገጥ ሙከራ ያደረጉ ‹‹ሳይንቲስቶች› ዘንድ የሰዎች ዘረመል የሰውን ዘርቁልጭ አድርጎ ያሳያል የሚል መላ ምት የነበራቸው ቢሆንም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ እስካሁን አንድ ሰው ከየትኛው አገር እንደመጣ የሚያሳይ አስተማማኝ መረጃ እንኳን ማግኘት አልተቻለም፡፡
በእነዚህ ጥናቶችን ተንተርስ ለአብነት ያህል ኢትዮጵያን እንደምሳሌ ብንወስድ የሚያሳየው የአንድ አገር ሰው በዘረመልም ሆነ በደም ከሌሎች አገራት ጋርም የሚመሳሰል ነው፡፡ እንደ ጥናቶቹ ኢትዮጵያዊያን ከቻይና፣ አብዛኛው የአረብና የኤሲያ አገራት፣ አንዳንድ የደቡብ አሜሪካና ሜክሲኮ ህዝቦች መካከል ከ10-15 የሚሆኑት በተመሳሳይ የኤ የደም ዘር ባለቤቶች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን፣ አብዛኛዎቹ የአፍሪካዊያን፣ የደቡብ አሜሪካ ኤሲያ ከ5-10 እና ከ10-15 የሚሆነው ህዝባቸው ቢ የደም አይነት ያለው ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያን ጨምሮ አፍሪካ፣ የመንና ሳውዲ የመሳሰሉ የአረብ አገራት፣ የተወሰነ የቻይና ከፍል፣ ጥቂት የምስራቅ አውሮፓ አገራት፣ ከደቡብ አሜሪካ አገራት መካከል አንዳንድ አካባቢዎች፣ የአውስትራሊያ ጠረፋማ ክፍሎች ከሚኖሩት ህዝቦች መካከል ከ40-70 ኦ የደም አይነት ባለቤቶች ናቸው፡፡ በ‹‹ብሄሮች›› መካከል ይህን ያህል የሚመሳሰል የዘረመልና የደም አይነት ለማግኘት አልተቻለም፡፡ በዓለም ህዝቦች ሁሉ ኤ፣ ቤ፣ ኤቤና ኦ የተባሉት የደም አይነቶች የትም የሚገኙ ሲሆን ከአንድ ቤተሰብ ይልቅ በተለያዩ አገራት ያሉ ህዝቦች ለሌላኛው ደም መስጠት ይችላሉ፡፡ በመሆኑም አንድ ኦሮሞ ከብሄሩ ያላገኘውን ተመሳሳይ የደም አይነት ወይንም ልብ፣ ኩላሊትና ሌሎች ተመሳሳይ የአካል ክፍሎች ከትግሬ፣ ከአማራ፣ ከጉራጌና ከሌሎች ብሄሮች አልፎ ደቡብ አሜሪካ፣ ኤሲያ፣ አውሮፓና አውስትራሊያ ከሚገኝ ነጭ ማግኘት ይችላል፡፡
አንድ ቋንቋ የሚናገሩና በተለያየ የአየር ንብረት ከሚኖሩ ህዝቦች በተሻለ የተለያየ ቋንቋ የሚናገሩና በተመሳሳይ የአየር ንብረት የሚኖሩ ህዝቦች ተመሳሳይ የሰውነት ገጽታ ይኖራቸዋል፡፡ ለአብነት ያህል በመተማና ሁመራ አካባቢ የሚኖሩ ትግርኛ እና አማርኛ ተናጋሪዎች በቆላማው ሶማሊና አፋር ክልሎች ከሚኖሩት የሶማልኛና አፋርኛ ተናጋሪ ህዝቦች ተመሳሳይ የሰውነት ገጽታ፣ አለባበስና አመጋገብ ባህል አላቸው፡፡ ከምንም በላይ በአገራችን ብሄር የፈጠራ ማንነት መሆኑን የሚያሳየው ሁለት የተለያየ ማንነት አላቸው ከተባሉ ቤተሰቦች የተገኘ ልጅ የእናቱን ማንነት ትቶ የአባቱን ማንነት በግድ እንዲቀበል የመመደቡ ጉዳይ ነው፡፡ አንድ ግለሰብ በተለያዩ ምክንያቶች የእናቱን አሊያም ግለሰባዊ ማንነቱን መቀበል ቢፈልግ የወቅቱ የአገራችን ስርዓት በግድ የአባቱን ብሄር አባል ያደርገዋል፡፡ ሰው የፖለቲካ እንሰሳ እንደመሆኑ ‹‹ብሄር››ን ሲፈጥር እንሰሳት ከሰው የተሻለ ቁርጥ ያለ ዘር ያላቸው ማንነታውን በሂደት በሚፈጠር ማህበራዊ ማንነት አሊያም የልሂቃን ፈጠራ የሚያወናብደው ፖለቲካዊና ማህበራዊ ምክንያት ባለመጠቀማቸው ብቻ ነው፡፡
ሶቭየት ወዲያ ኢትዮጵያ…
በአገራችን የ‹‹ብሄር›› ማንነት የሚጣረሰው ገና ከትርጉሙ ነው፡፡ ‹‹ብሄር›› በግዕዝ አገር ማለት ቢሆንም ከ1960ው ጥራዝ ነጠቅ ትውልድ ትርጉም በኋላ አገሪቱ የተሰራችባቸው ማንነቶች ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በእነ ስታሊኑ ትርጉም እንኳ ብንሄድ ብሄር የሚለውን ‹‹ተመሳሳይ ወይንም ተቀራራቢ ቋንቋ፣ ባህል፣ ታሪክ፣…..›› ለሚጋሩ ህዝቦች የሚሰጥ ነው፡፡ እንግዲህ እነዚህ ህዝቦች ከሌሎች የተለዩ፣ ማንነቱ ተፈጥራዊና ከሌሎች በፍጹም የተለየ በመሆኑ መቼም ቢሆን ይህን ባህላቸውን፣ ማንነታቸውን አይቀይሩም እንደማለት ነው፡፡ ‹‹የጋራ ታሪክ ያላቸው›› ብሎ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ወላይታ፣ (ቢሳካ ኖሮ ደግሞ ‹‹ወጋጎዳ)፣ ሲዳማ…ሲልም የአድዋና ማይጨውን ጨምሮ የሚጋሩት ታሪክ የላቸውም እያሉን ነው፡፡
በቭየት ህብረትና በኢትዮጵያ መካከል ከፍተኛ ልዩነት ነው ያለው፡፡ ሌኒን 15 አገራት አንድ ከማድረጉ በፊት ኢትዮጵያውያን በጋራ አገር ለመመስረት ለረዥም አመት ሰርተዋል፡፡ በአንጻሩ የሶቭየት ክፍሎች አንድ እስኪሆኑ ድረስ ያላቸው ታሪክ የተለየ ነው፡፡ የሶቭዬት ህብረት አባላት ህብረቱን ከመራችው ሩሲያም ሆነ ከሶቭየት ህብረት የተለየ የአገር ምስረታ ታሪክ አከናውነው የተቀላቀሉ ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ የሩሲያ መንግስት ከመስፋፋቱ በፊት በኦቶማን ቱርክና በሌሎች ቀኝ ገዥዎች ስርም የነበሩ ናቸው፡፡
የሶቬት ህብረት ፌደራል አወቃቀር በአገራት እንጅ አገር ውስጥ ባሉ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች የተመራ አልነበረም፡፡ ኢህአዴግም የነ ስታሊንን ስርዓት ሲገለብጥ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይ፣ አፋር፣ ሀረሪ…..እያንዳንዳቸው ‹‹አገር›› ሆነው ፌደራሊዝሙን እንደተቀላቀሉ እየነገረን ነው፡፡ በተቃራኒው ኢትዮጵያ ውስጥ በየ አካባቢው የነበሩ ነገስታት ኢትዮጵያን በራሳቸው መልክ ለመገንባት እንጅ የያዙትን አካባቢ ገንጥለው አገር ለመመስረት አልነበረም፡፡ የየራሳቸውን ግዛት ለመመስረት ነበር የሚል የፈጠራ መረጃ እንኳን ቢቀርብ ‹‹አገር›› ለመሆን የሚያስችል ቅርጽ ሳይዙ ማዕከላዊ መንግስት ውስጥ መጠቃለላቸው ከሶቬት አባላት በእጅጉ የተለዩ ያደርጋቸዋል፡፡
እንዲያው የስታሊኑን ትርጉም ብንወስድ እንኳን የእኛው የ‹‹ብሄር›› ትርጉም የተሳሳተ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ ኢትዮጵያውያን ቋንቋ ሳይገድባቸው እንጀራና ጥሬ ስጋ ይመገባሉ፡፡ ጠላና ጠጅ ይጠጣሉ፡፡ ተዋልደውና በጉድፍቻ አብረው ይኖራሉ፡፡ አተራረሳቸው፣ አመራረታቸውና ምርቶቻቸው በአየር ንብረት ካልሆነ በስተቀር ልዩነቱ ጎልቶ የሚተይ አይደለም፡፡ በጋራ አላማ ቅኝ ገዥዎችን ተዋግተዋል፡፡ አገር ገንብተዋል፡፡ በመሆኑም በስታሊኑ ቋንቋ ‹‹ተመሳሳይ ወይንም ተቀራራቢ ባህል፣ ታሪክ፣ አላማ….›› መሰረት አንድ ብሄር (አገር›› ውስጥ የሚካተቱበት እንጅ የሚነጣጠሉበት አልነበረም፡፡
በነገራችን ላይ ህዝቦች የተለያዩ ናቸው ተብሎ ‹‹ብሄር›› የተለያዩ ቋንቋ ተናገሪ ህዝቦች መጠሪያ በዋለበት እንደገና ‹‹ብሄር›› ማለት አገር ማለት መሆኑን ይነገረናል፡፡ ለአብነት ያህል ብሄራዊ ቡድን ሲባል የኦሮሞ፣ የአማራ፣ ትግሬ፣ ወላይታ ተጫዋቾች ብቻ የተሰባሰቡበት ሳይሆን የአገሪቱ ቡድን መሆኑ ነው፡፡ ብሄራዊ ባንክ ሲባልም ቢሆን የአገሪቱ ማዕከላዊ ባንክ እንጅ በሂደት ሲቀየር፣ ሲዋጥ፣ ሲያንሰራራ በኖሩት ቋንቋን መሰረት ያደረጉ ማንነቶች ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ከማርክሲስቱ ትርጉም ይልቅ የምዕራባዊያን ትርጓሜ ‹‹ብሄር›› የተወናበደ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፡፡ ብሄር (አገር) በእንግሊዘኛው (በምዕራባዊያኑ አስተሳሰብም) ‹‹Nation›› በሚለው ቃል ይገለጻል፡፡ ‹‹Nationality›› የሚለው ደግሞ አንድ ግለሰብ ከአገሩ ጋር ያለው ግንኙነት የሚገለጽበት ነው፡፡ ነዋሪ፣ ተወላጅ፣ ዜጋ በሚለው ልንወክለው እንችላለን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥም ቢሆን በፓስፖርትና በመሳሰሉት ‹‹Nationality›› ቋንቋ ሳይገድበው የሚገልጸው ዜግነትን ነው፡፡ ለፖለቲካው ዘርፍ ደግሞ ‹‹ከትልልቆቹ ብሄሮች ያነሱ›› የሚሏቸውን ማንነቶች ለመግለጽ ይውላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብሄር የሚባለው ‹‹Nation›› (አገርን) ሳይሆን ‹‹ethnicity›› የሚለውን ‹‹ማንነት›› እንዲወክል ተደርጓል፡፡ ‹‹ethnicity›› ደግሞ በወጉ ይተርጎም ከተባለ ከጎሳ ያለፈ ቃል ሊገኝለት አይችልም፡፡
ይህ የሚያሳየው መሰረታቸውን ካደረጉበት የስታሊኑ ትርጉም ጋር እንኳ አብረው መሄድ አለመቻላቸውን ነው፡፡ ይህ ተቃርኖ የሚመነጨው ብሄር ከሂደቱም ይልቅ ፖለቲካ ፈጠራው ማመዘኑ ነው፡፡ በአገራችን ደግሞ ከሁለቱም ትርጉሞች ሳይሆን ጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅም ላይ ማተኮሩ ተቃርኖውን ውስብስብ አድርጎታል፡፡




