Category Archives: Social and Culture

“የሰርቆ አደሮች” ስብሰባ

Daniel Kibret

ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

ሰሞኑን በአዲስ አበባ አንድ ትልቅ የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ የአዲስ አበባ ደረጃ አንድ ሌቦች ስብሰባ አድርገው ነበር፡፡ የስብሰባው መሪ ቃል ‹የሕዝቡን ጥያቄ ለመመለስ ሌቦች ምን ሊያደርጉ ይችላሉ?› የሚል ነው፡፡ ስብሰባው እንደተጀመረ አንደኛው የታወቀ ሌባ እጁን አወጣና ‹መፈክሩ ላይ የተጠቀስንበት ስም ትክክል አይደለም። ገጽታችንን የሚያበላሽ ነው› ሲል አስተያየት ሰጠ፡፡ ጭብጨባ አዳራሹን ሞላው፡፡

‹ታድያ ምን ይሁን፤ መቼም ሌባ መሆናችን ርግጥ ነው› አሉ ሰብሳቢው፡፡
‹ጠየም አድርጉት፤ እንደ ባለጌ ጥፊ ድርግም አይደረግም› አሉ ሌላ አስተያየት ሰጭ፡፡
‹እኮ ምን እንባል› አሉ ሰብሳቢው፡፡
‹ሌሎቹ ሠርቶ አደር፣ አርብቶ አደር፣ ወቶ አደር፣አርሶ አደር ከተባሉ እኛም ‹ነጥቆ አደር› ነው መባል ያለብን›
ይኼው ጸደቀ፡፡

‹የሕዝቡ ምሬት ጨምሯል፡፡ ሕዝቡ በሌቦች መማረሩን በተደጋጋሚ እየገለጠ ነው፡፡ አንድ ቀን መሣሪያ ቢያጣ እንኳን አካፋና ዶማ ይዞ መነሣቱ አይቀርም፡፡
ከተንተከተከ እሳቱ ጨምሮ
ክዳኑን ይገፋል የፈላበት ሽሮ
ሲባል አልሰማችሁም፡፡ ያን ጊዜ ደግሞ ለሁላችን መግቢያ ቀዳዳው ጠባብ ነው የሚሆነው፡፡ ለዚህ ጉዳይ እኛው ራሳችን መፍትሔ ማምጣት አለብን› አሉ ሰብሳቢው፡፡

‹ስንናገር ለይተን መናገር አለብን፡፡ ሌባ ሁሉ አንድ ዓይነት አይደለም፡፡ ኩሩ ሌባና ልክስክስ ሌባ፤ ጨዋ ሌባና ባለጌ ሌባ፤ ሸቃጭ ሌባና ኢንቨስተር ሌባ፤ ነጥቆ ሂያጅና ነጥቆ ገንቢ፤ ገፋፊ ሌባና ለካፊ ሌባ፣ እየተባለ የሚዘረዘር ብዙ ዓይነት ሌባ ነው ያለው፡፡ በስመ ሌባ ሁላችንም መሰደብ የለብንም› አሉ አንድ የታወቁ ሌባ፡፡

ሰብሳቢው የተገረሙ ይመስላሉ፤ አገጫቸውን በእጃቸው ይዘው ‹እኔም የእናንተን ያህል ባይሆንም መቼም በዚሁ ስም ተጠርቼበታለሁ፡፡ አሁን የዘረዘርከው ግን ምንድን ነው?› አሉት፡፡

ሰውዬው ዕውቀት በመጠየቁ ወንበሩ ላይ ተገላብጦ ተቀመጠና፣ ጉሮሮውን ጠራርጎ ‹መቼም ዕውቀት ማካፈል ደስ ይለኛል፡፡ ኩሩ ሌባ ማለት ከሚሊዮን በታች የማይነካ፤ ዝም ብሎ በመቶውም በሺውም የማይልከሰከስ ነው፡፡ ልክስክስ ሌባ ደግሞ የዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ ጨዋ ሌባ ማለት ደግሞ ሲሰርቅ በሕጉ መሠረት የሚሰርቅ ማለት ነው፡፡ ሰነድ አዘጋጅቶ፣ ጨረታ አጫርቶ፣ ማስታወቂያ አሠርቶ፣ ቃለ ጉባኤ አያይዞ፤ ዕቃ ገቢ አድርጎ የሚሰርቅ ማለት ነው፡፡ ባለጌ ሌባ ደግሞ የዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ ኢንቨስተር ሌባ ገንዘብ የሚቦጭቀው ከትላልቅ ኢንቨስትመንቶች ብቻ ነው፡፡ መጉመድ እንጂ መጉረስ የማያውቅ ቆፍጣና። መጉረድ እንጂ መቁረጥ ያልለመደ ጀግና፤ መቦጨቅ እንጂ መንጨት የማያውቅ ሆደ ሰፊ ማለት ነው፡፡ ሸቃጭ ሌባ ግን ከገቢውም፣ ከወጭውም፣ ከሱቁም፣ ከኅብረት ሱቁም የሚቀነጣጥብ ቀነጣጣቢ ነው፡፡ ነጥቆ ሂያጅና ነጥቆ ገንቢ ስለሚባሉት የሌባ ዓይነቶች በደንብ መግለጥ አለብኝ፡፡ ‹ነጥቆ ሂያጅ ሌባ› ማለት ካገኘ በኋላ እዚህ ሀገር የማይቀመጥ ሌባ ነው፡፡ ይኼ ዓይነቱ ሌባ ለሀገሪቱ ዕድገት ዕንቅፋት ነው፡፡ የሀገርን ገቢ ወደ ባዕድ ሀገር የሚያሸሽ ከሐዲ ሌባ ነው፡፡ የሀገር ፍቅር ስሜት ፈጽሞ የሌለው ሌባ ነው፡፡ እዚሁ ነጥቆ እዚሁ መብላት ሲገባው ሀገሩን ከድቶ ወጥቶ የሚበላ፡፡ እኛ ‹ወጥቶ በል ሌባ› ብለነዋል፡፡ ‹ነጥቆ ገንቢ ሌባ› ግን አገር ወዳድ ሌባ ነው፡፡ እዚሁ ነጥቆ እዚሁ ፎቁንም፣ ፋብሪካውንም፣ ሆቴሉንም፣ እርሻውንም ይገነባል፡፡ ለሀገሩም አጥብቆ ያስባል፡፡ እዚሁ ነጥቆ እዚሁ የሚሊዮን ብሩን መኪና ያሽቃብጠዋል፤ እዚሁ የመቶ ሺ ብር ውስኪ ያወርዳል፡፡

ነጥቆ ገንቢ ሌባ ደግ ሰው ነው፡፡ ሃይማኖተኛ ከሆነ ከነጠቀው ገንዘብ ወይ ለቸርች ወይ ለገዳም ይሰጣል፡፡ ነዳያን ያበላል፡፡ ድኻ ይረዳል፡፡ ሃይማኖተኛ ካልሆነ ደግሞ ለወጣት ማኅበራት ይለግሳል፤ ለቀበሌ ቲሸርት ያሠራል፤ በዓል ስፖንሰር ያደርጋል፤ እንዲህ ያለው ነጥቆ ገንቢ ሌባ ሊበረታታ ይገባዋል፡፡ ግን ምን ያደርጋል የሀገራችን ሕግና የኢንቨስትመንት ዐዋጁ በቂ ማበረታቻ ለዚህ ሀገር ወዳድ ሌባ አይሰጥም፡፡
በመጨረሻ የማብራራላችሁ ‹ገፋፊ ሌባና ለካፊ ሌባ› ስለሚባሉት ነው፡፡ ገፋፊ ሌባ ማለት ሥጋ ሲበላ አጥንት የማያስቀር፤ እንጀራ ሲበላ ሞሰብ የማይተርፈው፤ ሻይ ሲወስድ ከነ ብርጭቆው፤ የደራሲውን ድርሰት ወስዶ የደራሲውን ስም የሚያጠፋ፤ሚስቱን መንጠቁ ሳያንሰው ባሏን የሚገል፤ በመሬትህ ላይ ባለ ዘጠኝ ፎቅ ሊሠራ አንተን በዘጠነኛው የኮንዶሚኒየም ፎቅ ላይ የሚወረውርህ፣ ሃምሳ ዓመት የኖርክበትን ቤት ወስዶ ከከተማው ሃምሳ ኪሎ ሜትር አውጥቶ የሚጥልህ ማለት ነው፡፡ ለካፊዎቹ ሌቦች ዝም ብለው ነው፡፡ እዚህም እዚያም ለኮፍ ለኮፍ ነው የሚያደርጉት፡፡›

ሰውዬው ማብራሪያውን ሲጨርስ አድናቂዎቹ እየሳቁ አጨበጨቡ፡፡ ሰው የልቡን ሲነግሩት የኮረኮሩት ያህል ይስቃል ይባል የለ፡፡

‹ታድያ አሁን መፍትሔው ምንድን ነው› አሉ ሰብሳቢው ነገሩ ውስብስብ ብሎባቸው፡፡ አንዱ እጁን አወጣ፡፡
‹ለችግሩ መባባስ ዋነኞቹ ተጠያቂዎች ከመሐልና ከታች ያሉት ሌቦች ናቸው፡፡ አሁን እኔ ኩሩ ሌባ ነኝ፡፡ ልስረቅ አልስረቅ ሰፊው ሕዝብ አያውቅም። እይውልዎት፣ መንደር መንገድ ላይ ያለችውን ዛፍ የሚቆርጠውን እንጂ ደን ውስጥ ያለውን ዛፍ የሚቆርጠውን ማንም አያየውም። አሁን ለኛ ችግር የሆኑብን የመንደር ዛፍ ቆራጮች ናቸው። ለካፊ ሌቦች ከስኳሩም፣ ከጨውም፣ ከድንቹም፣ ከሸማቾቹም ይቀነጣጥቡና ሕዝቡን ያነሣሡታል፡፡ ሕዝቡኮ ስኳሩ ወደ ሸማቾች ከገባ በኋላ አለቀ ሲሉት እንጂ መጀመሪያውኑ ወደ ሸማቾች ባልመጣው ስኳር ላይ አይበሳጭም፡፡ ሃምሳ ኩንታሉን ወስደን ሃምሳውን ኩንታል ሩብ ሩብ ኪሎ ብናከፋፍለው ‹ተመስገን› ብሎ ነው ወደ ቤቱ የሚሄደው፡፡ ሥራው ግልጽነት ያለው እንዲመስል ደግሞ የመጣውን ሃምሳ ኩንታል ከሴቶች፣ ከወጣቶችና ከአዛውንት የተመረጡ ኮሚቴዎችን አሰልፎ እኩል እንዲያካፍሉ ማድረግ ነው፡፡ ›

‹ልክ ነው፡፡› አለ አንዱ ሰርቆ አደር ኢንቨስተር ‹ሰው መብራት ተቆራረጠብን አለ እንጂ የመብራቱን ኬብል እነማን ናቸው ከውጭ የሚያስገቡት ብሎ ጠየቀ? ዱቄቱ ወደ ሸማቾች በብዛት አልመጣም አለ እንጂ ዱቄቱን እነ እገሌ ብቻ ለምን ከውጭ ያስመጣሉ?ብሎ ጠየቀ፤ አልጠየቀም፡፡ ኮንደሚኒየም በትክክል አልደረሰኝም አለ እንጂ እነ እገሌ የከተማ ቦታ በካሬ 300 ሺብር የሚጫረቱት ብሩን ከየት ቢያመጡት ነው ብሎ ጠየቀ፤አልጠየቀም፡፡ ‹እገሌና እገሌ የተባሉ ዋና አከፋፋዮች ለምን አስወደዱብን፣ ለምን አሳነሱን› አለ እንጂ ‹ግን እነርሱ የውጭ ምንዛሬ ከየት እያገኙ ነው ዕቃውን ከውጭ የሚያመጡት?› ብሎ መች ጠየቀ፤ ስለዚህ ችግሩ እታች ያሉት አቀባባይ ሌቦች አሠራሩን ስላላወቁበት ነው ማለት ነው፡፡ አያችሁ ሕዝቡ የዋሕ ነው፡፡ በጥፍርህ ስትቧጭረው ‹ጥፍሩን ቁረጡልኝ› ነው የሚለው፡፡ ሰውዬውኮ የቧጨረው ጥፍር ስላለው አይደለም። በጥፍሩ እንዲቧጭር የሚያዝ ጭንቅላት ስላለው ነው፡፡ ሕዝቡ ‹ጥፍሩን አስቆርጦ› ወደ ቤቱ ይገባል። ለተወሰነ ጊዜ ቧጫሪው ዝም ይላል፡፡ ቆይቶ ግን ጥፍሩ ሲያድግ መቧጨሩን ይቀጥላል፡፡

መጀመሪያ ጥፍሩን ያሳደገው፤ ተቧጨር ብሎ መብት የሰጠው ማን ሆነና፡፡ አሁንም ያስቸገሩን ራሶቹ አይደሉም፡፡ ጥፍሮቹ ናቸው፡፡› እንደ ድጓ አድራሽ በሊቃውንት ፊት ዕውቀቱን ያስመሰከረ መስሎት ትከሻውን ሰበቀ፡፡

ሰብሳቢው ግራ እየገባቸውም ቢሆን ‹ሐሳቡን እንጠቅልለው፤ የመቋጫ ሐሳብ አምጡ› አሉ፡፡
ሁለት ሰዎች ተረዳድተው ያዘጋጁትን የአቋም መግለጫ ይዘው ወጡ፡፡ እነርሱ የአቋም መግለጫውን ሲያቀርቡ ተሰብሳቢዎቹ ወረቀትና ስክርቢቶ አዘጋጁ፡፡ አንደኛ፡- ኅብረተሰቡ ስርቆትን እንዲጠየፍ ስለ ስርቆት በመገናኛ ብዙኃን ትምህርት ይሰጥ (ይኼ ሲነበብ አንድ አምስቱ በቲቪና ሬዲዮ የሚቀርበውን ማስታወቂያ ለመሥራት እንዴት ከባለ ሥልጣናቱ ጋር እንደሚሠሩ ተንሾካሾኩ፤ አንድ ሁለቱ ደግሞ በእነርሱ ሬዲዮ ጣቢያ ይህን ፕሮግራም ለመሥራት የስፖንሰር ገንዘብ ሲቦጭቁ ታያቸው)

ሁለተኛ፡- በየቀበሌውና በየደረጃው ሕዝቡ ሌቦችን እንዲያጋልጥ ይደረግና ርምጃ ይወሰድ (የተወሰኑት ተሰብሳቢዎች ለቀበሌ ስብሰባዎች ሞንታርቦ፣ ውኃና ኮፍያ ያለ ጨረታ ለማቅረብ ተጠቃቀሱ)

ሦስተኛ፡- ሌብነትን የተመለከተ ዜማ በታዋቂ አርቲስቶች እንዲዘጋጅ ይደረግ (አርት ነክቶናል የሚሉ ነጥቆ አደር አርቲስቶች የሚዘጋጀውን የፀረ ስርቆት ቅስቀሳ ከእነርሱ እንዳይወጣ ዘየዱ)

አራተኛ፡- ስለ ስርቆት አስከፊነት የሚያስተምር ቢል ቦርድ በመላ ሀገሪቱ ይተከል (የማስታወቂያ ድርጅት ያላቸው ተሰብሳቢዎች ይቺ ፕሮጀክት ከኛ አታልፍም ብለው ማሉ) አምስተኛ፡- የፀረ ስርቆት ቀን በየዓመቱ ይከበር። (ቲሸርትና ኮፍያ፣ መድረክና መስተንግዶ የሚያቀርቡ ተሰብሳቢዎች ዓመታዊ ገቢ ተገኘ ብለው ጮቤ ረገጡ፡፡)

ተሰብሳቢዎቹ ሲወጡ የአዳራሹ ዘበኛ በኀዘን ለጓደኛቸው ‹በሬ ሞተና ፍትሐት ሲፈታ ከበሮው ድምጹ እንዳይሰማ ‹ትሽ፣ ትሽ፣ ትሽ› ይል ጀመር፡፡ ከዚያ በፊት ‹እድም፣ እድም፣ እድም› ሲል ይሰሙት የነበሩት ጽናጽንና መቋሚያ ‹ምነው ዛሬ ያለወትሮህ ድምጽ እንዳይሰማ ‹ትሽ፣ ትሽ፣ ትሽ› ትል ጀመር› ብለው ቢጠይቁት ‹የሞተው በሬ፤ የሚመታው የበሬ ቆዳ ሆኖብኝኮ ነው፡፡ እንዴት ከበሬ ቆዳ ተሠርቼ በሬ ሞተ ብዬ ከበሮ ልምታ› አላቸው ይባላል ብለው ተረቱ፡፡

እነ ኦኬሎ ኦኳይ ጥፋተኛ ተባሉ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ መጋቢት 28ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የቀድሞው የጋምቤላ ርዕሰ መስተዳድር ኦኬሎ ኦኳይ እና አብረዋቸው የተከሰሱት ስድስት ተከሳሾች ጥፋተኛ ናቸው ብሎ ውሳኔ አስተላለፈ።ፍርድ ቤቱ የቅጣት አስተያየት ለመስማት ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡

Okello Akuay

በሰኔ ወር 2006ዓ.ም የሽብር ክስ ተመሰርቶባቸው ክሳቸው እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ ኦኳይ በየካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ ለማስተላለፍ ለዛሬ ለሶስተኛ ጊዜ ተቀጥረው ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ዛሬ በችሎት ከተሰየሙት ሶስት ዳኞች መካካል የቀኝ ዳኛ የሆኑት አቶ ሳሙኤል ታደሰ የፍርድቤቱን ውሳኔ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዳኛ ሣሙኤል ታደሰ ወደ አንድ ስዓት በቆየው የፍርድ ውሳኔ ንባባቸው እንዳመለከቱት አቶ ኦኬሎና ስድስቱ ተከሳሾች የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ተንቀሳቅሰዋል፡፡ ከአሜሪካ ገንዘብ በማሰባሰብ እና የሽብር ቡድን ማስተባበራቸውን በንባባቸው ጠቅሰዋል፡፡

አቃቤ ህግ በነኦኬሎ ላይ ከዘረዘራቸው ክሶች መካከል ከኤርትራ መንግስት ጋር የሽብር ድርድር በማድረግ እና ከኦነግ እና ግንቦት 7 አመራሮች ጋር በተለይ ከሞት ፍርደኛው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር መገናኘት እንደሚገኙበት ዳኛ ሳሙኤል አስታውሰዋል፡፡ከዚህም በተጨማሪ ወጣቶችን ለሽብር ተግባር መመልመል፣ ወታደራዊ ስልጠና መስጠት በክሳቸው ላይ መጠቀሱን ዳኛው ተናግረዋል፡፡

ከክስ ንባብ መስማት በኃላ ወደ ሁለት አመት ያህል ፍርድቤት የተመላለሱት እነ ኦኬሎ አኳይ የክስ መቃወሚያ ካቀረቡበት ጊዜ አንስቶ ለውሳኔ እስከተቀጠሩበት ጊዜ ያለው ሂደት በዳኛው ተብራርቶ ቀርቧል፡፡
የእነ ኦኬሎ የክስ መቃወሚያ በፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ መደረጉን እና የተከሰሱበትን ክስ ክደው መከራከራቸውን ያስታወሱት ዳኛ ሳሙኤል በመቀጠል አቃቤህግ ምስክሮቹን አቅርቦ ማሰማቱን አስረደተዋል፡፡
ለወራት ከዘለቀው የምስክሮች መሰማት ሂደት በኃላ ፍርድቤቱ ተከሳሾቹን እንዲከላከሉ መወሰኑን ዳኛው ጠቅሰዋል፡፡ ተከሳሾቹ በምርመራ ወቅት በከፍተኛ ጫና እና ድብደባ ውስጥ እንዳለፉ ማስመዝገባቸውን ዳኛው ጠቁመዋል፡፡

የግራና የቀኙን ክርክር ያዳመጠው እና የቀረቡለትን ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤት በሁሉም ተከሳሾች ላይ የጥፋተኛ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ በሰው እና መማስረጃ የጋምቤላን ክልል ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በመሆን የአመራር ሰጪ ውሳኔዎችን ሲመራ በመቆየቱ አቃቤህግ በሰው እና በማስረጃ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳ ዳኛው በውሳኔው አመልክተዋል፡፡ተከሳሹ በበኩሉ የተከሳሽነት ቃል ከማሰማት በስተቀር መከላከያ ምስክሮችም ይሁን ሰነዶችን አቅርቦ በበቂ ሁኔታ እንዳልተከላከለ ዳኛው ገልፀዋል፡፡
ቀሪዎቹም ተከሳሾች በምርመራ ወቅት ለፖሊስ ቃላቸውን ተገደው ስለመስጠታቸው ያሰረዱ እንጂ የቀረበባቸውን ክስ የሰው ምስክር እና የሰነድ ማስረጃ አቅርበው እንዳልተከላከሉ በዳኛው ተገልጿል፡፡
“[ተከሳሾቹ] ምስክሮቻቸው ማዕከላዊ አብረዋቸው የነበሩ፣ በሌላ ወንጀል ተጠርጥረው ያሉ እና ተዓማኒነታቸው ጥርጣሬ ውስጥ የሚገባ ከመሆኑ በተጨማሪ ከዋናው ክስ እና የክስ ማስረጃ ጋር የማይገናኙ በመሆናቸው ክሳቸውን በደንብ አልተከላከሉም” ሲሉ ዳኛው ገልፀዋል፡፡

ክሱ መታየት ያለበት በፀረ ሽብር አዋጁ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ፍርድቤቱ መርምሮ በአንደኛ ተከሳሽ የተመሰረተው ጋህነን፣ የጋምቤላ ህዝብን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ የሽብር ቡድኖች ጋር የስልጠና ትብብር መጠየቃቸው በአቃቤ ህግ የተረጋገጠ ነው ብለዋል ዳኛው፡፡ ሆኖም ድርጊቱ የአገሪቷን አንድነት የማፈራረስ ሙከራን የሚያቋቁም እንደሆነ የገለፁት ዳኛው በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በፀረ ሽብር አዋጁ ሳይሆን የወንጀል ህጉን 241 በመተላለፋቸው በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህግ 149(1) የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ተናግረዋል፡፡

መጋቢት 28/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት የፍርድ ውሳኔ የተላለፈባቸው ሰባት ሰዎች ሲሆኑ፣ እነዚህም ኦኬሎ አኩዋይ፣ ዴቪድ ኦጅሉ፣ ኡቻል አፒዮ፣ ኡማን ኒኮዮ፣ ኡጅሉ ቻም፣ ኡታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡቡንግ ናቸው፡፡

ምንጭ፡- EHRP

የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት ይከበር!

ዞን 9

Zelalem Kibret

የዜጎች ከሀገር ሀገር የመንቀሳቀስ መብት በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ አባል ሆና በፈረመቻቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለማቀፍ ድንጋጌዎች የተጠበቀ ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 32/1 ላይ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ . . . ከሀገር የመውጣት ነጻነት አለው” በማለት ተደንግጓል፡፡ ኢትዮጵያ ፈራሚ አባል የሆነችበት ‘ዓለም አቀፉ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃልኪዳን’ በበኩሉ ማንኛውም ግለሰብ ሕጋዊ ማዕቀብ ካልተጣለበት በስተቀር ወደፈለገው ቦታ የመንቀሳቀስ ከሀገር መውጣትን የሚጨምር መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡ በኢትዮጵያ ህግም ብቸኛ ገደብ የሚያስቀምጠው የኢምግሬሽን አዋጅ ቁጥር 354/2003 በአንቀጽ 7 ላይ “ማንኛውም ሰው ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ ሊታገድ የሚችለው በሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ሲታዘዝ ብቻ ነው” በማለት የመንቀሳቀስ መብት ገደብን በማያሻማ መልኩ ያስቀምጠዋል፡፡

እንደሚታወሰው የዚህ የጡመራ መድረክ አባል የሆነው ዘላለም ክብረት በወንጀል ተጠርጥሮ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በራሱ ተነሳሽነት ክሱ እንዲቋረጥ በማድረጉ ከማሕሌት ፋንታሁን፣ ከአስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ከኤዶም ካሳዬና ከተስፋለም ወልደየስ ጋር ሐምሌ 01/2007 ከእስር ተፈትቷል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የሕግ አግባብ መሠረት ከሀገር እንዳይወጣ የሚያደርግ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ክልከላም የለበትም፡፡ ይሁንና ሕዳር 05/2008 ዘላለም ለቡድኑ የተበረከተ ሽልማትን ለመቀበል ወደ ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ለማቅናት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቢገኝም የጉዞ ሰነዱ (ፓስፖርቱ) ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ ተከልክሏል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች እንደተገለጸው ጦማሪው የጉዞ ሰነዱ እንዲመለስ እና የመንቀሳቀስ መብቱ እንዲከበር ያደረገው ሙከራ ከመጉላላት በቀር ምንም መፍትሔን አላስገኘም፡፡ እንዲያውም በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ መንግሥታዊ አካል መጥፋቱን ለመታዘብ ችለናል፡፡ በዚህም ምክንያት የተለያዩ ዕድሎችን ተጠቅሞ መማርም ሆነ መሥራት እንዳይችል ሁኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንም ይህንን የመብት ጥሰት ‹ጉዳዩ ከአቅሜ በላይ ነው› በሚል ምክንያት ሊያስቆም አልቻለም፡፡

በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ በታኅሣሥ 01/2008 ዓ.ም. ለትምህርት ወደ አሜሪካ ለመሔድ በሞከረችበት ወቅት የጉዞ ሰነዷን ተቀምታ ከሐገር መውጣት እንደማትችል የተነገራት ሲሆን፤ ለምን የጉዞ ሰነዷን እንደተነጠቀች በተደጋጋሚ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት መምሪያ ጥያቄ ብታቀርብም እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ማግኘት አልቻለችም፡፡

እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በጥር 11/2008 ዓ.ም. ወደ ጀርመን ሃገር ለስድስት ሳምንታት የጋዜጠኝነት ልምድ ለመቅሰም ያገኘውን አጋጣሚ ለመጠቀም ያደረገው ሙከራም በተመሳሳይ የጉዞ ሰነዱን ያለምንም ሕጋዊ ምክንያት በመነጠቁ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

ይባስ ብሎም ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ ለስድስት ሳምንታት ወደ ጀርመን ሃገር በመሔድ በጀርመኑ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ የቀረበለት የልምድ ልውውጥ ላይ ተሳትፎ ወደ ሃገሩ ሲመለስ በየካቲት 26/2008 ዓ.ም. በተመለሰበት ወቅት ‹ከሃገር እንዴት ልትወጣ ቻልክ› ከሚል ከባድ ዛቻና ማስፈራሪያ ጋር የጉዞ ሰነዱን ሊነጠቅ ችሏል፡፡

ይህንን ሕገ ወጥ ድርጊት ለማረም ሁሉንም ሕጋዊ መንገዶች አሟጠን የምንጠቀም ሲሆን፤ ሕግ አስፈጻሚው አካል ግን ይህንን ስህተቱን ማረም የሚጀምርበት ተጨማሪ ዕድል አግኝቷል፡፡ ዘላለም ክብረት የዘንድሮው The Nelson Mandela Fellowship ወይም በቀድሞው አጠራር Young African Leaders initiative (YALI) አሸናፊ ሆኗል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ ፌሎውሽፕ የአሜሪካው ፕሬዝዳነት ባራክ ኦባማ ወጣት አፍሪካውያን አህጉራቸውን የሚጠቅሙ መሪዎች እንዲሆኑ የሚያግዛቸውን ክህሎት እንዲጨብጡ በማሰብ እ.ኤ.አ. 2010 ይፋ ያደረጉት መርሐ-ግብር ሲሆን፤ በዚህ ስድስት ሳምንታት በሚፈጀው መርሐ-ግብር በየዓመቱ በርካታ አፍሪካውያን ለራሳቸውም ለአህጉራቸውም ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት ገብይተው ተመልሰዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር አሸናፊ የሆኑት ሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ዘላለም ክብረት በመጋቢት እና ሚያዝያ ወር ቅድመ ሁኔታዎችን አሟልተው በሰኔ አጋማሽ ወደ አሜሪካ እንደሚያቀኑ የመርሐ-ግብሩ የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል፡፡

እኛም ከጊዜ ወደ ጊዜ ጉዳዩ ሕጋዊ መልክ ይይዛልና ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም ነገሮች ግን እየተባባሱ እና የመብት ጥሰቱም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይሄም ድርጊት ዜጎች በሃገራቸው ሕግን አምነው ለመኖር አለመቻላቸው ማሳያም ነው፡፡ በመሆኑም የሚመለከተው የአስፈጻሚ አካል ያለምንም የሕግ አግባብ የጉዞ ሰነዳቸውን ተቀምተው የሚገኙ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች መብታቸው ተከብሮላቸው የጉዞ ሰነዶቻቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱላቸው እንዲያደርግ እና የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንጠይቃለን፡፡

ሕገ መንግሥቱ ይከበር!

ምንጭ፡ https://www.facebook.com/Zone9ers/?fref=nf

በኦሮሚያ ለግጭት ምክንያት የነበረው የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ

በውድነህ ዘነበ

Fekadu Tesema,Oromia PR

በኦሮሚያ ክልል ሕዝባዊ ጥያቄ የተነሳበት የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ፡፡ እነዚህ አወዛጋቢ የተባሉ አንቀጾች ከተሰረዙ በኋላ ባለፈው ሳምንት የተሰበሰበው ጨፌ ኦሮሚያ አዋጁን አፅድቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ተነስቶ ለነበረው ረብሻ የአዲስ አበባና ዙሪያዋ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንና የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ምክንያት እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የማስተር ፕላኑን ተግባራዊነት ማቆሙን በወቅቱ በይፋ የገለጸ ሲሆን፣ ለውዝግቡ መባባስ ምክንያት የነበሩ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች እንዲሰረዙ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተሰረዙት ሦስት አንቀጾች ከተሞችን መቀላቀል፣ የተቀላቀሉ ከተሞች ስያሜና ራዲዮ ፖሊ (የክልሉን ትልልቅ ከተሞች በተመለከተ) የሚያትቱ ናቸው፡፡ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ አንድ የክልሉ ከተማ በዙሪያው ካሉት አነስተኛ ከተሞችን (ሳተላይት) በመያዝ እንደ አዲስ ይደራጃል ይላል፡፡
ለፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆነው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ ያሉ ከተሞችን ከአዲስ አበባ (ፊንፊኔ) ጋር ለመቀላቀል ነው የሚሉ ግምቶችን ከተለያዩ ወገኖች በመስጠቱ ነው ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል የክልሉ ከተሞች ሲቀላቀሉ አንድ ስም የግድ ይመርጣሉ፡፡ ይህ ሁኔታ የክልሉን ታሪክና ባህል ያጠፋል፣ ልዩ ዞኑን ከአዲስ አበባ ጋር ለመቀላቀል ያለመ ነው የሚል ትንታኔ አሁንም በመስጠቱ ለችግሩ መንስዔ ነው ተብሏል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የተቀመጠው የራዲዮ ፖሊ ትንታኔ ነው፡፡ የአገሪቱ መዲና አዲስ አበባ የፌዴራል መንግሥት ከተማ ነች፡፡ የክልል ከተሞች ባህር ዳር፣ መቐለ፣ ሐዋሳ፣ ጅማ፣ አዳማና የመሳሰሉት ከተሞች በራዲዮ ፖሊ ምድብ ይገኛሉ፡፡
የፌዴራል መንግሥት ባወጣው የከተሞች ፖሊሲ ራዲዮ ፖሊ ከተሞች ከፌዴራል መንግሥት ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ታቅዷል፡፡

የኦሮሚያ ክልል በከተሞች አዋጅ ላይ ስለ ከተሞቹ የገለጸ ሲሆን፣ ለዚህ ጉዳይ ከተለያዩ ወገኖች የተሰጠው ምላሽ ግን የኦሮሚያ ከተሞች በፌዴራል ሥር ሊገቡ ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሦስት ጉዳዮች በኦሮሚያ ተከስቶ ለነበረው ደም አፋሳሽ ግጭት መንስዔ እንደነበሩ ተገልጿል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊና የካቢኔ አባል አቶ ፈቃዱ ተሰማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ሕዝብ ጥያቄ በማንሳቱና የኦሮሚያ መንግሥት ሕዝብ የማይስማማበትን አንቀጾቹን ከአዋጁ ውስጥ ፍቆታል፡፡

አቶ ፈቃዱ ‹‹እነዚህ አንቀጾች ጉዳት ኖሯቸው ሳይሆን ፅንፈኞች በአሉታዊ መንገድ ጉዳዩን እጅግ ያስተጋቡት በመሆኑና እኛ ደግሞ በተገቢው መንገድ ግልጽነት ስላልፈጠርን የተፈጠረው ብዥታ ከፍተኛ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እነዚህ ጉዳዮች የሕዝቡን ጥቅም የሚጎዱ ሆነው አይደለም፤›› በማለት ክልሉ ሐሳቡ የሕዝብ እስከሆነ ድረስ የሕዝብን ጥያቄ እንደሚቀበለው አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡

እነዚህ አንቀጾች ከመሰረዛቸው በተጨማሪ በሌሎች ሁለት ጉዳዮች ላይ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡ ፀድቆ በነበረው የከተሞች አዋጅ የክልሉ ከተሞች የሚሰበስቡትን ፋይናንስ ለራሳቸው ይጠቀማሉ የሚል አንቀጽ ነበር፡፡ ነገር ግን ገቢ የማመንጨት አቅም የሌላቸውን ከተሞች ስለሚጎዳ፣ በማዕከል ደረጃ በጀት ቢከፋፈል የተሻለ መሆኑ ስለታመነበት ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ቀደም ሲል በክልሉ ከተሞች በላይኛው የአስተዳደር እርከንና በቀበሌ መካከል ራሱን የቻለ የመንግሥት መዋቅር አልነበረም፡፡ ቀደም ብሎ ፀድቆ በነበረው አዋጅ የወረዳ መዋቅር እንዲከፈት ተደንግጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከወረዳ ይልቅ ክፍለ ከተማ የተሻለ መዋቅር ነው ተብሎ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸው፣ ትልልቅ ከተሞች የክፍለ ከተማ መዋቅር እንዲመሠርቱ በአዲሱ አዋጅ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

COINTELPRO: ተቃዋሚዎችን የመከፋፈያ ቀላል ዘዴ (ከአሜሪካ የተኮረጀ)

Befekadu Hailu

በፈቃዱ ኃይሉ

ይህንን ባለፈው በእንግሊዝኛ ጽፌው «በአማርኛ እና በኦሮምኛ ብትተረጉመው ጥሩ ነው» ተብዬ ነበር። በአማርኛ ይኸው፤ አፋን ኦሮሞ የምትችሉ ተርጉሙት።

ጋዜጠኛ ‪#‎እስክንድር_ነጋ‬ ነበር የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ልጠይቀው ቃሊቲ እስር ቤት ስሄድ ኮኢንቴልፕሮ (COINTELPRO) ስለሚባለው ነገር መጀመሪያ የነገረኝ። ቃሉ የአሜሪካ ፌዴራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ካውንተር ኢንተሊጀንስ ፕሮግራም ባጭሩ ሲጻፍ የተፈጠረ ነው። ፕሮግራሙ ድብቅ፣ አንዳንዴ ሕገ ወጥ፣ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ድርጅቶችን የመሰለል፣ ውስጣቸው ሰርጎ የመግባት፣ ተአማኒነት የማሳጣት እና የማስተጓጎል ተከታታይ ፕሮግራም ነው። ይህንን ጉዳይ አሁን ማንሳት ያስፈለገኝ ሰማያዊ ፓርቲ፣ እንደብዙዎቹ ከጨዋታ ውጪ እንደተደረጉ ፓርቲዎች በፈተና ውስጥ እያለፈ በመሆኑና ይህም የተቀናጀ ሴራ ውጤት ሊሆን ይችላል ብዬ መጠርጠሬ ነው።

«ማጋለጥ፣ ማስተጓጎል፣ ተአማኒነት ማሳጣት፣ ዝም ማሰኘት አሊያም ማጥፋት» ~ በወቅቱ የኤፍቢአይ ዳይሬክተር – ኤድጋር ሁቨር ለአንድ የኤፍቢአይ ኤጀንት የተሰጠ ትዕዛዝ ነው።
በዚህ መንገድ፣ ኤፍቢአይ በከፊልም ቢሆን የጥቁሮች የዕኩል መብት ጥያቄን፣ የፀረ-ቪየትናም ጦርነት እንቅስቃሴን እና ፀረ-ቅኝ ግዛት ድርጅቶችን አዳክሟል። በማልኮም ኤክስ እና በኤልያስ መሐመድ መካከል ያለውን አለመግባባት ኤፍቢአይ ማልኮም እንዲገደል በማድረግ ፕሮግራሙን ተጠቅሞበታል የሚሉ አሉ፤ ባይጠቀምበት እንኳ መረጃው እየደረሰው ዝም ብሏል።

በተመራማሪዎች እንደተሰበሰው ከሆነ፣ ኮኢንቴልፕሮ በመንግሥት ያልተፈለጉ እንቅስቃሴዎችን እና ድርጅቶችን የሚያስተጓጉልበት የተለያዩ ተግባራት (functions) እና ቅርፆች (forms) አሉት። ዴቪድ ካኒንንግሃም የዘረዘሩትን እነሆ፣
ተግባራት፣
1) መጥፎ ገፅታ መስጠት፤
2) ውስጣዊ አደረጃጀትን መሰባበር፤
3) በቡድኖች መካከል የርስበርስ ቅራኔ መፍጠር፤
4) ቡድኑ ለእንቅስቃሴው የሚረዱት ነገሮችን እንዳያገኝ መገደብ፤
5) የመቃወም አቅምን መገደብ፤
6) የተመረጡ ግለሰቦች እንቅስቃሴውን እንዳይቀላቀሉ ማድረግ፤
7) ግጭቶችን ማስቀየስ፤ እና
8) ስለላ ናቸው።
ቅርፆች
A) ምንጫቸው ያልታወቁ ደብዳቤዎች መላክ፤
B) በውሸት ማሕተም የተፈረመባቸውን ደብዳቤዎች መላክ፤
C) መጣጥፎችን ለብዙኃን መላክ፤
D) ለባለሥልጣናት መረጃ መስጠት፤
E) የውሸት ማስረጃ መቅበር፤
F) መረጃ ሰጪዎች መመልመል፤
G) ሚዲያዎችን መጠቀም፤
H) ኤፍቢአይ ያዘጋጃቸውን መረጃዎች ማሰራጨት፤
I) ለተመረጡ ሰዎች ቃለመጠይቅ ማድረግ፤
J) የተሳሳተ መረጃ መስጠት፤
K) የውሸት የስልክ ጥሪዎችን ማድረግ፤
L) ያለማቋረጥ ክትትልና ጥቃት ማድረግ፤
M) ለተቀናቃኞቻቸው ድጋፍ መስጠት፤ እና
N) ሥም አጥፊ መረጃዎችን መላክ።

(እነዚህ ሁሉ ተቃዋሚዎችን የማስተጓጎል ሙከራዎች በኢትዮጵያ ታይተዋል።)
የዚህ አጭር ማስታወሻ ዓላማ ዴሞክራሲያዊ የሆኑት አገሮች ሳይቀሩ ምን ያህል ተቀናቃኞቻቸውን ለማጥፋት እንደሚጓዙ ማስረዳት ነው። ኮኢንቴልፕሮ ከኤፕሪል 1971 ጀምሮ፣ በተግባር 15 ዓመት ከቆየ በኋላ፣ በይፋ ተዘግቷል። ነገር ግን፣ እንደኢትዮጵያ ላሉት ጨቋኝ መንግሥታት ትምህርት ሰጥቶ አልፏል። የፖለቲካ ፓርቲዎች እና አክቲቪስቶች መንግሥታቸው እነዚህን ሴራዎች እንደሚሸርብባቸው አውቀው ግብረመልስ ካዘጋጁ [ብቻ] በትግሉ ያሸንፋሉ።