Nine Ethiopian Journalists and bloggers were arrested

The journalists and bloggers were arrested by Ethiopian government on April 25-26, 2014. The journalists Asmamaw Hailegiorgis,  Tesfalem Woldeyes and Edom Kssaye from Addis Guday and Addis Standard magazine  respectively arrested. As the same time, 7 Ethiopian zone 9 bloggers and activists were also arrested.

zonThe bloggers and activists Befekadu Hailu, Atnaf Birhan, Mahlet Fantahun, Natnael Feleke, Abel Wabela and Zelalem Kibret   arrested at Maikelawi criminal investigation bureau of Addis Ababa police but still no charge at court related with them.

 

 

የኢትዮጵያ እውነታ እና ቀጣይ ዕጣ ፈንታ

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

ኢትዮጵያን በገሃዱ ዓለም ላያትና በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ለተመለከታት እራሱን በሁለት የተለያየ ዓለም ውስጥ ሆኖ ያገኘዋል፡፡ ለዚህም በኢቴቪ የሚመለከቷት ኢትዮጵያ አረንጓዴ፣ ለምለም የጥጋብ ምድር፣ የህዝቡን ኑሮ እየቀየሩ ያሉ የተንቆጠቆጡ ህንፃዎች፣ መንግስት በፈጠረላቸው ምቹ ሁኔታ የበለፀጉ ምንዱባንን፣የተለያዩ በስኬት በተጠናቀቁ የልማት ፕሮጀክቶች የሚደሰቱ ነዋሪዎች፣የገዥው ፓርቲ ታታሪነትና የሌሎች ተፎካካሪ ፓርቲዎች ድክመት፣…ይመለከታሉ፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ኢትዮጵያዊነት ሁሉ ፈተና ውስጥ የገባበት ዓይነት ሁኔታንም መመልከት እተለመደ መጥቷል፡፡
በገሃዱ ዓለም ያለው ትክክለኛው ኢትዮጵያ እውነታን ለተመለከተና እየተመለከተ ላለ ከላይ ከተጠቀሰው በእጅጉ ይለያል፡፡ ምንም እንኳ አብዛኞቹ የህንፃ ባለቤቶች የገዥው ስርዓት ቁንጮዎች፤ በተለይ በአዲስ አበባ የህወሓት ቁልፍ ሰዎች ንብረት ሲሆን አልፎ አልፎ ግን የስርዓቱ ታማኝ እና የነባር ነጋዴዎችም ህንፃ መኖሩ ባይካድም፡፡ የሀገሪቱም የኑሮ ምቾትና ዕድገት እየተለካ ያለውም የህዝብን ሀብት በሙስና በሚበዘብዙ ባለስልጣናትና ከላይ በተጠቀሱ ነጋዴዎች ልኬት ነው፡፡
በተለይም አሁን ያለውን የአብዛኛውን ኢትዮጵያዊ ነባራዊ ሁኔታ የተመለከትን እንደሆነ፤ በህልም ዓለም ተስፋ ውስጥ የሚዋኝ አካልን መመልከት አዲሰ አይደለም፤ ብሩ ቀንን በመናፈቅ፡፡ ከዛ ውጭ በስደት ዓለም ባሉ ቤተሰቦቻቸው ድጎማ ህይወታቸውንእያቆዩ ያሉትን እንደ ዕድለኛ በመቁጠር፡፡በርግጥ የመንገድ መሰረተልማት ጥገናዎች እየተከናወኑ ነው፤ አንድ ፖለቲካና ኢኮኖሚ ጠንካራ ማኀበረሰብ የመመስረት የፍቅር መንገድ ባይገነባም ቀድሞየነበረውን ፍቅርና አንድነት ለማፍረስ የሚወጣው ወጪ፣የሚባክነው ጊዜና ጉልበት ሲሰላ ብዙ ውጤታማ የማኀበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶችን መገንባት ይቻል ነበር፡፡
ቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ተሻለ ቀንን በጨለመ ተስፋ ውስጥ ሆኖ፤ ግማሹ በአስከፊው የሞት መንገድ የእግር ስደትን ምርጫው አድርጓል፡፡ በእግር ከሚሰደዱት ደግሞ ብዙዎቹ መንገድ ላይ ህይወታቸው ሲያልፍ፣ የቀሩት ግን እጅግ ከዘግናኝ ፈተና በኋላ ያሰቡበት ይደርሳሉ፡፡ የUNCHR መረጃዎች እና የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ፤እያየሁ ከምሞት በተስፋ እየተጓዝኩ ልሙት በሚል ምሬት አሁንም የስደተኞች ቁጥር በእጅጉን ጨምሯል፡፡ በየሄዱበት ሀገርም ጥገኝነት ከመጠየቅ ለዘመናት ያለምንም ስራ ፈቃድ ተደብቆ ቀናትን እስከማሳለፍ ድረስ፡፡ የዚህ ሁሉ መሰረቱ ደግሞ ያለው የፖለቲካ ስርዓት ውጤት መሆኑ ከማንም የሚደበቅ አይደለም፡፡ በአሁን ሰዓት በሀገሪቱ በተለያየ አቅጣጫዎች ቀን የሚጠብቁ የታመቁ ስሜቶች በስፋት እየተስተዋሉ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በመላ ሀገሪቱ ከፍተኛ ውጥረት እየተፈጠረ ሲሆን ፤ከወዲሁ በሁሉም ባለድርሻ አካል መፍትሄ ካልተበጀለት ነገ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ደግሞ ከወዲሁ መገመት አያስቸግርም፡፡ በተለይ የማኀበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ቀውሶች ተባብሰው መቀጠላቸው ችግሮችን የበለጠ ውስብስብ አድርጎታል፡፡

ማኀበራዊ ሁኔታ

በአሁን ወቅት በተለያየ የሀገሪቱ አካባቢ የማኀበራዊ ቀውስ ችግሮች ይታያለሁ፡፡ ከነዚህም መካከል ዜጎች የመኖሪያ ቤትም ሆነ የመኖሪያ ቤት የመስሪያ ቦታን ለማግኘት እንደድሮ ኢትዮጵያዊ ዜግነት መኖር ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ከዜግነት ይልቅ የገዥው ፓርቲ አባል ወይንም ዋነኛ ደገፊ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ አለበለዚያ መሬት የመንግስት ነው በሚል ፈሊጥ መንግስት ማን እንደሆነ እንኳ ለመለየት አስቸጋሪ በሆነበት በዚህ ወቅት እጅግ ውድ በሆነ የሊዝ (የመሬት ኪራይ) ክፍያ ማዘጋጀትን ይጠይቃል፤ይሄ ደግሞ ሀገር ውስጥ ለሚኳትን ኢትዮጵያዊ በቀላሉ የሚሞከር አይደለም፡፡pic3
ከመጠለያ በመቀጠል የጤና ዋስትና ጉዳይም እንዲሁ ከዕለት ወደዕለት እየተባባሰ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋነኛ ምክንያት የባለሙያዎች ለህዝቡ ያላቸው ተደራሽነት አነስተኛ መሆን እና በሙያው በቂ ክህሎትአለመኖር፣ በበቂ ሁኔታ የህክምና ቁሳቁስ በየህዝብ ህክምና ተቋማት በበቂ ሁኔታ አለመኖር ዋነኛው ችግር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሐኪሞች በሙያቸው ከተመረቁ በኋላ ለሚሰጡት አገልግሎት ተመጣጣን ክፍያ አለማግኘት ፣ በጤና ተቋማት በቂ የውሃ፣ የመብራትና ተያያዥ ግብዓቶች በበቂ ሁኔታ አለመኖር ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ እነኝህ ችግሮች እያሉ እንኳ መንግስት በጤና ሽፋን እና አገልግሎት ውጤታማ ነኝ ይላል፡፡ እውነታው ግን በየጊዜው ከህክምና ጋር በሚፈጠሩ ችግሮች የሚሞቱ ህፃናትና እናቶችን ቁጥር ቀንሰናል በሚል የመረጃ መጋገር በስተቀር ችግሩ አሁንም እንዳለ ነው፡፡
በየቀበሌው የተለያዩ አነስተኛ የጤናአገልግሎት መስጫ ተቋማት መገንባታቸው በአዎንታዊ ጎን የሚታይ ቢሆንም፤ ከቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት በስተቀር አገልግሎት ሰጪ ባለሙያዎች ላይ እና የህክምና መገልገያ መሳሪያዎች ላይ በቀላሉ መሻሻል የሚገባቸው በርካታ ችግሮች ይስተዋላሉ፡፡ በዕርዳታ የመጡ የህክምና መገልገያ ማሽኖች እንኳ ገና ስራ ሳይጀምሩ ተበላሽተዋል ተብለው የትና መቼ እንዲሁም ለማን አገልግሎት እንደሚሰጡ የማይታወቅበት ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡ ለዚህም በሀገሪቱ ትልቁ ሆስፒታል ጥቁር አንበሳ የነበሩ የኩላሊት ማጠበያ ማሽን፣ የካንሰር ምርመራ እና ህክምና ፣ ፊዚዮቴራፒ እና ሲቲስካን የት እንዳሉ አይታወቁም፤ ዜጎች ግን በከፍተኛ ወጪ ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ይታከማሉ፤አቅሙ የሌላቸው ደግሞ መኖር አየቻሉ ህይወታቸው ያልፋል፡፡ ደረጃቸውን የጠበቁና የአገልግሎት መቆያ ጊዜያቸውተጠበቀ መድኃኒቶች አለመኖርና አገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸው ምንም ለማያውቁ ታካሚዎች እየተሸጠ መሆኑም ሌላው ራስ ምታት ነው፡፡
የኃይማኖት ነፃነት ማጣት ጉዳይም በሰፊው እየታየ ያለ አንዱ የማኀበራዊ ቀውስ ክስተት ነው፡፡ ለዚህም በኢትዮጵያ ሙስሊሞች እና ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስቲያኖች ላይ በተደጋጋሚ እየተፈፀመ ያለው የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ሀገሪቱን ውጥረት ውስጥ መክተቱ አልቀረም፡፡ በተለይ ገዥው ስርዓት በሁሉም ኃይማኖቶች መሪዎች የኢህአዴግ ሰዎች እንዲሆኑለማድረግ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ከኃይማኖቱ ተካታዮች ቅሬታ ቢፈጥርምይህንን በግልፅ ተቃውሞ የጀመሩት ግን ሙስሊሞች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ተያያዥ ችግሮች እስካሁን ችግሩ አልተፈቱም፤በተለይ የሙስሊሙ ማበረሰብ ጥያቄው ባለመመለሱ ተቃውሞውእንደቀጠለ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ጭራሽ ከመንግስት የማይጠበቅ ሙስሊሙን እና ክርስቲያኑን ሊያጋጩ የሚችሉ እንደ “ጅሃዳዊ ሃረካት” የመሳሰሉ የተለያዩ ዘጋፊ ፊልሞች ተሰርተው በኢቴቪ በመሰራጨት ህዝቡን ስጋት ውስጥ ቢጥሉም፤ በክርስት እና በእስልምና ኃይማኖት ተከታዮች መካከል የነበረውን ኢትዮጵያዊ አንድነት ለመፈታተን እየተሞከረ ይገኛል፡፡ ምንም እንኳ በኃይማኖቱ ተከታዮች ተቀባይነት ባይኖረውም፡፡
የትምህርት ጥራት በተለይም እንደቀድሞው በሀገር አቀፍም ሆነ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆኑ ተማሪዎችን የማፍራት ዕድሉ ቢኖርም ስርዓቱ በዘርፉ የሚከተለው ፖሊሲ እውን ሊያደርግ አልቻለም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በየከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የአካዳሚክ ነፃነት መጥፋት እና በማስተማርም ሆነ በአስተዳደራዊው ዘርፍ የስርዓቱ ታማኞች ብቻ እንዲኖሩ የሚደረገው ጥረት ደግሞ የትምህርት ጥራቱን በመጉዳቱ የሚፈለገውን ውጤታማ የተማረ ኃይል ማፍራት እንደሎተሪ የሚቆጠርበት ጊዜ ተደርሷል፡፡ በዚህም ምክንያት ለዓመታት ለፍተው በየዓመቱ ከተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚመረቁ ተማሪዎች ስራ አጥ ሆነው መኳተናቸው እና ለድንጋይ ጠረባ መታጨታቸው ፖሊሲውና ስርዓቱ የፈጠሩት ችግር ለመሆኑ ምስክር አያሻም፡፡
በሀገሪቱ ያለው የኑሮ ውድነት በተለይም የምግብ ዋጋ መናር፣በቂ የትራንስፖርት አገልግሎት አለመኖር፣ የውሃ፣ መብራት እናየስልክተደጋጋሚ መቋረጥ እና ተደራሽነት በአግባቡ አለመኖር ሌላው ችግር ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ዜጎች እርስ በርስ በችግሮቻቸው ዙሪያ እንኳ እንዳይወያዩ እና መፍትሄ እንዳያበጁ አንድ ለአምስት በሚል ሁሉም ዜጋ በኢህአዴግ ጥብቅ ቁጥጥር ስር እንዲሆን ተደርጓል፤ እየተደረገም ነው፡፡ ዕድሮችና የኃይማኖት ተቋማት ከማኀበራዊ አገልግሎት ይልቅ የገዥው ስርዓት ፖለቲካ ማራመጃ እስከመሆን በመድረሳቸው የተቋቋሙለትን ዓላማ በመሳት ህዝባዊ አመኔታ በማሳጣት እና ጥርጣሬ በመፍጠር ዜጎችን እሴት አልባ የማድረግ ማኀበራዊ ቀውስ ተፈጥሯል፡፡

የኢኮኖሚ ሁኔታ

የሀገሪቱ የንግድ ስርዓትና ገበያ በጥቂት ግለሰቦች እና ድርጅቶች በመውደቁ የኢኮኖሚውን መስክ አደጋ ላይ ጥሎታል፡፡ እዚህ ላይ ትውልደ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ግን ሳውዲዓረቢያዊ የሆኑትሼህ መሐመድ ሁሴን አሊ ዓላሙዲን ብንመለከት የኢህአዴግ ቀኝ እጅ ሲሆኑ፤ ከሀገሪቱ ባንክ ከፍተኛው ብድር የተሰጣቸው ግለሰብም ናቸው፡፡ይሁን እንጂ በግለሰብ ደረጃ በርካታ ቦታዎችንና የተፈጥሮ ሃብቶችን ሆን ተብሎ ከዜጎች ተነጥቆ ግለሰቡ በሞኖፖል እንዲዙ ተደርጓል፡፡ ነገር ግን ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በብድር መልክ የወሰዱትን ከፍተና ብድር በአግባቡና በወቅቱ እንዳልመለሱ ቢነገርም የተወሰደ እርምጃ ግን የለም፡፡
ሌሎች ከስርዓቱ ጋር ድንገት ብቅ ያሉ በተለይ የህወሓት ልዩ ጥበቃና ድጋፍ የሚደረግላቸው በርካታ ግለሰቦችም ድንገት ከሰማይ እንደወረደ የተሰጣቸው ምንጩ ባልታወቀ ሃብት በአንዴ የህዝብን ኑሮ በመፈታተን የኢኮኖሚ ቀውስ እንዲፈጠር ዋነኛ ምክንያት ሆነዋል፡፡
በድርጅት ደረጃ የተመለከትን እንደሆነ ደግሞ የገዥው ኢህአዴግ የንግድ ድርጅቶች የሆኑት የህወሓቱ ኤፈርት፣ የኦህዴዱ ዲንሾ፣ የብአዴኑ ጥረት እና የደኢህዴኑ ወንዶ የተባሉ ግዙፍ የንግድ ኩባንያዎች የሀገሪቱን የገበያ ስርዓት በማወክ ከዚህ ቀደም ዜጎች በአግባቡ ሲያገለግሉ ነበሩና የተረጋጋ የንግድ ስርዓት የፈጠሩት በርካታ ነጋዴዎች ከገበያ ውጭ እንዲሆኑ ተደርጓል፡፡ ነባር ነጋዴዎችም ከስርዓቱ የንግድ እና የግብር ኢፍትሃዊ ስርዓት በመሸሽ በደቡብ ሱዳን፣ በደቡብ አፍሪካ እና በዱባይ ገንዘባቸውን ማንቀሳቀስ መጀመራቸው የውጭ ባለሃብቶችስ በኢትዮጵያ እንዴት ደፍረው ኢንቨስት ሊያደርጉ እንደሚችሉ ለመገመት ያስቸግራል፡፡
በአነስተኛና መካከለኛ ንግድ የተሰማሩ ግለሰቦች ላ ደግሞ ስርዓቱ የራሴ የሚላቸውን ሰዎች ለማሳደግ ሲል እጅግ የማይመጣጠን ከፍተኛ ግብር በመጣል ከገበያ ውጭ እንዲሆኑ እየተደረገ ሲሆን፤ ችግሩን ተቋቁመው የሚሰሩትም የደህንነት ስጋት እንደተጋረጠባቸው ይነገራል፡፡ በዚህም ነጋዴው በራሱ ላይ የሚፈጠረውን ችግር በቀጥታ ወደ ሸማቹ ህብረተሰብ ማውረዱ አልቀረም፡፡pic2
በተለይ በአሁን ወቅት እጅግ ፈተኛ በሆነ ወቅት ከዓለም ገበያ ዋጋ ጋር ባልተመጣጠነ መልኩ ከጎረቤት ሱዳን በቅርብ ርቀት ተጉዞ የሚመጣው ነዳጅ በየጊዜው ከፍተኛ የዋጋ እየተደረገ ሲሆን ፤ይህም በቀጥታ የሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ የራሱ የሆነ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳርፏል፡፡ መንግስት ነዳጅ ላይ ለረጅም ዘመናት ሲደረግ የነበረውን ድጎማ ከማንሳቱ በተጨማሪ ሌላ ዋጋ መጨመሩ እስካሁን እንቆቅልሽ ሆኗል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ በአንበሳ የከተማ አውቶብስ ላይ እንኳ በአንዴ እስከ 25 ሳንቲም ጭማሪ ተደርጓል፡፡ በቤት ፍጆታ፣ በአገር አቋራጭ፣ በጭነት እና በከተማ የታክሲ አገልግሎት ላይ ከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ ደግሞ ሌላው ችግር ነው፡፡
የሸቀጦች ዋጋ በየጊዜው መጨመር ደግሞ የበለጠ በኢትዮጵያ ላይ መኖር እጅግ ከባድ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ የነኚህ ድምር ውጤት በመላ ሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አለመረጋጋትን ፈጥሯል፡፡ በዚህም ምክንያት ዜጎች በቀን አንዴ መመገብን እንደመልካም አጋጣሚ የሚቆጥሩ ዜጎች መኖራቸው ሀገሪቱ በገሃዱ ዓለም ወዴት እየሄደች እንደሆነ ለማወቅ የግድ ሊቅ መሆንን አይጠይቅም፡፡ በተለይ እ.አ.አ.በ2013 ዓለም አቀፍ ጥናቶች እንሳታወቁት ከሆነ፤ዜጎቿ በቂ እና የተመጣጠነ ምግብ ከማያገኙ የዓለም ሀገሮች መካከል ኢትዮጵያውያ አንዲትን ሀገር ብቻ በመቅደም የመጨረሻ ደረጃ ላይ የምትገኝ አድርጓታል፡፡ ስለዚህ በምግብ እንኳ ዜጎች እራሳቸውን እንዲችሉ እየተደረገ ያለው አሰራር በ23 ዓመታት እንኳ ውጤታማ አለመሆኑ ዋነኛ የፖሊሲ ችግር መሆኑን ያመላክታል፡፡

የፖለቲካ አለመረጋጋት

ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ሞት በኋላ በገዥው ስርዓት ባሉ ፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል አለመረጋጋትመፈጠሩ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ መንገድ ዜጎችም በፖለቲካ ህይወታቸው እንዳይረጋጉ መደረጉ ሀገሪቱን ከድጡ ወደማጡ ወስዶታል፡፡ ይህን ተከትሎ የገዥው አመራሮች ተፎካካሪያቸውም ላይ ሆነ ችግሮቻቸውን የሚናገሩትን እንደጠላት በመቁጠር የነበረውን አለመረጋጋት ይበልጥ አባብሶታል፡፡ በአሁን ሰዓት አይታወቅም፤አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን መንበር ቢቆናጠጡም፤ በተግባር ሀገሪቱን በትክክልም ማን እየመራት እንደሆነ በርግጠኝነት መናገር ይከብዳል፡፡ በዚህም ስርዓቱ ወይም መለኮት አሊያም አየር እስኪመስል ድረስ ሁለት እና ከዛ በላይ ሆናችሁ በምታደርጉት እንቅስቃሴ ሁሉ እኔም እገኛለሁ/መገኘት አለብኝ ዓይነት አስተሳሰብ ተፀናውቶት ዜጎችን መፈናፈኛ አሳጥቷቸዋል፡፡ ይሄም በኢትዮጵያ ሌላ ዘግናኝና የአፈና ስርዓት መንገሱን ያሳያል፡፡
ስርዓቱን የሚዘውሩትም ቢሆኑ መሰረታቸውበጠባብ ፖለቲካዊ ዘረኝነት ቡድን ላይ የተንጠለጠለ በመሆኑ፤በተለይ ወጣቶች በሀገር አቀፍም ሆነ በዓለም አቀፍ እንኳ ተወዳዳሪ ሆነው እንዳይታዩ በቅድሚያ በዘርና በቋንቋ በመከፋፈል የኢትዮጵያዊነት ስነልቦናውንጎድተውታል፡፡ በዚህም ምክንያት ወጣቱ እራሱን አጥብቦ በብሔር ስም በጠባብ ወሰን ውስጥ እንዲቀር በማድረጉ ተወዳዳሪ መሆን ያልቻሉ በርካታ ወጣቶች ቢመረቁም አብዛኞቹ ስራ አጥ ናቸው፡፡ ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ የስርዓቱ ጠባቂና አቀንቃኝ አንድ የወረዳ አስተዳደር ከውሎ አበል ውጭ እስከ 4,000 ብር ወርሃዊ ደመወዝ ሲከፈለው ለበርካታ ዓመታት ተምሮ ዜጎችን የሚቀርፅ አንድ ፕሮፌሰር ደመወዝ ደግሞ ያለምንም የቀን ውሎ አበል ወርሃዊ ደመወዙ ከ5,000 ብር አይበልጥም፡፡ 7 ዓመታትን በትምህርት ያሳለፉ የህክምና ተማሪዎችም ያለምንም ውሎ አበል ወርሃዊ ደመወዛቸው በአማካይ ከ3,000 ብር አይበልጥም፡፡
በተለይ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያውያን የህክምና ዶክተሮች ከ4,400 እንደማይበልጡ፤ ከነዚህም ውስጥ በሀገር ውስጥ ለ90 ሚሊዮን ህዝብ አገልግሎት እየሰጡ ያሉት ከ700 እንደማይበልጡ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ ቀሪዎቹ 3,700 ዶክተሮች የፖለቲካውና በኢኮኖሚው ጫና ምክንያት በስደት እየኖሩ ይገኛሉ፡፡
ዜጎች በፖለቲካዊ አመለካከታቸው አሸባሪ የሚል ቅፅል ስም እየተሰጣቸው በእስር የሚማቅቁ በርካቶች ሲሆኑ፤ የወጣቶች ቁጥር ደግሞ አብላጫውን አሀዝ ይይዛል፡፡ በዚህም ምክንያት ብልሹ አሰራርን እና በዜጎች መካከል የሚፈጠር አድሎዓዊ አሰራርን የሚቃወሙ፣ በህግ የተሰጠ እና ተፈጥሯዊ መብቶች ለዜጎች እንዲከበሩ አበክረው የሚጠይቁና የጠየቁ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ከነዚህም መካከል ከጋዜጠኞች እስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ሰለሞን ከበደ እና ዩሱፍ ጌታቸውን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከፖለቲከኞች ደግሞ አንዱዓለም አራጌ፣ በቀለ ገርባ (የእስር ጊዜው ቢጠናቀቅም እስካሁን ያልተፈታ)፣ ናትናኤል መኮንን፣ ኦልባና ሌሊሳን በጥቂቱ ማንሳት ይቻላል፡፡pic1
በቅርቡ ደግሞ መጪውን ምርጫ 2007ዓ.ም. ታሳቢ በማድረግ በሰፊው የነፃውፕሬስ ጋዜጠኞችን እና ፖለቲካኞችን ለማሰር አሊያም ለመወንጀል በህዝብ ግብር በሚተዳደሩ መገናኛ ብዙኃን ማስፈራሪያውና ዛቻው ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በሌላው የዓለም ሀገር የህዝባዊ አስተዳደር ምርጫ የሚደረገው ህዝቡ የሀገሪቱ ከፍተኛ የስልጣን ባለቤቱ መሆኑን ከማረጋገጥ ባለፈ የዜጎችን እስር፣ ግድያ ስደትና ጭንቀት ለመቀነስ ነው፡፡ በአንፃሩ በኢትዮጵያ ምርጫ ሲመጣ ደግሞ በተለይ በገዥው ፓርቲ የሚፈፀም እስር፣ ግድያ፣ ስደት እና ጭንቀት ከሌሎች ግዚያቶች በበለጠ ተጠናክሮ የሚቀጥልበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ለዚህም ከሰሞኑ በገዥው አመራሮችና ዋነኛ የጥቅም ተጋሪ ደጋፊዎቻቸው በአደባባይ የሌለውን እና ያልተፈጠረውን የቀለም አብዮት በሚል ዲስኩር የሚፈፀሙ ማስፈራሪያዎች እና ዛቻዎች ምርጫ 2007 ዓ.ም. ከመድረሱ በፊት ሊወሰድ ስለታሰበው እኩይ ተግባር አመላካች ነው፡፡ ስለዚህ ንፁሃን ዜጎች በምርጫ ወቅት በሰበብ አስባቡ የሚታሰሩ፣ የሚገደሉ፣ የሚሰደዱና የሚሰቃዩ ከሆነ ምርጫው ከገንዘብ፣ ከጊዜና ከውድ የሰው ህይወት ብክነት በስተቀር አስፈላጊነት አጠያያቂ ነው፡፡
ከላይ በተጠቀሱት ምክንያቶች በመላ ሀገሪቱ አሁን ያለው የፖለቲካ ድባብ እጅግ ውጥረት የበዛበት፣ ያልተረጋጋና እና አስፈሪ ሁኔታ መኖሩን ከማመላከት በተጨማሪ፤ በገዥው ፓርቲ ባሉ አመራሮች መካከልየራስ መተማመን ስሜት አለመኖሩን እና እርስ በርስ እንኳ አለመተማመን እና አለመረጋጋትንም ያሳያል፡፡ በዚህም ምክንያት በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫዎች የሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉ ታፍኗል በሚል ወደ ትጥቅ ትግል የገቡ አልታጡም፡፡ ለዚህም የትግራዩ ትህዴን፣የአፋሩ አርዱፍ፣ የኦሮሚያው ኦነግ፣ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሉ ኦብነግ፣በደቡብ የሲዳማው ሲአግ፣ በጋምቤላ እና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ያሉትን እና ሌሎች ሀገር አቀፍ የትጥቅ ትግል የሚያደርጉ እንደነ አርበኞች ግንባር እና ግንቦት ሰባትን ማንሳት ይቻላል፡፡
በአጠቃላይ ከሐረሪ ክልል፣ ከድሬዳዋ እና አዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር በስተቀር በሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች የትጥቅ ትግል እየተደረገ ይገኛል፡፡ የዚህ ሁሉ መነሻው ደግሞ በሀገሪቱ ለሁሉም ዜጎች እኩል የሆነ የውድድር መድረክ አለመኖሩ፣ ህዝባዊ ነፃ የመንግስት (ዴሞክራሲያዊ) አስተዳደር አለመኖሩ፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አለመከበር፣ ነፃነትና ገለልተኛ ህዝባዊ ወይም መንግስታዊ የዴሞክራሲ ተቋማት ባለመኖራቸው የተፈጠረ ነው፡፡ ምናልባት የተጠቀሱት ችግሮች አፋጣን መፍትሄ ካላገኙ እና ልክ እንደ ሱዳን ሀገሪቱ ወደ ብሔራዊ እርቅ ካልገባች ውሎ ቢያድርም የታፈነው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደ አደባባይ አመፅ ሊቀየር ይችላል፡፡ አሁን ለው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ደግሞ ሰላማዊ የአደባባይ ህዝባዊ አመፁን በቀላሉ በጦር መሳሪያ ብቻ ለማቆም ቢሞከር እንኳ ካለው አስከፊ ችግር የተነሳ ህዝባዊ አመፁ ተጠናክሮ ከመቀጠል ባለፈ ሊቆም አይችልም፡፡
ሌላው በሀገሪቱ ህግ ተቋቁመው የፖለቲካ ትግል የሚያደርጉ እና እያደረጉ ያሉት ከፍተኛ ዋጋ እየከፈሉ ቢሆንም፤ እርስ በርስ ተስማምተው በሚያሰራቸውቸው አጀንዳ እንኳ አንድ ሆነው መስራት ባለመቻላቸውበሀገሪቱ እና በህዝቡ የነፃነት እንቅስቃሴ ላይ ጥቁር ጥላ ማጥላታቸው አልቀረም፡፡ ምክንያቱም በፖለቲካ ፓርቲዎች ስም በገዥው ስርዓት የሚደገፉ እንዳሉ ሆነው ለህዝብ ቆመናል የሚሉየተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል ያለው የስልጣን ጥም በፈጠረው አለመተማመን እና ጥርጣሬ የራሳቸውንም ሆነ የተከታዮቻቸውን ዕጣ ፈንታቸው እስርና ግድያ ማድረጉ የአደባባይ ምስጢር ነውና፡፡ በአጠቃላይ አሁን ባለው የሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ የማይካድ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማኀበራዊ ቀውስ ተፈጥሯል፡፡ ይሄንንም ለማሻሻል ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከእርስ በርስ ጥላቻ፣ ቂም በቀል፣ጥርጣሬና አለመተማን በመውጣት ፤ሁሉም ኢትዮጵያዊበመፈቃቀርና በመከባበር ለሁሉም ዜጋ መብትና ጥቅም በአንድነት መቆም ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ የህዝቡ ሰቆቃና መከራ እየቀጠለ መጪውን ጊዜ ዕጣ ፈንታ የበለጠ አስከፊና አስፈሪ ያደርገዋል፡፡

 

በሐረር የተከሰተው ተደጋጋሚ የእሳት አደጋ ጥያቄ ማስነሳቱን ቀጥሏል

 

በታሪካዊቷ ሐረር ከተማ ባለፈው ካቲት 30 ቀን 2006 ዓ.ም. በሸዋበር የንግድ ሱቆች ላይ በተደጋጋሚ የደርሰው የእሳት አደጋ የከተማው ነዋሪና የአካባቢው የንግድ ማኀበረሰብ ላይ ከፍተኛ ጥርጣሬ በመፍጠሩ ጥያቄ ማስነሳቱ ዛሬም ቀጥሏል፡፡ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሶስት ጊዜ ሱቆቻቸው የተቃጠለባቸው እና አሁንም ለከፍተኛ ኪሳራ የተዳረጉም እንዳሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የከተማው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ በተደጋጋሚ ስለሚነሳው የእሳት አደጋ ምክንያት አደጋው የደረሰባቸው መንግስት ተገቢውን ጥበቃ አላደረገም በሚል ሰልፍ ከመውጣታቸው ጋር ተያይዞ መንግስት አደጋው ለደረሰባቸው ነጋዴዎች ምን እንዳሰበ በጋዜጠኛ ተጠይቀው፤ ሰልፍ የወጡት የጎዳና ተዳዳሪዎች ናቸው፣እርምጃ እንወስድባቸዋለን ማለታቸው ይበልጥ ቁጣመቀስቀሱን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ምንም እንኳ እስካሁን የእሳት አደጋው መንስኤ ተጣርቶ ይፋ ባይሆንም እንደምንጮች ገለፃ ከሆነ ከተፈጠረው እሳት አደጋ ጀርባ የመንግስት እጅ ሳይኖርበት አይቀርም በሚል የህዝብ ግንኙነቷን መልስ ዋቢ በማድረግ ነዋሪዎቹ ጥርጣሬ እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡hara

በከተማው የንግድ ሱቆች ላይ በተደጋጋሚ እየተከሰተ ስላለው የእሳት አደጋ ጋር በተያያዘ የጠየቅናቸው አቶ አብዱላሂ እንዳሉት ከሆነ፤ አደጋውን የክልሉ ባለስልጣናት ሆን ብለው እንዳደረጉትና መሬቱን ለራሳቸው ሰዎች ለመስጠት አስበው ሊሆን እንደሚችል ጥርጣሬ እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም በምክንያትነት ያነሱት ከአንድ ሺህ ዓመታት በላይ ያስቀጠረችና እና በዓለም ቅርስነት በዩኔስኮ የተመዘገበች ታሪካዊ ከተማ ያውም በንግድ ሱቆች ላይ ተደጋጋሚ የእሳት አደጋ መከሰቱ ከመንግስት ሌላ እጅ ይኖራል ተብሎ አይታሰብም፣ ይህም በከተማው ወደፊት ኢንቨስት ለማድረግ የሚፈልጉ ዜጎችንም ሆነ የውጭ ባለሃብቶች የሚያበራታታ አይደለም ብለዋል፡፡har

በአደጋው እስካሁን በቁጥር ተለይቶ ባይታወቅም እጅግብዙ ንብረቶች መውደማቸውም ተጠቁሟል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ ሙራድ አብዱላሂ በአደጋው ንብረቶቻቸው ለወደመባቸው ነጋዴዎች መንግስት በጀት መመደቡን ማስታወቃቸው የተነገረ ሲሆን፤ አንዳንድ ነጋዴዎች ግን ስለተግባራዊነት ጥርጣሬ እንዳላቸው አልሸሸጉም፡፡

በሆሳዕና ከተማ የመብራት ኃይል ገመድ ተበጥሶ የሰው ህይወት አጠፋ

 

power1በደቡብ ክልል ሆሳዕና ከተማ የኤልክትሪክ ገመድ ተበጥሶ የ13 ዓመት ልጅ ህይወት ማጥፋቱ ተገለፀ፡፡ አደጋው የደረሰው በጎፈር ሜዳ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ቦቢቾ በተባለ ቀበሌ ሰኞ መጋቢት 8 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ለረጅም ጊዜ ምሰሶው ሊወድቅ የደረሰ የኤሌክትሪክ ገመድ ተበጥሶ አንድ የ13 ዓመት ልጅ ከመኖሪያ ቤቱ ወደ ትምህርት ቤት እየሄደ ሳለ በደረሰ አደጋ ወዲያው ህይወቱ ማለፉ ተሰምቷል፡፡ hossana

አዲስሚዲያ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለፁት ከሆነ ምሰሶው በመንገድ ጥገና ቁፋሮ ምክንያት በመላላቱ የኤሌክትሪክ ገመዱ ረግቦ እንደነበርና ይህንንም በመፍራት በተደጋጋሚ ለከተማው መስተዳደርና በከተማው ለሚገኝ የመብራት ኃይል ዲስትሪክት ቅሬታ ቢያቀርቡም ሰሚ ባለማግኘታቸው አደጋው መድረሱን አስታውሰዋል፡፡ ከሟቹ ልጅ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን ላደረሰው የቸልተኝነት አደጋ ምን ምላሽ እንዳለው ለማጣራት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወደ ሆኑት አቶ ምስክር ነጋሽ ደውለን ለማጣራት ብንሞክርም ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ ሊሆኑ አልቻሉም፡፡

አንድነት እና መኢአድ የፊታችን ሐሙስ ውህደት ሊፈራረሙ ነው

 

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት(መኢአድ) ነገ ሐሙስ መጋቢት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ቅድመ ውህደት ሊፈራረሙ ነው፡፡ ፓርቲዎቹ እስካሁን በተናጠል የሚደረገው ፖለቲካ ትግል ለሀገሪቱም ሆነ ለህዝቧ እንዲሁም ለራሳቸው አዋጭ አለመሆኑን በማመን ተዋህደው አንድ ጠንካራ የፖለቲካ ማኀበር መስርቶ ለመታገል የሚያስችላቸውን ስምምነት በመጨረስ ቅድመ ውህደቱን ለመፈራረም ቀነ ቀጠሮ መያዛቸው ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ ዋናው የውህደት ስምምነት የሚጠናቀቀው የሁለቱም ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔ ጥሪ ተደርጎ ሲፀድቅ ሲሆን፤ከዚህ ቀደም የሁለቱም ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ውህደቱ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ውሳኔ ማሳለፋቸው አይዘነጋም፡፡ በዚህም ምክንያት ስምምነቱ ተጠናቆ የፊታችን ሐሙስ ድርድሩን ሲያካሂዱ የነበሩት አካላትና የሁለቱም ፓርቲ አመራሮች በተገኙበት የአንድነት ፓርቲ ፕሬዘዳንት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው እና የመኢአድ ፕሬዘዳንት አቶ አበባው መሐሪ ፓርቲያቸውን በመወከል ስምምነቱን እንደሚፈራረሙ ይጠበቃል፡፡udj

ሁለቱም ፓርቲዎች የፕሮግራም ልዩነት እንደሌላቸው የሚታወቅ ሲሆን፤ በተለይ አንድነት ፓርቲ ከዚህ ቀደም ከብርሃን ፓርቲ ጋር በመዋሃድ በፖለቲካው እንቅስቃሴ ለውጥ መፍጠር ችሏል፡፡ አሁን ደግሞ ከመኢአድ ጋር በመዋሃድ ጠንካራ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለማድረግ ስምምነት ላይ ደርሷል፡፡ የውስጥ አዋቂ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሆነ አንድነት ከመኢአድ በተጨማሪ ከሌሎችም ፓርቲዎች ጋር ውህደት ለመፍጠር አንድ ግብረኃይል በማቋቋም ሰፊ ስራ እየሰራ መሆኑንና በቅርቡም ሌሎች ፓርቲዎችም አብረውት ሊዋሃዱ እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ አንድነት ከመድረክ አባል ፓርቲዎች ጋር በግንባር ተጣምሮ እስካሁን ቢቆይም በአባላቱ የሚጠበቀው ለውጥ ባለመምጣቱ ውህደት ላይ ማተኮሩ ይነገራል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መረጃ እንደሚመለክተው ከሆነ፤ በአሁን ወቅት ተመዝግበው የእውቅና ሰርተፍኬት የተሰጣቸው 66 የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ከአራት ፓርቲዎች ውጭ ሌሎቹ ከምርጫ ወቅት በስተቀር የት እንዳሉና ምን እየሰሩ እንደሆነ ለማወቅ አልተቻለም፡፡ በዚህም ምክንያት ህዝቡ በተለያየ ጊዜ በጥቂቱም ቢሆን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎችን ከተናጥል ይልቅ አንድ ጠንካራ የፖለቲካ ድርጅት ሆነው እንዲቀርቡ በተደጋጋሚ መጠየቁ ይታወሳል፡፡