በኦሮሚያ ክልል ባሉ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ ከ5 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፤ በርካቶች ቆስለዋል
ህዳር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ ከተማ እንደገና የተጀመረው አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ትግበራን የተቃወሙ ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ እስካሁን የ5 ሰዎች ህይወት መጥፋቱ እና በርካታ ተማሪዎችም መጎዳታቸው ታውቋል፡፡ በተለይ እንደ አዲስሚዲያ ምጮች ከሆነ፤ የተማሪዎች ተቃውሞ በምዕራብ ኢትዮጵያ በጊኒጪ፣ በአምቦ፣ በምዕራብ ወለጋ የተቀጣጠለው ተቃውሞ ሌሎችንም የምዕራብ ሸዋ ከተሞችን አዳርሶ ወደ ምስራቅ ኢትዮጵያ ሐረማያ ዩኒቨርስቲ መድረሱ ታውቋል፡፡

በተለይ በሐረማያ ዩኒቨርስቲ ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጥያቄ ባነሱ ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ 1 ተማሪ ሲገደል፣ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቁ በርካቶች ጉዳት እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡ በተለይ ህዳር 23 ቀን 2008 ዓ.ም. ሐረማያ ዩኒቨርስቲ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በዩኒቨርስቲው ክልኒክ እና በሐረር ሆስፒታል የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ከነበሩት መካከል በዩኒቨርስቲው ክልኒክ የህክምና እርዳታ ሲደረግለት የነበረ አንድ ተማሪ ህይወቱ ማለፉን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተማሪዎች ላይ እየወሰዱ ባሉት የኃይል እርምጃ በምዕራብ ወለጋ ግሊሶ ከተማ ሌላ አንድ ተማሪ መገደሉ የተጠቆመ ሲሆን፤ እስካሁን በፀጥታ ኃይሉ የተገደሉ ተማሪዎች ቁጥርም 5 መድረሱ ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ በሱሉልታ ጫንጮ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ባነሱት ተመሳሳይ ጥያቄ በርካታ ተማሪዎች በመንግሥት በተወሰደባቸው የኃይል እርምጃ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ ተቃውሞው በኦሮሚያ ክልል ካሉ አንደኛ ደረጃ እስከ ዩኒቨርስቲ የተቀጣጠለ ሲሆን፤ በተለይ በጫንጮ አንደኛ እና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ የአንደኛ ደረጃ ህፃን ተማሪዎች ላይ ሳይቀር ጉዳት መድረሱን ምስልን አስደግፈው የአካባቢው ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

መንግሥት በተማሪዎች ላይ እየወሰደ ባለው የኃይል እርምጃ ከክልሉ ተወላጆች በተጨማሪ በርካታ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ላይ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን፤ ተቃውሞው ወደክልሉ ሌሎች ከተሞች እና ዩኒቨርስቲዎችም እየተዛመተ በመሆኑ በየአካባቢው ከተሞች ባሉ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እና ዩኒቨርስቲዎች ከፍተኛ የፀጥታ ጥበቃ ቁጥጥር ላይ መሆናቸው ተሰምቷል፡፡ ተቃውሞው ወደባሌ መዳወላቡ ዪኒቨርስቲም መዛመቱ መዛመቱን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በደቡብ ምዕራብ ሸዋ በበቾ እና በቱሉቦሎ ከተማ እንደዚሁም በደቡብ ሸዋ ወሊሶ አካባቢ በዲላላ ከተማ ውስጥ ያሉ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተቃውሞ እያደረጉ እንደሆነም የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ አመልክቷል፡፡ የተቃውሞው ዋነኛ ምክንያትም መንግሥት ይፋ ያደረውና እስካሁንም ከህዝብ ጋር ያልተመከረበትና ተግባራዊ ለማድረግ ከመንቀሳቀስ በስተቀር በምስጢር ተይዟል የተባለለት አዲሱ የአዲስ አበባ እና የአካባቢው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች የጋራ የተቀናጀ ማስተር ፕላን በአካባቢው ያሉ ገበሬዎችን ያለ በቂ ካሳ ያፈናቅላል፣ የአካባቢው ኦሮሞ ማኀበረሰብ ባህልና ቋንቋ ያጠፋል እና ኦሮሚያ ክልልን ለሁለት ይከፍላል የሚሉ ጥያቄዎች እንደሚገኙበት ለአዲስ ሚዲያ የደረሱ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፤ አዲሱ የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ ባለፈው ግንቦት 2006 ዓ.ም. ተቀስቅሶ በነበረው ተመሳሳይ የተማሪዎች ተቃውሞ ከ40 በላይ ወጣቶች ሲገደሉ፤ በርካቶች መጎዳታቸው አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ ተቃውሞውን አነሳስታችኋል ተብለው የታሰሩ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አሉ፡፡ በተለይ ዛሬ ህዳር 23 ቀን 2008 ዓ.ም. በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ልደታ ምድብ ችሎት ከግንቦት 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ከነበሩት 6 ተማሪዎች መካከል 5ቱን ጥፋኛ ሲል መበየኑን እና እንዲከላከሉ ለማክሰኞ ጥር 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ መስጠቱን ታውቋል፡፡ ጥፋተኛ ተብለው እንዲከላከሉ ከተበየነባቸው ተማሪዎች መካከል አበበ ኡርጌሳ፣ መገርሳ ወርቁ፣ አዱኛ ኬሶ፣ቢሊሱማ ዳመነ እና ተሾመ በቀለ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ከተማሪ ተሾመ በቀለ በስተቀር የቀሪዎቹ አራቱን ተከሳሾች የዋስትና መብት ጥያቄ ውድቅ መደረጉንም የአዲስ ስታንዳርድ ዘገባ አመልክቷል፡፡
በጎንደር የ17 ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን መንግሥት ሲያምን፤ አንዱን የገደልኩት እኔ ነኝ ብሏል
በጎንደር ህዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በእስር ቤት ላይ በደረሰ ቃጠሎ የበርካታ ሰዎች ሕይወት መጥፋቱ ተነገረ፡፡ መንግሥት ከቃጠሎው ወቅት አንድ ሰው መግደሉን ሲያምን ሌሎቹ 16 ሰዎች ህይወት የጠፋው በቃጠሎው ወቅት ከ እስር ቤቱ ለማምለጥ ሲጋፉ ነው ብሏል፡፡
የአማራ ክልል ፖሊስ ለመንግስት ሚድያ በሰጠው መግለጫው በህዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በጎንደር ወህኒ ቤት ከቀኑ 7፡30 ሰዓት አካባቢ በተነሳ የእሳት ቃጠሎ እስረኞች ከቃጠሎው ለመውጣት በተደረገው ግፊያ የ16 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ አንድ ሰው ሊያመልጥ ሲል ከፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መገደሉን አምኗል፡፡

እንደ ዓይን እማኞች ከሆነ ሕይወታቸው ያለፈው ሰዎች ቁጥር ከ42 በላይ እንደሚሆን እና መንግሥት ቁጥሩን ዝቅ በማድረግ በእጁ የጠፉትን ቁጥር ወደ አንድ ብቻ ማሳነሱ እንዳሳዘናቸው ተናግረዋል፡፡ እንደ ዓይን እማኞች ገለፃ ከሆነ በቃጠሎው ወቅት መንግሥት በእስረኞች ላይ ጠከታታይ ተኩስ ከፍቶ እንደነበርና የእስረኞችንም ህይወት ለማትረፍ ማንም ወደ አቅራቢያው እንዳይጠጋ የጥብቃ ኃይሎች እና ፖሊሶች ማንም የውጭ ሰው እንዳይጠጋ ሲያስፈራሩ እንደነበር ጠቁመው፤ ከሞቱት መካከል አብዛኛው በመንግሥት እጅ የተገደሉ እንጂ ከእስር ቤት ከእሳት ለማምለጥና ለመውጣት ሲጋፉ እንዳልነበረ ተናግረዋል፡፡
ከሞቱት በተጨማሪ በቃጠሎው በርካታ እስረኞች ጉዳት እንደደረሰባቸውና በጎንደር ሆስፒታል የህክምና እርዳታም እየተደረገላቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ የቃጠሎውን መንስኤና የተጎዱትንም ሆነ የሞቱን በተመለከተ እስካሁን በገለልተኛ አካል የተጣራ ነገር አለመኖሩ ታውቋል፡፡
በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ከቃጠሎው በፊት ባሉት ቀናት የቅማንት ማኀረሰብ ባነሱት የመብት ጥያቄ ፖሊስ በወሰደው የኃይል እርምጃ እስካሁን በገለልተኛ አካልም ሆነ በመንግሥት ተጣርቶ ይፋ ባይደርግም በርካታ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውና የተወሰኑትም ምስሎቻቸውም በማኀበራዊ ሚዲያ ይፋ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡
የወህኒ ቤቱ ኃላፊ በቃጠሎውም ሆነ በመንግሥት ኃይሎች እርምጃ የሞተ ሰው የለም በሚል ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን መግለጫ የሰጡ ሲሆን፤ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ 16ቱ በቃጠሎው ወቅት በተፈጠረ መገፋፋት ሲሞቱ አንዱ ግን ሊያመልጥ ሲል በወህኒ ቤቱ ጥበቃ አባላት መገደሉን በማመን እስካሁን 17 ሰዎች መሞታቸውን አምነዋል፡፡ በተለይ በዞኑ ሰሜን ጎንደር መንግሥት በህዝቡ ላይ እየወሰደ ስላለው የኃይል እርምጃ እና በጎንደር ወህኒ ቤት በቃጠሎው እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት ሰዎች ቁጥር መደበቅና መቀነስ የተበሳጩ የጎንደር ዩኒቨርስቲ በተለይ ማራኪ እየተባለ በሚጠራው ግቢ የተማሪዎች ተቃውሞ መቀስቀሱን ተሰምቷል፡፡ በአሁን ወቅትም ተቃውሞው ወደሌሎች የዩኒቨርስቲው ግቢ እና ወደ ሌሎች የክልሉ ተቋማት ሊስፋፋ ይችላል በሚል ስጋት ዩኒቨርስቲው በመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች ተከቦ ጥብቅ ቁጥር እየተደረገበት መሆኑንም የአዲስ ሚዲያ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የዞን 9 ብሎገሮች የ2015 የዓመቱን የፕሬስ ነፃነት ሽልማት ተቀበሉ
በአሜሪካ ኒዮርክ ከተማ ዋና ቢሮውን ያደረገው ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች (Committee to Protect Journalists) በዘንድሮው የ2015 የዓመቱ የዓለም አቀፍ የፕሬስ ነፃነት ላበረከቱት አስተዋፅዖ ኢትዮጵያውያኑ ዞን 9 ብሎገሮች ሽልማት ተቀበሉ፡፡ በስፍራው ማክሰኞ ህዳር 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በተከናወነው ምሽት የዞን 9 አባላት መካከል እንዳልካቸው ኃይለሚካኤል እና ሶሊያና ሽመልስ ሽልማታቸውን ተቀብለዋል፡፡

ሀገር ቤት የሚገኙት ቀሪዎቹ የዞን 9 አባለት ከአንድ ዓመት እስር ቆይታ በኋላ ቢለቀቁም ከሀገር እንዳይወጡ የጉዞ እገዳ የተጣለባቸውና የጉዞ ሰነድ የተነጠቁም እንዳሉ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ ለፕሬስ ነፃነት በሀገሪቱ ውስጥ ላበረከቱት አስተዋፅዕ ሲፒጄን ጨምሮ መቀመጫውን በፈረንሳይ ፓሪስ ያደረገው ድንበር የለሽ የጋዜጠኞች ቡድን የዓለም አቀፍ ተሸላሚ መሆናቸው ታውቋል፡፡
በዕለቱ በእንግድነት የተገኘችው በቅርቡ የተፈረደባትን እስር አጠናቃ ከእስር የወጣችው ርዕዮት ዓለሙ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላታል፡፡ በያዝነው ዓመት የሲፒጄ ዓለም አቀፍ የፕሬስ ነፃነት ከኢትዮጵያውያኑ ዞን 9 በተጨማሪ ሶሪያዊ እና ማሌዥያዊ ጋዜጠኛ እና አክቲቪስቶችም ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ በተመሳሳይ ከ አምስት ዓመት በፊት የቀድሞው የአውራምባ ታየምስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ዳዊት ከበደ ማግኘቱ ይታወሳል፡፡ ሲፒጄ ዓለም አቀፍ የሃዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት ሲሆን፤በተለይ የኢትዮጵያ መንግሥት በፕሬስ ነፃነት እና በጋዜጠኞች ላይ የሚወስደውን አፈና አጥብቆ በመኮነን ይታወቃል፡፡
የፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከአስመራ የትግል ሜዳ ወደ አውሮፓ መዲና ቤልጀም ብራሰልስ መጠራት
ብስራት ወልደሚካኤል
ፕሮፌሰሩ ለረቡዕ ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. (December 2, 2015) ከአስመራ ወደ ቤልጄየም ብራሰልስ የተጠሩት በሀገራችን ኢትዮጵያ ድርቅን ተከትሎ በተከሰተው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ውድቀት ወለድ ርሃብ ጉዳይ ላይ ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ንግግር፣ ምክክር እና ውይይት ለማድረግ እንደሆነ ይነገራል፡፡ የኢህአዴግ የ11 በመቶ የቁጥር ኢኮኒሚ ዕድገት ጋጋታ ገደል የከተተውና በምግብ ራሳችንን ችለናል መዝሙር ከአዳራሹ ነፋስ እንደወሰደው የሚያሳብቀው ከ15 ሚሊዮን በላይ ህዝብ በርሃብ አለነጋ ከመገረፍ አልፎ አስቸኳይ የምግብ ርዳት እንደሚያስፈልገው የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅቶች እና የተባበሩት መንግሥታት ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሄንን እውነታ ለመደበቅ መንግሥት ከፍተኛ ወጪ በማውጣት ለማስተባበልና በርሃቡ ወደተጎ ዜጎች አካባቢ ሚዲያ ድርሽ እንዳይል እና እንዳይዘገብ በውስጥ መመሪያ መተላለፉንም ከሰማን ሰነበትን፡፡

ይሄ ሁሉ የራስን የጥፋት ገመና ለመሸፈን ሲባል ህዝብ ርሃቡ ከእኛ ቁጥጥር ውጭ አይደለም ሲባል ለሀገሬው ዜጋ በቋንቋው ሲነገር፤ ለዓለም አቀፍ ለጋሽ ሀገሮች ደግሞ በእንግሊዘኛ በሀገሪቱ ከፍተኛ የርሃብ አደጋ መከሰቱን እና በሀገሪቱ የእርዳታ ማስተባበሪያ የጠገኘው እህል ከአንድ ወር እንደማያልፍ በመግለፅ ተማፅኖውን ማሰማቱን ቀጥሏል፡፡ ይህንን ስንሰማ የኢህአዴግ መንግሥት አስተዳደር ኃላፊነቱ ለነጮች ነው ወይስ ለኢትዮጵያውያን የሚል ጥያቄ ቢያጭርም ከተለመድ የተለየ ነገር ግን የለም፡፡ ለዓመታት የተለመደ የመረጃ (ዳታ) ጋገራ መግለጫና ፕሮፖጋንዳ በተጨማሪ በግልፅ መረጃ ለማፈን ከፍተኛ በጀት መድቦ መንቀሳቀስ ከጀመረ እነሆ ከ10 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ልዕለ ኃያሏ አሜሪካም ብትሆን ከስርዓቱ ያላትን የፀጥታ ጉዳይ ትብብር (ወታደሮችን ለአላስፈላጊ እልቂት ማገዳ ካላት ስምምነት) አኳይ እንደ ጥሩ አጋር ብትቆጥርም የስርዓቱን አምባገነንነት፣ ዘረኛ አገዛዝ፣ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት አለመኖር፣ የፍትህ እጦት፣ ሙስና እና ተጠያቂነት የሌለው አሰራር የሚከተለው ስርዓት እንደሆነ ልትሸሽገው አልቻለችም፡፡

ይሁን እንጂ የአውሮፓ ህብረት የተለመደ ሰብዓዊ እርዳታውን በስሱም ቢሆን መለገሱን ባያቆምም የምንጊዜም የስርዓቱ ቀኝ እጅ የሆኑት እንግሊዝ፣ ጣሊያን እና አየርላንድ እንደድሮ ለስርዓቱ ሰዎች ፊት መስጠቱን የቀነሱ ይመስላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያን በሚመለከት በአውሮፓ ህብረት አሊያም በአውሮፓ ኢኮኖሚ ቅንጅት የጋራ አባል ሀገሮች በኩል ውሳኔ እንዲያልፍ እየተደረገ መሆኑን እየታዘብን ነው፡፡ ወቅታዊውን ርሃብ ለማስታገስና ለተጎዱ ወገኖች የሚደረው ሰብዓዊ እርዳታ እንኳ እንደቀድሞ በቀጥታ ለመንግሥት ከመስጠት ይልቅ በእርዳታ መልክ የተሰጠው ገንዘብ በሌሎች በጎ አድራጎት ድርጅቶች በኩል በቀጥታ ለተጎጂዎች እንዲደርስ የሚያስችል አሰራር እየተከተሉ እንደሆነ የስርዓቱ አጋር አሜሪካ እና በቅርቡም ስውድን የወሰደችው እርምጃ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ስርዓቱ በተለያዩ ለጋሽ ሀገሮች እንኳ እምነት እንደታጣበት እና የተለመደው የመረጃ ጋገራ ሪፖርትና ጋጋታ ፋይዳቢስ መሆኑን የተገነዘቡ ይመስላል፡፡
እነሆ አሁን ደግሞ የኢትዮጵያውን ርሃብ በተመለከተ ህዝባዊ ዓመኔታና ቅቡልነት ባይኖረው ኃላፊነት ያለበት መንግሥት እያለ ስርዓቱን ለመገርሰስ ከሚታገሉት መካከል ተዓማኒና ትክክለኛ መረጃና ትንታኔ ይሰጣሉ ተብለው ከታመኑት መካከል በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አማካኝነት ከአስመራ የትግል ሜዳ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተጋብዘዋል፡፡ በርግጥ ፕሮፌሰሩ ካላቸው የፖለቲካ ስብዕና በተጨማሪ በሙያቸው ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት ባለሙያና ተመራማሪ እንደመሆናቸው መጠን በስፍራው መጋበዛቸው የህብረቱ ትክክለኛ ምርጫ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ይሄ ደግሞ የስርዓቱን ሰዎች የበለጠ ምክንያታዊ መሸሸጊያ የሚያሳጣ ወቅታዊ የመረጃ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የሚገርመው በኢትዮጵያ ስም ስርዓቱን ወክሎ በቤልጀየም ከፍተኛ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር እያሉ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ መረጃና ትንታኔ እንዲሰጡ ከበረሃ የትግል ሜዳ የፕሮፌሰሩ መጋበዝ ለስርዓቱ ትልቅ ራስምታት ነው፡፡ ምክንያቱም ፕሮፌሰሩን እና የሚመሩትን የፖለቲካ ድርጅትና አባላት በሽብርተኝነት ለማስፈረጅ ለዓመታት በተለመደ የመረጃ ጋገራ ቢሞከርም በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ተቀባይነት አላገኘምና፡፡
በተለይ በመረጃ እና ሐሳቡን ለመግለፅ ለታፈነው የኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ አጋጣሚ ሲሆን፤ ለፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና ለሚመሩት ድርጅት እንደ አንድእመረታ ሊታይ ይችላል፡፡ እንደ አንዳንድ የስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጥቆማ ከሆነ መንግሥት ርሃቡን ከሀገሬው ሰው በመደበቅ ለጋሽ ሀገራት በተማፅኞ በማጨናነቅ ዕርዳታቸውን በጥሬ ገንዘብ ወይም ዶላር እንዲሆን እየሰራ እንዳለ እና ለዚህም ያቀረበው ምክንያት ገንዘቡ ከተሰጠኝ ከሀገር ውስጥ ነጋዴዎች እህሉን ራሴ ገዝቼ በማከፋፈል ጊዜና ጉልበት መቆጠብ እችላለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡ ይህ ለተጎጂዎች ታስቦ ሳይሆን መንግሥት በሀገሪቱ ከደረሰበት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት የተነሳ አጋጣሚውንም እንደ ጥሩ ዕድል ሊጠቀምበት እንዳሰበና እስካሁንም እንዳልተሳካለት ለስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ተጠቁሟል፡፡
በአሁን ወቅት ከአስከፊው ርሃብ በተጨማሪ በሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት በመከሰቱ የተለያዩ አስመጪዎች እና ኢንዱስትሪዎች ለአብነትም ቴክኖ ሞባይል የስልክ መገጣጠሚያን የመሳሰሉት ስራ ማቆማቸውም መነገር ከተጀመረ ሰነባብቷል፡፡ በዚህ ሁሉ የስርዓቱ አጣብቂኝ ውስጥ ፕሮፌሰሩ የበለጠ ተዓማኒነትና ተቀባይነት አግኝነተው በአውሮፓ ህብረት መጋበዛቸው በቀጣይ ምን ሊያሳየን ይሆን የሚለውን ወደፊት አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡
አዲሱ ማስተር ፕላን አሁንም ተቃውሞ ቀስቅሷል
አዲስ አበባን ከሌሎች አጎራባች ከተሞች በመሰረተ ልማት ለማስተሳሰር በሚል በመንግሥት ይፋ ባደረገው አዲሱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ከትናንት ጀምሮ በድጋሚ ተቃውሞ አስነስቷል፡፡

በተለይ በምዕራብ ሸዋ አምቦ፣ ጊኒጪ እና ምዕራብ ወለጋ ተቃውሞው ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ በተቃውሞው ከተሰለፉት መካከል በመንግሥት በተወሰደ ርምጃ በምዕራብ ሸዋ ድሬ ኢንጪኒ አካባቢ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች እንዳሉም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በዋናነት ተቃውሞን የቀሰቀሰው አዲሱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችን ያከተተ በመሆኑ እና የዞኑን እና የክልሉን ጥቅም እንዲሁም ገበሬዎችን ያለምንም በቂ ካሳና ቦታ በማፈናቀል ለጎዳና ህይወት ይዳርጋል የሚሉ ሐሳቦች እንደሚገኙበት የተጠቆሙ ሲሆን፤ ይህንን ፕላን ተግባራዊ ለማድረግ ኢህአዴግ የፖለቲካ ድርጅት አባል ከሆነው ከኦህዴድ አመራር አባላት ከመፅደቁ ውጭ ወደ ህዝብ ያልወረደና ለምክክርም እንዳልቀረበ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት የዚህ ማስተር ፕላን ተቋውሞው በ2006 ዓ.ም. በመንግሥት በተወሰደ እርምጃ በርካታ ተማሪዎች እና የተቃውሞ ታዳሚዎች ግድያ ከቆመ በኋላ ድጋሚ ማገርሸቱ ተሰምቷል፡፡

በአንዳንድ ከተሞች የመኪና መንገዶች የተዘጉ ሲሆን፤ በተቃውሞው የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎችም መካተታቸው ታውቋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ከመንግሥት ምንም የተሰጠ ማብራሪያም ሆነ አስተያየት የለም፡፡