አንድነት ፓርቲ የምርጫ ቦርድ ውሳኔን እንደማይቀበለውና በሁለት ሳምንት ውስጥ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ አስታወቀ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራና ሪፖርቱን እንዲያቀርብ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ባለፈው እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ አድርጎ አቶ በላይ ፈቃዱን በድጋሚ የፓርቲው ፕሬዘዳንት አድርጎ መርጧል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው በድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ የሁለት ሳምንት ጊዜ መስጠቱን ተከትሎ አንድነት በድጋሚ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ ፓርቲው ጥር 8 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በተያያዘ ዜና የመላው ኢትዮጵ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)ም እንዲሁ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ ምርቻ ቦርድ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አድርጎ አቶ ማሙሸት አማረን ፕሬዘዳንት አድርጎ መምረጡ ቢታወቅም፤ ምርጫ ቦርድ በበኩሉ ድርጅቱ ድጋሚ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ የሉለት ሳምንት ጊዜ መስጠቱን አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መኢአድ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ የሰጠውን ትዕዛዝና ያስተላለፈውን ውሳኔ እንደማይቀበለውና በድጋሚም ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡
መኢአድና አንድነት ለሁለተኛ ጊዜ ጥር 3 ቀን 2007 ኣ.ም. ያደረጉትን ጠቅላላ ጉባኤ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንዲታዘብ ህጉ በመደንገጉና ፓርቲዎቹ በደብዳቤ ጥሪ ቢያደርጉለትም ምርጫ ቦርድ በሁለቱም ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ተወካዩን አለመላኩ ታውቋል፡፡
በተለይ አንድነት ፓርቲ ድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማይጠራ ይፋ ከማድረጉ በተጨማሪ “ይህ በማን አለብኝ ሰሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሻንፍ የሚያደረግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡” ብሏል፡፡
የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-
የመድብለ ፓርቲ ስርዓት እንዳይፈጠር የምርጫ ቦርድ ታሪካዊ ወንጀል እየፈፀመ ነው፡፡
———-
ከአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
የተሰጠ መግለጫ
————————-
የአንድነት ፓርቲ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲፈጠር በምንም መለኪያ በገለልተኝነት የማንጠብቃቸውን የዲሞክራሲ ተቋማት በተግባር ለመፈተን እንዲቻል የሁለት ሺ ሰባት ምርጫን በሁሉም ሂደቶች ህዝቡን በማሳተፍ እንደሚወዳደር እና ህዝብን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ እና የኢህአዴግ አገዛዝ የመጨረሻ እንዲሆን በቁርጠኝነት እንደሚሰራ መወሰኑ ይታወቃል፡፡ ይህን ስንወስን እነዚህ ተቋማት ገለልተኝነታቸውን አረጋግጠው ታሪክ የሚሰሩበት እድልም ያገኛሉ የሚል ተሰፋ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ይህን እድል ከመጠቀም እና በህግ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት ከመወጣት ይልቅ ለገዢው ፓርቲ ያለውን ወገንተኝነት በምርጫው ሂደት ዋዜማ በይፋ እያረጋገጠ ይገኛል፡፡ አሁንም ቦርዱ ወሰነ ተብሎ በሚዲያ የተገለፀው እንዲሁም ለፓርቲያችን በፅሁፍ የተሰጠው “በአስራ አምስት ቀን ውስጥ በጋራ ጉባዔ አድርጉ” የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ በተደጋጋሚ ፓርቲያችንን ደንብ እንዲያከብር እየጠየኩ ነው በማለት ከደንብ ውጭ እንድንሰራ የአዛኝ ቂብ አንጓች ሆኖዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ የመጥራት ኃላፊትን ያለበት የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ወይም ደግሞ በአባላት ጥያቄ የጠቀላላ ጉባዔ አባላትን አንድ ሶስተኛ ፊርማ አስባስበው በኦዲትና ኢንስፔክሽን ትዕዛዝ መሆኑ በግልፅ እየታወቀ ከፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ ውጭ በ15 ቀን ውስጥ ጉባዔ ጥሩ የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ ከገዢው ፓርቲ ጎን ተሰልፉ እየተጫወተ አንድነትን ከጫወታ ለማስወጣት ካለሆነ ሌላ ምንም ትርጉም ልንሰጠው አንችልም፡፡ ይህ ደግሞ ቦርዱ እየሰራ ያለውን ታሪካዊ ወንጀል ይፋ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህ በማን አለብኝ ሰሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሻንፍ የሚያደረግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡
በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ የሰላማዊ ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እና ህዝቡን የስልጣን ባለቤት የማድረግ እንቅስቃሴውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና በቀጣይ ሳምንታትም በመንግሰትና በቦርዱ ላይ ጫና ማሳደሩን እንደሚቀጥልበት እያረጋገጥን አንድነት ፓርቲ ወደ ህገወጥነት የሚወሰደውን “የጋራ ጉባዔ” አካሂዱ የሚለው የምርጫ ቦርድ ውሳኔ የማንቀበለው መሆኑን ለመላው አባላትና ደጋፊዎች ማረጋገጥ እንወዳለን፡፡
ጥር 8 ቀን 2007
ድል የህዝብ ነው!!!
አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
መኢዴፓና ኢብአፓ በፓርቲዎች ላይ የሚፈፀመው ደባና ዛቻ እንዲቆም ጠየቁ
-
“ምርጫ ቦርድ የኢህአዴግ አምስተኛ አባል ፓርቲ ሆኗል”-ፓርቲዎቹ
የመላው ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (መኢዴፓ) እና
የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት ፓርቲ (ኢብአፓ) በምርጫ ዋዜማ
ገዥው ፓርቲና ምርጫ ቦርድ በተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለይም
በሰማያዊ፣ አንድነትና መኢአድ ላይ የሚፈፅሙትን ደባና ዛቻ
እንዲያቆሙ ጠየቁ፡፡ ፓርቲዎቹ ህዳር 7/2007 ዓ.ም ‹‹በምርጫ
ዋዜማ በፓርቲዎች ላይ የሚደርሰው ደባና ዛቻ በአስቸኳይ
ይቁም›› በሚል በጋራ ባወጡት መግለጫ ኢህአዴግ ምርጫ
ቦርድን በመሳሪያነት በመጠቀም ሰማያዊ፣ አንድነትና መኢአድ
ላይ ወከባና ዛቻ እየፈፀመ ነው ሲሉ ወቅሰዋል፡፡ መግለጫው
ምርጫ ቦርድ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጉ እያለ ለማዋከብ ቢጥርም
መኢአድና አንድነት የተዋጣለት ጠቅላላ ጉባኤ አድርገዋል
ብሏል፡፡
ፓርቲዎቹ በመግለጫቸው ሰማያዊ ፓርቲ አገራዊ ግዴታውን
እየተወጣ በመሆኑ፣ እንዲሁም መኢአድና አንድነት ብቃት ያላቸው
ልሂቃንን ማፍራት ስለቻሉ በተፈጠረበት ስጋት ፓርቲዎቹን
ለማጥፋት እየጣረ መሆኑንና ምርጫ ቦርድም የኢህአዴግ
አምስተኛ አባል ፓርቲ እስኪመስል ድርስ የገዥው ፓርቲ
መጠቀሚያ ሆኗል ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከገዥው ፓርቲ መሳሪያነት
ወጥቶ የተጣለበትን ኃላፊነት እንዲወጣም ፓርቲዎቹ
በመግለጫቸው ማሳሰባቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
ምርጫ ቦርድ በሶስቱ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ላይ ውሳኔ ማሳለፉን አስታወቀ
ዛሬ ጥር 5 ቀን 2007 ዓ.ም. ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በአንድነት፣ በመኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች ላይ ውሳሳለፉን አስታውቋል፡፡ ቦርዱ ውሳኔ ብሎ ያስተላለፈው ፤ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) እንዲሁም የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የውስጥ ችግራቸውን መፍታት አልቻሉም በሚል ለዛሬው ውሳኔ እሰጣለሁ ብሎ የነበረው ምርጫ ቦርድ ሁለቱ ፓርቲዎች በሁለት ሳምንት ውስጥ የውስጥ ችግራቸውን ፈትተው ሌላ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርጉ የመጨረሻ ጊዜ ሰጥቻቸዋለሁ ሲል ገልጾአል፡፡
ቦርዱ ዛሬ ከሰዓት በሰጠው መግለጫ በአንድነትና መኢአድ ስም የተለያዩ ጉባኤዎች በመደረጋቸው ሁለቱ ፓርቲዎች ጥር 3 ያደረጉትን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ አለመገኘቱን፣ አንድነት የ2004 ዓ.ም እንዲሁም የመኢአድን የ2001 ዓ.ም ደንብን እንጅ ከዛ በኋላ ያሉትን የፓርቲውን ደንቦች እንደማያውቅ በመግለጽ በሁለት ሳምንት ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ችግራቸውን እንዲፈቱ የመጨረሻ ጊዜ ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡
በሌላ በኩል መድረክ ረግጦ በመውጣት፣ ሌሎች ፓርቲዎች እንዲያድሙ በማድረግ፣ ቦርዱ የማያውቀው ትብብር በመመስረት በሚል በምርጫ ቦርድ ክስ የቀረበበትና ይቅርታ እንደማይጠይቅ በደብዳቤ ለገለጸው ሰማያዊ ፓርቲ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ ማስጠንቀቂያውን የማያከብር ከሆነም ቦርዱ ህጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏል፡፡
የቦርዱ ባለስልጣናት ‹‹ሰማያዊ ፓርቲን ህገ ወጥ ትብብር በመመስረት ስትከሱ ሌሎቹን የትብብሩን አባል ፓርቲዎች ለምን አልከሰሳችሁም?›› በሚል ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹ፓርቲዎቹ 9 መሆናቸውን የሰማሁት አሁን ነው፡፡›› ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ ‹‹እስካሁን ሌሎች ትብብሮችን ምርጫ ቦርድ አያውቃቸውም ብላችሁ ከሳችሁ አታውቁም›› በሚል የ9ኙን ፓርቲዎች ትብብር ህገ ወጥ ነው ካሉ ገዠው ፓርቲ ከአጋሮቹ ጋር ያለውን ግንኙነትን ለምን ህገ ወጥ ነው እንደማይሉ ለቀረበላቸው ጥያቄም ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹ኢህአዴግ እንደገዥ ፓርቲ አጋር ፓርቲዎች ሊኖሩት ይቻላል፡፡ እንደ ገዥ ፓርቲ ከአጋሮች ጋር መስራት ይችላል፡፡ እንዲህ አይነት ነገሮችን ቦርዱ አይመለከተውም›› ሲሉ መልሰዋል፡፡
አንድነትና መኢአድ በሁለት ሳምንት ውስጥ ችግራቸውን እንዲፈቱ ተጨማሪ ጊዜ ሰጥቻለሁ ያለው ምርጫ ቦርድ በሁለት ሳምንት ውስጥ ችግራቸውን ካልፈቱ ቦርዱ ተሰብስቦ ውሳኔውን አሳውቃለሁ ማለቱን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ ያመለክታል፡፡ አንድነት እና መኢአድ ምርጫ ቦርድ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔ አድርጉ ባለው መሰረት ያለፈው እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ባደረጉት ጠቅላላ ጉባኤ አንድነት ፓርቲ በድጋሚ አቶ በላይ ፈቃዱን ፕሬዘዳንት አድርጎ ሲመርጥ፤ መኢአድም እንዲሁ በተመሳሳይ ቀን ጠቅላላ ጉባዔ ያደረገ ሲሆን፤ በዕለቱ ምርጫ ቦርድ በህጉ መሰረት በሁለቱም ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንዲገኝ የጥሪ ደብዳቤ ቢደርሰውም በሁለቱም ጉባኤ ላይ የቦርዱ ተወካይ እንዳልተገኘ ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ ቦርዱ አሁንም ለሶስተኛ ጊዜ ሁለቱም ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔ እንዲያደርጉ የሁለት ሳምንት ጊዜ ሰጥቻቸዋለሁ ሲል ዛሬ በፅህፈት ቤቱ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡
…….
9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የጠሩት ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባና እስር ተቋረጠ
ዛሬ ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ.ም. በ9ኙ ፓርቲዎች ለትብብር ለ24 ሰዓት በመስቀል አደባባይ የተጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በደህንነት፣ ፌደራልና የአዲስ አበባ ፖሊስ ድብደባና እስር ምክንያት መቋረጡ ተገለፀ፡፡ ሰልፉን ሲያስተባብሩና ሲመሩ የነበሩ በርካታ የፓርቲዎቹ አባላትና ደጋፊዎች ተደብድበው መታሰራቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ በተለይም ከአመራሮች የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፣ የጌዴኦ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሊቀመንበር አቶ አለሳ መንገሻ እና የከንባታ ህዝቦች ኮንግረንስ ሊቀመንበር አቶ ኤርጫፎ በፖሊስ ታግተው መታሰራቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ከዋና አመራሮቹ በተጨማሪ አቶ ወሮታው ዋሴ፣ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ኢየሩስ ተስፋው፣ ጋዜጠኛ በላይ ማናየ፣ ወይንሸት ሞላ፣ ሳሙኤል አበበ፣ እያስፔድ ተስፋዬ፣ሜሮን አለማየሁ፣ ንግስት ወንዲፍራው፣ ወይንሸት ንጉሴ፣ ምኞት መኮንን፣ አቤል ኤፍሬም፣ ኤፍሬም ደግፌ፣ ኃይለማሪያም፣ ሜሮን፣ ኢብራሂም አብዱልሰላም፣ እና ሌሎችም የትብብሩ አመራሮችና አባላት ከፍተኛ ቁጥር ባለው ፌደራል ፖሊስ መያዛቸውን እና በታገቱበት ድብደባ እየተፈፀመባቸው እንደነበር የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ የታሰሩት አለመለቀቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሰላማዊ ሰልፉ ወቅት የታፈሱት አመራሮች ቂርቆስ ፖፖላሬ ፖሊስ ጣቢያ እንደሚገኙ የተጠቆመ ሲሆን፤ ከታሰሩት መካከል ወጣት አቤል ኤፍሬም በተፈፀመበት ከፍተኛ ድብደባ ራሱን ስቶ የካቲት 12 ሆስፒታል እንተኛ እና አቶ ይልቃል ጌትነትም ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ቢቢ ኤን ሬዲዮን ጨምሮ የተለያዩ የማኀበራዊ ገፆች መረጃ አመልክቷል፡፡ ሰላማዊ ሰልፉን በተመለከተ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ፅህፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ የሆኑት አቶ አሰግድ ጌታቸው ለከተማ አስተዳደሩ በከተማዋ ውስጥ የ24 ሰዓታት የአዳር ሰልፍ ለማካሄድ ጥያቄ ቀርቦ እንደነበርና አስተዳደሩ ግን ፍቃድ አለመስጠቱን መናገራቸውን ድሬ-ቲዩብ ዘግቧል፡፡
የመንግስት ሹሙ ለሰልፉ ፈቃድ አልሰጠንም ቢሉም፤ በህገ መንግስቱ አንቀፅ 30(1) ማንኛውም ሰው ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብቱ እንደሆነ እና ሰላማዊ ሰልፍን በተመለተ የወጣው አዋጅ እንደሚያመለክተው ከሆነ፤ የተቃውሞም ሆነ የድጋፍ ሰላማዊ ሰልፍ አደባባይ ለመውጣት ማሳወቅ እንጂ ማስፈቀድ ድንጋጌ እንደሌለ ይታወቃል፡፡
ኢህአዴግ በክልል የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ማሰርና መደብደቡን ቀጥሏል
የታሰሩ አመራሮች የአንድነት፣መኢአድ፣ ሰማያዊ እና አረና ፓር እና የሲቪክ ተቋም አመራር ይገኙበታል፡፡ እነኚህም ከአንድነት ከሰሜን ጎንደር ምዕራብ አርማጭሆ አቶ አንጋው ተገኝ፣ አቶ አባይ ዘውዱ፣ አቶ እንግዳው ዋኘው እንዲሁም ከመተማ አቶ በላይነህ ሲሳይ እና አቶ አለባቸው ማሞ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም.፤ ከበመቀሌ የአንድነት አባል የሆነው አቶ ሺሻይ አዘናው ደግሞ ጥቅምት 26 2007 ዓም ተይዘው እስካሁን ባልታወቀ ስፍራ በመንግስት ፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መሰወራቸው ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይ ወቅት ሌሎች የአንድነት አመራሮች ከወረታ አቶ አለበል ዘለቀ፣ከምዕራብ ጎጃም ደጋ ዳሞት ወረዳ አቶ ጥላሁን አበበ በመንግስት ፀጥታ ይሎች ታፍነው ወዳልታወቀ ቦታ መታሰራቸው ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ሌላው የአንድነት ፓርቲ የወላይታ ዞን አመራሮች አቶ ማሞ ጎሙ፣ አቶ ወኖ መናሳ እና አቶ አልታዬ አቦታ በመንግስት የደህንነት ኃይሎች ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸውና የህክምና ዕርዳታም እየተደረገላቸው እንደሆነ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ አንድነታ ፓርቲ ድርጊቱን በመቃወምና በማውገዝ ጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም. መግለጫ ማውጣቱ ታውቋል፡፡
ከመኢአድ የቀድሞው የፓርቲው ዋና ፀሐፊነ አመራር ተስፋዬ ታሪኩ ከጎጃም ደጀን በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መወሰዳቸው እንዲሁም ከሰማያዊ ፓርቲ ደግሞ የሰሜን ጎንደር የዞን አመራር የሆኑት አቶ አግባው ሰጠኝ ጎንደር ከተማ ውስጥ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም. በተመሳሳይ በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ታፍነው ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሰወሯቸው ፓርቲዎቹ አስታውቀዋል፡፡ በተያያዘ ዜና ከአረና ትግራይ ፓርቲ ደግሞ በትግራይ ክልል የሚገኙ አመራሮቹና አባሎቹ ቀሺ ብርሃኑ ቀባዕ፣ኣቶ ኣያሌው ጣዕምያለው፣,አቶ ሓለፎም ገብረዝጊ እና ቀሺ ገብረእግኣብሄር ካሳዬ ጥቅምት 26 ቀን 2007 ዓ.ም.በተመሳሳይ በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መወሰዳቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ከወዲሁ ታሳቢ በማድረግ ከላይ የተጠቀሱ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ወጣት አመራሮችን ማሰር፣ መሰወርና መደብደቡን አጠናክሮ መቀጠሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመግባባት፣ አንድነትና ሰላም (ሰላም) ማህበር የተሰኘው የሲቪክ ተቋም ስራ አስኪያጅ አቶ ፋንታሁን ብርሃኑ ጥቅምት 23 ቀን 2007 ዓ.ም.መታሰራቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ ፋንታሁን ማኀበራቸው በህግ የተፈቀደለትንና የቆመለትን ዓላማ ለማስፈፀም ሲንቀሳቀሱ አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ተይዘው መታሰራቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ ያመለክታል፡፡
በተለይ የፓርቲዎቹ ወጣት አመራሮች ላይ በተከታታይ እየደረሰ ያለውን እስርና ድብደባ ምክንያት በተመለከተ ምላሽ እንዲሰጡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ጥረት ቢደረግም አልተሳካም፡፡ በተለይ ከሚያዚያ 2006 ኣ.ም. ጀምሮ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኞችን፣ ብሎገሮችን እና ወጣት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በጅምላ ማሰሩን አጠናክሮ መቀጠሉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡



