በደቡብ አፍሪካ የ7 ሰዎችን ህይወት ያጠፋው የጥላቻ አመፅ ወደሌሎች ከተሞችም መዛመቱ እየተነገረ ነው
በደቡብ አፍሪካ በያዝነው ሚያዝያ ወር 2007 ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ በወደብ ከተማዋ ደርባን ጥቁር የውጭ አፍሪካውያን ነጋዴዎች ላይ የተቀሰቀሰው ጥላቻ የ6 ሰዎች ህይወትን እንዳጠፋ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያ ዘገባ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በሌሎች የአፍሪካ ጥቁር ዜጎች ላይ የተጀመረው ጥላቻ ከደርባን ከተማ ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የተዛመተ ሲሆን፤ ትናንት ቅዳሜ ጆሃንስበርግ ከተማ ላይ አንድ ሞዛምቢካዊ መግደላቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በጥቃቱ በብዛት ሰለባ የሆኑት የኢትዮጵያ፣ የሶማሌ፣የናይጄሪያ፣የሞዛምቢክ፣የዙምባቤና የማላዊ ዜጎች የገለፀ ሲሆን፤ ከተገደሉት መካከልም 3ቱ ኢትዮጵውን መሆናቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጥቃቱ ምክንያት ኬንያ፣ ማላዊ እና ዙምባቤ ወዲያውኑ ዜጎቻቸውን ከደቡብ አፍሪካ ለማስወጣት የሞከሩ ሲሆን፤ በተለይ ዙምባቤ እና ቦትስዋና ዜጎቻቸው በሰላም እስኪወጡ ድረስ ከጥቃቱ ለመከላከል ልዩ የጦር ኃይል ወደስፍራው መላካቸው ተሰምቷል፡፡ ሞዛምቢክ በበኩሏ ዜጎቿና የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ሌሎች ጥቁር አፍሪካውያንን ለመታደግ ድንበሯን የከፈተች ስትሆን፤ ጥቃቱ ወዳለበት ስፍራ ድረስ በመሄድ ዜጎቻቿን ለመታደግ ትራስፖርትና አስፈላጊውን ነገር ሁሉ ስታቀርብ ተስተውሏል፡፡
በተለይ ናይጄሪያና የሶማሊያ መንግሥት ድርጊቱን ከማውገዝ አልፎ፤ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት የተፈጠረውን ቀውስ በአስቸኳይ እንዲቆጣጠርና እንዲያቆም ማስጠንቀቂያ ጠይቀዋል፡፡ በናይጄሪያ በዓለም አቀፍ አሸባሪነት የተፈረጀው ቦኮ ሃራም በበኩሉ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት በናይጄሪያውያን ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በ24 ሰዓታት ውስጥ ማስቆም ካልቻለ በምዕራብ አፍሪካ ባሉ የደቡብ አፍሪካ ኤምባሲና ዜጎቿ ላይ እርምጃ እንደሚወስድ ከመዛት በተጨማሪ የደቡብ አፍሪካዋን ጆሃንስ በርግን ባግዳድ አደርጋታለሁ ሲል ማስጠንቀቁ አነጋግሯል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ በደቡብ አፍሪካ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አገኘሁት ባለው መረጃ መሰረት በጥቃቱ የሞተው አንድ ኢትዮጵዊ መሆኑን በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮረፖሬሽን አስታውቋል፡፡
በደርባን የተቀሰቀሰው በተለምዶ የውጭ ሀገር ዜጋን የመጥላት “ዜኖፎቢያ” ዘመቻ በአሁን ሰዓት ጋብ ያለ ቢመስልም፤ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች መዛመቱንና ችግሩ ከከተማ ውጭ የሚሰሩ ሌሎች ጥቁር የአፍሪካ ዜጎች አደጋ ላይ መሆናቸውንና እስካሁንም የደረሰባቸውን ችግር ለማወቅ እንዳልተቻለም ተጠቁሟል፡፡ ድርጊቱንም የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ፕሬዘዳንት ጃኮብ ዙማና የተለያዩ የሀገሪቱ ዜጎች በይፋ ቢቃወሙም፤የአመፁ ዋና ቀስቃሽ ተደርገው የተወሰዱት በደርባን ያሉት የዙሉ ጎሳ ንጉስ ጉድዊል በወቅቱ በአንድ መድረክ ባደረጉት የጥላቻ ንግግር መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የፕሬዘዳንቱ ጃኮብ ዙማ ልጅም ድርጊቱን የሚያበረታታ ነገር ከዚህ በፊት በሌላ መድረክ መናገራቸው እየተጠቆመ ይገኛል፡፡ በጥቃቱም ሁለት ጥቁር አፍሪካውያን ከነ ህይወታቸው በደቡብ አፍሪካውያን የተቃጠሉ ሲሆን ሌሎቹ ስለት ባላቸው መሳሪያዎችና በድንጋይ ተደደብድበው መገደላቸው ታውቋል፡፡
በተቀሰቀሰው የጥላቻ አመፅም የኢትዮጵያውንን ጨምሮ የበርካታ የጥቁር አፍሪካውያን ሱቆች ተዘርፈዋል፣ ከዝርፊው የተረፉትም ተቃጥለዋል፡፡ ድርጊቱን ዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ቢያወግዘውም ወደሌሎች ከተሞች መዛሙቱ አሁንም ስጋትን ጭሯል፡፡ በርካቶችም የንግድ ሱቆቻቸውን ጥለው በተለይ በደርባን ከተማ ጊዘየያዊ የስደተኛ መተጠለያ ጣቢያና በፖሊስ ጣቢያዎች እንደተጠለሉም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ በጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በተፈፀመ ተመሳሳይ ጥቁር አፍሪካውያን ስደተኞች በተሰማሩበት የንግድ ስራ ጥላቻ ከ60 ያላነሱ ሰዎች መገደላቸውንና የበርካቶች ሱቆችና ሌሎች የንግድ ተቋማት መዘረፋቸውን መረጃዎች አመለክተዋል፡፡
ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን አነስተኛ የንግድ ሱቅ በሚሰሩ አፍሪካውያን ላይ በጥላቻ ቢዘምቱም፤ለዛሬው ነፃነታቸው ያበቋቸው በዋናነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች አፍሪካውያን ትልቅ ሚና እንደነበራቸው አይዘነጋም፡፡
በኬንያ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ በአል-ሸዓባብ በተፈፀመ ጥቃት የሟቾች ቁጥር 147 ደርሷል
በኬንያ ሰሜን ምስራቅ በምትገኘው ጋሪሳ የሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ ሐሙስ ጠዋት መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ግቢ ውስጥ በመግባት በከፈተው ጥቃት ሁለት የዩኒቨርስቲው ጠባቂዎችን፣ሶስት የፖሊስ ኦፊሰሮችን እና 142 ተማሪዎች በአጠቃላይ 147 ሰዎች መገደላቸውን የሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ጆሴፍ ነካይዘሪ ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርገዋል፡፡ በጥቃቱ ከሟቾች በተጨማሪ 79 ተማሪዎች የቆሰሉ ሲሆን፤ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቀ በታጣቂው ኃይል ታግተው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
ይህንንም ተከትሎ የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ በፖሊስ እጥረት ምክንያት አላስፈላጊ ዋጋ መክፈል የለብንም በማለት ከፍተኛ የፖሊስ ቁጥር እንዲጨምርና ወደስልጠና እንዲገቡ ትዕዛዝ መስጠታቸውን አደጋው በደረሰ ቀን ባስተላለፉት የሀዘን መግለጫ ላይ አስታውቀዋል፡፡ የሶማሊው ታጣቂ አልሸዓባብ በኬንያ ንፁሃን ላይ የሚያደርሰው ጥቃት እየተበራከተ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በናይሮቢ ዌስትጌት የንግድ ማዕከል ውስጥ በፈፀመው ጥቃት 67 ሰዎች መግደሉ ይታወሳል፡፡ ከዛም በኋላ የሐሙሱን የጋሪሳ ዩኒቨረድስቲ ኮሌጅን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በርካታ ጥቃቶችን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ የጥቃቲ ኢላማዎችም ሙስሊም ያልሆነ ማንኛውም አካል ሲሆን፤ በተለይ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃቱ መጨመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
እንደ ሀገሪቱ ፖሊስ መጃ መሰረት ከ2004 ዓ.ም. እስከ ታህሳሥ 2007 ዓ.ም. ብቻ የአልቃይዳ ክንፍ በሆነው በሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አልሸዓባብ የተገደሉ ኬኒያውያን ቁጥር 312 ደርሶ ነበር፡፡ በጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ የተፈፀመውን የጅምላ ግድያ ጨምሮ በሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ የተገደሉ ኬንያውያን 459 ደርሷል፡፡
በዩኒቨርስቲ ኮሌጁ ተማሪዎች ላይ ታጣቂው ከፈፀመው የጅምላ ግድያ በኋላ አራት የታጣቂ ቡድኑ አባላት ሲገደሉ፣ አምስት ተጠርጣሪ የቡድኑ አባላት በቁጥጥር መዋላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ውስጥ የተገደሉ ሰዎችን ማንነት ለመለየትና ወደ የቤተሰቦቻቸው ለመላክ አሰከሬናቸው ወደ ናይሮቢ መላኩም ታውቋል፡፡
ጋሪሳ ከናይሮቢ ሰሜን ምስራቅ 367 ኪሎ ሜትር ስትርቅ፤ ከኬንያ ሶማሊያ ድንበር ያላት ርቀት ደግሞ 147 ኪሎ ሜትር ነው፡፡ የታጣቂ ቡድኑ በተመሳሳይ መልኩ በዩጋንዳ የትምህርት ተቋማት ላይ ጥቃት ለመፈፀም ዕቅድ እንዳለው ተጠቁሞ፤ የዩጋንዳ የደህንነትና ፀጥታ አካላት የሀገሪቱን ደህንነት ከመቼውም ጊዜ በላቀ በተጠንቀቅ ላይ ሆነው እንዲጠብቁ መደረጉንም የዩጋንዳ ከፍተኛ ፖሊስ ኦፊሰርን ጠቅሶ የአውስትራሊያው ኤቢሲ ዘግቧል፡፡
በተለይ ከጥቃቱ በስተጀርባ ዋና አቀናባሪና በጋሪሳ ከተማ የእስላማዊ ትምህርት ቤት መምህር እንደነበር የተጠቆመው መሐመድ መሐሙድ የገደለ ወይም ያለበትን የጠቆመም እንዲሁም ይዞ ለሚያስረክብ የኬንያ መንግሥት ፖሊስ 215 ሺህ የአሜሪካን ዶላር (200 ሚሊዮን የኬንያ ሽንልንግ)እንደሚሰጥ ቃል ገብቷል፡፡ ጥቃቱን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋነ ፀሐፊ ባን ኪ ሙንን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ማኀበረሰቦች ያወገዙት ሲሆን፤ ታጣቂው አልሸዓባብ በበኩሉ ድርጊቱ የፈፀመው ከኬንያ ጋ ጦርነት ውጊያ ላይ ስለሆንን ነው ማለቱን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የመሐል ዳኛው ሸለመ በቀለ ራሳቸውን ከተሰየሙበት ችሎት አገለሉ፤ ፤የጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮቹ ጉዳይ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀርቧል
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለተከታታይ ሶስት ቀናት ፍርድ ቤት ሲመላለሱ የነበሩት 9 ተጠርጣሪዎች ዛሬ ለ19ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንደትላንትናው ሁሉ ዘግይቶ ተጀመረው ቸሎት የመሃል ዳኛው አንዲነሱ የቀረበውን አቤቱታ ምርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር ፡፡ በዚህም መሰረት ያለመሃል ዳኛ የመጡት ሁለት የግራ እና የቀኝ ዳኞች ተሰይመው አቤቱታውን ካነበቡ በኋላ ማለትም
1.ዳኛው ለአቃቤ ህግ ተደጋጋሚ የማሻሻል እድል በመስጠት አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብታችንን ነፍገውናል
2. ፍርድ ቤቱ ራሱ የሰጠውን ትእዛዝ ራሱ ሽሮ ያለምንም የፍሬ ሃሳብ ለውጥ ያለተሻሻለ ክስ ተቀብሏል
3. ሃሳባችንን ስንገልጽ ክልከላዎች ይደረጉብናል በመሆኑም ለዚህ የፍትህ መጓደል መሃል ዳኛው ሚና ዋሳኝ ነው ብለን ስለምናምን አንዲቀየሩልን እንጠይቃለን የሚል ሲሆን ዳኞቹ አቤቱታው አግባብነት የሌለው ነው ውሳኜው በመሃል ዳኞች ብቻ ሳይሆነ በጋራ የሚወሰን ስለሆነም ጭምር አቤቱታውን ውድቅ አድርገነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም እንዲህ አይነት አቤቱታ ውድቅ ሲሆን ለእያንዳንዳቸው ተከሳሾች 500 ብር የሚያስቀጣ ቢሆንም በስሜታውነት ነው ያቀረቡት በማለት ፍርድ ቤቱ አልፎታል ብለዋል ፡፡
በመቀጠል መሃል ዳኛውን ይዘው በመምጣት ችሎቱን አሟልተው አንደሚመለሱ ገልጸው መሃል ዳኛውን ይዘው መጥተው ደግመው ተሰይመዋል፡፡ መሃል ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ እነደተሰየሙ የምናገረው ነገር አለኝ በማለት ” ምንም አንኳን ሌሎቹ ዳኞች በዳኝነት አንድቀጥል ቢፈቅዱልኝም እኔ ግን በዚህ ክስ መቀጠል አልፈልግም ከዚህ በኋላ የምሰጠውም ዳኝነትም ቢሆን አመኔታ ስለማያገኝ አንድቀየር ማመልከቻ አስገብቻለሁ በማለት ራሳቸውን ከችሎቱ እንዲያገሉ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን ተከትሎ አዲስ ዳኛ ተተክቶ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል አንደሚቀበል እና ሌላ ቀጠሮ እነደሚሰጥ ተገልጿል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው ይህ ጉዳይ ተጠናቆ መቅረብ ሲገባው እነደገና ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱ አግባብ ስላልሆነ አጭር ቀጠሮ ይሰጥልን በማለታቸው የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ለየካቲት 11 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ጦማሪ አቤል ዋበላ ላይ እየደረሰ ያለ ማሰቃየት
ጦማሪ አቤክ ዋበላ በበኩሉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ለማቅረብ አንደሚፈልግ ተናግሮ ሲፈቀድለት ትላንትና ከፍርድ ቤት መልስ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ እንዳደረና ሲሰደብና ሲያዋርዱት አንደነበር ተናግሯል፡፡ ትላንትና ከፍርድ ቤት ወደ ማረሚያ ቤት በሚመለሱበት ወቅት ጠባቂዎቹ በካቴና ሳያስሩት አንደረሱት እና በራሳቸው ጥፋት የተነሳ ለምን አልታሰርክም ሲሉኝ ራሳችሁ ስላላሰራችሁኝ ብዬ በመመለሴ እናሳይሃለን በሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ወደ ቅሊንጦ መመለሱን አና እዚያ ከደረሰ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ ማደሩን ማእከላዊ በደረሰበት ድብደባ የተነሳ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያ ለማድረግ ተገዶ የነበረ በመሆኑ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያውንም አንደተቀማ ገልጾ ከዚህ ስወጣ ምን አንደሚጠብቀኝም አላውቅም ህይወቴ አደጋ ላይ ነው ሲል በከፍተኛ ምሬት እንባ እየተናነቀው ተናግሯል ፡፡ አቤት የደረሰበትን ሰቆቃ ሲናገር ችሎቱን ሲታደሙ የነበሩት ወላጅ አባቱ እህቱና ሌሎች ጓደኞች ሲያለቅሱ ታይተዋል፡፡
በቦታው የነበሩት የማረሚያ ቤቱ ተጠሪ ምክትል ሳጅን ዘውዱ በፍርድ ቤቱ ተጠርተው የተጠየቁ ሲሆን የማውቀው ነገር የለኝም በማለት መልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቤልን አቤቱታ በጽሁፍ አንዲያስገባ የተናገረ ሲሆነ ማረሚያ ቤቱ በሚቀጥለው ቀጠሮ ምላሹን ይዞ እነዲመጣ በማዘዝ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡
በተያያ ዜና በእስር ላይ በሚገኙት የዞን 9 ብሎገሮችና ጋዜጠኞች የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ጉዳይ ለተባበሩት መንግሰታት ድርጅት አለአግባብ እስር የተፈጸመባቸው ዜጎችን ጉዳይ lሚያይ ቡደን ቀርቧል ፡፡ በቡድኑ አሰራር መሰረት የኢትዬጲያ መንግሰት የቀረበበትን አቤቱታ አስመልክቶ መልስ ለመስጠት ጊዜ ይሰጠዋል፡፡ አቤቱታው
የታሰሩትን ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ያጋጠማቸውን የመብት ጥሰት ዝርዝር
2. የመታሰራቸው ምክንያት አግባብ አለመሆን የክሱን አለም አቀፍ መብቶችንም ሆነ የወንጀል ህግ መሰረቶች የጣሰ እና ሃሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ሲሆን መንግሰት ላይ የቀረበውን ክስ ያዘጋጁት Ethiopian Human Rights Project እና Freedom Now በተባሉ ድርጅቶች ናቸው፡፡
የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ
የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ
ቀን 02/06/2007 ዓ.ም
ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
አዲስ አበባ
ጉዳዩ፡- የልጄ ተመስገን ደሳለኝን ጉብኝት ይመለከታል
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከአብራኬ የወጣ ሁለተኛ ልጄ ነው፡፡ ገና ከህፃንነቱ ጀምሮ ለሰው አሣቢ፣ ሀገር ወዳድና ታታሪ ስለመሆኑ ከእኔ በላይ የሚያውቁት ይመሰክራሉ፡፡ ልጄ ተመስገን ለወገኔ አሰብኩ ባለ በእስር ቤት ያለጎብኚ እየተሰቃየብኝ ይገኛል፡፡ መቼም፣ የእናት ሆድ አያስችልምና እባካችሁ ልጄን ታደጉት፡፡ እባካችሁ ቢያንስ ካለበት እየሄድኩ የልጄን አይን እንዳይ እንዲፈቀድልኝ ተባበሩኝ፡፡ የልጄን ድምጽ ከሠማሁ ይኸዉ አንድ ወር ሞላኝ፡፡ ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ ደሳለኝ ለወንድሙ ብሎ የቋጠረዉን ምሣ ይዞ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቢሄድም በማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ተደብድቦ የያዘውን ምግብ እንኳ ሣያደርስ ሜዳ ላይ ተደፍቶ ተመልሷል፡፡ መቼም እናንተም ልጆች ይኖራችኋል፤ ደግሞም የልጅን ነገር ታውቁታላችሁ፡፡ እኔ አሁን በእርጅና ዕድሜዬ ላይ እገኛለሁ፡፡ ከአሁን በኋላ ብቆይም ለትንሽ ጊዜያት ነው፡፡ በዚህች ጊዜ ውስጥ ልጄን እየተመላለስኩ እየጠየኩ፣ ድምፁን እያሰማሁ፣ አይዞህ እያልኩ ብኖር ለእኔ መታደል ነበር፡፡ እባካችሁ እርዱኝ የልጄ ድምጽ ናፈቀኝ፡፡ እሱን መጎብኘት የተከለከለበት ምክንያት ምን እንደሆነ እንኳን እስካሁን አላወቅሁም፡፡ ከወንድሙ ድብደባ በኋላም ጥር 10 ወደ ጠዋት አካባቢ የሄዱት ጓደኞቹ እና ወንድሞቹ ሳያዩት ተመልሰዋል፡፡
ተምዬ ስታመም የሚያስታምመኝ፣ “አይዞሽ እማዬ” የሚለኝ ረዳቴ ነው፡፡ ሌላ ዘመድ የለኝም፡፡ የምተዳደረውም ልጆቼ ለፍተውና ደክመው በሚያመጧት ትንሽ ብር ነው፡፡ ዛሬ ግን ይኸዉ ልጆቼም ወንድማቸውን ለማየት እየተንከራተቱ ነው፡፡
በእናታችሁ ይዣችኋለሁ፤ ከቻላችሁ ልጄ እንዲፈታልኝ እና እኔም ያለችኝን ቀሪ የእድሜ ዘመን አይን አይኑን እያየሁ እንድኖር እንድታደርጉልኝ፤ ይህን ማድረግ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ካለበት ድረስ እየተመላለስኩ እኔና ሌሎች ልጆቼ እንዲሁም ወገኖቹ እንዲጠይቁት ቢደረግልኝ ስል በአክብሮት እጠይቃችኋለሁ፡፡ ልጄን አውቀዋለሁ፡፡ አንድ ነገር ሲገጥመዉ ሆድ ይብሰዋል፡፡ ቢያንስ እንኳን ቤተሰቦቹን ሲያይ ስለሚፅናና ይኸዉ እንዲፈቀድልኝ እማፀናለሁ፡፡ እኔ ምንም አቅም የሌለኝ አሮጊት ነኝ፡፡ ሁሉንም ለናንተ ሠጥቻችኋለሁ፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር እንደምታስተካክሉልኝ እና እንደገና የልጄን ፊት እንዳይ እንደምታደርጉኝ ሙሉ ተስፋ አለኝ፡፡
እንግዲህ የየካዉ ቅዱስ ሚካኤል ይከተላችሁ፡፡ መቼም የእናትን ሆድ ታውቁታላችሁ፤ የልጅ ነገር አያስችልም፡፡ ሆድም ቶሎ ይሸበራል፡፡ ስለዚህ እባካችሁ እኔንም ልጆቼንም እርዱን እንላለን፡፡
ግልባጭ
_ ለጠ/ሚኒስተር ፅ/ቤት
_ የህግና፣ ፍትህና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ
_ ለአፈ-ጉባኤ ፅ/ቤት
_ የሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ)
_ ለእምባ ጠባቂ
_ ለአሜሪካ ኢምባሲ
_ ለእንግሊዝ ኢምባሲ
ከሰላምታ ጋር
ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው
“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት
በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************
የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡
የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።
በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።
የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡
ድል የህዝብ ነው!!!
አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 26 ቀን 2007








