“ተወይኖብኛል… በዶ/ር አድማሱ ፀጋዬ ተልዕኮ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተባርሬአለሁ”
ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ከሦስት አሥርት ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ በሚሌኒየሙ መባቻ ወደ አገራቸው ተመልሰው ላለፉት ሰባት ዓመታት በማስተማር ሥራ ላይ ቆይተዋል፡፡ ምሁሩ በዋናነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር ቢኾኑም በሕግ ፋክልቲ፣ በሴንተር ፎር ሂዩማን ራይትስ፣ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም፣ በአምስት ኪሎ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፋክልቲ፣ በቴአትሪካል አርትስና በያሬድ የሙዚቃ ት/ቤትም አስተምረዋል፡፡ ለሰባት ተከታታይ ዓመታት በተጠቀሱት የትምህርት መስኮች በተለያየ ጊዜ ሲያስተምሩ ቢቆዩም ከጠየቁት የዓመት ዕረፍት (sabbatical leave) ጋር ተያይዞ ከዩኒቨርስቲው መሰናበታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲስ አድማስ ጋዜጣ በጉዳዩ ዙሪያ ከዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጋር ተከታዩን አጭር ቃለምልልስ አድርጓል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እና በእርስዎ መካከል ምንድን ነው የተፈጠረው?
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ጋር በኹለት ጥያቄዎች ዙሪያ የማይታረቅ ልዩነት ተፈጥሯል፡፡ በመጀመሪያ የዩኒቨርስቲው የሴኔት ሕግና የቅጥር ውሌ ላይ በግልጽ እንደሰፈረው÷ አንድ መምህር ለስድስት ዓመት በተከታታይ ከአስተማረ፣ ለአገለገለበት ዘመን የአንድ ዓመት የጥናትና ምርምር ዕረፍት (sabbatical leave) እንደሚሰጠው ተደንግጓል፡፡ ኾኖም ግን ዩኒቨርስቲው ‹‹የጡረታ ሥርዓተ – ሒደቱን አላሟላኽም›› በሚል በሕጉ ፊት የማይጸና ሰበብ ፈጥረው ይገባኻል ብለው ከፈቀዱልኝ በኋላ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ለማንኛውም መምህር ሥርዓተ ሒደቱን የማስፈጸም ሓላፊነት የሰው ሀብት አስተዳደሩ ድርሻ ኾኖ ሳለ፣ እኔን ተጠያቂ ማድረጋቸው ብዙዎችን አስገርሟል::
በነገራችን ላይ የጥናት ዕረፍት ፈቃዴን የጠየቅኹት ከሦስት ዓመት በፊት፣ ስድሳ ዓመት ሳይሞላኝ ነበር፡፡ በየሰበቡ ሲጓተት ስለቆየ ወደ ስድሳ ዓመቱ ገደብ ደረስኹ፡፡ ጉዳዩ ወደ ማኅበራዊ ፍርድ ቤት ከመሔዱ አስቀድሞ ውስጣዊ ተቋማዊ መፍትሔ ለማበጀት ወደ ዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ ቀርቦ ምላሽ ስጠባበቅ ከሦስት ወራት በላይ ተቆጥረዋል፡፡
የሥራ ውሌን በተመለከተ፣ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል የእኔን የአገልግሎት ቆይታ እንደሚፈልግና በተለይም በቅርቡ ለሚጀምረው የሦስተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ተሳትፎዬ እንደሚጠቅም በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ በመወሰኑ ውሌ እንዲራዘም ለማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ አካዳሚክ ኮሚሽን ጽፎልኝ ነበር፡፡ የማኅበራዊ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሓላፊዎች በተሰበሰቡበት፣ ኮሚሽኑ ጉዳዩን በአጀንዳ ይዞ ከተወያየበት በኋላ የፍልስፍና ትምህርት ክፍሉን ጥያቄ ዳግመኛ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶበት፣ ውሳኔው በማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ ዲኑ በፕ/ር ወልደ አምላክ በዕውቀት በኩል የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት ይኹንታቸውን እንዲሰጡበት(እንዲያጸድቁት) ተጠይቆ ነበር፡፡ ፕሬዝዳንቱ ግን ከአራት ወራት ያኽል ቸልተኝነት በኋላ ‹‹ወረቀቱ ይመጣለታል›› በሚል ለተከታዩ ሴሚስተር እንዳልደለደል በአዲሱ ዲን በኩል ለትምህርት ክፍሉ ሊቀ መንበር መመሪያ አስተላለፉ፡፡ መመሪያው የእኔን መሰል ጥያቄ ባቀረቡ ሌሎች መምህራን ላይም የተላለፈ ነበር፡፡ ከሦስት ወራት በላይ ደመወዜን ይዘው መክፈል ከአቆሙ በኋላ ‹‹ለሚመጣው ሴሚስተር አትመድቡት›› ማለት በአካዳሚያ ቋንቋ ግለሰቡ ተሰናብቷል ማለት ነው፡፡
በመሠረቱ፣ የትምህርት ክፍሌና አካዳሚክ ኮሚሽኑ የሥራ ውሌን መራዘም ተስማምተው ላቀረቡት ጥያቄ ሲኾን እንደወጉ ማጽደቅ አልያም በአስቸኳይ ውሳኔን ማሳወቅ ሲገባ፣ ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ወራት በላይ ማቆየታቸው ኢ-ሕጋዊ ነው፤ ሕጉን ጠብቆ በወጉ ለቀረበ ጥያቄ ከሦስት ወራት በላይ ምላሽ አለመስጠት እብሪት፣ ትዕቢትና ማናለብኝነት እንጂ ሌላ ሊኾን አይችልም፤ በተመሳሳይ ወቅት አንድ ዐይነት ጥያቄ በደብዳቤ ከአቀረብነው መምህራን መካከል፣ ለምሳሌ ከኛው ትምህርት ክፍል ዶ/ር በቀለ ጉተማ በሥራው እንዲቀጥል በቃል ትእዛዝ ፈቅደው፣ ለእኔ በአግባቡ ውሳኔ ሳይሰጡ ‹በሚቀጥለው ሴሚስተር እንዳትመድቡት’ ማለት የአድልዎ አቀራረብ ብቻ ሳይኾን በዘፈቀደና በግፊት የሚካሔድ አመራር መኾኑን ያረጋግጣል፡፡ በሌላ በኩል፣ ፕሬዝዳንቱ ዶ/ር አድማሱ ዩኒቨርስቲውን ለመምራት ያላቸውን ብቃት ከዚህ ቀደም በአደባባይ ስለጠየቅኹ በቂም በቀልና ኹን ብለው እኔን ለመጉዳት የደረሱበት ውሳኔ ነው፡፡
የጥናትና ምርምር ዕረፍት(sabbatical leave) በተመለከተ በጊዜው የኮሌጁ ዲን የነበሩት ዶ/ር ገብሬ ይንቴሶ፤ የፕሬዝዳንቱን ፍላጎት ተከትለው ከላይ እንደጠቀስኹት የሰጡኝን ፈቃድ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ጉዳዩን ለማየት ሥልጣን ወዳለው ፍርድ ቤት ከማምራቴ በፊት፣ የፕሬዝዳንቱን ምላሽ ከወዲኹ ባውቀውም አቤቱታዬን የግድ ለእርሳቸው ማቅረብ ነበረብኝ፡፡
በኮሌጁ የቀድሞ ዲን ውሳኔ ላይ ከዐሥር ገጽ ያላነሰ አባሪ ሰነዶች አያይዤ ጠዋት ላቀረብኹት አቤቱታ፣ ከቀትር በኋላ ‹‹በጥልቅ መርምረን›› በሚል በአንድ መሥመር የኮሌጁ ውሳኔ እንደማይሻር የሚገልጽ ፌዝና የቀልድ ምላሽ ነው የተሰጠኝ፡፡ ይህ የሚያሳየው ፕሬዝዳንቱ ለዩኒቨርስቲው መምህራን ከበሬታ የሌላቸውና አመራራቸውም ከሞራላዊነት የተራቆተ መኾኑን ነው፡፡ እኔ ግን ታዋቂው አርበኛ አበበ አረጋይ በአንድ ወቅት በፋሽስት ጣልያንና በባንዳ ለተከቡበት የተራቡ ጭፍሮቻቸው ‹‹ሞተን አንጠብቃቸውም፤ ተረጋግታችኹ ብሉ›› እንዳሉት፣ ከማባረር ያልተናነሰ የዘገየ አንድ ብጣሽ ወረቀት ገና ለገና ይመጣል ብዬ ሞቼ አልጠብቃቸውም፡፡
ከዚህ ቀደም የጡረታ ጊዜያቸው ደርሶ ለማራዘም የተፈቀደላቸው መምህራን አሉ ? ማለትም በዩኒቨርስቲው አሠራር የጡረታ ጊዜያቸው የደረሰ መምህራን ውላቸውን ማራዘም ይችላሉ?
በተለምዶ ስድሳ ዓመት የሞላቸው መምህራን የውል ማራዘሚያ ጊዜ ይጠይቃሉ፡፡ እኔ የማውቃቸውና በተደጋጋሚ የተጨመረላቸው መምህራንም አሉ፡፡ በጣም አስገራሚና በግቢው አነጋጋሪ የኾነው የእኔና የዶ/ር መረራ ጉዲና የውል ማራዘሚያ ጊዜ መከልከሉ ነው፡፡
ግን የዚህ ኹሉ መነሻ ምንድን ነው ብለው ይገምታሉ?
ከኹሉ በፊት የእኔ መከልከልና መሰናበት ከፖሊቲካ እይታ አኳያ የመነጨ መኾኑ የታወቀ ነው፡፡
ማለት…
በዩኒቨርስቲው በማስተማር ሥራ በቆየኹባቸው ባለፉት ሰባት ዓመታት፣ በጽሑፍና በተለያዩ መድረኮች የማደርጋቸው የዐደባባይ አእምሯዊ እንቅስቃሴዎች አልተወደዱም፡፡ እንዲያውም ለሹመኞች ቅርበት ያላቸው አንዳንድ ወዳጆቼ እንዳጫወቱኝ፣ ‹‹ዳኛቸው፣ ዩኒቨርስቲውን እንደ ደጀንና ገዥ መሬት ተጠቅሞ መድፍ ሲተኩስብን ቆይቷል›› ተብዬአለኹ፡፡ በርግጥ ይህ ዓይነቱ አቋም ከተወሰደ በኋላ በሥራ ገበታዬ እንድቀጥል አለመደረጉ አይገርመኝም፡፡
ከዩኒቨርስቲው በዚኽ መልኩ ሲሰናበቱ ምን ተሰማዎ?
እንደ እውነቱ ከኾነ የተደበላለቀ ስሜት ነው በውስጤ የተፈጠረው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ፣ ይህ ነገር ከሰባት ዓመት በኋላ መኾኑ አስደስቶኛል። ይኸውም የመጣኹበትን የማስተማር ዓላማ ከሌሎች ባልደረቦቼ ጋር በመኾን ለመስኩ ተተኪና ምሉዕ የኾኑ ተማሪዎች ለማፍራት በመብቃታችን አስደስቶኛል፡፡ ይህ ክልከላና ስንብት በቂ ምሩቃን ባላፈራንበት ከሦስትና ከአራት ዓመት በፊት ቢከሠት ኖሮ አዝን ነበር፡፡ በኹለተኛ ደረጃ፣ ‹የዓመት ዕረፍት(ሳባቲካል) አይሰጥኽም፤ ከእንግዲኽ ማስተማርም አትችልም› ስባል ለራሴ በጥልቀት ተሰምቶኝ ያልኹት፣ ‹‹አኹን ገና ኢትዮጵያዊ ኾንኩ፤ ኢትዮጵያዊ ማለት መብቱ የሚረገጥ ማለት ነው›› የሚል ነበር፡፡ በዚኽ ሰባት ዓመት ቆይታዬ ከአሜሪካ ሳልፈታ ይዠው የመጣኹት የነፃነትና የመብት አቅዋም፣ ከአገራችን ፖሊቲካዊ ነባራዊ ዕቀባ በተፃራሪው እንደ ልቤ እንድተችና ያለገደብ እንድናገር አስችሎኝ ነበር፡፡ አኹን ግን ሥርዓቱ ‹ይኼ አሜሪካ አይደለም፤ እንደ ጎረቤትኽ ሳይኾን እንደቤትኽ እደር› ብሎኛል፡፡ ይህን ስል ግን፣ እኔ በዕድሜዬ የምወልዳቸው ልጆች በኾነ ባልኾነ ክሥ ወኅኒ ቤት ተወርውረው ባሉበት ኹኔታ ከሥራ አባረሩኝ ብዬ የማለቅስ ሰው አይደለኹም፡፡ በእኒኽ ብሩህ ተስፋ ባላቸው ወጣቶች ላይ ከደረሰው አንጻር ሲታይ መብቴ መረገጡ እውነት ቢኾንም፣ የአገራችን ተረት ‹‹እናቱ ውኃ ልትቀዳ የወረደች ልጅና እናቱ የሞተችበት ልጅ አንድ ጋር ቆመው ያለቅሳሉ›› እንደሚባለው ይመስልብኛል፡፡
በመጨረሻም በአንድ በኩል፣ በውጭ ለብዙ ዓመት ቆይቼ ስመጣ የኢትዮጵያ ሕዝብ የት ከረምክ ሳይለኝ፣ ችሎታዬ በሚፈቅድልኝ ቦታ ሥራ ሰጠኝ፡፡ ለዚኽ ትልቅ ምስጋና ነው የማቀርበው፡፡ ኾኖም በሌላ በኩል የውስጥ አስተዳደሩና የውጭ የፖሊቲካ ኃይሎች በመተባበር መክረው ከሕዝብ ባገኘኹት ቸርነት ላይ ወይነውብኛል!
ከዚኽ በኋላስ ምን ዓይነት ሥራ ላይ ለማተኮር ያስባሉ?
ይህን ጥያቄ ዴሞክራሲና የሕግ የበላይነት ባለበት አገር ብትጠይቀኝ ኖሮ፣ ጉዳዩ በራሴ የሚወሰን በመኾኑ አኹኑኑ እመልስልኽ ነበር፤ ነገር ግን እንደ ቤትኽ እደር ተብዬአለኹና የጥያቄው ምላሽ በእኔ ብቻ የሚወሰን አይደለም፡፡ እንዲያውም ጥያቄው በአንድ ወቅት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ አሉ የተባለውን ያስታውሰኛል፡፡ አንድ ሹም ጃንሆይ ፊት ቀርበው የንጉሡ ትችትና ተግሣጽ ሲገጥማቸው፣ ‹‹እንዲያውም ግርማዊ ሆይ፣ የሰጡኝ ሹመት ይቅርብኝ፤ የአባቴን ርስት እያረስኩ እኖራለኹ›› አሏቸው፡፡ ጃንሆይም ወዲያው ‹‹እርሱንም እኛ ስንፈቅድ ነው…›› አሉ ይባላል፡፡
እኔም እንደ አቅሜ ለመሥራት ፍላጎት ቢኖረኝም፣ በቀጣይ ምን መሥራት እንደምችልና እንደማልችል ብያኔው በመሠረቱ ከእኔ ውጭ ነው፡፡ በተቻለኝ መጠን ግን በአለችኝ ቀሪ ዕድሜ አገሬን ለማገልገል ዝግጁ ነኝ፡ በዚኹ አጋጣሚ በቅርቡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሚገኝበትን ተቋማዊ ኹኔታ በተመለከተ አንድ ጽሑፍ እንደማቀርብ ከወዲኹ ለማሳወቅ እወዳለኹ፡፡
ምንጭ፡-አዲስ አድማስ ጋዜጣ
የማለዳ ወግ … ለሃጅ ጸሎት መጥቶ ሳውዲ የቀረው ገበሬ እንግልት
ነብዩ ሲራክ
(ከሳውዲ ዓረቢያ)
ወንድም ራያ ጀማል የ5 ወንድ እና የ3 ሴት ልጆች ጎልማሳ አባት ነው። ወደ ሳውዲ የመጣው ድህነት ፣ የኑሮ ውድነት ፣ የፖለቲካው ሙቀት አለያም የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ገፍቶት አይደለም ። ሳውዲ የመጣው ፣ በእስልምና እምነቱ በሚያዘው መሰረት በህይወት ዘመኑ የሚጠበቅበትን ለማድረግ ከብቶቹን ሽጦ የሃጅ ጸሎት ለማድረግ ነበር … ዳሩ ግና የጅማው ገበሬ ራያ ጀማል እንደ ቀሩት ጓደኞቹ ጸሎቱን አድርጎ ለመመለስ አልቀናውም! ከሀጃጅ ጓደኞቹ ተለይቶ ከቤተሰብ እንደራቀ ፣ ላለፉት ሁለት አመት ከመንፈቅ ገደማ ሳውዲ በእንግልት ጊዜውን ሊገፋ ግድ ብሎታል ። ምክንያቱም የሃጅ ጸሎቱን ከውኖ መካ ውስጥ መኪና አደጋ ደረሰበትና ነው !
የራያ ጀማል ጉዳት …
ራያ ጀማል በደረሰበት የመኪና ግጭት የተለያየ የአካሉ ክፍል በጠና ስለተጎዳ በከፍተኛ ህክምና መካ ውስጥ ለሁለት አመት ተኩል ገደማ በሳውዲ የመንግስት ሆስፒታል ሲረዳ ቆይቷል። የመጓጓዣ የማረፊያና የኢንሹራንስ እስከ 55 ሽህ ብር የሚደርስ ገንዘብ ከፍሏቸው ለጸሎት ያማጡት የሃጅ ኮሚቴዎችም ሆኑ የጅዳ ቆንስል ራያ ጀማልን ሊረዱት ቀርቶ ሊያዩት አልቻሉም! ይህ የሆነው ስለ ራያ ጀማል መረጃ ስላልነበራቸው አይመስለኝም ፣ ይህን ስል መረጃው እንደነበራቸው እኔም መረጃ አለኝና ነው!
ለሃጅ ጸሎት መጥቶ ስለደረሰበት የመኪና አደጋ በያዝነው ሳምንት የ50 ኢዩቬልዩ በአሉን ባከበረው የጀርመን ራዲዮ ዜናውን አቅርበነው ነበርና የቆንስሉም የሃጅ ኮሚቴ ኃላፊዎች ያውቃሉ ! ከዚህ ሁሉ በኋላም ልክ የዛሬ አንድ አመት ገደማ የጅዳ ቆንስል ተወካይ ራያ ጀማል በነበረበት የሽሻ ሆስፒታል ለሌላ ጉዳይ ሄደው አግኝተውትም እንደነበር ተገፊው ወንድም አጫውቶኛል ። ተወካዩ ራያ ጀማልን ስላጋጠመው የመኪና አደጋ በዝርዝር ጠይቀውት መመለሳቸውን ከተጎጅው ጋር በያዝነው ሳምንት ባንድ ምሽት ከወደቀበት የጅዳ ቆንስል አካባቢ በሚገኘው የአንድ አረብ ሃብታም አጥር ኩርትም ብሎ ባገኘሁት አጋጣሚ አጫውቶኛል። ይህ ሁሉ ሆኖ የዜጎች ጉዳይ የሚለመከታቸው የቆንስል ኃላፊዎች ራያ ጀማልም ሆነ ጉዳዩ የት ደረሰ ? ብለው አልጠየቁም !
ራያ ጀማልን ሳገኘው …
የወንድም ራያ ጀማልን ወደ ጅዳ መምጣትና አቤቱታ የማቅረቡ መረጃ ደረሰኝ ። ፈልጌ አጣሁት ። አንድ ምሽት ወደ ኮሚኒቲ ካፍቴሪያ ሳዘግም ከግቢው ውጭ ባለ አጥር ታዛ ተኝቶ አየሁት ። ራያ ጀማል ነው ግን አላልኩም። ተጠግቸ ለማነጋገር ብሞክርም መተኛቱን ተረዳሁና ትቸው ሄድኩ። በካፍቴሪያ አካባቢ ስለወደቀው ወንድም ጠየቅኩ ፣ ራያ ጀማል ለመሆኑ በቂ ምልክቱ በምርኩዝ “ክራንች ” እየታገዘ እንደሚመላለስ ሲነገረኝ አገግሞ ከመካ ሽሻ ሆስፒታል የወጣው ራያ ጀማል መሆኑን ተረዳሁ።
ራያ ጀማልን በቀጣዩ ቀን አግኝቸው አወጋን ። ከሁለት አመት በላይ በሳውዲ የመንግስት ሃኪም ቤት በህክምና ሲረዳ የቆየው ኢትዮጵያዊ በቀኝ ጎኑ ደገፍ በሚልባት ምርኩዝ “ክራንች” እየታገዘ ፣ አያነከስ ጉዳዩን ለማስፈጸም ላይ ታች ይላል። ፍትህ ሊያገኝና ወደ ሀገሩ ሊሸኝ ፣ የሞት መርዶውን ሰምተው ያለቀሱ ቤተሰቡን ተሰናክሎም ቢሆን ይቀላቀል ዘንድ ተስፋ ሰንቆ ከመጣበት ቤቱ የሚደግፈውም ሆነ ፣ ለጎኑ ማሳረፊያ መጠለያ የሚሰጠው አጥቷል ። የገዛ ሃገሩ ሰዎች ክብር አልሰጠነውምና በዚህ ሙቀት ከቆንስሉ ርቆ ባለው የአረብ ግንብ ጠጋ ብሎ ውሎ ያድራል …
ራያ ጀማልን ከፍ ሲል ኢትዮጵያዊነቱ ፣ ዝቅ ሲል ቋንቋውን የሚናገሩት የቀየው ልጆች ሞልተው ተርፈዋል ፣ ሁላችንም ግን ጉዳቱን እንኳ ጠጋ ብለን መጠየቅ ገዶናል ። አቅም የለሾቹ በጥድፊያው ብንወጠር ጧትና ማታ የሚያዩት የቆንስል ዲፕሎማቶችና የልማት ማህበር አባላት ብሶቱን ሰምተው ለምን ጨከኑበት ? ማለቴ አልቀረም …መልስ የለኝምና አዘንኩ !
የወንድም ራያ ጀማልን ጉዳይ በቅርብ ርቀት ላለፉት ሁለት ሳምንታት ላላነሰ ጊዜ ስከታተል ቆየሁ ። ጉዳዩ በቆንስ ኃላፊዎች በኩል ለጉዳይ ፈጻሚው ተላልፎ ጉዳዩ ሲንከባለል ቢሰነብትም ወደ መጨረሻ ራያ ጀማል ወደ ሀገሩ ለመላክ መወሰኑና ቲኬት ኮሚኒቲው እንዲያቀርብ ትብብር በቆንስል ሸሪፍ የመጠየቁ መረጃ ከአንድ የኮሚኒቲ የምክር ቤት አባል መረጃው ደረሰኝ ።
( በዚህ ዙሪያ ትናንት ባቀረብኩት ተመሳሳይ መረጃ ቅሬታ ያቀረቡልኝ አንድ ጠቋሚ ሃሳብ በመቀበል ሳጣራ ግን ቆንድል ሸሪፍ ኬሩ ራያ የ ጀማል የቲኬት ጥያቄውን ለኮሚኒቲ እንዲያቀርብ በስሙ ደበዳቤ ጽፈው ማዘጋጀታቸውንና ለኮሚኒቲው ምክትል በስልክ “ተባበሩት “ማለታቸውን ማረጋገጥ ችያለሁ)
ከቆንስሉ ግቢ ለቀን ወደ ኮሚኒቲ ጉዳዩን ለማጣራት ራያና እኔ ተያይዘን ስንወጣ ከቆንስሉ ባለጉዳዮች መግቢያ በር ነጻ ግልጋሎት የሚሰጡትን የድርጅትና የኦሮሞ ልማት ማህበር አባል ጋር ተገናኘን ። ሳያቸው በስጨት አልኩና ስማቸውን ጠርቸ ” የዚህ ወንድም ጉዳይ ወደ ሃገሩ ለመላክ ሲወሰን አንድም እንደ ዜጋ አለያም እንደ ተወላጅ ለምን መብቱን ማስከበር ለምን ተሳናችሁ? ” ስል ጠየቅኳቸው ። ግራ ተጋብተው …” ይህ ወንድም እንደ ተገልጋይ ሲወጣ ሲገባ ከማየት ውጭ ታሪኩን አላውቅም! ” ብለው ሲመልሱልኝ ራያን እንዲጠይቁት አድርጌ በኦሮምኛ አውርተው ጨረሱ ፣ወደኔ መለስ ብለው ” እውነት እልሃለሁ ፣ ምንም አይነት መረጃ የለኝም!” በማለት በአግርሞት መልሰውልኝ በእንግልቱ ዙሪያ ስናወጋ ሌላው የጅዳ ኮሚኒቲና የኦሮምያ ድርብ ስልጣን ያላቸው እድሜ ጠገብ ወዳጀን አገኘኋቸው …
ለኃላፊው ኮሚኒቲውም ቲኬት እንዲያቀርብ መጠየቁን በማውሳት “ራያው ጀማል ጉዳዩን ሳይጨርስ ለምን ቲኬት ለመስጠት ተስማማችሁ? ” ብየ ጠየቅኳቸው ። ኃላፊውም ስለ ቲኬቱ ጥያቄው መቅረቡን ከማመን ባለፈ በጉዳዩ ላይ ውሳኔ አለመሰጠቱን ጠቁመው ጉዳዩን ከቆንስል ሸሪፍ ኬሩ ጋር እየተነጋገሩበት እንደሆነ ጠቁመውኛል ። ከእኒህ ወዳጀ ጋር ውይይታችን እንደቀጠልን ወደ ካፍቴርያው አመራን። በድጋሜ ከራያ ጀማል ማግኘት አለባቸው የምለውን መረጃ ጠይቀው እንዲረዱ አደረግኩ ። መጠለያን በሚመለከትም ሃላፊነቱን ቆንስሉ ከወሰደ መጠጊያ እንደማይጠፋ በመጠቆም ፈቃድ ያመጡልኝ ዘንድም አሳሰብኳቸው ። ከሰነበተበት ሜዳ ወደ የግል መጠለያ ለመውሰድ ፍቃዱን እንደሚጠይቁልኝ አጫወቱኝ ። ኃላፊው የሰጡኝን ምላሽ ሁሉንም ለማመን ሞከሬ እንዲከታተሉት ጭምር ተመካክረን ተለያየን !
ይህ ከሆነ ከአንድ ቀን በኋላ የኦሮሞ ተወላጆች ማህበር አመታዊ በአላቸውን ሊያከብሩ ስለ አከባበሩ ዝግጅት መክረው ሲወጡ የኦሮሞው ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ራያ ጀማል ጉዳይ በተሰብሳቢዎች ተነስቶ ራያ ጀማልን ማነጋገራቸውን ሰማሁ ። ሁሉም በሆነው አዝነው በተለይም የድርጅት አባላቱ በቁጭት ለመፍትሄው ከቆንስሉ ጋር እንደሚመክሩ ጠቁመው ፣ ማረፊያ እስኪ ያዘጋጁለት በቆንስሉ ግቢ እንዲያድር አድረገው ተለያዩ ።
መሽቶ ነጋ ፣ የተባለው ደረሰ ፣ ቃል የገቡት የውሃ ሽታ ሆነው ቀሩ ! ባዩት ያዘኑት ሰብዕና አስገድዷቸው ለወንድም ራያ ጀማል ጎኑን የሚያሳርፍባት ፍራሽና መላብስ እንባቸውን እያዘሩ አቀብለውት ብቻ አልሄዱም ። እስከ ዛሬ ደረስ አደየመጡ ይጠይቁታል ! ራያ ጀማል ከዚያች ቀን በኋላ በኦሮሚያ ማህበር አባላት የዚያች ምሽት ተማጽኖ ከኮሚኒቲው ግቢ ማደር ቢችልም በቀጣዩ ቀናት ከቆንስሉና ከኮሚኒ ቲው ግቢ እንዳያድር ተከለከለ ! ወንድም ራያ ጀማል ያገገመው ስብራቱ በእንግልቱ እየተቀሰቀሰ እየወጋው እየተሰቃየ ነው ። ከሃገሩ ባንዴራ የቅርብ ርቀት ባሉት የአረብ ሃብታሞች አጥር ታዛ ኑሮን በመከራ በመግፋት ላይ ነው !
“ጉዳዩ ተሸፋፍኖ ሊሄድ ነው!” ብለን የሰጋነው የራያ ጀማል ጉዳይ ብዙዎቻችን ያስቆጨ ቢሆንም ዛሬ ነገሮች ተቀያይረዋል ብየ ነበር ከቀናት በፊት ። ይህንንም ያልኩት የቆንስሉ ጉዳይ ፈጻሚ አቶ መሃዲና ወንድም ራያ ጀማል ወደ መካ በማቅናት ከመካ ትራፊክ ፖሊስ ጋር የመነጋገራቸውን ሰናይ መረጃ ሰምቸ ነበርና ነው … እቀጥልበታለሁ ብየ ጉዳዩን በእንጥልጥል የተውኩት ጉዳይ ፈጻሚውና ወንድም ራያ ጀማል ከመካው ጉዞ ያገኙትን ውጤት ይዠ ለማምጣት ይቻለኛልና ነበር ። አነሆ ጉዳዩ የተያዘበትን የመካ ትራፊክ ፖሊስን ያነጋገሩት ጉዳይ ፈጻሚ የራያን መዝገብ አስቀርበው የገጨውን መኪና ባለቤት በስልክ ማነጋገራቸውን ተገፊው ወንድም አጫውቶኛል። ከዚህ ቀደም ራያ በሆስፒታል እያለ 10 ሽህ የሳውዲ ሪያል ሊሰጡት ፈቃደኛ ሆነው የነበሩት ሳውዲ ዛሬ 3 ሽህ ሪያል ካሳ ሊከፍሉ ፍቃደኛ መሆናቸውን መግለጻቸው ይህም ካልተቀበሉ ወደ ፍርድ ቤት መሄድ እንደሚችሉ መነገራቸውን ራያ ጀማል ገልጾልኛል። ወንድም ራያ ከአመት በፊት የሆነውን እያስታወሰ ይህው ሳውዲ የገጨው መኪና ባለቤት ወደ ሆስፒታል መጥተው “10 ሽህ ሪያል ካሳ ልክፈልህ እና ሹፊሬ ከእስር ይፈታ !” ብለው የሆስፒታሉ ዶክተሮች መቃወማቸውን ይናገራል። ምክንያታቸው ደግሞ “ጉዳቱ ከፍተኛ በመሆኑ በክፍያው ማነስ የተነሳ ኢንባሲ ቢጠይቀን አደጋ እንወድቃለን” በማለት ዶክተሮች ፈቃደኛ ባለመሆናቸውን ጉዳዩ መጨናገፉን ራያ ጀማል ከኦሮምኛና አረብኛውን ከአማርኛ ጋር እየቀላቀለ በቁጭት አጫውቶኛል።
ትናንት ምሽት ወንድም ራያ ጀማልን ደጋግሞ ስልክ ደውሎ እንድጎበኘው ጠይቆኝ ላነጋግረው ሄድኩ …ጉዳዩን ሰምቶ ብዙዎች ተስፋ ሰጥተነው የነበረው ተስፋ ተሟጦበት አገኘሁት ። ዛሬስ ምን አዲስ ነገር አለ ምን ሆንል አልኩት!
” አይይ አቶ ነቢዩ ትናንትና ዛሬ ሙቀቱም ነው መሰል ወገቤን መላ የተጎዳ አካሌን ይጠዘጥዘኛል፣ ያመኛል፣ ማረፊያ የለኝም ፣ ሜዳ ላይ ለ18 ቀናት ስሰቃይ ማረፊያ ያልሰጡኝ የሚረዱኝ አይመስለኝም ፣ ጉዳየን አሁን አንደዚህ በሜዳ ላይ ሆኘ በፍርድ ቤት ለመከታተል አልችልም!
እዚህ ላይ ራያ ጀማል አደጋ ከደረሰበት ጊዜ ጀምሮ አይተውት የማያውቁት የሃጅ ኮሚቴ ሃላፊዎችም ሆኑ የጅዳ ቆንስል የት ነበሩ? አልልም ። የጅዳን ኮሚኒቲ ቲኬት ከመጠየቁ በፊት መደረግ የነበረበት ጉዳይ ለምን ክትትል አልተደረገም ? አልልም ! የራያ ጀማል ጉዳይ አይነት እና ከዚያም የከፉ የመብት ጥሰቶች ተፈጽመው ቆንስል መስሪያ ቤቱ እያሸማገለ የጨረሳቸው ጉዳዮች በርካታ ናቸው። ያም ሆኖ ጉዳትን ከግምት ያሰረገባ ሽምግልና ነበር ብሎ ለማናገር እንቸገራለን። ይህ ካልሆነ ደግሞ ቢቀር ይሻላል። የመብት ጥሰትን በተልካሻ ካሳ ከማሸማገል ወደ ተገቢ ህጋዊ ፍርድ ቤት ማድረስ ይቀላልና ቢታሰብበት መልካም ነው ። ይህ ከማድግ ባለፈ እያሸማገሉ ጉዳዩን ሸፋፍኖ ተበዳይን ወደ ሀገር መሸኘት ሊቆም ይገባል ! ትናንት በቆንስል መስሪያ ቤቱ ዙሪያ የምናውቀው ፣ ጩኸን ማስቆም ያልቻልነው ጉዳይ በሽፍንፍንና በግዴለሽነት ዛሬ ሁነኛ ኃላፊ መጥተው ነገሮች እየተስተካከሉ ባለበት ሁኔታ በደል በቆዩት ዲፕሎማቶችና በሰራተኞች በእንዝላልነትና በሽፍንፍን ሲያልፍ ማየት ግን ነፍሴ አትፈቅድም !
በራያ ጀማል ጉዳይ እሱ እንዳለው ወራት የሚጨርሰውን ጉዳዩን እዚህ ሆኖ ለመከታተል ይከብዳል። ማረፊያ የለውምና ለከፋ ችግር ላይ ነው ። ራያ ጀማል ያለው ተጨባጭ አማራጭ አንድም መሄድና ወክልና መላክ ፣ መጠላያ አግኝቶ ጉዳዩን መከታተል ፣ ይህ ካልሆነም የሚሰጡትን ተቀብሎ ወደ ቀየው መቀላቀል ብቻ ነው። በእኒህ ውስብስብ አማራጮች ላይ ብቻውን ይወስን ለማለት የሚከብደው የሚሰጠው ሀሳብ ከችግር ጭንቀቱ አንጻር ይሆናልና ተበዳዩ ይጎዳል። የቆንስል ሃላፊዎችና የሚመለከታቸው በዚህ ረገድ አማራጮችን ከህግ አንጻር ተመልክተውና አዋቂ አመካክረው አስፈላጊውን ድጋፍ ቢያደርጉለት ቤተሰቡን በትኖ ለከፋ አደጋ በተዳረገው ወንድም ነፍስ መታደግ መቻል በምድርም በሰማይ ጽድቁ ለራስ ነው! ስለ ራያ ጀማል የማጠቃለው መብቱ እናስከብርለት ፣ የቻልን እንደ አቅማችን እንርዳው በማለት ነው ፣ የምለው ከዚህ ያለፈ አይደለም !
ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው
በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቃገኘው የክስ መዝገብ የተከሰሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በመያዝ የሕግ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው፡፡ ድብደባው የተፈፀመባቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ..ም. እነ አብርሃ ደስታ በነበራቸው የፍርደ ቤት ቀጠሮ ተገኝተው የሚጠበቅባቸውን የሕግ አገልግሎት ሰጥተው ከፍርደ ቤት ከወጡ በኋላ ብሔራዊ አረቄ ፋብሪካ አካባቢ ወደ አዋሳ ለሌላ የህግ አገልግሎት ለመስጠት እያመሩ በነበረበት ወቅት በማያውቁት ግለሰብ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክታል፡፡
ደብዳቢው ግለሰቡ ድብደባ ከፈፀመ በኋላ እሮጦ ለማምለጥ ሲሞክር በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ትብብር የተያዘ ሲሆን፤ በወቅቱም ደብዳቢው የአእምሮ ችግር እንዳለበት ለመምሰል ከሞከረ በኋላ የብአዴን-ኢህአዴግ አባል እንደሆነና 400 ብርም እንደተከፈለው መናገሩን እንዲሁም አዲስ አበባ ለቡ አካባቢ 105 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቶት ቤት እየሰራ እንደሆነ መግለፁን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ጠበቃ ተማም ነገ አዋሳ ላይ ሌላ የነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የፍርድ ቤት ጉዳይ ስላለ ዛሬ የግድ ሄደው ማደር ስለነበረባቸው ደብዳቢውን እንዲለቀቅ አድርገው ወደ አዋሳ ማምራታቸው ታውቋል፡፡
ጠበቃ ተማም ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በተጨማሪ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎችን፣ የተለያዩ ጋዜጠኞችን፣በሀገር ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን እና ሌሎች በርካታ የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ለማኀበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ከጥብቅና አገልግሎት በተጨማሪ በተለያዩ ጋዜጦች የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ይፅፉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ በዚህም ከመንግሥትና ከስርዓቱ ደጋፊዎች ከፍተኛ ጫና እየተደረገባቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች ቅጣት ተላለፈባቸው
᎐ተጨማሪ ቅጣትም ይጠብቃቸዋል፡፡
• “እኛ የደፈርነው ችሎት አሻንጉሊት ችሎት ነው” አብርሃ ደስታ
• “ችሎቱ ላይ ያጨበጨብነው በማፌዝ ሳይሆን በምሬት ነው” የሺዋስ አሰፋ
• “ፍትህ ተጠምተናል፣ ፍትህ ለኢትዮጵያ ህዝብ!” ዳንኤል ሺበሽ
በዘለዓለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ከስምንት ወራት በላይ በእስር ላይ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነት እንዲሁም የዓረና ትግራይ ፓርቲዎች አመራሮች ‹ችሎት በመድፈር ወንጀል› ጥፋተኛ በመባላቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም በልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት በሦስቱ አመራሮች ላይ እያንዳንዳቸው በሰባት ወራት እስራት እንዲቀጡ ተወስኖባቸዋል፡፡
የካቲት 26 ቀን 2007 ዓ.ም ተከሳሾች በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸውና ንብረትም እንደተወሰደባቸው በመግለጽ አቅርበውት ለነበረው አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ሙሉ ለሙሉ በመቀበል አቤቱታቸውን ውድቅ ማድረጉን ተከትሎ 5ኛ ተከሳሽ አቶ የሺዋስ አሰፋ በማጨብጨቡና 3ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታና 4ኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል ሺበሽ ሳይፈቀድላቸው ‹‹ጥሩ ፍርድ፣ ጥሩ ብይን›› በማለት አቶ የሺዋስን በመደገፍ ችሎት ደፍረዋል ተብለው ጥፋተኛ መሰኘታቸው ይታወሳል፡፡ በዚህ መሰረት ፍርድ ቤቱ ለዛሬ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ተሰይሞ በአብርሃ ደስታ፣ በየሺዋስ አሰፋ እና ዳንኤል ሺበሽ ላይ የ7 ወራት እስራት በይኖባቸዋል፡፡ ሦስቱም ተከሳሾች ፍርድ ቤቱ የሰጠውን ውሳኔ በመቃወም ድጋሜ ችሎት ውስጥ አጨብጭበዋል፡፡ በዚህም ድጋሜ ጥፋተኛ ተብለዋል፤ ከሁለት ቀናት በኋላም የቅጣት ውሳኔ ይወሰንባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሦስቱ ተከሳሾች ‹‹እድል ስጡን እንናገር፣ አቤቱታም አለን ተቀበሉን›› ቢሉም ፍርድ ቤቱ ሊሰማቸው አልፈለገም፡፡
በተለይ ዳንኤል ሺበሺ ‹‹ሌላ አቤቱታ አለኝ፣ ፍርድ ቤቱ ያዳምጠኝ›› ብሏል፡፡ ፍርድ ቤቱ አሁንም ችሎቱ ላይ እያፌዛችሁ ነው በሚል ጥፋተኛ ሲላቸው ሦስቱም አመራሮች ፍርድ ቤቱን ማስፈቀድ ሳያስፈልጋቸው አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ‹‹እኛ የደፈርነው ችሎት አሻንጉሊት ችሎት ነው፡፡ ‹Already› የተደፈረ ችሎት ነው›› ሲል አብርሃ ደስታ ተናግሯል፡፡ በዚህ ጊዜ ዳኞቹ ጣልቃ በመግባት፣ ‹‹የምትናገረው ነገር እንደገና ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ የሚወስድህ ጉዳይ ነው፤ ምርመራ ይደረግበታል›› ሲሉ አብርሃ በበኩሉ ‹‹አሁንስ ቢሆን የምናገረውን ፖሊስ እየሰማ አይደለምን?›› ሲል መልሷል፡፡ አቶ የሺዋስ አሰፋ በበኩሉ ‹‹ከስምንት ወር በላይ ታፍነናል፡፡ በህግ አይደለም የተያዝነው፡፡ ደግሞ ማጨብጨባችን በችሎቱ ከማፌዝ ሳይሆን ከምሬት በመነጨ ነው፡፡ ህገ-መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል፡፡ እኔ ለምሳሌ የሰማያዊ ፓርቲ አባል በመሆኔ ነው የታሰርኩት፡፡›› ብሏል፡፡
አቶ ዳንኤል ሺበሽ ድግሞ ‹‹አሁንም ችሎት ደፍራችኋል ካላችሁ ቅጣቱን ጨምሩብንና ሸኙን፡፡ በእርግጥ ዳኞች ላይ ያለውን ጫና እንረዳለን፡፡›› ሲል ችሎት ውስጥ ተናግሯል፡፡
በዚህ ሁኔታ በተከሳሾችና በችሎቱ መካከል ያለው አለመግባባት ሲጨምር ዳኞቹ መጋቢት 3/2007 ዓ.ም ለሁለተኛ ጊዜ የቅጣት ውሳኔ እንደሚሰጥ በመጥቀስ ሦስቱ ተከሳሾች ከችሎት በፖሊስ እንዲወጡ ተደርገዋል፡፡ ከችሎት እየወጡ እያሉም አቶ ዳንኤል ሺበሽ ‹‹ፍትህ ተጠምተናል፤ ፍትህ ለኢትዮጵያ ህዝብ!›› እያለ ችሎቱን ለቅቆ ወጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ሦስቱ ተከሳሾች ከችሎት መውጣታቸውን ተከትሎ፣ከዚህ ቀደም በማረሚያ ቤቱ ላይ በቀረበው አቤቱታ ዳኞች በሰጡት አስተያየት ላይ አቤቱታ አቅርቦ እንደነበር በማስታወስ አቤቱታው እንዲመዘገብለት የጠየቀው አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ ‹‹በበኩሌ ያሉኝን መረጃዎች እያቀረብኩ ስነ-ስርዓቱን አክብሬ ክርክሩን አቀጥላለሁ›› ሲል ተናግሯል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ- ኢትዮጵያ
የማለዳ ወግ…ለተሃድሶ ጀማሪዎች ለጅዳ ቆንሰል ተማጽኖየ !
* ፖለቲካውን እንደርስበታለን መብት በማስከበሩ ላይ በርቱ
ሰሞነኛ ወጋችን ፍተሻ ፣ አሰሳ ፣ ማጣራት ሆነና ልብን በሃዘን የሚሰብሩት ጩኸት እንዳይረሳ ሰጋሁ ። ለነገሩ የሳውዲ መገናኛ ብዙሃን በሚለቋቸው መረጃዎች ልክ መረጃ ተለዋውጠናል ባይባልም ፣ ያለፈውን አመትና የቆየውን ሁከት የሚያሳይ የቆየ ተንቀሳቃሽ ምስል እየለጠፉ የቆየነው አዲስ ነው ሳይሉና ሳያሳውቁን መረጃውን የሚለቁ የራሳቸን ሰዎች ተበራክተዋል። በዚህም ፍተሻ አለ የለም ወደሚለው አተካራ እየተዶልን ይመስላል። ተወደደም ተጠላ የሰው ሃገር የሰው ነው ፣ ሳውዲዎች በሃገራቸው ሰማይ ስር እንኳንስ በአደባባይ በተናገሩት ጊዜ ባሻቸው ጊዜ ህገ ወጥ ያሉትን ይዘው የማባረር መብት አላቸው ። አለመቀደም ነው እንጅ ሲላቸው ም የጠራረጉትን ጠራርገው ሲያበቁ ሁሉ ትተው የምህረት አዋጅ ሲሉ እናውቃለን ። ይህ ሲወርድ ሲዋረድ የምናውቀው አሰራራቸው ነው ። የዘንድሮውን ለየት የሚያፈርገው ” የምህረት አዋጅ የሚባል ነገር አይታሰብም “ማለቱ አይደለም ። ይልቁንም ስራቸውን በጣም በተረጋጋ ሁኔታ የመብት ጥሰት እንዳይኖርና ማህበራዊ ገጾች ጥሰቱን እየተቀባበሉ እንዳያወግዟቸው በጥንቃቄ እየተሰራ መሆኑን ልብ ብለን የግንባር ስጋ ከመሆን ካመለጥን መልካም ነው !
ከሰሞነኛው መረጃ ቅበላ ጎን ለጎን በተለያዪ አላባቢዎች ያሉ ወዳጆቸ ከሚያደርሱኝ መረጃዎች መካከል ሰሞነኛው የአፈሳ ፣ እስራት ፣ ማጣራቱ መረጃ ከአዕምሮየ አላዳፍን ያላቸውን የሚያሙ ግን ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባ ጉዳዮችን ማንሳት ወደድኩ ! ለዚህ የማለዳ ወግ መነሻ የሆነኝ ባሳለፍነው ሳምንት የዲያስፖራ ምክር ቤት የሚሉትን ለማቋቋም ከተሰበሰቡት የድርጅት ሰዎች አጠራርና የህዝብ ውክልና ጉዳይ ነው። ከአንድ አፍቃሬ ህወሃት ወዳጀ ጋር በዚህ ዙሪያ ስናወጋ ” ያን ሰሞን ተሃድሶ አድራጊውን ቆንስል እንዳላመሰገንክ ዛሬ በዲያስፖራው ጉዳይ ነካከህው! ” ነበር … ቀድሞውንም አሁንም በማይረባውና በማንግባባበትን የፖለቲካ ጉዳይ እንደርስበታለን መብት በማስከበሩ ላይ ግን ኢህአዴግ ምንቴስ ሳንል እንትጋ ፣ በርቱ እንበርታ ስል ባደረግነው ማሳረጊያ ተገወባባን … እናም ሰሞነኛ የመረጃ ግብአቱ ቦታውን ሳያጣብበው ለተገፋት የወገኖቻችን መብት እንደጋገፍ እንበርታ ስል የደረሰኝን መረጃ ተከትሎ በውስጤ ከሚጉላሉት ብዙ አሳዛኝ ታሪኮችን በጨረፍታ ዳስሸ መብት በማስከበሩ ረገድ መስማት የጀመሩት የጅዳ ቆንስል ተወካዮቻችንን ለመብታችን መከበር ጽኑልን ስለ መማጸን ፈለግኩ …
የሰሚራ ጉዳት …
ባሳለፍነው አንድ ቀር ገደማ በጥይት ተመታ በቢሻ ሆስፒታል በጥይት ተመታ ቆስላ በሆስፒታል ስለምትገኘው እህት ጉዳይ በማህበራዊ መረጃ መረቡ በኩል መረጃው ሲሰራጭ እኔም እጅ ገባ ። ብዙም ሳይቆይ በየድህረ ገጾች ተለቀቀ ። እኔም መረጃውን ለማጣራት ያፈረግኩት ሙከራ በተሳካ ማግስት በጅዳ የጅዳ ቆንስል መስሪያ ቤት ወደ ቦታው በማቅናት ተጎጅዋን ማግኘታቸውን፣ ማነጋገራቸውንና ጉዳዩን እየተከታተሉት የመሆኑን የምስራች አበሰሩን ፣ ደስም አለን! ምስጋናም አቀረብን !
ይህ ከሆነ ከሳምንት በኋላ የሰሚራን ጉዳይ ለመከታተል ስሞክር በመረጃ አሰባሰቡ ዙሪያ ያልጠበቅኩት ችግር መከሰቱን ሰማሁ ፣ ረፋዱ ላይ ወደ ጅዳ ቆብስል ጎራ በማለት ጉዳዩን ከያዙት ዲፕሎማት የደረሰኝን መረጃ መሰረት በማድረግ ለማጣራት ብሞክርም ሃላፊው ለስራ ስለወጡ ማግኘት አልቻልኩም ። ያም ሆኖ በቦታው ላገኘኋቸው መልዕክቴን አስተላልፊ ተመለስኩ ! ይህ በእንዲህ እንዳለ በጉዳዩ ዙሪያ ያናከርኩት አንድ ወዳጀ በደረሰኝ መረጃ ዙሪያ አንድ ወንድም ዘርዘር ያለ መረጃ ያለው መልዕክት ከነ ተንቀሳቃሽ ፊልም ጭምር የያዘ መረጃ ማስተላለፉን ጠቆመኝ ። መረጃውን ከያዘው ወንድም መረጃ ትመለከቱት ዘንድ ከዚህ ገሰር አያይዠዋለሁ !
ሩቅያ …
ከወራት በፊት እዚህ ጅዳ ውስጥ በአንድ ት/ቤት የቅርብ ርቀት በተከሰተ የመኪና አደጋ የአሰሪዎቿን ልጆች ለማዳን ስትል ለከባድ አደጋ የተጋለጠች ሩቅያ የተባከች እህት አሳዛኝ ታሪክ አውቃለሁ። የሩቅያ ታሪክ በአረብ መገናኛ ብዙሃን ሳይቀር ቀርቧል። ከአደጋው በኋላ ራሷን የማታውቀው ሩቅያ በአንድ ሆስፒታል ለወራት ስትታከም ቆይታ ” ከህመሟ አገግማለች !” ተብሎ ከሆስፒታል ወጥታለች ። ያለ ወገን ደገሰፊ አምስት እህት ወንድሞችዋን የምታስተምር ትጉህ ክጅ አግር ናት ሰሚራ። ለህክምና ብትወጣም እርዳታ በማድረግ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ነዋሪዎች ግን አልረሷትም ። አደጋ ያደረሰባት ደግሞ ከእስር ወጥቷል ። እንዴት ወጣ አይታወቅም ። በውል ቋሚ የሆነ የሚደግፍ የሚረዳት ግን የለም ። ጉዳዩን በፊት ገጼ ካቀረብኩት በኋላ ለጅዳ ቆንስል አሳውቄ ነበር ። በወቅቱ ሄደው ጠይቀዋታል።እየተመላለሱም ጉዳዩን የተከታተሉ መሆኑን የገለጹልኝ የጅዳ ቆንስል ባለደረባ የሩቅያን ጉዳይ እንዳልረሱት ከቀናት በፊት አጫውተውኛል ። ይሁን … ብዙዎች ግን የሩቅያ ጉዳይ ተድበስብሶ እንዳይቀር እንማጸናለን !
መሐመድ …
መሃመድ ይባላል ፣ በ3 አመት የብላቴና እድሜው ድክ ድክ እያለ ለቀላል ቀዶ ህክምና ወደ ሃኪም ቤት ገባ ፣ ከቀዶ ጥገናው ክፍል ከገባ ከሰአታት በኋላ ከቀዶ ህክምናው ቢወጣም አልነቃ አለ። ሰአታት ተቆጠሩ ፣ ቀኖች ሲከተሉ ጉዳይ አስደንጋጭ እየሆነ መጣ ! ወላጅና የቤተሰብ አባላት የሚይዙ የሚጨብጡት ጠፋባቸው። ህክምናውን ያከናወኑት የሚሰጡት የተስፋ መልስ ጭብጥ እውንት ጠፋበት … ቀናት በቀናት ተተክተው ሳምታት ወርን ሲወልዱ የብላቴናው አለመንቃት በሆስፒታሉ ሃኪሞች ስህተት እንደሆነ ይፋ ተነገረ ! ይህ ሲሆን ታዲያ ከሆስፒታሉ የተሰጠው ምላሽ አስደንጋጭ ነበር ። የሶስት አምት ልጃቸው መሃመድ በህክምና ስህተት ማደንዘዣ በዝቶበት እንዳልነቃነና ይህን ስህተት የፈጸመው ዶር ከስራው መባረሩ ተገልጾላቸው መሃመድ እስኪነቃ አስፈላጊ ህክምናና ክፍል ተሰጥቶት ህክምናውን በነጻ እንደሚቀጥል ለወላጆች መርዶ ተነገራቸው ! ይህንን በደል ለማሰማት ወላጆቹ ከጅዳ ቆንሰል ከፍ እስካሉ የመንግስት መ/ቤቶች ቢደርሱም ሰሚ አላገኙም። እንዲያ ሆኖ ብላቴናው ከሰመመንና ከተኛበት አልጋ ሳይነቃ 11 ኛ አመቱን ዘንድሮ ይዟል …
ጉዳዩ አሳዛኝ ነው ከማለት በላይ ነው … ይህ በደል ወደ ሳውዲ ከፍተኛ የመንግስት አካላት ስለመታወቁ ግን አሁንም እጠራጠራለሁ ፣ ይህንኑ ለማጣራት አምድ ወዳጀ ከቤተሰብ አባላቱ ጋር ሊያገናኘኝ ቃል ገብቶልኛል። ያ ሙሉ አሳዛኙን መረጃ በዝርዝር እናወጋዋለን ! .. ባሳለፋቸው የብላቴናውና የወላጆቹ አስከፊ የጨለማ የመከራ አመታት ብላቴናውን የአልጋ ቁራኛ ህክምና በሚሰጠው ክፍል ሄጀ ለማየት ካንድም ሁለት ሶስቴ በሩ ላይ ደረስ ደርሸ ህመሙን መቋቋም ሳልችል ቀርቸ ሳላየው ተመልሻለሁ ! መውለድ ከባድ መሆኑንም የተረዳሁት ያኔ ነበር … የመሃመድ ጉዳይ በአንባሳደር ተክለአብ በአንባሳደር መርዋን እና በቆንስል ጀኔራል ዘነበ እየታወቀ እልባት የሚሰጥ የሚከታተለው ጠፍቶ ጉዳዩ ተድበስብሶ እዚህ ደርሷል ። ይህም ያማል ! ዘንድሮ ግን በቆንስሉ ትጉህ የተሃድሶው መሪዎች መፍትሔ ያገኙለት ዘንድ እንማጸናለን !
ስላለፈው ወቃሹ ታሪክ እንጅ እኛ አይደለንም፣ አንወቃቀስም …
የጀዛኑን ካልድ ለሶስት አመታት የቀጠለ አበሳ ሰሞኑን እልባት ሊያገኝ መሆኑን ሰምቻለሁ ፣ በካልድም ጉዳይም ሆነ በስም አይጠሬውን የአንድ እህት ሬሳ ታሪክ የምናወራው ዛሬ አይደለም ፣ አልነካካውም ! ስላለፈው መብት ጥሰትና የመብት ጥበቃ ጉድለት መረጃዎችን ከመሰብሰብ አልፈን ፣ ያለፈውን ጉዳይ እያነሳን መወቃቀሱ አይጠቅምም !
ዛሬ ሌላ ቀን ነው ፣ ላለፉት 11 ዓመታት እልባት ካልተሰጠው ከመሃመድ ጉዳይ ጀምሮ እስከ ጀዛኑን ካልድ ፣ በአሰሪዋ የፈላ ውሃ የተደፋባትና ላለፉት አንድ አመት ጉዳዩዋን በጅዳ ቆንስል ሆና የምትከታተለው የሄለን ጉዳይ ፣ በቅርብ በጥይት ከተመታችው የሰሚራ ጉዳይ እና መኪና ተገጭታ አካሏ እስከ ጎደለው ሩቅያ የዜጎችን መብት ለማስከበር የመንግስት ተወካዮች የተከፈተው በር እንዳይዘጋ ስንማጸን ፣ መረጃዎችን በማሰባሰቡ ረገድ ግልጽ መረጃ በመለዋዎጥ የመንግስት ተወካዮች መብታችም ያስከብሩልን ዘንድ ደጋግሜ እማጸናችኋለሁ !





