Tag Archives: Ethiopia

የመሐል ዳኛው ሸለመ በቀለ ራሳቸውን ከተሰየሙበት ችሎት አገለሉ፤ ፤የጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮቹ ጉዳይ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀርቧል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለተከታታይ ሶስት ቀናት ፍርድ ቤት ሲመላለሱ የነበሩት 9 ተጠርጣሪዎች ዛሬ ለ19ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንደትላንትናው ሁሉ ዘግይቶ ተጀመረው ቸሎት የመሃል ዳኛው አንዲነሱ የቀረበውን አቤቱታ ምርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር ፡፡ በዚህም መሰረት ያለመሃል ዳኛ የመጡት ሁለት የግራ እና የቀኝ ዳኞች ተሰይመው አቤቱታውን ካነበቡ በኋላ ማለትም
1.ዳኛው ለአቃቤ ህግ ተደጋጋሚ የማሻሻል እድል በመስጠት አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብታችንን ነፍገውናል
2. ፍርድ ቤቱ ራሱ የሰጠውን ትእዛዝ ራሱ ሽሮ ያለምንም የፍሬ ሃሳብ ለውጥ ያለተሻሻለ ክስ ተቀብሏል
3. ሃሳባችንን ስንገልጽ ክልከላዎች ይደረጉብናል በመሆኑም ለዚህ የፍትህ መጓደል መሃል ዳኛው ሚና ዋሳኝ ነው ብለን ስለምናምን አንዲቀየሩልን እንጠይቃለን የሚል ሲሆን ዳኞቹ አቤቱታው አግባብነት የሌለው ነው ውሳኜው በመሃል ዳኞች ብቻ ሳይሆነ በጋራ የሚወሰን ስለሆነም ጭምር አቤቱታውን ውድቅ አድርገነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም እንዲህ አይነት አቤቱታ ውድቅ ሲሆን ለእያንዳንዳቸው ተከሳሾች 500 ብር የሚያስቀጣ ቢሆንም በስሜታውነት ነው ያቀረቡት በማለት ፍርድ ቤቱ አልፎታል ብለዋል ፡፡

በመቀጠል መሃል ዳኛውን ይዘው በመምጣት ችሎቱን አሟልተው አንደሚመለሱ ገልጸው መሃል ዳኛውን ይዘው መጥተው ደግመው ተሰይመዋል፡፡ መሃል ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ እነደተሰየሙ የምናገረው ነገር አለኝ በማለት ” ምንም አንኳን ሌሎቹ ዳኞች በዳኝነት አንድቀጥል ቢፈቅዱልኝም እኔ ግን በዚህ ክስ መቀጠል አልፈልግም ከዚህ በኋላ የምሰጠውም ዳኝነትም ቢሆን አመኔታ ስለማያገኝ አንድቀየር ማመልከቻ አስገብቻለሁ በማለት ራሳቸውን ከችሎቱ እንዲያገሉ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን ተከትሎ አዲስ ዳኛ ተተክቶ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል አንደሚቀበል እና ሌላ ቀጠሮ እነደሚሰጥ ተገልጿል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው ይህ ጉዳይ ተጠናቆ መቅረብ ሲገባው እነደገና ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱ አግባብ ስላልሆነ አጭር ቀጠሮ ይሰጥልን በማለታቸው የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ለየካቲት 11 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ጦማሪ አቤል ዋበላ ላይ እየደረሰ ያለ ማሰቃየት

ጦማሪ አቤክ ዋበላ በበኩሉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ለማቅረብ አንደሚፈልግ ተናግሮ ሲፈቀድለት ትላንትና ከፍርድ ቤት መልስ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ እንዳደረና ሲሰደብና ሲያዋርዱት አንደነበር ተናግሯል፡፡ ትላንትና ከፍርድ ቤት ወደ ማረሚያ ቤት በሚመለሱበት ወቅት ጠባቂዎቹ በካቴና ሳያስሩት አንደረሱት እና በራሳቸው ጥፋት የተነሳ ለምን አልታሰርክም ሲሉኝ ራሳችሁ ስላላሰራችሁኝ ብዬ በመመለሴ እናሳይሃለን በሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ወደ ቅሊንጦ መመለሱን አና እዚያ ከደረሰ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ ማደሩን ማእከላዊ በደረሰበት ድብደባ የተነሳ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያ ለማድረግ ተገዶ የነበረ በመሆኑ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያውንም አንደተቀማ ገልጾ ከዚህ ስወጣ ምን አንደሚጠብቀኝም አላውቅም ህይወቴ አደጋ ላይ ነው ሲል በከፍተኛ ምሬት እንባ እየተናነቀው ተናግሯል ፡፡ አቤት የደረሰበትን ሰቆቃ ሲናገር ችሎቱን ሲታደሙ የነበሩት ወላጅ አባቱ እህቱና ሌሎች ጓደኞች ሲያለቅሱ ታይተዋል፡፡

በቦታው የነበሩት የማረሚያ ቤቱ ተጠሪ ምክትል ሳጅን ዘውዱ በፍርድ ቤቱ ተጠርተው የተጠየቁ ሲሆን የማውቀው ነገር የለኝም በማለት መልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቤልን አቤቱታ በጽሁፍ አንዲያስገባ የተናገረ ሲሆነ ማረሚያ ቤቱ በሚቀጥለው ቀጠሮ ምላሹን ይዞ እነዲመጣ በማዘዝ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡

UN

በተያያ ዜና  በእስር ላይ በሚገኙት የዞን 9 ብሎገሮችና  ጋዜጠኞች  የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ጉዳይ ለተባበሩት መንግሰታት ድርጅት አለአግባብ እስር የተፈጸመባቸው ዜጎችን ጉዳይ lሚያይ ቡደን ቀርቧል ፡፡ በቡድኑ አሰራር መሰረት የኢትዬጲያ መንግሰት የቀረበበትን አቤቱታ አስመልክቶ መልስ ለመስጠት ጊዜ ይሰጠዋል፡፡ አቤቱታው

የታሰሩትን ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ያጋጠማቸውን የመብት ጥሰት ዝርዝር
2. የመታሰራቸው ምክንያት አግባብ አለመሆን የክሱን አለም አቀፍ መብቶችንም ሆነ የወንጀል ህግ መሰረቶች የጣሰ እና ሃሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ሲሆን መንግሰት ላይ የቀረበውን ክስ ያዘጋጁት Ethiopian Human Rights Project እና Freedom Now በተባሉ ድርጅቶች ናቸው፡፡

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

ቀን 02/06/2007 ዓ.ም
ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን

አዲስ አበባ

ጉዳዩ፡- የልጄ ተመስገን ደሳለኝን ጉብኝት ይመለከታል

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከአብራኬ የወጣ ሁለተኛ ልጄ ነው፡፡ ገና ከህፃንነቱ ጀምሮ ለሰው አሣቢ፣ ሀገር ወዳድና ታታሪ ስለመሆኑ ከእኔ በላይ የሚያውቁት ይመሰክራሉ፡፡ ልጄ ተመስገን ለወገኔ አሰብኩ ባለ በእስር ቤት ያለጎብኚ እየተሰቃየብኝ ይገኛል፡፡ መቼም፣ የእናት ሆድ አያስችልምና እባካችሁ ልጄን ታደጉት፡፡ እባካችሁ ቢያንስ ካለበት እየሄድኩ የልጄን አይን እንዳይ እንዲፈቀድልኝ ተባበሩኝ፡፡ የልጄን ድምጽ ከሠማሁ ይኸዉ አንድ ወር ሞላኝ፡፡ ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ ደሳለኝ ለወንድሙ ብሎ የቋጠረዉን ምሣ ይዞ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቢሄድም በማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ተደብድቦ የያዘውን ምግብ እንኳ ሣያደርስ ሜዳ ላይ ተደፍቶ ተመልሷል፡፡ መቼም እናንተም ልጆች ይኖራችኋል፤ ደግሞም የልጅን ነገር ታውቁታላችሁ፡፡ እኔ አሁን በእርጅና ዕድሜዬ ላይ እገኛለሁ፡፡ ከአሁን በኋላ ብቆይም ለትንሽ ጊዜያት ነው፡፡ በዚህች ጊዜ ውስጥ ልጄን እየተመላለስኩ እየጠየኩ፣ ድምፁን እያሰማሁ፣ አይዞህ እያልኩ ብኖር ለእኔ መታደል ነበር፡፡ እባካችሁ እርዱኝ የልጄ ድምጽ ናፈቀኝ፡፡ እሱን መጎብኘት የተከለከለበት ምክንያት ምን እንደሆነ እንኳን እስካሁን አላወቅሁም፡፡ ከወንድሙ ድብደባ በኋላም ጥር 10 ወደ ጠዋት አካባቢ የሄዱት ጓደኞቹ እና ወንድሞቹ ሳያዩት ተመልሰዋል፡፡

ተምዬ ስታመም የሚያስታምመኝ፣ “አይዞሽ እማዬ” የሚለኝ ረዳቴ ነው፡፡ ሌላ ዘመድ የለኝም፡፡ የምተዳደረውም ልጆቼ ለፍተውና ደክመው በሚያመጧት ትንሽ ብር ነው፡፡ ዛሬ ግን ይኸዉ ልጆቼም ወንድማቸውን ለማየት እየተንከራተቱ ነው፡፡

በእናታችሁ ይዣችኋለሁ፤ ከቻላችሁ ልጄ እንዲፈታልኝ እና እኔም ያለችኝን ቀሪ የእድሜ ዘመን አይን አይኑን እያየሁ እንድኖር እንድታደርጉልኝ፤ ይህን ማድረግ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ካለበት ድረስ እየተመላለስኩ እኔና ሌሎች ልጆቼ እንዲሁም ወገኖቹ እንዲጠይቁት ቢደረግልኝ ስል በአክብሮት እጠይቃችኋለሁ፡፡ ልጄን አውቀዋለሁ፡፡ አንድ ነገር ሲገጥመዉ ሆድ ይብሰዋል፡፡ ቢያንስ እንኳን ቤተሰቦቹን ሲያይ ስለሚፅናና ይኸዉ እንዲፈቀድልኝ እማፀናለሁ፡፡ እኔ ምንም አቅም የሌለኝ አሮጊት ነኝ፡፡ ሁሉንም ለናንተ ሠጥቻችኋለሁ፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር እንደምታስተካክሉልኝ እና እንደገና የልጄን ፊት እንዳይ እንደምታደርጉኝ ሙሉ ተስፋ አለኝ፡፡

እንግዲህ የየካዉ ቅዱስ ሚካኤል ይከተላችሁ፡፡ መቼም የእናትን ሆድ ታውቁታላችሁ፤ የልጅ ነገር አያስችልም፡፡ ሆድም ቶሎ ይሸበራል፡፡ ስለዚህ እባካችሁ እኔንም ልጆቼንም እርዱን እንላለን፡፡

ግልባጭ
_ ለጠ/ሚኒስተር ፅ/ቤት
_ የህግና፣ ፍትህና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ
_ ለአፈ-ጉባኤ ፅ/ቤት
_ የሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ)
_ ለእምባ ጠባቂ
_ ለአሜሪካ ኢምባሲ
_ ለእንግሊዝ ኢምባሲ

ከሰላምታ ጋር
ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

የአንድነት ፓርቲ አባላት በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን ተቀላቀሉ

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ በወሰኑብን ፖለቲካዊ ውሳኔ ምክንያት አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን ተነጥቀናል ያሉ የአንድነት ፓርቲ አባላት› በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስታወቁ፡፡

በእነ በላይ ፍቃዱ አመራርነት አንድነት ፓርቲን በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ሲመሩ የነበሩ አመራሮች ዛሬ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት ከቀድሞ ፓርቲያቸው አንድነት ጋር የፕሮግራምም ሆነ የስትራቴጂ ተመሳሳይነት ወዳለው ሰማያዊ ፓርቲ ተቀላቅለው ሰላማዊ ትግላቸውን ለመቀጠል መወሰናቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡

መግለጫውን የ”ቀድሞው አንድነት ፓርቲ” አፈ ጉባዔ የነበሩት አቶ አበበ አካሉ፣ ምክትል አፈ ጉባዔው አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እንዲሁም የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊው አቶ ስንታየሁ ቸኮል ሌሎችን በመወከል ሰጥተዋል፡፡

“የምናምነው በሰላማዊ ትግል ብቻ ነው፡፡ ይህን ሰላማዊ ትግል ለመምራት ደግሞ ሰማያዊ ፓርቲ ብቁ ነው ብለን በማመን ፓርቲውን ተቀላቅለናል” ብለዋል በመግለጫው ላይ የተወከሉት አዲሶቹ የሰማያዊ አባላት፡፡
በዚህ መሰረትም በርከት ያሉ አመራሮችና አባላት በይፋ የሰማያዊ ፓርቲ የአባልነት ፎርም ሞልተዋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአንድነት አባላት ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስመልክቶ መግለጫ ለመስጠት ወደ ሰማያዊ ቢሮ ባቀኑበት ወቅት፤ፖሊስ ሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ድረስ በመግባት “በሰማያዊ ስም መግለጫ የሚሰጡ አካላት እንዳሉ ሰለሰማን ነው” በሚል ለፓርቲው አመራሮች ጥያቄ ማቅረባቸውን ከስፍራው የደረሰን ዘገባ አመልክቷል፡፡

“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት

በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-

udj

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************

የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡

የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።

በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።

የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ጥር 26 ቀን 2007

ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የዞን ዘጠኝ ብሎገሮችና ጋዜጠኞች፤ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ፡፡
ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ለ17ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ልደታ ምድብ 9ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ሸለመ በቀለ “የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስከበሩልንም” በሚል ከችሎት እንዲነሱ በጽሑፍ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተሰየመው ተሻሽሎ ቀርቧል በተባለው የአቃቤ ህግ ክስ ላይ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመስማት እንደነበር ዳኞቹ ቢናገሩም፣ ተከሳሾች አቤቱታ እንዳላቸው በመግለጽ የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ዝግጁዎች አለመሆናቸውን ለችሎቱ ማስረዳት ችለዋል፡፡
ተከሳሾች ‹‹እኛ በሰብሳቢ ዳኛው ላይ አቤቱታ አለን፤ ፍርድ ቤቱ የራሱን ውሳኔ እንኳ አላከበረም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የእምነት ክህደት ቃላችንን ለመስጠት ዝግጁዎች አይደለንም›› በሚል ፍርድ ቤቱ አቤቱታቸውን እንዲቀበል ጠይቀዋል፡፡

ዳኛ ሸለመ በቀለ “ፍርድ ቤቱ ቃሉን አላከበረም›› በሚለው ጉዳይ ላይ መልስ ሲሰጡ ‹‹የእኛን ውሳኔ የማትቀበሉ ከሆነ ጉዳዩን በይግባኝ እንዲታይ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
“ላለፉት ስድስት ወራት በነበረው የክርክሩ ሂደት የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ሂደቱን በአግባቡ በመምራት የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስጠበቁልንም፡፡ በተለያየ ጊዜም ሐሳባችን ለመግለጽ ስንሞክር ክልከላ አድርገውብናል፡፡ አሁን ደግሞ ችሎቱ ራሱ የሰጠውን ትዕዛዝ ራሱ ሽሮ ፈጽሞ ልንረዳው በማንችለውና የመከላከል መብታችንን በሚያጣብብ የክስ ሁኔታ ክርክሩን እንድንቀጥል ሲበየንብን የችሎቱ ሰብሳቢ ወሳኝ ሚና ነበራቸው” ሲሉ ተከሳሾች በሰብሳቢ ዳኛው ላይ ቅሬታቸውን በአቤቱታቸው ገልፀዋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ከችሎት እንዲነሱ የሚጠይቀውን አቤቱታ አይቶ ነገ ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል ሲል ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡