Tag Archives: Ethiopian freedom of expression

በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፣ የመብት አራማጆች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ የበርካታ ዜጎች እስር አሁንም እንደቀጠለ ነው

የኢትዮጵያ መንግሥት የተነሳበት ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ባወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጋዜጠኞችን፣ የመብት አራማጆችን፣ የማኀበራዊ ገፅ አምደኞችን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራርና አባለትን ጨምሮ በርካታ ዜጎችን ማሰሩን ቀጥሏል፡፡

በተለይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈፀም እንደተቋቋመ የተነገረለት ኮማንድ ፖስት ጠረጠርኳቸው ያላቸውን ዜጎች ሁሉ እያሰረ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት ጋዜጠኛ አናኒያ ሶሪ፣ ጋዜጠኛ አሊያስ ገብሩ፣ ጋዜጠኛ አብዱ ገዳ፣ የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ የነበሩት እና ከዚህ ቀደም ከአንድ ዓመት በላይ በመንግሥት ታስረው በነፃ የተሰናበቱት አቶ ዳንኤል ሺበሺ እና የማኀበራዊ ሚዲያ አምደኛው ኢዩኤል ፍስሃ መታሰራቸው ታውቋል፡፡

elias-anania-and-daniel

እንደ አሜሪካ ደምፅ ሬዲዮ ዘገባ ከሆነ፤ ሰማያዊው ፓርቲ እስካሁን 23 አባላቶቹና ከ80 በላይ ደጋፊዎቹ እንደታሰሩበት አስታውቋል፡፡የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክረሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) እና የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ሕብረት በርካታ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው መታሰራቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡
መንግሥት ህዝባዊ አመፁን ለመቆጣጠርና ለማረጋጋት ብሎ በሰየመው ኮማንድ ፖስት ከሳምንት በፊት የታሰረው ጋዜጠኛ እና የዞን 9 ብሎገር በፈቃዱ ኃይሉን ጨምሮ ከ11,600 በላይ ዜጎችን ማሰሩን ቢያምንም፤ የመብት አራማጆችና የመንግሥት ተቃዋሚዎች በበኩላቸው የታሰሩ ሰላማዊ ዜጎች ቁጥር መንግሥት ካመነው ከ3 እጥፍ በላይ እንደሚልቅ ሲናገሩ ይስተዋላል፡፡

እንደ አካባቢ ምንጮች እና የመብት አራማጆች ከሆነ፤ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ያሉ የተለያዩ ወረዳዎች የመንግሥትን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና የኃይል ርምጃ በመቃወም የአፀፋ መልስ እየሰጡ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ቀላል የማይባል የመንግሥት ወታደራዊ ኃይሎች ከፍተኛ ጥቃት እንደተሰነዘረባቸውና ከገበሬዎችም የተጎዱ እንዳሉ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

በተለይ በአማራ ክልል የፀረ አገዛዝ ጭቆና ህዝባዊ ተቃውሞ ከተጀመረበት ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ አሁንም ድረስ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና የአካል ማጉደል ድርጊት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተከትሎ ፤ ድርጊቱን የተቃወሙ የአካባቢው ነዋሪዎች አካባቢያቸውን እና መኖሪያ ቤታቸውን ጥለው በመሄድ ለአፀፋ መልስ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

መንግሥት ከባለፈው ዓመት ህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ዛሬም ድረስ እንዳልቆመ የሚነገርለትን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መንስኤው የመንግሥት ሹማምንት ስልጣናቸውን ለግል ጥቅማቸው በማዋል የተፈጠረ የመልካም አስተዳደር ችግር ነው በሚል ከዚህ በፊት ከነበሩት 30 ሚኒስትሮች መካከል 21 የቀድሞ ሚኒስትሮችን፣ ሁለት የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረጎችን እና በሚኒስትርነት ማዕረግ የነበሩ በርካታ አማካሪዎችን አሰናብቷል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ከዛሬ ሶስት ሳምንት በፊት፤ ለህዝባዊ ተቃውሞና ለተፈጠረው ችግር ተገቢውን ምላሽ ይሰጣሉ በሚል 21 አዳዲስ ሚኒስትሮችን በመሾም ከነባር 9 ሚኒስትሮች ጋር እንዲሰሩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲፀድቅ ማድረጋቸው ይታወሰል፡፡ ምክር ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የገዥው የኢህአዴግ ፓርቲ ተወካዮች ብቻ የተሞላ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኃላ በተወሰነ መልኩ የተረጋጋ ሁኔታ እንተፈጠረ መንግሥት ቢናገርም አሁንም በተለይ በአማራ ክልል እና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞዎች የቀጠሉ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡ ፡

ምንም እንኳ ህዝባዊ ተቃውሞ የተፈጠረው በራሱ በመንግሥት ብልሹ በሆነ የመልካም አስተዳደር ችግር እንደሆነ ራሱ መንግሥት ቢያምንም፤ በፀጥታ ኃይሎች በሚወሰድ የኃይል ርምጃ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚፈፀመው ግድያ፣ እስርና እንግልት ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ቀጥሏል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል

*ጌታቸው ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል

Getachew Shiferaw

ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ለፍርድ ቤት ሰጥቷል፡፡

አርብ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ መሆኑን ተከትሎ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ በችሎቱ ተጠይቆ ‹‹የቀረበብኝን የወንጀል ድርጊት አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛም አይደለሁም›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡

መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሹ ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያን መርምሮ ብይን ለመስጠት ሲሆን፣ ጉዳዩን የሚያየው 14ኛ ወንጀል ችሎት የተከሳሹን መቃወሚያ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡ ችሎቱ የመቃወሚያ ብይኑን በንባብ ከማሰማት ይልቅ በጥቅሉ “የቀረበውን መቃወሚያ ውድቅ አድርገነዋል” ሲል ለተከሳሹ ገልጹዋል፡፡

”በአጭሩ የክስ አቀራረቡ ከተጠቀሰው የወንጀሉ ክፍል አለመጣጣምን በተመለከተ የቀረበው መቃወሚያ አልተቀበልነውም፤ ዝርዘሩን ማስረጃ ስንመዝን እናየዋለን፡፡ የቀረበው ክስ ግልጽ አይደለም የተባለውን በተመለከተም፣ ክሱን ስንመለከተው በተብራራ መልኩ የቀረበ መሆኑን ስለተገነዘብን ውድቅ አድርገነዋል” በማለት የመቃወሚያው ውድቅ መሆንን ችሎቱ በቃል ለተከሳሹ አስረድቷል፡፡

ችሎቱ ተከሳሹ የእምነት ክህደት ቃሉን ሲሰጥ ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ጥፋተኛም አይደለሁም ማለቱን ተከትሎ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህጉ በበኩሉ ከክስ ማመልከቻ ጋር ያያያዘው የሰነድ ማስረጃ ተመርምሮ ብይን እንዲሰጥለት አመልክቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም የሰነድ ማስረጃውን መርምሮ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ ከሳሽ ያቀረበበት የሰው ማስረጃ እንደሌለ በችሎቱ ተገልጹዋል፡፡

ምንጭ፡- EHRP

በጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው የሽብር ክስ በንባብ ተሰምቷል

*ተከሳሹ ጥቁር ልብስ ለብሰሃል በሚል በቀጠሮው ሰዓት አለመቅረቡ ታውቋል

Getachew Shiferaw

የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በሆነው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. የመሰረተው የሽብር ክስ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡

ተከሳሹ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርቦ ክሱ ሊነበብለት የነበር ቢሆንም ከጠበቃው ጋር ሳይመካከር ክሱ እንዲነበብለት እንደማይፈልግ በመግለጹ በቀጠሮ ሰንብቶ ዛሬ ተነቦለታል፡፡ ከክስ ዝርዝሩ መረዳት እንደተቻለው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው ክስ የጸረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ሆኗል፡፡

አቃቤ ህግ በክሱ ላይ እንዳመለከተው ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል ጠቅሷል፡፡

ተከሳሹ ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡

ችሎቱ ክሱን በንባብ አሰምቶ ሲያጠናቅቅ በተከሳሹ ላይ የተጠቀሱ የአቃቤ ህግ የማስረጃ ዝርዝሮችን በተመለከተ እንደገለጸው፣ ተከሳሹ የተጠቀሰበት ማስረጃ የሰነድ ማስረጃ ብቻ መሆኑ ተገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኝ ሲሆን፣ በዛሬው የችሎት ቀጠሮ በጠዋት እንዲቀርብ የሚል ቢሆንም የእስር ቤቱ አስተዳደር ‹‹ጥቁር ልብስ ለብሰህ ፍርድ ቤት መሄድ አትችልም›› በሚል ጠዋት ሳያቀርቡት ከቆዩ በኋላ ከሰዓት ሊያቀርቡት ችለዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተከሳሽ የክስ መቃወሚያን ለመቀበል ለሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- EHRP

“ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ መብትና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡት ድርጊት ልከሰስ አይገባም” አቶ ዮናታን ተስፋዬ

ታምሩ ጽጌ

በፌስቡክ አድራሻቸው አመፁና ብጥብጥ ቀስቃሽ ጽሑፎችን በማሠራጨት፣ የኦነግን ዓላማ ለማስፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ተብለው በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው የተከሰሱት የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ የቀረበባቸውን ክስ ተቃወሙ፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ ‹‹ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትና በክሱ የተጠቀሰው ብጥብጥና አመፅ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡበት ሁኔታ ልከሰስ አይገባም፤›› ሲሉም ተቃውሞአቸውን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

Yonatan Tesfaye

በኦሮሚያ ክልል ተከስቶ የነበረው ብጥብጥና አመፅ ‹‹የመልካም አስተዳደር ዕጦት ችግር ነው፡፡ የሌላ ሦስተኛ አካል ተሳትፎ የለበትም፤›› በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ማረጋገጣቸውን ያስረዱት ተከሳሹ አቶ ዮናታን፣ የተለያዩ የፌደራልና የክልል ሥራ ኃላፊዎችና ባለሥልጣናትም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር በማጠናከር፣ ዕርምጃ የወሰዱበትና በርካታ ሹማምንትም ከኃላፊነት መነሳታቸውን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ የሚያውቀውና ከማንም ያልተደበቀ በመሆኑ፣ ግልጽ የሆነ የሕግ ግምት (Judicial Notice) የሚወስድበት ጉዳይ መሆኑን አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ዞኖች፣ ወረዳዎችና ቀበሌዎች የተደረገው አመፅና ብጥብጥ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑ ተረጋግጦ ሳለ፣ በቀረበባቸው ክስ ላይ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) እንደተጀመረና እሳቸው በፌስቡክ ገጻቸው ባሠራጩት መጣጥፍ ለማስቀጠል የተደረገ እንደሆነ መገለጹ፣ ከአዋጁ መንፈስ ውጪ መሆኑን በመጠቆም ክሱ ውድቅ ተደርጐ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

አቶ ዮናታን በክስ መቃሚያቸው ላይ እንዳብራሩት፣ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (4)ን መተላለፋቸው ተገልጿል፡፡ በአንቀጹ እንደተገለጸው ተላልፈዋል የተባለው ድርጊት ማቀድ፣ መዘጋጀት፣ ማሴር፣ ማነሳሳትና መሞከር የሚል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ በክሱ ያሰፈረው አቶ ዮናታን ኦነግ ያስጀመረውን አመፅና ብጥብጥ ለማስቀጠል በፌስቡክ ገጻቸው ላይ የተለያዩ ቀስቃሽ ጽሑፎችን ማሠራጨታቸውን የሚገልጽ በመሆኑ፣ በአዋጁ አንቀጽ ሥር ከተመለከቱት ውስጥ በአንዱም የማይሸፈን መሆኑን በመግለጽ አብራርተዋል፡፡ በመሆኑም የዓቃቤ ሕግ ክስ በወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 112 የተደነገገውን ማለትም ‹‹… ወንጀለኛው የፈጸመው ተግባር፣ ወንጀል ከሚያደርገው የሕግ አነጋገር ጋር በጣም የተቀራረበ መሆን አለበት፤›› ከሚለው ድንጋጌ ጋር የሚጋጭ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

አቶ ዮናታን ፈጽመውታል ለተባለው ክስ በማስረጃነት የቀረበው የሰነድ ማስረጃ በፌስቡክ ገጻቸው ተሠራጨ የተባለው መጣጥፍ መሆኑን ገልጸው፣ ፌስቡክ ደግሞ ዘመናዊ የመልዕክት መለዋወጫ ዘዴ መሆኑን፣ ይኼም በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ድንጋጌ ከመሆኑ አንፃር፣ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በየትኛውም ሕግ ገደብና ክልከላ ያልተደረገባቸውና በቀረበባቸው ክስ በተጠቀሰው አንቀጽ ሥር የማይሸፈንና የሽብርተኝነት ተግባር አለመሆኑንም አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ ሕገ መንግሥታዊና ሰብዓዊ መብታቸውን ለማስከበር የተቀመጡ መርሆዎችንና ድንጋጌዎችን የማያሟላ ክስ መሆኑን ገልጸው፣ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸው ክስ ሐሳቡና ይዘቱ አርትኦትና የቃላት ማስተካከል የጎደለው ከመሆኑም በተጨማሪ ለመረዳት የሚያስቸግር፣ በረጃጅም ዓረፍተ ነገሮችና አባባሎች አሳሳች ሆኖ የቀረበ በመሆኑ በወንጀል መዝገብ ሥነ ሥርዓት ቁጥር 111 ድንጋጌን ማለትም፣ ‹‹… የክስ ማመልከቻ ቀን፣ ዓመተ ምሕረት የተጻፈበትና የተፈረመበት…›› የሚለውን የማያሟላ መሆኑን አቶ ዮናታን ጠቁመው፣ ክሱ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ክሱን የሚያሻሽል ከሆነም በሕጉ አግባብ ሥነ ሥርዓቱን ተከትሎ በሚያቀርበው ክስ ላይ የሚጠቅሰው የሕግ አንቀጽ፣ ከክሱ ጋር የሚቀራረብና የተከሳሹን የመከራከር መብት የማያጣብብ አድርጐ እንዲያዘጋጅ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው፣ ጉዳዩን ለሚከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. አመልክተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም የዓቃቤ ሕግን ምላሽ ለመጠባበቅ ለግንቦት 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የሽብርተኝነት ክስ ተመሰረተበት

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

Getachew Shiferaw

የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው ክስ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡

በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የዕንቁ መፅሔት አምደኛ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ፣ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መስራች አባልና የጊዜያዊ አስተባባሪው አመራር እንዲሁም አዲስ ሚዲያ ተባባሪ እና በራሱ የማኀበራዊ ገፅ ብሎገር እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- EHRP.