Tag Archives: Ethiopian Ministry of Education

የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ወደ ሐምሌ 4 ተራዘመ

(አዲስ ሚዲያ)  ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ተራዘመ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር ባለፈው ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ሊሰጥ የነበረው ፈተና መከካከል ሁለት የትምህርት ዓይነቶች ቀድመው በማኀበራዊ ሚዲያ ከነመልሶቻቸው መለቀቃቸውን ተከትሎ እንዲቋረጥ የተደረገው ፈተና ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ለመስጠት ትምህርት ሚኒስቴር መርሃ ግብሩን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ቅሬታና ተቃውሞ አስከትሎ ነበር ፡፡

Ethiopian Minstry of education
በተለይ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. መካከል የረመዳን ፆም ፍቺ በዓል ላይ የሚውል ተቃውሞ በመቅረቡ፣ ትምህርት ሚኒስቴርም ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ቅሬታ በመቅረቡ ፈተናው በአንድ ሳምንት ተራዝሞ ከሐምሌ 4-7 ቀን 2008 ዓ.ም. እንደሚሰጥ አስታውቋል ፡፡

ቀደም ሲል ግንቦት ሊሰጥ የታሰበውን መርሃ ግብር እንዲቀየር ያስገደዱት የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎችም ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚሰጠው አዲሱ መርሃ ግብር ላይ ሌላ ተቃውሞ እንደማያስነሱና ከባለስልጣናቱ ጋር እልህ መጋባቱ አላስፈላጊ መሆኑን በመጥቀስ፣ ተማሪዎች ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚሰጠውን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተረጋግተው እንዲፈተኑ ጠይቀዋል፡፡

ትምህርት ሚኒስቴር እና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች በየበኩላቸው በየአካባቢው ያሉ መምህራን፣ ወላጆች፣ አስተዳደሮች እና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ ለተማሪዎች እንዲያደርጉላቸው የትብብር ጥያቄ አቅርበዋል፡፡

 

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበር ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ይፋ አደረጉ

ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ

ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሊቀመንበር ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ይፋ አደረገ፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ራሳቸውን ለማንሳት የተገደዱት፤ በትምህርት ክፍሉ ከ28 ዓመታት በላይ በፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ውል በዩኒቨርስቲው አስተዳደር መቋረጡን ተከትሎ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ዶ/ር ካሳሁን የዶ/ር መረራ የጡረታ ጊዜ እንዲራዘም ያስገቡት ጥያቄ በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ውድቅ መደረጉ እና ከዚያም የትምህርት ክፍሉ ስለሚፈልጋቸው በራሱ የኮንትራት ውል አስፈርሞ ለሰባት ወራት ያሰራበት ክፍያ አለመፈፀሙን ተከትሎ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለዩኒቨርስቲው አስተዳደር ማስገባታቸው ታውቋል፡፡

በተለይ እንደ አሜሪካ ድምፅ ዘገባ ከሆነ፤ ዶ/ር ካሳሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል በዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ የተወሰደውን ርምጃ ተከትሎ “ የዩኒቨርስቲው አስተዳደር ለትምህርት ክፍሉ ጥያቄና ፍላጎት ምላሽ ባለመስጠቱ፤ የትምህርት ክፍሉን እያስተባበርኩ መቀጠል ከሞራልም አኳያ ተቀባይነት እንደሌለው ይሰማኛል፡፡” በማለት ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ለመልቀቅ መወሰናቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡ ዶ/ር መረራ በበኩላቸው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስዱት አስታውቀዋል፡፡ በአሁን ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጡረታ ጊዜያቸው እንዲራዘም ጠይቀው የተፈቀደላቸውና እየሰሩ የሚገኙ በርካታ መምህራን እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ባልተገለፀ ምክንያት የዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ጥያቄ ብቻ ተቀባይነትን ሊያገኝ አለመቻሉ ታውቋል፡፡

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደም ለሙሉ ፕሮፌሰርነት የሚያበቃ በርካታ ጥናቶችን አጠናቀው ማዕረጉን ለማግኘት ያቀረቡት ማመልከቻ በሚመለከተው የመንግሥት አካል ተቀባይነት እንዳላገኘ የሚታወቅ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደምም ሆነ አሁን የተወሰደባቸው እርምጃ በተቃውሞ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ እንደሆነ የተጠቆመ ሲሆን፤ በአሁን ወቅትም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ ሊቀመንበር እና የአራት ፓርቲዎች ግንባር የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ምክትል ፕሬዘዳንት እና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡

ድብደባ ከተፈጸመባቸው ሁለት የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መካከል የአንደኛው ሕይወቱ አለፈ

ምሩ ጽጌ

ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር ውለው በምርመራ ላይ ናቸው

በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አካባቢ በሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፋኩልቲ፣ ሁለት ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው የጥበቃ ሠራተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸው አንደኛው ሕይወቱ ማለፉ ተረጋገጠ፡፡

 aastu

ጥር 23 ቀን 2007 ዓ.ም. የግማሽ ዓመት ፈተናቸውን ካጠናቀቁት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች መካከል፣ ሙሉቀን ከበደና ታምራት አባተ የተባሉ ተማሪዎች በዕለቱ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ታውቋል፡፡ ተማሪዎቹ ፈተናቸውን እንዳጠናቀቁ ከግቢ ወጥተው ሲዝናኑ ካመሹ በኋላ ወደ ማደሪያ ክፍላቸው ሲመለሱ፣ ፀደቀ አድማሱ ከሚባለው ተጠርጣሪ የጥበቃ ሠራተኛ ጋር መጋጨታቸውን ከፖሊስ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

ተማሪዎቹ ወደ ዩኒቨርሲቲው ግቢ ሊገቡ ሲሉ ተጠርጣሪው እንዲቆሙ ሲያደርጋቸው ተማሪ መሆናቸውን የሚያረጋግጡበትን መታወቂያ ቢያሳዩም፣ ከተጠርጣሪው ጋር ሊግባቡ ባለመቻላቸው ድብድቡ መጀመሩ ታውቋል፡፡ ተጠርጣሪው በወቅቱ ይዞት በነበረው የእንጨት ዱላ ደጋግሞ ሲደበድባቸው የተመለከተ ሾፌር፣ ሌሎች የተኙ ጥበቃዎችን በማስነሳቱ የተፈጠረው ድብድብ የቆመ ቢሆንም፣ ተማሪዎቹ በደረሰባቸው ድብደባ ተጎድተው ስለነበር በአቅራቢያቸው በሚገኘው ጥሩነሽ ቤጂንግ ጠቅላላ ሆስፒታል መወሰዳቸውም ተጠቁሟል፡፡

ታምራት አባተ የተባለው ተማሪ በጥሩነሽ ቤጂንግ ጠቅላላ ሆስፒታል በተደረገለት ሕክምና የተረፈ ቢሆንም፣ የደረሰበት ድብደባ ከባድ በመሆኑ ለተጨማሪ ሕክምና ሪፈር የተደረገው ተማሪ ሙሉቀን፣ በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በሕክምና ላይ እያለ ጥር 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ሕይወቱ ማለፉ ታውቋል፡፡ ፖሊስ በድብደባው ተሳትፈዋል በማለት በቁጥጥር ሥር ያዋላቸውን ተጠርጣሪ የዩኒቨርሲቲውን የጥበቃ ሠራተኞችን ፍርድ ቤት አቅርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በመጠየቅ በምርምራ ላይ መሆኑን ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡