Tag Archives: Ethiopian press freedom

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ተላለፈበት

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲሁም በመፅሔት አሳታሚ ድርጅቱ ላይ የ200 ሺህ ብር ቅጣት ተወስኖበታል። ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ ከዓመት በፊት የሶስት ዓመት ከ3 ወር እስራት እንደተፈረደበት ይታወሳል።

ግዛው ታዬ

ግዛው ታዬ

ከ800 ሺህ ብር በላይ ታክስ በማጭበርበርና በሌሎች 14 ክሶች ጥፋተኛ የተባለው የሎሚ መጽሄት ዋና ስራ አስኪያጅ በ18 ዓመት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነ።
ውሳኔውን የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት ነው ያስተላለፈው።
ተከሳሾቹ ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ታዬ ግዛው ናቸው።
የፌደራል ገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፥ ድርጅቱም ሆነ ስራ አስኪያጁ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ክሱ እስከተመሰረተበት ድረስ ለተከታታይ 5 ዓመታት ኦዲት አልተደረጉም።
በዚህ ሂደትም ድርጅቱም ሆነ ግለሰቡ የታክስ ማጭበርበሮችን ሲያከናውን ቆይቷል ሲል የአቃቤ ህግ ክስ ያስረዳል።
የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የገቢ ግብር መሰወር የሚለውም በወንጀል ድርጊቱ ማስረጃዎች ጉዳይ ሲሆን፥ እንደ አቃቤ ህግ ገለጻ በዚህ ሂደት ውስጥ ድርጅቱ እና ስራ አስኪያጁ ለመንግስት መግባት የነበረበትን ከ800 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል ይላል።
በዚህ የክስ መዝገብም ግለሰቡ በችሎቱ አልቀረበም።
ይህን ተከትሎም የክስ ሂደቱ በሌሉበት እንዲቀጥል በተሰጠው በይን መሰረት አቃቤ ህግ የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
ጉዳዩን ሲመለክት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት በተከሳሾች ላይ የቀረበው ማስረጃ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ነው ሲል ቅጣቱን አስተላልፏል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንተኛ የወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ችሎት ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት በ200 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛውታዬ ላይ ደግሞ የ18 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ100 ሺህ የገንዘብ ቅጣት አስተላልፏል።
የድርጅቱ ሎሚ መፅሔት (ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንት) ባለቤትና ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ አቶ ግዛው ታዬ ከዚህ በፊት “አመጽ በማስነሳት እና መሰል የሽብርተኝነት ወንጀሎች” ክስ ተመስርቶበት በ50 ሺህ ብር ዋስ ከተለቀቀ በኋላ መሰደዱ ይታወቃል፡፡ የአሁኑ ክስና ፍርድም ተከሳሹ በሌለበት ተወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በተመለከተ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንን/ሬዲዮ ፋናን/ ዋቢ በማድረግ ቃልኪዳን ትዩብ ዘግቧል፡፡

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ ዓለም አቀፍ ተሸላሚ ሆነ

በሽብርተኝነት ተከስሶ 18 አመት የተፈረደበትና በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ ደረጃ አንድ ሰብዓዊነት (PEN Canada’s One Humanity Award) ሽልማት ተሸላሚ መሆኑን ፔን ካናዳ ይፋ አድርጓል፡፡

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በፈረንጆቹ ግንቦት 2012 የባርባር ጎልድ ስሚዝ ሽልማት እንዲሁም በሰኔ 2014 የጎልደን ፔን ሽልማት ተሸላሚ እንደሆነ ይታወሳል፡፡ በካናዳ ቶሮንቶ እየተደረገ በሚገኘው 36ኛው ዓለም አቀፍ የፀሃፊዎች ፌስቲባል የፔን ካናዳ ደረጃ አንድ ሰብዓዊነት ሽልማትን ተሸልሟል፡፡
እ.ኤ.አ በ2011 የአረብ አብዮትን ተከትሎ መንግስት ለውጥ የማያደርግ ከሆነ ተመሳሳይ ህዝባዊ ንቅናቄ በኢትዮጵያም ሊከሰት ይችላል የሚል አስተያየቱን ማንጸባረቁን ተከትሎ ለእስር የተዳረገውና በፀረ ሽብር ህጉ ተከስሶ 18 አመት የተፈረደበት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ አምነስቲ ኢንተርናሽናልን ጨምሮ በበርካታ የሰብአዊ መብት ተቋማት ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ ዓለማቀፍ መብቱን መጠቀሙን በማስታወስ እስክንድር የህሊና እስረኛ እንደሆነ በመግለፅ ከእስር እንዲለቀቅ መጠየቃቸውን ቀጥለዋል፡፡ ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ከእስር እንዲለቅ ሲያሳስብ ቆይቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በእስር ቤቱ ከሚደረግበት ከፍተኛ ቁጥጥርና ጫና ባሻገር ከቤተሰብ ውጭ እንዳይጠየቅ ተከልክሎ ይገኛል፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ

ሰበር ዜና፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ሶስት ጋዜጠኞችን እና ሁለት የዞን 9 ብሎገሮችን ከእስር መልቀቁን አስታወቀ

ከሚያዚያ አጋማሽ 2007 ዓ.ም. በፌደራሉ አቃቤ ህግ በ”ሽብርተኝነት” ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ እየታየ ከነበረው የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች መካከል፤ ሶስቱን ጋዜጠኞች እና ሁለቱን ብሎገሮች ክሳቸው በፍትህ ሚኒስቴር ውድቅ ተደርጎ መፈታታቸውን የገዥው መንግሥት ደጋፊ የሆነው ሬዲዮ ፋናን ዋቢ በማድረግ አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡
ዛሬ ሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ከእስር የተፈቱት ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ፤ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን እንደሆኑ ታውቋል፡፡
እንደሬዲዮ ፋና ዘገባ ከሆኑ ቀሪዎቹ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል በእስር ላይ የሚገኙት በፍቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ የክስ ጉዳዩን እንደሚቀጥል የፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ ማስታወቁን ጨምሮ ዘግቧል፡፡

ከግራ ወደቀኝ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ማህሌት ፋንታሁን

ከግራ ወደቀኝ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ማህሌት ፋንታሁን

ጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮች ቀደም ሲል በፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ በ”ሽብር ወንጀል” ተከሰው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ለብይን ተቀጥሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡

በኢትዮጵያ የግል የሬዲዮ ጣቢያዎች ፈርሰው ከመንግስት ቻናል እንዲከራዩ ለማድረግ ታቅዷል

በኢንተርኔት የሚሰራጩ  ፅሑፎችን፣ ምስሎችንና ቪዲዮዎችን ለመቆጣጠር ታስቧል

 ebaበኢትዮጵያ የሬዲዮና የቴሌቪዥን ስርጭቶችን ለመቆጣጠር ከስምንት ዓመት በፊት በታወጀው ህግ ላይ አዳዲስ ቁጥጥሮችን የሚጨምርና እንዲሁም የኢንተርኔት ስርጭቶችንና ድረገፆችን የሚያካትት ህግ ተዘጋጀ፡፡

ከተለያዩ የሚዲያ ተቋማት ጋር ከትናንት በስቲያ ሃሙስ ውይይት የተካሄደበት ረቂቅ ህግ፣ ነባሩ አዋጅ ውስጥ የሰፈሩ የባለቤትነትና የፈቃድ አሰጣጥ ቁጥጥሮችን የሚዘረዝር ሲሆን፤ በኩባንያ መልክ እንጂ በግለሰብ የሬዲዮ ወይም የቴሌቪዥን ድርጅት ማቋቋም እንደማይቻል ይጠቅሳል፡፡ የዝምድና ወይም የጋብቻ ግንኙነት ያላቸው ሰዎች ለብቻቸው ባለአክሲዮን የሆኑበት ኩባንያ ፈቃድ እንደማይገኝም ተደንግጓል፡፡  ምንም እንኳ እስከዛሬ ተግባራዊ ባይሆንም በ1999 ዓ.ም በወጣው ህግ፣ የግል የቴሌቪዥን ጣቢያ ለማቋቋም ፈቃድ እንደሚሰጥ ተገልፆ የነበረ ሲሆን፤ አሁን በተረቀቀው ህግ ግን የቴሌቪዥን ጣቢያ በግል ማቋቋም እንደማይቻል ይደነግጋል፡፡

መንግስት የቴሌቪዥን ማሰራጫ ኔትዎርክ እንደሚዘረጋ የሚገልፀው ይሄው አዲስ አዋጅ፤ የግል ኩባንያዎች ከመንግስት ቻናል እየተከራዩ ለመስራት ማመልከትና ፈቃድ መጠየቅ ይችላሉ ይላል፡፡

የግል ኩባንያዎች ለጊዜው የራሳቸው የሬዲዮ ጣቢያ ለማቋቋም ፈቃድ የሚያገኙበት እድል ሊኖር እንደሚችል አዲሱ ህግ ይጠቁማል፡፡ ወደፊት ግን በግል ባቋቋሙት የማሰራጫ ጣቢያ ሳይሆን ከመንግስት የማሰራጫ ጣቢያ ቻናል እየተከራዩ እንዲሰሩ ይደረጋል ተብሏል፡፡ ለዚህም መመሪያ እንደሚዘጋጅ በረቂቁ ህግ ተጠቅሷል፡፡

በረቂቁ ህግ ከተካተቱ 60 አንቀፆች መካከል አብዛኞች በሬዲዮና በቴሌቭዥን ስርጭት ቁጥጥር ላይ ያተኮሩ ሲሆን፤ በኢንተርኔት የሚሰራጩና በድረገፅ የሚቀርቡ መረጃዎችን ለመቆጣጠር የታቀዱ ሦስት አንቀፆች ተጨምረውበታል፡፡ የሬዲዮና የቴሌቪዥን የግል ድርጅቶች ስለዲሞክራሲና ስለ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች የመዘገብ ግዴታ በህጉ የተጣለባቸው ሲሆን፤ በኢንተርኔትና በድረገፅ የሚሰራጩ መረጃዎች እንዲህ አይነት ግዴታ ባይኖርባቸውም ትክክለኛነታቸው ያልተረጋገጡ መረጃዎችን ማቅረብና ሌሎች በአንቀፅ 33 የተዘረዘሩ ድርጊቶችን ከፈፀሙ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ረቂቅ ህጉ ይገልፃል፡፡

አመፅና፣ ግጭትና ጦርነት መቀስቀስ፣ እንዲሁም የሰውን ስምና ነፃነትን የሚያጠፋ መረጃ ክልክል መሆኑን የሚዘረዘረው አዲሱ ህግ፤ ምን ማለት እንደሆነ በግልጽ ባይብራራም የሃይማኖትን፣ የዘርን፣ የፆታን ክብር መንካት ክልክል ነው ይላል፡፡  በደፈናው ስነምግባርን የሚፃረርና የልጆችን አስተሳሰብ ወደአልተፈለገ አቅጣጫ እንዲያዘነብል መገፋፋትም ህገወጥ መሆኑን ይገልፃል፡፡

እንደ ፌስቡክ እና ቲዊተር የመሳሰሉትን ጨምሮ አብዛኞቹ ድረገፆች በውጭ አገር የሚገኙ በመሆናቸው እንዴት ሊቆጣጠራቸው እንዳሰበ ሲጠቁም፣ በፅሁፍ ማስጠንቀቂያ እንደሚሰጥና ድረገፁ ከሚገኝበት አገር መንግስት ጋር በመተባበር እርምጃ እንደሚወስድ ህጉ ይገልፃል፡፡
ብዙዎቹ ድረገፆች በሚገኙበት በአሜሪካ “ሃሰት አሰራጨህ ወይም ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ትገፋፋለህ” የሚል የአስተሳሰብ ቁጥጥር እንደሌለ ይታወቃል፡፡

ምንጭ፡- አዲስ አድማስ ጋዜጣ

ከታሳሪ ዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሕገ መንግስታችንን ያክብሩ!

ግልጽ ደብዳቤ ”ለጠቅላይ ሚኒስትር” ኃይለማርያም ደሳለኝ

ከታሳሪ ዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሕገ መንግስታችንን ያክብሩ!

ሠላም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር!? እንዴት ነዎት? ያስታውሱ ከሆነ የዛሬ ሁለት ዓመት አካባቢከፊሉ የዚህ ማስታወሻ ፀሃፊዎች ‘ግልፅ ደብዳቤ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ’

“ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር እባክዎትን የተለያዩ የመንግስት አካላት የሕገ መንግስታችንን ድንጋጌዎች እየጣሱ ነውና እርስዎም በሕገ መንግስቱ አንቀፅ 74/13/ መሠረት ሕገ መንስቱን የማስከበርና የማክበር ግዴታ ስላለብዎት ሕገ መንግስቱን ያክብሩ”በማለት አንዲት አጭር ደብዳቤ ፅፈንልዎት ነበር፡፡

ድንገት በተለያዩ ምክንያቶች የጻፍንልዎትን ደብዳቤ ካላነበቡት ወይም ማስታወስ ካልቻሉ ዛሬ ይሄን ማስታወሻ ስለምንፅፍልዎት ግለሰቦች አንድ ሌላ ማስታወሻ እንስጥዎ፡ ከ6ወራት በፊት /በሚያዚያ 2006 ዓ.ም/ ሶስት ጋዜጠኞችንና ስድስት ጦማሪያንን ‘ሕገ መንግስቱንና ሕገ መንግስታዊ ስርዓቱን በኃይል ለመናድ በመሞከር ወንጀል ጠርጥሬያችኋለሁ’ በማለት መንግስትዎ ልማታዊ ርምጃ (አብዮታዊ ርምጃ እንደሚባለው) ወስዶ ነበር፡፡

እኛም የዚህ ማስታወሻ ፀሃፊዎች የዚህ ‘ልማታዊ ርምጃ’ ሰለባ የሆንን ግለሰቦች ነን፡፡በርግጥ ከሁለት ዓመታት በፊት ‘ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሕገ መንግስቱን’ ያስከብሩልን በማለት ጥያቄ ያቀረብንልዎት ግለሰቦች ‘ከ6 ወራትበፊት ሕገ መንግስቱን ለመናድ ሞክራችኋል’ በማለት መንግስትዎ ሲያስረን ሕገ መንግስቱ እንዲከበር ጠይቀን ሕገ መንግስቱን ለመናድ በመሞከር ወንጀል ተጠርጥረን ስንታሰር እስሩ በጣም ግራ አጋብቶን ነበር፡፡በዚህ ያልቆመው መንግስትዎ ክሱን ‘ሕብረተሰቡንና ሀገሪቱን ለማሸበር አቅዳችኋል ሞክራችኋል አሲራችኋል…’ በማለት ወደ ‘ሽብርተኝነት’ያሳደገው ሲሆን እርስዎም ከዚህ ጋር በተያያዘ ሃሳብዎትን ሲሰጡ ስለተመለከትንዎ ትንሽ ቅሬታ ይዘን መጣን፡፡

በቅድሚያ አሁን ያለንበትን ሁኔታ በትንሹ ብናስረዳዎት ቅሬታችንን ለመረዳት ያስችልዎታልና አንዳንድ ጉዳዮችን እንንገርዎት፡፡

zone9ይሄን ማስታወሻ በምንፅፍልዎት ወቅት ከታሰርን ከ 200 ቀናት የተቆጠሩ ሲሆን፣ነገር ግንጉዳያችን ገና በቅድመ ክስ (Pre Trial) የክርክር ሂደት ላይ ይገኛል፡፡ ይሄ የሆነበት ዋነኛ ምክንያትም መንግስትዎ እንኳን ለእኛ ለተከሳሾች ለከሳሽ አካልም ግልፅ ያልሆነ ክስ በማቅረቡ ነው፡፡ ይሄንንም ስንል ልትፈፅሙት ነበር የተባለው ‘የሽብርተኝነት ድርጊት’ ሳይጠቀስ ‘በቃ የሽብርተኝነት ድርጊት ልትፈፅሙ ነበር’ በማለት በጨበጣ ስለመጣብን ነው፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር እንግዲህ የብዙ ድብደባ፣ ዛቻ እና ስድብ ሰለባዎች ከሆንን በኋላምየቀረበው ይሄ ክስ ነው ከ6 ወራት በኋላም ተከሳሾች ከሳሾቻችንምሳንረዳው በየቀጠሮው እየታሸ ነው የሚገኘው፡፡ ‘የተፋጠነ ፍትህ’ ሕገ መንግስትዊ መብት ነውና የተፋጠነ ፍትህ ይሰጠን፣ እርስዎምይሄን ሕገ መንግስታዊ መብት ያክብሩ እያልንዎት አይደለም ‘ሕገ መንግስቱ ተከብሮ እያለ ሕገ መንግስቱ ይከበር በማለቴ ጥፋተኛ ነኝ’በማለት ‘ጥፋት የሚያሳምን’ ( አንዱ የዚህ ደብዳቤ ጸሃፌ ጦማሪ ጥፋት ብሎ አንዲፈርም የተገደደው ህገ መንግስቱ ተከብሮ እያለህገመንግስቱ ይከበር ማለቴ ጥፋት ነው ብሎ መሆኑ መንግስትዎን መልክ ግልጽ አድርጎ ያሳያል) መንግስት አለዎትና ይህ ጥያቄ አንደሚበዛብዎትእናውቃለን፡፡

ይልቁንም ቀላልና ግልፅ ቅሬታን ነው ይዘን የመጣነው፡፡ ይሄውም የኢፌድሪ ሕገ መንግስትበአንቀፅ 20/3/ ላይ

‘የተከሠሡ ሰዎች[…] በፍርድ ሂደት ባሉበት ጊዜ በተከሰሱበት ወንጀል እንደ ጥፋተኛ ያለመቆጠር[…]መብት አላቸው::’

በማለት የደነገገ ሲሆን፣ ይሄንን ሕገ መንግስታዊ መብትም ማንኛውም የመንግስት አካል እንዲሁም ግለሰብ የማክበር ግዴታ አለበት፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር እርስዎና መንግስትዎም በተደጋጋሚ ‘ሕገ መንግስቱ ሳይሸራረፍ እናስከብራለን’ ይላሉና ይሄን ሕገ መንግስታዊ ድንጋጌ የምታውቁት ይመስለናል፡፡ ነገር ግን ከታሰርን ወዲህ ስለእኛ የእስር ጉዳይ በተጠየቁባቸውጊዜያት ይሄን ሕገ መንግስታዊ ድንጋጌ በመጣስ ‘ፍርድዎትን’ በተደጋጋሚ ሲሰጡ ታዝበናል፡፡ እናስረዳዎ፡- ሐምሌ 12/2006 ዓ.ም በሰጡት ጋዜጣሚ መግለጫ ላይ ስለእኛ እስር ጉዳይ ለቀረበልዎት ጥያቄ ሲመልሱ፡-

‘ከአስመራ እስከ ሞቃዲሾ የተዘረጋው የሽብር ሰንሰለት ውስጥ አንዴከገቡ በኋላ ብሎገር ነኝ፣ ጋዜጠኛ ነኝ ማለት ዋጋ የለውም’

በማለት ብዙ ነገሮችን ተናገሩ፡፡ ይሔውልዎት ስህተትዎ፡-

1. የክሳችን ዋነኛ ጭብጥ በሃገርውስጥ ‘የሽብርተኛ ድርጅት በማቋቋም ‘የሽብርተኝነት’ ተግባራትን ለመፈጸም አሲረዋል፡ አቅደዋል… የሚል እንጂ፣ እርስዎም እንደሚሉት ‘ሰንሰለት’ ምናምን አይደለም፣

2. እሺ አሸባሪዎችም ይበሉን፣ነገር ግን ሕገ መንግስቱ እንደሚደነግገው በፍርድ ቤት ‘ጥፋተኝነታችን’ እስሚረጋገጥ ቢጠብቁስ ምናለበት? ይህ የሚያመለክተው እርስዎም እንደ ማእከላዊ መርማሪዎች ነፃ ሆኖ የመገመት (presumption of innocence) መብታችንን እያከበሩልን እንዳይደለ ነው፡፡

ይሄ ነገር የሆነው በድንገት ሊሆን ይችላል ብለንዝም ብንልም እርስዎ ግን በድጋሚ ጥቅምት 6/2007 ዓ.ም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ከምክር ቤቱ አባል ለቀረበልዎ ጥያቄሲመልሱ፡-

“የብሎገር ጭምብልአጥልቆና በጋዜጠኝነት ሙያ ውስጥ ተሸሽጎ ከተከሳሽነት ማምለጥ አይቻልም፡፡ ሽብርተኝነትን መዋጋታችን ይቀጥላል…” እያሉ እርስዎ ያሉትን የብሎገር ጭምብል አውልቀውና ተሸሸጉበት ያሉትን የጋዜጠኝነት ሙያመሸሸጊያ አፍርሰው ባንዴ ‘የአሸባሪነት’ ካባ ደረቡልን፡፡

ክቡር ጥቅላይ ሚኒስቴር፣ እያልን ያለነው የአንድ ሰው ‘አሸባሪነት/ወንጀለኝነት’ የሚረጋገጠው በፍርድ ቤት እንደሆነ ሕገ መንግስቱ ደንግጎ እያለ፣ እርስዎ ግን ነፃ ሆኖ የመገመት መብታችን ወደ ጎን ብለው እንደ ከሳሽም እንደፈራጅም በመሆን ‘አሸባሪዎች’… እያሉን ይገኛሉ ነው፡፡

ምናልባት ‘ስራ አስፈጻሚው ከሳሽ ነውና እኔም የስራ አስፈጻሚው አካል መሪ ስለሆንኩ የፈለኩትን አስተያየት የመስጠት መብት አለኝ’ ብለው ከሆነ፣ ሕገ መንግስቱን የማክበር ጉዳይ ‘ርስዎን ጨምሮ ሁሉም ዜጎች ላይ የተጣለ ግዴታነው፡፡ እርስዎ ‘L’e’tat, c’est moi’ ይሉት አይነት የራስ ግምት ውስጥዎ ከሌለ በስተቀር እንዲህ በግልፅ እየጠየቅንዎት ‘ሕገ መንግስትቱን አላከብርም’ በማለት ገና ዋነኛ ክርክሩ እንኳንያ ልተጀመረ ክስን (ዋነኛ ክርክር ካለው) መሠረት በማድረግ ከዚህ በኋላ እኛን ‘አሸባሪዎች’ አይሉንም ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ይህን ተመሳሳይ ምላሽ “በእርግጠኝነት አሸባሪ ናቸው” በሚል ቃና ለቢቢሲ ለኢንቢሲ ለመሳሰሉት አለም አቀፍ ሚዲያ ተቋማትም መስጠትዎን ሰምተናል፡፡

ሌላው ልናስታውስዎ የምንፈልገው ጉዳይ እንደኛ አይነት የተራገበ( በሰፊው በታወቀ የአደባባይ)የፍርድ ጉዳይ ([un] popular case) ላይ የመንግስት አካላት አስተያየት (say) ያለውን ተፅእኖ እንዲያስቡት ነው፡፡እርስዎ በምክር ቤት ቀርበው የአሸባሪነት ፍርድ ከበየኑብን (አሁን እያደረጉት እንዳሉት) ፍርድ ቤትም ሆነ ሌሎች የመንግስትዎ አካላትምን ሊያስቡ እንደሚችሉ አስተውለውታልን?!

ይሄን ሁሉ ስንልዎ እንዲያው ሕጉን ያክብሩልን ለማለት ያክል ነው እንጅ፣ ከሽብርተኝነትጋር የሚያገናኘን ቅንጣት ያክል እውነት /A segment of fact/ እንደሌለና የሰው ልጆች መልካምና ደስተኛ ሕይወት እንዲኖራቸውከመመኘትና ለአገራችን ያገባናል ከማለት ያለፈ ሕይወትም ፍላጎትም እንደሌለን እኛም እናውቀዋለን እርስዎና መንግስትዎም ያውቁታል፡፡ነገር ግን ካለፉት ስድስት ወራት አንስቶ ጨዋታውን በግድ ካልተጫወታችሁ ተብለናልና እየተጫወትን ነው፡፡ የአሁኑ ጥያቄያችን ግን በጣም ቀላል ነው፣ ጨዋታው ገና በደንብ እንኳን ሳይጀመር ውጤቱን እይወስኑት ነው፡፡

እርስዎ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት የስልጣን ደረጃ በወጡ ሰሞን አብዛኞች የዚህ ማስታወሻፀሃፊዎች መጠነኛ ለውጥና ማሻሻዎች ያደርጋሉ የሚል ተስፋ ሰንቀን “The First 100 Days” ወዘተ እያልን ብዙ ጠብቀንዎት ነበር፡፡ ከሁለት ዓመት በሚበልጥ ግዜ እንደተመለከትንዎ ግን ተስፋችን ፍሬ ሊያፈራልን አልቻለም፡፡ አሁንም አዲስ ተስፋ ሰንቀን ግን ፡- “ክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር እባክዎትን ሕገ መንግስቱን ያክብሩ! የእኛንም መብት ያክብሩልን” እንላለን፡፡

‘’የብሎገር ካልሲ አድርጎ፣ የጋዜጠኝነት ጫማ ተጫምቶ የሽብረተኝነት ሰንሰለት ውስጥ ከገቡ በኋላ ሕገ መንግስቱን ያክብሩልኝ ማለት ዋጋ የለውም!’’በማለት ተስፋችን ዋጋ እንደማያሳጡት ተስፋ አለን፡፡

ከአክብሮት ጋር

ጦማርያን ጋዜጠኞች

ጦማሪያን፡- ዘለዓለም ክብረት          ጋዜጠኞች፡-  ኤዶም ካሳዬ

ናትናኤል ፈለቀ                                ተስፋዓለም ወልደየስ

በፈቃዱ ኃይሉ                                   አስማማው ኃይለጊዮርጊስ

አጥናፍ ብርሃኔ

አቤል ዋበላ

ማህሌት ፋንታሁን

 

ምንጭ፡-  ዞን 9 (ኢትዮጵያ)