Tag Archives: National Electoral Board of Ethiopia

የኦሕዴህ አባላት በሰማያዊ ምልክት ሊወዳደሩ ነው

  • “ለአንድ አላማ እንታገላለን” አቶ ግርማ በቀለ
  • “መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

የኦሞ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት (ኦሕዲኅ) አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ምልክት ለመወዳደር መወሰናቸውን የኦሕዲኅ ሊቀመንበር አቶ ግርማ በቀለ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጹ፡፡ ‹‹ጥቅምት 26/2006 ዓ.ም ፓርቲው ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ አባላቱና አመራሩ ከአገር አቀፍ ፓርቲዎች ጋር በውህደት መስራት እንዳለባቸውና በኦሕዲኅ ስም የሚደረገው የመጨረሻ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲሆን ወስነው ነበር›› ያሉት ሊቀመንበሩ የፓርቲው እጩዎች በሰማያዊ ፓርቲ ስምና ምልክት መመዝገባቸው አባላቱና አመራሩ ‹‹አገራዊ ፓርቲ ጋር በውህደት አሊያም በሌላ መንገድ አብረን መስራት አለብን፡፡›› በሚል በጠቅላላ ጉባኤው ያስተላለፉት ውሳኔ አካል ነው ብለዋል፡፡

አቶ ግርማ ፓርቲያቸው ከሰማያዊ ጋር ሆኖ ለመታገል የተነሳበትን ምክንያትም ‹‹አሉ ከሚባሉት 70 ያህል ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ የክልል ፓርቲዎች ናቸው፡፡ የክልል ፓርቲዎች በአገራችን ፖለቲካ ፋይዳ ያለው ለውጥ እያመጡ አይደለም፡፡ የክልል ፓርቲዎች ሲጠናከሩም ቢሆን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው እንደሚያመዝን ተረድተናል፡፡ በተቃራኒው አገር አቀፍ ፓርቲዎች ሲጠናከሩ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ይችላሉ›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ግርማ አክለውም ‹‹እስካሁን የክልልና አገራዊ ፓርቲ ተባብለን ተበታትነን ቆይተናል፡፡ አሁን ግን የተሻለ ለውጥ ለማምጣት አንድ አይነት ጥያቄ አንስተን፣ በአንድ አላማ ለመታገል ወስነናል፡፡ አንድነት ኃይል በመሆኑ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የተሻለ ለውጥ እንደምናመጣ የሚል ትልቅ ተስፋ አለን›› ብለዋል፡፡

ፓርቲው ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ስምምነት በመፈረሙ አባላቱ በሰማያዊ ፓርቲ ስር ሆነው እንዲወዳደሩ ለምርጫ ቦርድ ባስገባው ደብዳቤም ‹‹የዚህ ስምምነት አላማ ፈራሚዎች ለ2007 ዓ.ም አጠቀላይ አገራዊ ምርጫ አባላትን በጋራ በአንድ የመወዳደሪያ ምልክት ማቅረብ፣ ማለትም የአንዱ ፓርቲ አባልና አመራር በሌላው ፓርቲ ሥምና ምልክት የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ስምምነት ሲደረስም ተግባራዊ ማድረግ ነው›› ብለዋል፡፡

በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የቀድሞ የአንድነት አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ መምጣታቸውን አስታውሰው አሁንም የኦሕዲኅ አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ስር ለመወዳደር በፓርቲው ጥላ ስር መሰባሰባቸው ሰላማዊ ትግሉን እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአንድነት መቆማችንና መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል፡፡ ኢህአዴግ የአንድነት አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ በመምጣታቸው፣ ሰማያዊም እጁን ዘርግቶ በመቀበሉ ከፍተኛ ፍርሃት ተፈጥሮበታል፡፡›› ብለዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል አክለውም ‹‹አሁንም ሌሎች ፓርቲዎች መቀላቀላቸው ለኢህአዴግ ትልቅ ስጋት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በቴሎቪዥንና በራዲዮ እጩ ያቀረቡ ፓርቲዎችን ሲያስተዋውቅ የሰማያዊን ስም ሳይጠቅስ ቀርቷል፡፡ በተቃራኒው በሬዲዮና በቴሊቪዥን ሰማያዊ ተቋማትን አይቀበልም እያለ በሀሰት እየወነጀለ ያለው የተቃውሞ ጎራው በአንድነት በመቆም እየተጠናከረ በመምጣቱ ነው፡፡›› ሲሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በሰማያዊ ስር መሰባሰባቸው ያለውን ፋይዳ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ እስር ቤት በደረሰባቸው ችግር ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ

መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ

መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ

የህዳር 27 እና 28 ቀን 2007 ዓ.ም. የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የጠራው የአዳር ሰልፍ ወቅት ተይዘው በደረሰባቸው ከፍተኛ ድብደባ እና ለሶስት ቀን የስኳር በሽታ መድሃኒት እንዳይገባላቸው በመከልከላቸው ለህመም የተዳረጉት የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) ምክትል ፀኃፊ መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ ከእስር ከተፈቱበት ጊዜ ጀምሮ ለሁለት ወር ሆስፒታል ከቆዩ በኋላ በዛሬው ዕለት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡

መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ በአዳሩ ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ተይዘው ከፍተኛ ድብደባ የደረሰባቸው ሲሆን ለአምስት ቀናት ቀዝቃዛና ጨለማ ቤት ውስጥ ታስረው ቆይተዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ከታሰሩበት ጊዜ ጀምሮ ይዘውት የነበረውን የስኳር በሽታ መድሃኒታቸውን በመቀማታቸው፣ እንዳይገባላቸው በመከልከላቸውና በወቅቱም ህክምናም ባለማግኘታቸው ለከፍተኛ ህመም በመዳረጋቸው ለሁለት ወር ያህል ዘውዲቱ ሆስፒታል ቆይተዋል፡፡

መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ እስር ቤት እያሉ በደረሰባቸው ችግር ምክንያት ዘውዲቱ ሆስፒታል ከገቡበት ታህሳስ 4 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ከፍተኛ ህመም እየተሰቃዩ እንደነበሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የመቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ የቀብር ስነስርዓት ዛሬ ጥር 27 ቀን 2007 ዓ.ም በቦሌ ሚካኤል እንደሚፈጸም ተጠቁሟል፡፡

ከዚህ በፊት ከኬንያ በህወሓት ደህንነት ታፍነው አዲስ አበባ ቃሊቲ በሚገኘው ወህኒ ቤት ታስረው በህወሓት ፖሊሶችና ደህንነቶች በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ድብደባ ኢንጂነር ተስፋሁን ጨመዳን ጨምሮ መገናኛ ብዙኃን ይፋ ያላወጣቸው የተለያዩ ኢትዮጵያውያን መሞታቸው ይታወቃል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድ የፓርቲዎች ሚዲያ አጠቃቀም ድልድል ፍትሃዊ አለመሆኑን አስታወቀ

Semayawi-Party

ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድ ያወጣው ረቂቅ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ውድድር የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ሰዓት አጠቃቀም ድልድል ፍትሃዊና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ አለመሆኑን አስታወቀ፡፡

ጥር 25 ቀን 2007 ዓ.ም የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሀገር አቀፍ ፓርቲዎችን በረቂቅ የሰዓት ድልድሉ ላይ ጊዮን ሆቴል ጋብዞ ውይይት አድርጓል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ) ኃላፊዎች ረቂቁን ለውይይት ያቀረቡ ሲሆን፣ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ እና ሌሎች ኃላፊዎችም በውይይቱ ተገኝተዋል፡፡

የኢብኮ/ኢቴቪ ኃላፊዎች ባቀረቡት የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚዲያ አጠቃቀም ረቂቅ ድልድል መሰረት 55 ፐርሰንት በፓርላማ መቀመጫ ወንበር ላላቸው ፓርቲዎች፣ 20 ፐርሰንት ፓርቲዎቹ በሚያቀርቧቸው ዕጩዎች ብዛት እንዲሁም ቀሪ 25 ፐርሰንቱ ለሁሉም ፓርቲዎች በዕኩል የሚከፋፈል እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲን በመወከል በውይይቱ ላይ የተገኙት የፓርቲው የህግ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ይድነቃቸው ከበደ ለነገረ ኢትዮጵያ እንደገለጹት፣ ረቂቅ የሚዲያ አጠቃቀሙ ድልድል ሲወጣ እንደ መስፈርት የተጠቀሙባቸው ነጥቦች ችግር ያሉባቸው ናቸው፡፡
‹‹በእኛ እምነት መስፈርቱም ልክ አይደለም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የሚዲያ ሰዓት አጠቃቀም ድልድል ሲወጣ ሁለት መስፈርቶች በቂና ትክክለኛ ናቸው ብሎ ያምናል፡፡ እነዚህ ነጥቦች በሚቀርቡ እጩዎች ብዛት እና በእኩልነት የሚከፋፈል የድልድል መስፈርት መሆን አለባቸው›› ብለዋል አቶ ይድነቃቸው፡፡

በእርግጥ ረቂቁን ያቀረበው ኢብኮ እንደ መመዘኛ መስፈርት የተጠቀመው ‹‹እኩልነትና ፍትሃዊነት›› የሚሉ መርሆዎችን ነው፡፡ ‹‹ኢብኮ በቃላት ደረጃ የገለጻቸው ‹ፍትሃዊነትና እኩልነት› በተግባር ረቂቅ ድልድሉ ላይ አልታዩም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በእኩልነትና ፍትሃዊነት መርሆዎች ላይ ችግር የለበትም፡፡ መርሁን መሰረት አድርጎ ወጣ የተባለው የሚዲያ ድልድል መጠን ግን በትክክል መርሁን የተከተለ አይደለም፡፡ ስለሆነም ለውጥ ሊደረግበት ይገባል›› ብለዋል አቶ ይድነቃቸው፡፡

አቶ ይድነቃቸው የሰዓት አጠቃቀም ድልድሉ ላይ ስንወያይ ነጻ ሚዲያ በሌለበት፣ ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በተገደበበት፣ ጋዜጠኞች በታሰሩበትና በተሰደዱበት፣ አማራጭ የሚዲያ ተቋማት በሌሉበት በዚህ አጣብቂኝ ወቅት ላይ በህዝብ ሀብት በሚተዳደሩ ሚዲያዎች ላይ የፍትሃዊነት ችግር ይዘን መወያያታችን አሳዛኝ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ሳንሱር በህገ-መንግስቱ ተነስቷል፤ ይሁን እንጂ ኢብኮ የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለያዩ ጊዜያት ለህዝብ የሚያስተላልፏቸው አማራጭ ሀሳቦችና ፖሊሲዎቻቸውን በቆርጦ ቀጥል ሲያዛባ እናስተውላለን፤ ይህ ሁኔታ መወገድ ያለበት ነው፡፡››

በውይይቱ ላይ ኢህአዴግ የድልድሉ መስፈርት ላይ እንደሚስማማ በመግለጽ፣ በፐርሰንቱ የተቀመጠው መጠን ላይ ግን መሻሻል እንዲደረግ እንደሚፈልግ መግለጹ ታውቋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ አባላት በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን ተቀላቀሉ

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ በወሰኑብን ፖለቲካዊ ውሳኔ ምክንያት አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን ተነጥቀናል ያሉ የአንድነት ፓርቲ አባላት› በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስታወቁ፡፡

በእነ በላይ ፍቃዱ አመራርነት አንድነት ፓርቲን በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ሲመሩ የነበሩ አመራሮች ዛሬ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት ከቀድሞ ፓርቲያቸው አንድነት ጋር የፕሮግራምም ሆነ የስትራቴጂ ተመሳሳይነት ወዳለው ሰማያዊ ፓርቲ ተቀላቅለው ሰላማዊ ትግላቸውን ለመቀጠል መወሰናቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡

መግለጫውን የ”ቀድሞው አንድነት ፓርቲ” አፈ ጉባዔ የነበሩት አቶ አበበ አካሉ፣ ምክትል አፈ ጉባዔው አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እንዲሁም የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊው አቶ ስንታየሁ ቸኮል ሌሎችን በመወከል ሰጥተዋል፡፡

“የምናምነው በሰላማዊ ትግል ብቻ ነው፡፡ ይህን ሰላማዊ ትግል ለመምራት ደግሞ ሰማያዊ ፓርቲ ብቁ ነው ብለን በማመን ፓርቲውን ተቀላቅለናል” ብለዋል በመግለጫው ላይ የተወከሉት አዲሶቹ የሰማያዊ አባላት፡፡
በዚህ መሰረትም በርከት ያሉ አመራሮችና አባላት በይፋ የሰማያዊ ፓርቲ የአባልነት ፎርም ሞልተዋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአንድነት አባላት ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስመልክቶ መግለጫ ለመስጠት ወደ ሰማያዊ ቢሮ ባቀኑበት ወቅት፤ፖሊስ ሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ድረስ በመግባት “በሰማያዊ ስም መግለጫ የሚሰጡ አካላት እንዳሉ ሰለሰማን ነው” በሚል ለፓርቲው አመራሮች ጥያቄ ማቅረባቸውን ከስፍራው የደረሰን ዘገባ አመልክቷል፡፡

የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደረገ

prisoners

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ውድቅ ተደረገባቸው፡፡ አመራሮቹ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ችሎት ቀርበዋል፡፡

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱት የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች መቃወሚያቸው በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡

ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የቀረቡባቸው የተለያዩ የክስ ይዘቶች ላይ መቃወሚያቸውን አቅርበው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ የተከሳሽ መቃወሚያ ውድቅ እንዲደረግለት የጠየቀውን በመቀበል ‹‹በመቃወሚያው ላይ የተነሱት ነጥቦች በአብዛኛው ማስረጃ በማሰማት ሂደት ወቅት ሊረጋገጡ የሚችሉ ስለሆኑ›› በሚል መቃወሚያቸው ውድቅ ተደርጓል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤት በቀረበው ክስ አግባብ የክስ ሂደቱ እንዲቀጥል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ በሚገኙበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ላይ ‹‹የመብት ጥሰት እየተፈጸመብን ነው›› በሚል አቤቱታ አቅርበው የነበር ሲሆን በአቤቱታው ላይ እስካሁን ከማረሚያ ቤቱ መልስ አለመሰጠቱ ታውቋል፡፡ አቤቱታው በጽሑፍ ተገልብጦ ለማረሚያ ቤቱ መላኩን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ ለአቤቱታው መልስ ከማረሚያ ቤቱ እየተጠበቀ እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

በመሆኑም ይህንኑ የማረሚያ ቤቱን መልስ ለመስማትና የክሱን ሂደት ለመቀጠል ፍርድ ቤቱ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ፡-ነገረ-ኢትዮጵያ