Tag Archives: Oromo Protest Ethiopia

እነ በቀለ ገርባ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ገለፁ

”ፍርድ ቤቱ ገለልተኛ ነው ብዬ ስለማላምን ቃሌን አልሰጥም” አቶ በቀለ ገርባ

Bekele Gerba

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የቀረበባቸው የኦፌኮ አመራሮችና አባላት በቀረበባቸው ክስ ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ጉዳያቸውን ለሚያየው ችሎት ገልጸዋል፡፡
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 5 ቀን 2008 ዓ.ም መዝገቡን የቀጠረው የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ሲሆን፣ ችሎቱ ተከሳሾችን አንድ በአንድ በስማቸው እየጠራ የቀረበባቸውን የወንጀል ድርጊት ስለመፈጸም አለመፈጸማቸው የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡት ጠይቋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ አቶ ጉርሜሳ አያኖ የቀረበባቸውን ክስ የወንጀል ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም ተብለው ሲጠየቁ፣ ‹‹ይሄ ክስ ለእኔ ግልጽ አይደለም፡፡ በመቃወሚያ ላይ ይህን ገልጫለሁ፡፡ እኔ በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ የሚታገል ፓርቲ አባል ሆኜ ስታገል የኦነግ አባል ሆነሃል ተብዬ መከሰስ የለብኝም፡፡ ይህ የምታገልለትን ህዝብ እንደመወንጀል ይቆጠራል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ አሸባሪ ከተባለ እኔም አሸባሪ ነኝ፡፡ ይህ በደል ነው፡፡ ስለዚህ እኔ እዚህ ቆሜ ቃሌን መስጠት አያስፈልገኝም›› በማለት ተናግረዋል፡፡

2ኛ ተከሳሽ አቶ ደጀኔ ጣፋ በበኩላቸው ‹‹እኔ የምታገልለት ህዝብ በመንግስት ጦር እያለቀ ባለበት ሰዓት እኔ እዚህ ቆሜ ቃሌን መስጠት አልፈልግም፡፡ ይህ ፍርድ ቤትም ህገ-መንግስቱን የጣሰ ውሳኔ ስላሳለፈብኝ ለዚህ ፍርድ ቤት ቃሌን መስጠት ታሪካዊ ስህተት ነው የሚሆነው፡፡ ድጋሜ እዚህ ፍርድ ቤት መቅረብም አልፈልግም›› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ አዲሱ ቡላላም በተመሳሳይ ቃላቸውን ለመስጠት እንደማይፈልጉ ተናግረዋል፡፡ ‹‹የደረሰን በክስ መልክ የቀረበ ድረሰት ግልጽ አይደለም፡፡ በባህላችን ውሻ እንኳ ዝም ተብሎ አይነካም፡፡ ከተነካም ባለቤቱን መናቅ ነው የሚሆነው፡፡ እኔ ለኦሮሞ ህዝብ በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ እታገላለሁ፡፡ የተሰጠኝ ድርሰት ግን የኦነግ አባል ሆነሃል የሚል ነው፡፡ እኔ የኦፌኮ አባል እንጂ የኦነግ አባል አይደለሁም፡፡ ስለዚህ በፍርድ ቤቱ ወንጀሉን ፈጽመሃል አልፈጸምህም ተብዬ ስጠየቅ ያሳፍረኛል፡፡ ከዚህ በኋላ አስገዳጅ ሁኔታ ካልተፈጠረ በቀር እዚህ ችሎት መቅረብ አልፈልግም፡፡ ውሳኔያችሁን ልትልኩልኝ ትችላላችሁ›› በማለት ለችሎቱ ተናግረዋል፡፡

የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ታደለ ተገኝ ተከሳሾቹ በአጭሩ ድርጊቱን ስለመፈጸም አለመፈጸማቸው ብቻ መልስ እንዲሰጡ፣ ሌላ ረጂም ንግግር ማድረግ ተገቢ እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ማሳሰቢያ ሲሰጡ ተደምጠዋል፡፡
ከማሳሰቢያው በኋላ፣ 4ኛ ተከሳሽ የሆኑት የኦፌኮ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ በቀለ ገርባ ደግሞ፣ ‹‹በክስ መቃወሚያችን ወንጀሉ ተፈጸመ በተባለበት ቦታ እንዳኝ ብለን ጠይቀን ይህ ችሎት ውድቅ አድርጎታል፡፡ ጥያቄያችን ህገ-መንግስታዊ ነበር፡፡ ግን አልተቀበላችሁትም፡፡ ስለዚህ ይህ ፍርድ ቤቱ ገለልተኛ ነው ብዬ ስለማላስብ ቃሌን ለመስጠት አልፈልግም፡፡ ካሁን በፊትም የሀሰት ማስረጃ ቀርቦብኝ ስምንት አመት ፈርዶብኛል፡፡ የዚህንም ውሳኔ ባለሁበት ልትልኩልኝ ትችላላችሁ›› ብለዋል፡፡

ከ5ኛ ተከሳሽ ጀምሮ እንዲሁ በተመሳሳይ ቃላቸውን እንዲሰጡ እየተጠየቁ በአብዛኛው ተመሳሳይ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ከተከሳሾች መካከል 10ኛ እና 12ኛ ተከሳሾች ብቻ ‹‹ድርጊቱን አልፈጸምንም›› የሚል ቀጥተኛ የክህደት ቃላቸውን ሲሰጡ 13ኛ ተከሳሽ በበኩሉ የዝምታ ምላሽን ሰጥቷል፡፡ 7ኛ ተከሳሽ ‹‹ክሱ ንቀትና ጥላቻ የታጨቀበት ስለሆነ መልስ አልሰጥም›› ሲል ቀሪዎቹ ክሱ ግልጽ አይደለም፣ ፍርድ ቤቱም ገለልተኛ ነው ብለን አናምንም በሚል የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ለችሎቱ ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር 11ኛ እና 19ኛ ተከሳሾችን ‹‹በስራ ጫና ምክንያት ቆጥረን አረጋግጠን ማቅረብ አልቻልንም›› የሚል መልስ በሰጠበት ምክንያት ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡ ይህን በተመለከተ ጠበቃቸው በሰጡት አስተያየት ደበኞቻቸው ላይ የደህንት ስጋት ተጋርጦባቸው ሊሆን እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸው ፍርድ ቤቱ ይህንኑ ስጋታቸውን እንዲመዘግብላቸው አሳስበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ አስተዳደሩ በነገው ዕለት እንዲያቀርባቸው በማዘዝ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመቀበል ቀጠሮ ይዟል፡፡

ፍርድ ቤቱ ዛሬ የቀረቡት ተከሳሾች ቃላቸውን ለመስጠት ፍቃደኛ አለመሆናቸውን ከመዘገበ በኋላ ‹‹ወንጀሉን አልፈጸምንም›› እንዳሉ ተቆጥሮ ክደው እንደተከራከሩ በመመዝገብ ያለ አቃቤ ህግ አሳሳቢነት የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በሚል ከህዳር 02-16 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ የሰው ምስክሮች በርካታ በመሆናቸው ተከታታይ የቀጠሮ ቀናትን መስጠቱን ገልጹዋል፡፡
በዛሬው የችሎት ውሎ ተከሳሾቹ ዳኞች ወደ ችሎት ሲገቡም ሆነ ችሎቱ ጉዳያቸውን ሲያይ በችሎቱ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ ለመግለጽ ከመቀመጫቸው ሳይነሱ ቀርተዋል፡፡
ምንጭ፡-EHRP

በኢትዮጵያ በሁለት ቀናት ብቻ በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ዜጎች ተገደሉ

(አዲስ ሚዲያ) በኢትዮጵያ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እና አማራ ክልል በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል ርምጃ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ በርካታ ሰላማዊ ንፁሃን ዜጎች ተገደሉ፡፡ በተለይ እንደ መብት አራማጆች እና የአካባቢው ምንጮች መረጃ ከሆነ በሁለቱ ቀን የኦሮሚያ እና አማራ ክልል የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ንፁሃን ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡

በተለይ እንደ መብት አራማጆች መረጃ ከሆነ፤መነሻውን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን በማድረግ ወደ ጠቃላይ ሀገራዊ ይዘት የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የኦሮሞ ተቃውሞ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል ባሉ ከተሞች አጠቃላይ በተጠራው የረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ 67 ያህል ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደራዊ ርምጃ ሲገደሉ፤ ከ500 ያላነሱ በፅኑ ቆስለው በክምና ላይ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ትናንት በነበረው የኦሮሚያ ክልል እና የአዲስ አበባ ተቃውሞ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎች መታሰራቸውም ተጠቁሟል፡፡

Oromo Protest, Adama

በትናንትናው ተቃውሞ በኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ ግድያ ከተፈፀመባቸው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች መካከል በምዕራብ አርሲ አሳሳ፣ በምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ እና ሐረማያ እንዲሁም በምስራቅ ወለቃ ነቀምት ከተሞች ዋነኛ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በነበረው የኦሮሚያ ተቃውሞም የህወሓት መንግሥት በቃን፣ የኦሮሞን ህዝብ መግደል ይቁም፣ የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ፣አሸባሪ አይደለንም፣ አማራ የእኛ ነው፣ የጎንደር አማራዎችን መግደል ይቁም፣ የወልቃይት ጥያቄ ሕገ መንግሥታዊ ነው፣ወያኔ ሌባ፣…የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡ በነበሩ የተቃውሞ ሰልፍ ከተሞች እና አካባቢዎች በርካታ ሰዎች መሳተፋቸውን ከኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ፣ ማኀበራዊ ሚዲያ እና ከተለያዩ አካባቢዎች ያገኘናቸው የዓይን እማኞች መረጃ ማወቅ ተችሏል፡፡

በተመሳሳይም በአማራ ክልል በተለይም በደቡብ ጎንደር ዞን ደብረ ታቦር ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. በተጠራው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ ላይ መንግሥት በወሰደው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ ከ6 ያላነሱ ሰዎች ወዲያው ሲገደሉ በርካቶች በመቁሰላቸው፣ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች እና በደቡብ ጎንደር ጋይንት ጨምሮ የተለያዩ ወረዳቸዎች ነዋሪዎች በመቆጣት በድንገት የተቃውሞ ሰለፍ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ መነሻውን የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ በማድረግ ወደ አጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የአማራ ተቃውሞን ተከትሎ መንግሥት ከደብረ ታቦር በተጨማሪ የተቃውሞ ሰልፎች በነበሩበት ስፍራዎች ሁሉ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በመወሰዱ የህዝቡ ቁጣ ተባብሱ የህወሓት ደጋፊና ተባባሪ ናቸው የተባሉ የንግድ ተቋማት፣ የመንግሥት ተሸከርካሪዎች እና ተቋማት ላይ እንዲሁም በጎንደር አዘዞ የሚገኘውን የመከላከያ ወታደራዊ ካምፕ ከጥቅም ውጭ ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡

በሰሜን ጎንደር ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በሰሜን ጎንደር ሳንጃ፣ ቆላ ድባ፣ ዳባት፣ አርማጭሆ፣…በመሳሰሉ ቦታዎች በመንግሥት ወታደሮች እና በህዝቡ መካከል ውጊያ መኖሩን እና የመንግሥት ወታደሮችን እና ከህዝቡም በርካታ ሰዎች መሞታቸውን እና መቁሰላቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በባህርዳር ከተማ በነበረው የአማራ የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ከ30 ያላነሱ ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ታውቋል፡፡ በአማራ ክልል ዛሬ የተገደሉ 30 ያህል እና ትናንት ደብረ ታቦር ከተገደሉ 6ቱ በተጨማሪ ሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች በተደረገ የትናንት እና የዛሬ ተቃውሞ 29 ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡ ህዝቡም በባህርዳር የተለያዩ ህዝባዊ ተቋማት ሰንደቅ ላይ የብአዴን እና በኢህአዴግ የፀደቀውን የፌደራሉን ሰንደቅ ዓላማ በማውረድ የቀድሞውን አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቅሉ እና ሲያውለበልቡ ተስተውሏል፡፡ በአጠቃላይ በሁለቱ ቀን የአማራ ክልል ተቃውሞ 65 ያህል ዜች ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎችም መቁሰላቸውን እና የህክምና ርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡

AmharaProtest, Bahirdar

በተለይ በደብረ ታቦር እና ባህርዳር በተደረገው የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ፤ ወልቃይት የአማራ እንጂ የትግሬ አይደለም፣ ወልቃይት አማራ ነው፣ ለሱዳን የተሸጠው መሬታችን ይመለስ፣ የታሰሩት ይፈቱ፣ በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ የሚደረገው ግድያ ይቁም፣ በቀለ ገርባ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ ኢትዮጵያዊነት አሸባሪነት አይደለም፣በኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ አንደራደርም፣ወያኔ ሌባ፣አንዳርጋቸው ጽጌ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ የህወሓት አገዛዝ በቃን፣ ግድያ ይቁም፣….የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡

በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እየተካሄደ ባለው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ በርካታ መረጃዎች በመታፈናቸው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደረዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ እና የቆሰሉ ዜጎች ቁጥር ከተጠቀሰው ሊጨምር እንደሚችል ይገመታል፡፡

በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል በነበሩ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በጠፋው የሰው ህይወት እና በወደሙ ንብረቶች ዙሪያ እስካሁን ከገለልተኛ አካል የተጣራ ይፋ ማብራሪያም ሆነ መግለጫ የለም፡፡ ይሁን እንጂ በሁለቱም ክልሎች ባሉ በርካታ ወረዳዎችና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ አለመረጋጋቱ እንደቀጠሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የመንግሥት የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ ቀጥሏል

(አዲስ ሚዲያ) በኦሮሚያ ክልል ዘጠነኛ ወሩን ያስቆጠረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለው የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል፡፡ ዛሬ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ ከተማ በነበረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ 6 ሰዎች በልዩ አልሞ ተኳሽ የፀጥታ ኃይል ሲገደሉ፤ በዊልቸር የሚንቀሳቀስ አካል ጉዳተኛን ጨምሮ 20 ያህሉ መቁሰላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በፀጥታ ኃይሉ ተኩስ የቆሰሉ ሰዎችም በሐረር እና ድሬዳዋ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው መሆን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

Aweday rally
በተመሳሳይም በሐረማያ ህዝባዊ ተቃውሞ መቀስቀሱ የተጠቆመ ሲሆን፤ በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ታዳሚው ላይ በመንግሥት በተወሰደ ርምጃ ጉዳት መድረሱ ቢነገርም እስካሁን በዝርዝር ለማወቅ አልተቻለም፡፡ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በህዝቡ ላይ የወሰዱትን የኃይል ርምጃ ተከትሎ በተለይ የአወዳይ ከተማ ነዋሪ ከአዲስ አበባ ሐረር እና ጅግጅጋ መንገድን ሙሉ ለሙሉ ዘግቶ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡ በዚህ በተገባደደው ሳምንት በምዕራብ አርሲ እና ምዕራብ ሐረርጌን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የወረዳ ከተሞች ጭምር የተለያዩ ህዝባዊ ተቃውሞች መደረጋቸውና ይህንንም ተከትሎ በቅርቡ ከአዳማ ዩኒቨርስቲ የተመረቀ ተማሪን ጨምሮ ሌሎች ንፁሃን ዜጎችም በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን በመግለፅ የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ ከተማ ዳግም በተቀሰቀሰው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ እስካሁን ከ500 በላይ ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና በርካቶችም ቆስለው ህክምና ሲከታተሉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው በዚህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከ30 ሺህ በላይ ዜጎች እንደታሰሩ የመብት አራማጆች ያስታወቁ ሲሆን፤ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የተለያዩ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችም ለእስር ተዳርገዋል፡፡

አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ በቃሊቲ እና ቂሊንጦ ወህኒ ቤቶች የሚከገኙ የተለያዩ የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች በወህኒ ቤቱ አስተዳደርና በሌሎች የፍትህ አካላት እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመቃወም ላለፉት 10 ቀናት የርሃብ አድማ በመምታቸው ራሳቸውን ስተው በጉሉኮዝ እገዛ እንደነበሩ ፍርድ ቤት ከቀረባ አቤቱታ መረዳት ተችሏል፡፡

በእነ በቀለ ገርባ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላለፈ

*ወህኒ ቤት ለአቶ በቀለ ገርባ የታዘዘውን መድሃኒት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል

Bekele Gerba

በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኙት እነ በቀለ ገርባ (22 ሰዎች) የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሰባቸው መሆኑን ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤት ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ችሎቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት (ጉዳያቸውን ያይ የነበረው 19ኛ ወንጀል ችሎት እንደነበር ይታወሳል 19ኛ ችሎት ለሁለት ተከፍሎ አዲስ 4ተኛ ችሎት የሽብር ጉዳዮችን ማየት ጀምሯል) በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሰኔ ቀን 2008 ዓ.ም የሰጠውን መልስ ተመልክቶ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾች ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ ድብደባ እንደደረሰባቸው፣ ልብሶቻቸው እንደተወሰዱባቸው፣ በጨለማ ቤት ስለመታሰራቸው፣ በህክምና የታዘዘን መድሃኒት እንዳያገኙ ስለመደረጋቸው፣ ቤተ መጽሐፍት እንዳልተሟላላቸው፣ በቤተሰቦቻቸው እንዳይጎበኙ ገደብ እንደተጣለባቸው፣ ገንዘብ እንደተወሰደባቸው እና ሌሎች የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንደደረሱባቸው አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር በበኩሉ አቤቱታቸውን ‹‹የተቋሙን ስም ለማጥፋት›› የቀረበ ነው ሲል አጣጥሎ መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡

በዚህ ላይ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ውሳኔውን አሳውቋል፡፡ በዚህ መሰረት በሀኪም የታዘዘን መድሃኒት ማግኘት አልቻልንም በሚል ተከሳሾች ላቀረቡት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የእስር ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣሪዎቹ መድሃኒቱን እንዲያገኙ እንዲፈቅድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ድብደባ ደርሶብናል፣ ገንዘብም ተወስዶብናል በሚል ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ድርጊቱ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀል ስለሆነ አስፈላጊውን ማጣራት አድርገው ተከሳሾች በህግ ሊጠይቁ የሚገባቸው ስለሚሆን በዚህ የክስ መዝገብ ውሳኔ ሊሰጥበት አይችልም ብሏል፡፡
ተከሳሾች በጨለማ ክፍል መታሰራቸው ህግን ያልተከተለና የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በተመለከተ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ‹‹በማረሚያ ቤቱ በኩል ጨለማ ቤት የለም ተብሏል፤ ተከሳሾች ደግሞ ጨለማ ክፍል ታስረናል ብለዋል፡፡ ይህ ጉዳይ ማጣራትን የሚጠይቅ ስለሆነ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ጉዳዩን አጣርቶ ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም አስተያየቱን ይስጥበት›› የሚል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

የቤተ መጽሐፍትና የቴሌቪዥን አለመሟላትን እና የቤተሰብ ጥየቃ ሰዓትን በተመለከተ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ‹የማረሚያ ቤቱን አስተዳደራዊ አሰራር የሚመለከት ስለሆነ ውሳኔ አንሰጥበትም› በሚል አልፎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አቶ ደጀኔ ጣፋ በቤተሰብ መጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታችን እንጂ የአስተዳደር ጉዳይ ነው ተብሎ የሚታለፍ እንዳልነበር በመጥቀስ በውሳኔው ላይ ቅሬታቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡

ሌላ የተሰሙ አቤቱታዎች

ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ በተከሳሾች ለቀረቡት አቤቱታዎች ውሳኔ ቢያሳልፍም ዛሬም ሌሎች አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡ በዋናነት አቶ በቀለ ገርባ የታዘዘላቸውን መድሃኒት አለማግኘታቸውን በተመለከተ የቀረበ አቤቱታ ሲሆን፣ አቶ በቀለ መድሃኒት ከታዘዘላቸው ሁለት ወራት ቢቆጠርም መድሃኒቱን ማግኘት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ዋና ኦፊሰር የሆኑት ተሾመ ስዩም በጽሁፍና በቃል በሰጡት መልስ እንደተመለከተው ለአቶ በቀለ ገርባ በሀኪም የታዘዘላቸው መድሃኒት በአስተዳደሩ ባለሙያዎች በመንግስትና በከነማ መድሃኒት ቤቶች ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ‹‹መድሃኒቱ ተፈልጎ አለመገኘቱንና የሚችሉ ከሆነ በቤተሰብ በኩል እንዲሞክሩ ለአቶ በቀለ ነግሬያቸዋለሁ›› ብለዋል ዋና ኦፊሰሩ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው በኦፊሰሩ የተሰጠው መልስ ስህተት ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ፍርድ ቤት እንደምቀርብ አውቀው የተዘጋጁበት መልስ ነው፡፡ ለእኔ የነገሩኝ ነገር የለም›› ብለዋል አቶ በቀለ፡፡ ፍርድ ቤቱ ይህን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ በቤተሰብ በኩል መድሃኒቱ ተገዝቶ እንዲገባ እንዲፈቅድ ማሳሰቢያ በመስጠት አልፎታል፡፡

ሌላው አቶ በቀለን ከሚኖሩበት አዳማ ከተማ ተመላልሰው ከሚጠይቋቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ልጃቸው ቦንቱ በቀለ ባለተገለጸ ምክንያት አባቷን በእስር ቤት እንዳትጠይቅና ምግብ እንዳታደርስላቸው መከልከሏን የአቶ በቀለ ጠበቃ ለችሎት በመግለጽ፣ ልጃቸው አባቷን እንድትጠይቅና ስንቅ እንድታቀብላቸው እንዲፈቀድላት ችሎቱን ጠይቀዋል፡፡ ችሎቱ ዋና ኦፊሰር ተሾምን ስለጉዳዩ ቢጠይቅም፣ ኦፊሰሩ ‹የማውቀው ነገር የለም፣ ግን ለሚመለከታቸው አካላት አሳውቃለሁ› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡

በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ የስዋህሊኛ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በተደጋጋሚ አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ስዋህሊኛ አስተርጓሚ ኬንያ ኤምባሲ ጭምር ተፈልጎ ማግኘት እንዳልተቻለ ተገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሹ በመጠኑ እግሊዝኛ ቋንቋ ስለሚረዱ የእንግሊዝኛ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በጠበቃቸው በኩል አሳስበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የመቃወሚያ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

ምንጭ፡- EHRP

እነ በቀለ ገርባ ላቀረቡት የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ምላሽ ለመስጠት ዳግም ቀጠሮ ሰጠ

– አቶ ደጀኔ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መገናኘት እንዲችሉ ፍርድቤቱ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
– አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አቤት ብለዋል፡፡
– አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ሰለታመሙ ህክምና እንዲያገኙ ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
– ተከሳሾች ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀው፡ ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሏል፡፡

Bekele-June-27-court-150x150

ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ጉርሜሳ አያኖ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች አመራሮች(22 ተከሳሾች) ዛሬ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ችሎቱን ከሚመሩት ሶስት ዳኞች መካከል ዳኛ ታደለ ተገኝ ስልጠና ላይ በመሆናቸው የተከሳሾችን አቤቱታ እና የማረሚያ ቤቱን ምላሽ መርምረው ብይን መስራት እንዳልቻሉ ዳኛ ሳሙኤል ታደሰ ለተከሳሾች አስረደተዋል፡፡

ፍርድቤቱ ብይኑን ለመሰጠት ማክሰኞ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም ከሰዓት በኃላ ቀጥሯል፡፡
የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት አዲስ አበባ ድረስ መጥተው በጡረታ መታወቂያ ልጃቸውን ለማየት እንደተከለከሉ ያሰረዱት የተከሳሽ ጠበቃ ፍርድቤቱ መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀው ፍርድቤቱ በተለየ ሁናቴ የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት ስም ከነአባት በዝርዘር ጠይቆ ለማረሚያ ቤቱ ጉብኝት እንደፈቀድላቸው ትዕዛዝ እንደሚሰጥ ገልጿል፡፡

አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አመልክተዋል ፤በሌላ በኩል አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ታመው ህክምና ቢጠይቁ ከህመም ማስታገሻ ውጪ ምንም እርዳታ እንዳልተሰጣቸው እና ለከፍተኛ ህመም መጋለጣቸውን አስርድተዋል፡፡ ፍርድቤቱ ህክምናን በተመለከተ ተከሳሾቹ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ ትዕዛዝ ለማረሚያ ቤቱ ስጥቷል፡፡

በተያያዘ የተከሳሾችን አቤቱታ ሲሰማ የዋለው ችሎት ተከሳሾች ክስ ተመስርቶባቸው ከማዕከላዊ ፖሊስ ምርመራ ወደ ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተከሳሾች ብራቸውን ቆጥረው ለማረሚያ ቤቱ እንዳስረከቡ ምስክሮች አሉን ቢሉም ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሎ ለፍርድቤቱ ደብዳቤ ልኮ አስታውቋል፡፡

ምንጭ፡-የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት