Tag Archives: Oromo Protest Ethiopia

በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ በተቀሰቀሰ ግጭት 4 ሰዎች ተገደሉ

(አዲስ ሚዲያ)በምስራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ ትናንት ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት በመንግሥት ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት የ9 ዓመት ህፃንን ጨምሮ 4 ያህል ነዋሪዎች በከተማው አስተዳደርና በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኘው የሐሮማያ ሆስፒታል በበኩሉ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 4 መሆኑን እና የቆሰሉ 3 ሰዎች በሆስፒታሉ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ተጠቁሟል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 6 እንደሆነ እና በፅኑ የቆሰሉት ደግሞ 4 እንደነበሩ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

Aweday firing

በዕለቱ የግጭቱ መነሻ እንደሆነ የተነገረው በአወዳይ ከተማ ውስጥ ያለ አንድ የሞባይል ስልክ መሸጫ ሱቅና አጠገቡ ያለው የፍራሽ መሸጫ ሱቅ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠላቸው የተነሣ የአከባቢው ህዝብ እሳቱን ለማጥፋት ጥረት ቢያደርግም ሊሳካ ባለመቻሉ በአከባቢው ያሉትን የባለሥልጣናት ለእርዳታ ቢማፀኑም ቆመው ከመሳቅ ባለፈ ምንም እርዳታ ባለማድረጋቸው የተበሳጩ ነዋሪዎች “ድሮም እናንተ የምታደርጉልን ነገር የለም” ስለዚህ ከዚህ ሂዱ ብለው በመናገራቸው የፀጥታ ኃይሎች በስልክ ወደ ቦታው መጠራታቸውንና ግጭቱ መከሰቱን የአካባቢውን ነዋሪ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የነጋዴዎቹን ሱቅ ቃጠሎ ተከትሎ በህዝቡና በመንግሥት በተለይም በአካባቢው አስተዳደር አካለትና የፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት የአወዳይ ቀበሌ 02 ሊቀመንበር አቶ አብዲ ኢድሪስ በቃጠሎው ስፍራ የነበሩ ነዋሪዎች ላይ በከፈቱት ተኩስ የ9 እና የ13 ዓመት ህፃናት ቆሰሉ፡፡ በሊቀመንበሩ የቆሰሉ ህፃናትም ወደ አካባቢው የጤና ተቋም ቢወሰዱም ወዲያው ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች በቁጣና በጩኸት ወደቆሰሉ ህፃናት ሲመጡ የኦሮሚያ ልዩ ፖሊስ እና የፌደራል ፖሊስ በድንገት ወደስፍራው በመምጣት፣ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ተኩስ ከፍቶ 3 ወጣቶች ወዲያው ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎችም በፅኑ መቁሰላቸውን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኝ ተናግረዋል፡፡

Aweday town protest

በመንግሥትና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት በአወዳይ የሐረር መንገድ ዝግ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ይሁን እንጂ በግጭቱ ዙሪያ እስካሁን ከመንግሥት አካል የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ማግኘት አልተቻለም፡፡

በኦሮሚያ ክልል ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በነበረው ተቃውሞ ከ400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ሂውማን ራይትስ ዎች ይፋ አደረገ

ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች ከ400 በላይ የሚሆኑ ሰልፈኞችን የገደሉ ሲሆን ከአስር ሺህ በላይ የሚቆጠሩትን ደግሞ ማሰራቸውን አስታውቋል፡፡ የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ “የኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ እስራቶችንና ሌሎች የመብት ጥሰቶች በአስቸኳይ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኛ የሆነ ማጣሪያ እንዲካሄድ ድጋፍ ማድረግ አለበት።” ሲል ባለ 61 ገፅ ሪፖርት ይፋ አድርጓል፡፡

HRW logo

ድርጅቱ ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው ባለ 61 ገጽ ሪፖርት “ጭካኔ የተሞላበት አፈና’ – የግድያ እና የእስራት ምላሽ፤ ለኢትዮጵያ የኦሮሞ ተቃውሞ” የሚል ነበር፡፡ መንግሥትም በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ ርምጃ መውሰዱን በመግለፅ ድርጊቱን አውግዟል፡፡ ሪፖርቱ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ እንዲሁም ሀሳባቸውን በነጻነት በሚገልጹ ዜጎች ላይ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን፣ ከ125 በላይ የሚሆኑ የተቃውሞ ሰልፎች ተሳታፊዎችን፣ ጉዳዩን በአንክሮ ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦችን፣ በተለያዩ ጊዜያት የመብት ጥሰት የተካሄደባቸውና ጉዳት የደረሰባቸውን ግለሰቦች ያካተተ ቃለ መጠይቅ ማድረጉንም አስታውቋል፡፡

በመንግሥት የተቋቋም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮምሽን ይህንን የኦሮሚያ ክልል ተቋውሞ ተከትሎ በተወሰደ ርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 173 ብቻ መሆናቸውን እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃም “ተገቢና ተመጣጣኝ” ነው ሲሉ ኮሚሽነሩ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ሰኔ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. “ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት” እና ለጋዜጠኞች ገልፀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ተገቢና ተመጣጣኝ ያሉት ርምጃ የተወሰደው በመከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል መሆኑንም ለጋዜጠኞች ጠቁመዋል፡፡

Oromo Protest_Ethiopia

መንግሥታዊ ያልሆነው ሀገር በቀል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፤ በኦሮሚያ ክልል በነበረው ተቃውሞ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃ ተገቢና ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ቀደም ሲል ይፋ ባደረገው ዝርዝር ሪፖርት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በነበረውን ተቃውሞ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ፤ ሀገር በቀል የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ባለፈው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም በመግለፅ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

ሙሉውን የሂውማን ራይትስ ዎች ሪፖርት እዚህ https://www.hrw.org/news/2016/06/15/ethiopia-protest-crackdown-killed-hundreds  ያገኙታል፡፡

የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ወደ ሐምሌ 4 ተራዘመ

(አዲስ ሚዲያ)  ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ተራዘመ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር ባለፈው ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ሊሰጥ የነበረው ፈተና መከካከል ሁለት የትምህርት ዓይነቶች ቀድመው በማኀበራዊ ሚዲያ ከነመልሶቻቸው መለቀቃቸውን ተከትሎ እንዲቋረጥ የተደረገው ፈተና ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ለመስጠት ትምህርት ሚኒስቴር መርሃ ግብሩን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ቅሬታና ተቃውሞ አስከትሎ ነበር ፡፡

Ethiopian Minstry of education
በተለይ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. መካከል የረመዳን ፆም ፍቺ በዓል ላይ የሚውል ተቃውሞ በመቅረቡ፣ ትምህርት ሚኒስቴርም ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ቅሬታ በመቅረቡ ፈተናው በአንድ ሳምንት ተራዝሞ ከሐምሌ 4-7 ቀን 2008 ዓ.ም. እንደሚሰጥ አስታውቋል ፡፡

ቀደም ሲል ግንቦት ሊሰጥ የታሰበውን መርሃ ግብር እንዲቀየር ያስገደዱት የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎችም ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚሰጠው አዲሱ መርሃ ግብር ላይ ሌላ ተቃውሞ እንደማያስነሱና ከባለስልጣናቱ ጋር እልህ መጋባቱ አላስፈላጊ መሆኑን በመጥቀስ፣ ተማሪዎች ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚሰጠውን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተረጋግተው እንዲፈተኑ ጠይቀዋል፡፡

ትምህርት ሚኒስቴር እና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች በየበኩላቸው በየአካባቢው ያሉ መምህራን፣ ወላጆች፣ አስተዳደሮች እና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ ለተማሪዎች እንዲያደርጉላቸው የትብብር ጥያቄ አቅርበዋል፡፡

 

ትምህርት ሚኒስቴር በአዲሱ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና መርሃ ግብር በድጋሚ ተቃውሞ ገጠመው

(አዲስ ሚዲያ) የትምህርት ሚኒስቴር ከግንቦት 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ ያዘጋጀውን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በገጠመው ተቃውሞ ፈተናው ከመሰጠቱ ቀናት አስቀድሞ የእንግሊዘኛ እና ሒሳብ ትምህርት ፈተናዎች ከነመልሶቻቸው በማኀበራዊ ገፅ ይፋ በመደረጉ ምክንያት ፈተናው ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ከተደረገ በኋላ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. ብሔራዊ ፈተናውን ለመስጠት አዲሱ መርሃ ግብሩ ይፋ አድርጓል፡፡

 

Ethiopian Minstry of education

ይሁን እንጂ ይህ አዲሱ የዩነቨርስቲ መግቢያ ፈተና ቀደም ሲል በተለይም በኦሮሚያ ለወራት በዘለቀውን ህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት በተለያዩ አካባቢዎች ትምህርት በመቋረጡ ፈተናው እንዲራዘም የጠየቁት ጥያቄ በመንግሥት በኩል በጎ ምላሽ ባለመገኘቱ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች እርምጃውን እንደወሰዱ አስታውቀው፤አዲስ የወጣውም የፈተና መርሃ ግብር ቢያንስ ለሁለት ወራት እንዲራዘም ምክረ-ሐሳብ አቀርበዋል፡፡ በተለይም እንደ አስተባባሪዎቹ ገለፃ ከሆነ፤ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው ፈተና በኦሮሚያ አካባቢ የነበረውን የትምህርት መቋረጥ እና አለመረጋጋት ግምት ውስጥ ያላስገባ ከመሆኑ በተጨማሪ በሀገሪቱ የሙስሊሞች ረመዳን በዓል የሚውለው ፈተናው ሊሰጥ በተገለፁ ቀናቶች በመሆኑ በድጋሚ የፈተናው መርሃ ግብር እንዲራዘም ጠይቀዋል፡፡

በተመሳሳይም የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ድምፃችን ይሰማ አስተባባሪዎችም አዲሱ የፈተና መርሃ ግብር የሙስሊም ተማሪዎች በፆምና በዓል ምክንያት ፈተናው ላይ ተረጋግተው ሊቀመጡ ስለማይችሉ ፈተናው ሊራዘም እንደሚገባ ጠይቀዋል፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በበኩላቸው ለፋና ቢሲ እንደገለፁት ከሆነ አዲሱ የፈተና መርሃ ግብር የሙስሊሞችን በዓል ታሳቢ ያደረገ እንደሆነ እና በዓሉ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. ውስጥ ከዋለ፤ በበዓሉ ዕለት ፈተና እንደማይኖር አስታውቀዋል፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ተወካይ ኃላፊው አቶ መሐመድ ሲራጅ በበኩላቸው መስሪያ ቤታቸው አዲሱን የፈተና መርሃ ግብር ሲያወጣ በዓሉን ሳይዘነጋ መሆኑን እና ከፈተናው ጋር ተያይዘው በሚኖሩ ዝግጅቶች፣ የተማሪዎች ጭንቀት እና ከፈተና በኋላ በሚኖር እርማት፣ ውጤት እንዲሁም የዩኒቨርስቲ ምደባ ጊዜንም ታሳቢ በማድረግ ስለሆነ መርሃ-ግብሩ በችግር የወጣ ነው፤ ያለውን ጫና ህዝቡ ይረዳልናል ብለን እናምናለን ሲሉ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ አስታውቀዋል፡፡

በተለይ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች ፈተናው ቢያንስ ለሁለት ወር እንዲራዘም የጠየቁት ጥያቄ እና ምከረ-ሐሳባቸው በመንግሥት በኩል ተቀባይነት የማያገኝ ከሆነ እና ፈተናው ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚሰጥ ከሆነ ተመሳሳይ እርምጃ ሊወስዱ እንደሚችሉ፤ በዚህም ምክንያት ለሚደርሰው ማንኛውም ኪሳራ መንግሥት ሙሉ ኃላፊነቱን መውሰድ እንዳለበት አስጠንቅቀዋል፡፡

ከሰኔ 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው ፈተና እንዲሰረዝ በመደረጉ ምክንያት ከ285 ሚሊዮን ብር ያላነሰ መንግሥት ላይ ኪሳራ ማድረሱ አይዘነጋም፡፡

 

 

 

እነ አቶ በቀለ ገርባ በባዶ እግራቸው፣ ከፈል ሰውነትን በሚያሳይ የውስጥ ካናቴራ እና በቁምጣ ፍርድ ቤት ቀረቡ

“ምግብ ሳንመገብ በካቴና ታስረን ጨለማ ቤት ነው ያለነው” አቶ በቀለ ገርባ

Bekele Gerba

በኦሮሚያ ክልል የተነሳውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ የሽብር ክስ በእነ ጉርሜሳ አያኖ መዝገብ የተመሰረተባቸው የኦፌኮ ተቀዳሚ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች አመራሮች ዛሬ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ግማሾቹ በባዶ እግር ሌሎቹ በፓካውት እና በቁምጣ ቀርበዋል፡፡

ፍርድቤቱ ተከሳሾቹን ለዛሬ የቀጠረው ግንቦት 3 ቀን 2008 ዓ.ም በነበረው የፍርድ ቤቱ ቀጠሮ የቅሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ለምን ተከሳሾቹን ፍርድቤት እንዳላቀረበ መልስ ለመቀበል እና የተከሳሾችን የክስ መቃወሚያ ለመስማት ነበር፡፡

የክስ መቃወሚያቸውን ከአንደኛ ተከሳሽ እስከ አራተኛ ተከሳሾች በአንድ ላይ አቅርበዋል፡፡ ከአምስተኛ እስከ ሃያ ሁለተኛ ተከሳሾች ደሞ በጋራ መቃወሚያቸውን አስገብተዋል፡፡ ሰባተኛ ተከሳሽ ደግሞ መቃወሚያቸው ለፍርድቤቱ በቃል እንዲደመጥ ጠይቀው ፍርድቤቱ መቃወሚያውን አድምጧል፡፡
ተከሳሾች አቃቤህግ ያቀረበው ክስ እንዲስተካከል አሊያም ውድቅ እንዲደረግ የተለያዩ ነጥቦችን በማንሳት ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን ጉዳይ ለማየት ያለውን የሥረ- ነገር እና የከባቢ የዳኝነት ( Jurisdiction) ስልጣን በተመለከተ ባቀረቡት መቃወሚያ ክሱ ውስጥ ወንጀል ተፈፅሟል የተባለው ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በመሆኑ በአዋጅ ቁጥር 25/88፣ 138/01፣ 321/95 እና አዋጅ 141/200 መሠረት ይህንን ጉዳይ ለማየት ስልጣን ያለው የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድቤት በመሆኑ ይህ የተከበረው ፍርድ ቤት የሥረ- ነገር ስልጣን የለውም ብለው ተቃውመዋል፡፡

የህጋዊነት መርህን በተመለከተ ባቀረቡት መቃወሚያም፡አቃቤህግ በክሱ “ተከሳሾች የአዲስ አበባ እና ፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልማት ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን እና የኦሮሚያ ከተሞች የዕድገት ፕላን የኦሮሚያን ህዝብ ቋንቋ እና ባህል የሚያጠፋ የኦሮሞን ህዝብ ከመሬቱ ሚያፈናቅል ነው በማለት እንደ ፓርቲ ወስነው በኦሮሚያ የተለያዩ ቦታዎች ህብረተሰቡ ወደ አመፅ እንዲገባ በመቀስቀስ ወይም በማነሳሳት በሰው ህይወት እና አካል እና ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ አድርጓል ” በማለት የከሰሰውን በተመለከተ ተከሳሾች ሲቃወሙ አንድ ፓርቲ ሕገመንግስቱን ጥሶ ከተገኛ መከሰስ ያለበት አባላቱን ሳይሆን ድርጅቱ እንደሆነ በፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ ተደንግጎ በክሱ እንደተጠቀሰው “እንደ ፓርቲ ወስነው” ከሆነ እንኳን እንደግለሰብ መከሰሳቸውን ተቃውመዋል፡፡

ክሱ የእኩልነት መርህን እንደሚጥስም ጠቅሰው መቃወሚያ ያቀረቡት ተከሳሾች መንግስት በማያሻማ ሁኔታ በህዝብ የተጠየቁ ጥያቄዎች ትክክለኛ እንደሆኑ እና በመልካም አስተዳደር ችግር በወቅቱ መልስ ስላልተሰጣቸው ወደ ረብሻ መቀየሩን እና የሶስተኛ ወገኖች ተሳትፎ እንደሌለበት ገልፆ ኃላፊነቱን በመውሰድ ማሰተር ፕላኑ እንዲቀር ወስኖ ሳለ ተከሳሾችም የዚሁ ህዝብ አካል በመሆናቸው ህዝቡ ይቅርታ ተጠይቆ እነሱ የሚከሰሱበትን አግባብ ተቃውመዋል፡፡

በክሱ እያንዳንዱ ተከሳሽ የሽብር ድርጊቱን ፈፅሟል የተባለበት ቦታ እና ጊዜ በአግባቡ አለመጠቀሱን የተቃወሙት ተከሳሾች ፈፀሙ በተባለው የወንጀል ድረጊት ክሱ ወደመ ብሎ ሰለሚገልፀው ንብረት ያለበት ቦታ፣ ንብረቱ መቼ እንደወደመ፣ ማን ተጠያቂ እንደሆን በግልፅ ስለማያስቀምጥ ክሱ ውድቅ እንዲሆን ጠይቀዋል፡፡

የአቃቤ ህግ ማስረጃዎችን በተመለከተም መቃወሚያ ያስገቡት ተከሳሾች የኢፌዲሪ ብሔራዊ ደህንነት እና አገልግሎት መረጃን ሰብስቦ የማቅረብ ስልጣን ያለው እንጂ መረጃዎችን ሰብስቦ መደምደሚያ እና ትርጉም የመስጠት ስላልሆን አቃቤህግ ያቀረበው ማስረጃ በመስሪያቤቱ የቀረበ መደምደሚያ ስለሆን ወድቅ ይሁንልን ብለዋል፡፡

የሰው ምስክሮችን በተመለከተ አቃቤህግ ያለፍርድቤት ትዕዛዝ ፍርድቤት የምስክሮች ህይወት አደጋ ላይ ሰለመሆኑ ሳይወሰን የምስክሮች ስም ዝርዝር በክሱ አለመካተቱን ተቃወመው እንዲካተትላቸው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ፍርድቤቱ የተከሳሾችን የክስ መቃወሚያ ከሰማና መተቀበለ በኃላ አቃቤህግ ምላሽ እንዲሰጥ አዟል፡፡
የእስረኞች አያያዝ በተያያዘም የቅሊንጦ ማረሚያ ቤት ለከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ ማረሚያ ቤቱ ተከሳሾቹን ግንቦት 3 ቀን 2008 ያላቀረበበት ምክንያት የፍርድቤት ትዕዛዝ ስላልደረስን ነው የሚል ምላሽ እንደሰጠ የዕለቱን ችሎት የመሩት ዳኛ ታደለ ተገኝ ደብዳቤውን በማንበብ ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡

ተከሳሾች በበኩላቸው ግንቦት 3 ቀን 2008ዓ.ም ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለመቅረታቸው ምክንያት የሆነውን ጉዳይ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ ተከሳሾቹን በመወከል ለፍርድ ቤቱ በቃል አሰምተዋል፡፡

“በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ቦታዎች ከሁለት መቶ በላይ ሰዎች ከሁለት ወር ባነሰ ጊዜ በመንግስት ታጣቂዎች መገደላቸውን ተከትሎ የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን ለመግለፅ ጥቁር ልብስ ለብስን ወደ ፍርድቤት ልንመጣ ስንል ካላወለቃችሁ አትሄዱም ተባልን፡፡ የትኛውንም ልብስ ለመልበስ የሚከለክል ህግ ስለሌለ አናወልቅም አልን፡፡” ያሉት አቶ በቀለ ገርባ ከፍርድቤት ለመቅረታቸው ምክንያት የለበሱት ልብስ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

“ትናንትና ደግሞ በዚህ ክስ መዝገብ ውስጥ ያለን 22 ተከሳሾች በጠቅላላ ልብሳቹን ይዛችሁ ውጡ ተብለን ከማረፊያው ክልል ስንወጣ ልብሶቻችንን ወስደው ሜዳ ላይ ጣሉት፡፡ እኛን ጨለማ ቤት ከተቱን፡፡ ያለምንም ልብስ ምግብ ሳንበላ በካቴና ታስረን ውለን አድረናል” ሲሉ ተናግረው ልብሶቻቸው በጠቅላላ ሰለተወሰደባቸው በባዶ እግር፣ በፓካውት እና በቁምጣ ለመምጣት መገደዳቸውን በሃዘን ሰሜት ተሞልተው ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡

Bekele Gerba and other prisoners

በማረሚያ ቤቱ ጥቁር ልብስ በተመለከተ የወሰደውንም እርምጃ ሲገልፁ “ከታሰርንም በኃላ ግማሾቻችን ላይ ድብደባ እየተፈፀመብን ነው፡፡ ከኛ የክስ መዝገብ ውጪ በሌላ ክስ ተከሰው በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ክሳቸውን እየተከታተሉ ያሉ ጥቁር የለበሱ የኦሮሚያ ክልል ተወላጆች ከሌሎች ክልል ተወላጆች እየተመረጡ እየተደበደቡ ነው፡፡ ይህ በኦሮሚያ ህዝብ ላይ እየተደረገ ያለ ጥቃት ነው” ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ተከሳሾቹን ወክለው የተናገሩት አቶ በቀለ ለፍርድ ቤቱ ጥያቄ አቅርበዋል “በቤተሰቦቻችን እንዳንጎበኝ በማረሚያ ቤቱ ተከልክለናል ፡፡ እንደዜጋ እየታየን አይደለም፡፡ እኔም ላይ በተደጋጋሚ ዛቻ እና ማስፈራሪያ እየደረሰብኝ ነው፡፡ ቅሊንጦ ማረሚያ ቤት ለህይወታችን ስጋት ሰለሆን ፍርድቤቱ ሌላ ማረሚያ ቤት እንዲያሰቀምጠን እንጠይቃልን፡፡ በዳግም ቀጠሮ ከዚህ ማረሚያ ቤት በህይወት ስለመመለሳችን እርግጠኛ አይደለንም”ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡

ፍርድቤቱን ወክለው የመሃል ዳኛው ታረቀኝ አማረ በግንቦት 3 ቀን 2008 ዓ.ም ተከሳሾቹ ፍርድ ቤት አለመቅረባቸውን በተመለከተ ብይን ሲሰጡ ማረሚያ ቤቱ በሁሉም ችሎት ማረሚያ ቤቱን ወክሎ የተከሳሾችን ችሎት የሚከታተል የችሎት አሰፈፃሚ እያለ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አልደረሰንም ማለቱን በቂ ሆኖ አላገኘነውም ብለዋል፡፡

ተከሳሾች በማረሚያ ቤቱ እየደረሰብን ነው የሚሉትን የመብት ጥሰት አስመልክቶም ዳኛ ታረቀን “አቤቱታችሁን ለፍርድቤቱ በፅሁፍ አስግቡ፡፡ ፍርድ ቤቱ አቤቱታውን ተመልክቶ ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡ ችሎቱ አለባበስን በተመለከተ ይህን ልበሱ ይህን አትልበሱ የሚልበት ምክንያት የለውም፡፡ የጊዜ ቀጠሮን የሚያስተናግድ ሌላ ማረሚያቤት ስለሌለ ማረሚያቤቱ በአቤቱታችሁ ላይ መልስ እንዲሰጥ አቤቱታውን በፅሁፍ አቅርቡ ብለዋል፡፡

ዳኛው ታረቀኝ ተከሳሾቹ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ደረሰብን የሚሉ ከሆነም ከፍርድቤቱ ትዕዛዝ በተጨማሪ ለሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ማመልከት እንደሚችሉም ለተከሳሾቹ ተናግረዋል፡፡
ፍርድቤቱ የስዋኽሊ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብ እና አቃቤህግ የክሰ መቃወሚያውን ተመልክቶ አስተያየቱን እንዲሰጥ ተለዋጭ ቀጠሮ ለሰኔ 20፣ 2008 ዓም ተለዋጭ ቀጠሮ ስጥቷል፡፡
ተከሳሾች በከፍተኛ ወከባ፣ ጥበቃና አጀብ በጀርባ በር ተደብቀው የገቡ ሲሆን ታዋቂው ጠበቃ አምሃ መኮንንን እና አቶ ወንድሙን ጨምሮ ስድስት ጠበቆቻቸው አብረዋቸው ነበሩ ፡፡
ምንጭ፡- EHRP