Tag Archives: Oromo Protest Ethiopia

አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባላት በሽብር ተከሰሱ

 

Bekele Gerba

የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ ባለፈው ሰኞ ሚያዝያ 10/2008 ዓ.ም ተዘጋጅቶ ሚያዝያ 14/2008 ዓ.ም በፌደራል አቃቤ ህግ ክስ የቀረበባቸው 22 ተከሳሾች ክሳቸው ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡

በአቶ ጉርሜሳ አያናው መዝገብ የተከፈተው ክስ ላይ እንደተመለከተው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ በአራተኛ ተከሳሽነት ስማቸው ተቀምጧል፡፡ ተከሳሾቹ በ2001 ዓ.ም የወጣውን የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 የተለያዩ አንቀጾችን በመተላለፍ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን፣ ተከሳሾች ለ122 ሰዎች ጉዳት፣ ለንብረት ውድመት፣ ለመሰረተ ልማት መስተጓጎል፣ ለትምህርት መስተጓጎል ተጠያቂዎች ናቸው ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ አመልክቷል፡፡

ተከሳሾች በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ሽብርተኛ ተብሎ በተፈረጀው ኦነግ ውስጥ በአመራርነትና በአባልነት በመሳተፍ የሽብር ወንጀልን መፈጸማቸውን ክሱ በንባብ ሲሰማ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ ተከሳሾች በአዲስ አበባ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ምክንያት የተቀሰቀሰውን የህዝብ ተቃውሞ በማነሳሳትም ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡

በዚህ መዝገብ የተካተቱት ተከሳሾች ዝርዝር የሚከተለው ነው፡-
1. ጉርሜሳ አያናው
2. ደጄኔ ጣፋ
3. አዲሱ ቡላላ
4. በቀለ ገርባ
5. አብደታ ነጋሳ
6. ገላና ነገረ
7. ጭምሳ አብዲሳ
8. ጌቱ ግርማ
9. ፍራኦል ቶላ
10. ጌታቸው ደረጄ
11. በየነ ሩዶ
12. ተስፋዬ ሊበን
13. አሸብር ደሳለኝ
14. ደረጄ መርጋ
15. የሱፍ አለማየሁ
16. ሂካ ተክሉ
17. ገመቹ ሸንቆ
18. መገርሳ አስፋው
19. ለሚ ኤዴቶ
20. አብዲ ታምራት
21. አብደላ ከመሳ
22. ሀራኮኖ ቆንጮራ፣ ናቸው፡፡

ተከሳሾቹ ዛሬ ክሳቸው በንባብ ሲሰማ አንዳቸውም ጠበቃ አልነበራቸውም፡፡ ከተከሳሾች መካከል ሰባቱ አማርኛ ቋንቋ እንደማይችሉ ገልጸው ክሱን እንዳልሰሙ ተናግረዋል፡፡ 22ኛ ተከሳሽ በበኩሉ ኦሮምኛም አማርኛም እንደማይችል አስረድቶ፣ ኪስዋህሊ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብለት ጠይቋል፡፡

ፍ/ቤቱም አስተርጓሚ እንዳላቀረበ ገልጾ በቀጣይ ማክሰኞ ሚያዝያ 18/2008 ዓ.ም አስተርጓሚ በመመደብ ተከሳሾች የሚያመለክቱት አቤቱታ ካለ ሊቀበል እንደሚችል ገልጾ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ከችሎት ወጥተው ወደመኪና ሲጫኑ በጋራ መዝሙር ያሰሙ ነበር፡፡

ምንጭ፡-EHRP

 

በኦሮሚያ ለግጭት ምክንያት የነበረው የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ

በውድነህ ዘነበ

Fekadu Tesema,Oromia PR

በኦሮሚያ ክልል ሕዝባዊ ጥያቄ የተነሳበት የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ፡፡ እነዚህ አወዛጋቢ የተባሉ አንቀጾች ከተሰረዙ በኋላ ባለፈው ሳምንት የተሰበሰበው ጨፌ ኦሮሚያ አዋጁን አፅድቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ተነስቶ ለነበረው ረብሻ የአዲስ አበባና ዙሪያዋ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንና የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ምክንያት እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የማስተር ፕላኑን ተግባራዊነት ማቆሙን በወቅቱ በይፋ የገለጸ ሲሆን፣ ለውዝግቡ መባባስ ምክንያት የነበሩ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች እንዲሰረዙ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተሰረዙት ሦስት አንቀጾች ከተሞችን መቀላቀል፣ የተቀላቀሉ ከተሞች ስያሜና ራዲዮ ፖሊ (የክልሉን ትልልቅ ከተሞች በተመለከተ) የሚያትቱ ናቸው፡፡ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ አንድ የክልሉ ከተማ በዙሪያው ካሉት አነስተኛ ከተሞችን (ሳተላይት) በመያዝ እንደ አዲስ ይደራጃል ይላል፡፡
ለፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆነው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ ያሉ ከተሞችን ከአዲስ አበባ (ፊንፊኔ) ጋር ለመቀላቀል ነው የሚሉ ግምቶችን ከተለያዩ ወገኖች በመስጠቱ ነው ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል የክልሉ ከተሞች ሲቀላቀሉ አንድ ስም የግድ ይመርጣሉ፡፡ ይህ ሁኔታ የክልሉን ታሪክና ባህል ያጠፋል፣ ልዩ ዞኑን ከአዲስ አበባ ጋር ለመቀላቀል ያለመ ነው የሚል ትንታኔ አሁንም በመስጠቱ ለችግሩ መንስዔ ነው ተብሏል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የተቀመጠው የራዲዮ ፖሊ ትንታኔ ነው፡፡ የአገሪቱ መዲና አዲስ አበባ የፌዴራል መንግሥት ከተማ ነች፡፡ የክልል ከተሞች ባህር ዳር፣ መቐለ፣ ሐዋሳ፣ ጅማ፣ አዳማና የመሳሰሉት ከተሞች በራዲዮ ፖሊ ምድብ ይገኛሉ፡፡
የፌዴራል መንግሥት ባወጣው የከተሞች ፖሊሲ ራዲዮ ፖሊ ከተሞች ከፌዴራል መንግሥት ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ታቅዷል፡፡

የኦሮሚያ ክልል በከተሞች አዋጅ ላይ ስለ ከተሞቹ የገለጸ ሲሆን፣ ለዚህ ጉዳይ ከተለያዩ ወገኖች የተሰጠው ምላሽ ግን የኦሮሚያ ከተሞች በፌዴራል ሥር ሊገቡ ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሦስት ጉዳዮች በኦሮሚያ ተከስቶ ለነበረው ደም አፋሳሽ ግጭት መንስዔ እንደነበሩ ተገልጿል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊና የካቢኔ አባል አቶ ፈቃዱ ተሰማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ሕዝብ ጥያቄ በማንሳቱና የኦሮሚያ መንግሥት ሕዝብ የማይስማማበትን አንቀጾቹን ከአዋጁ ውስጥ ፍቆታል፡፡

አቶ ፈቃዱ ‹‹እነዚህ አንቀጾች ጉዳት ኖሯቸው ሳይሆን ፅንፈኞች በአሉታዊ መንገድ ጉዳዩን እጅግ ያስተጋቡት በመሆኑና እኛ ደግሞ በተገቢው መንገድ ግልጽነት ስላልፈጠርን የተፈጠረው ብዥታ ከፍተኛ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እነዚህ ጉዳዮች የሕዝቡን ጥቅም የሚጎዱ ሆነው አይደለም፤›› በማለት ክልሉ ሐሳቡ የሕዝብ እስከሆነ ድረስ የሕዝብን ጥያቄ እንደሚቀበለው አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡

እነዚህ አንቀጾች ከመሰረዛቸው በተጨማሪ በሌሎች ሁለት ጉዳዮች ላይ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡ ፀድቆ በነበረው የከተሞች አዋጅ የክልሉ ከተሞች የሚሰበስቡትን ፋይናንስ ለራሳቸው ይጠቀማሉ የሚል አንቀጽ ነበር፡፡ ነገር ግን ገቢ የማመንጨት አቅም የሌላቸውን ከተሞች ስለሚጎዳ፣ በማዕከል ደረጃ በጀት ቢከፋፈል የተሻለ መሆኑ ስለታመነበት ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ቀደም ሲል በክልሉ ከተሞች በላይኛው የአስተዳደር እርከንና በቀበሌ መካከል ራሱን የቻለ የመንግሥት መዋቅር አልነበረም፡፡ ቀደም ብሎ ፀድቆ በነበረው አዋጅ የወረዳ መዋቅር እንዲከፈት ተደንግጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከወረዳ ይልቅ ክፍለ ከተማ የተሻለ መዋቅር ነው ተብሎ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸው፣ ትልልቅ ከተሞች የክፍለ ከተማ መዋቅር እንዲመሠርቱ በአዲሱ አዋጅ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

በኦሮሚያ ክልል የደረሰውን የሰብዓዊ ጉዳት አስመልክቶ በ33 ወረዳዎች ብቻ 103 ዜጎች መገደላቸውን የሚገልፅ ገለልተኛ የምርመራ ሪፖርት ይፋ ሆነ

HRCO-logo-150x150

ከህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ተጀምሮ በነበረው እና መላው ኦሮሚያ ክልልን ያዳረሰው ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ የደረሰው ሰብዓዊ ጉዳት ልዩ የምርመራ ሪፖርት መግለጫ ይፋ ሆነ፡፡ ልዩ መግለጫው ይፋ የሆነው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሰመጉ ዋና ጽህፈት ቤት ሲሆን፤ መግለጫውም የ103 ዜጎች ህይወት መጥፋቱን አስታውቋል፡፡

ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ይባል የነበረውና በኋላም የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ(ሰመጉ) እየተባለ የሚጠራው ብቸኛው ሀገር በቀል መነግሥታዊ ያልሆነ ገለልተኛ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት ሲሆን፤ ባለፉት አራት ወራት በተጀመረውና እስካሁንም በቀጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ የሰብዓዊ ጉዳት ቀዳሚውን ልዩ መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡ ሰመጉ በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም ጠቁሟል፡፡

TPLF victims in Oromia region

ሰመጉ 34 ገፅ ባለው ልዩ መግለጫው እንዳስታወቀው ከሆነ፤ የደረሰው የሰብዓዊ ጉዳት ምርመራ የሚያካትተው ከህዳር 2 ቀን እስከ የካቲት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሱ የሰብዓዊ ጉዳቶች ብቻ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በተለይ በምርመራ ወቅት ድርጅቱ የጋጠሙትን ችግሮችም የጠቀሰ ሲሆን በተለይም የገንዘብ ፣ የሰው ኃይልና የምርመራ መሳሪያ እጥረት፣ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ሁኔታ ውጥረት የተሞላበት በመሆኑ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተው ቀውስ እንደልብ ተዘዋውሮ ለመስራት አለመቻል፣የመንግሥት የደህንነት እና የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ጫና እና ክትትል ማድረጋቸው፣ ሕዝቡ ከፍተኛ ፍርሃት ውስጥ በመግባት ማንንም ሰው አለማመን እና መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆን ዋነኞቹ መሆናቸው ጠቅሷል፡፡

በክልሉ አሁንም በተለያዩ ቦታዎች ተቃውሞች መቀጠላቸውንም በመጥቀስ፣ ማንኛውም የሰብዓዊ መብት የሚመለከተው አካል የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን ሰብዓዊ መብት እንዲያከብር፣ እንዲያስከብርና እንዲያስጠበቅ ጫና እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡

ሙሉ መግለጫውን ከዚህ ቀጥሎ ያለውን መስፈንጠሪያ (ሊንክ) በመጠቀም ያገኙታል፡- http://ehrco.org/wp-content/uploads/2016/03/The-Human-Rights-Council-HRCO-140th-Special-Report-Amharic-Scanned-March-14-2016.pdf

አቶ ኃይለማርያም በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ ምክንያት መንግሥታቸው እና ፓርቲያቸው መሆኑን ቢገልፁም፤ ህዝባዊ ተቃውሞው እንደቀጠለ ነው

ባለፈው ህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በድጋሚ የጀመረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች እና ወረዳዎች ቀጥሏል፡፡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ በተቃውሞው ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለው የኃይል እርምጃም ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ በዚህም የሟቾች ቁጥር መጨመሩ ታውቋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተቃውሞን ለማፈን እና ለማርገብ እየተወሰደ ባለው የኃይል እርምጃ ከሚገደሉት በተጨማሪ ጉዳት የደረሰባቸውና የታሰሩ ሰዎች ቁጥርም ጨምሯል፡፡ ተቃውሞን እና የርሃቡን ሁኔታ ለመዘገብ ባለፈው የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም.ወደ ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል ለዘገባ ተንቀሳቅሰው የነበሩት የብሉምበርግ ዘጋቢ ዊሊያም ዳቪሰን እና ለተለያየ መገናኛ ብዙኃን በኢትዮጵያ ወኪል ሆና የምትሰራው ጄሲ ፎርትንና አስተርጓሚያቸው በኢትዮጵያ የፀጥታ ሃይሎች ያለምንም ማብራሪያ ከአዋሽ ከተማ ወደ አዲስ አበባ በፌዴራል ፖሊስ ታጅበው እንዲመለሱ ከተደረገ በኋላ አዳር ታስረው መለቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኞቹም ለአንድ ቀን ከታሰሩ በኋላ መለቀቃቸውንም ጋዜጠኞቹ በማኀበራዊ ገፆቻቸው ላይ ይፋ አድርገዋል፡፡

Halemariam Desalegn

ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርም ደሳለኝ ባለፈው ሳምንት መጋቢት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. የመንግሥታቸውን የ6 ወር የስራ አፈፃፀም ሪፖርት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት፤ በኦሮሚያውም ሆነ በአማራ ክልል ጎንደር እና በሌሎች አካባቢዎች የተፈጠረው ችግር በመንግሥታቸው አስተዳደር ውስጥ ባለ የመልካም አስተዳደር አለመኖር፣ ሙስና እና ኪራይ ሰብሳቢነት ችግር መሆኑን እና በሌላ አካል ላይ ጣት መቀሰር እንደማይፈልጉ በመጥቀስ ለዚህም መንግሥትና እና ፓርቲያቸው ኢህአዴግ ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስተር አቶ ጌታቸው ረዳን ጨምሮ የተለያዩ የመንግሥት ኃላፊዎች ከህዝባዊ ተቃውሞው ጀርባ ኦነግ፣ አርበኞች ግንቦት 7 ፣ የኤርትራ መንግሥት እና በሀገር ቤት በይፋ የሚንቀሳቀሰውን ኦፌኮ/መድረክን ተጠያቂ ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም፤ በፓርላማው የሪፖርት ውሎ ግን የተለየ ምክንያት ሲሰጡ ተስተውሏል፡፡

እንደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አባባል ከሆነ የህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት ማንም ላይ ማላከክ አይቻልም፣ ኦሮሚያ ስለተነሳ ሌላ ቦታ ችግር የለም ማለት አይደለም፣ ይሄ ሁሉ ባለው ብልሹ አሰራር የተፈጠረ ችግር ነው፣ ለዚህም መንግሥት ኃላፊነቱን በመውሰድ ህዝቡን ይቅርታ ይጠቃል ብለዋል፡፡ ምንም እንኳ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኦሮሚያም ሆነ በአማራ ክልል በተለይ የቅማንት ማኀበረሰብ የማንነት ጥያቄ ጋ ተያይዞ ለተፈጠረው ችግር መንግሥታቸውና ፓርቲያቸው ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ቢገልፁም ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ መንግሥት የወሰደውን እና እየወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ ሲቃወሙ የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትና አመራሮች፣ ጋዜጠኞች እና ተማሪዎችን ጨምሮ ከ4 ሺህ በላይ ስለታሰሩት፣ ከ270 በላይ ስለተገደሉትና በርካቶች ስለቆሰሉ ዜጎች ጉዳይ ከመናገር ተቆጥበዋል፡፡

በተለይ በኦሮሚያ ክልሉን ያስተዳድራል የሚባለውና የኢህአዴግ አባል ድርጅት የሆነው ኦህዴድ መዕከላዊ ኮሚቴ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በቅርቡ በአዳማ/ናዝሬት ባደረገው ድንገተኛ ልዩ ስብሰባ አቶ ዳባ ደበሌ እና አቶ ዘለዓለም ጀማነህ የተባሉ የክልሉና የፌደራል ከፍተኛ ኃላፊዎችን ከነበሩበት የክልሉም ሆነ የፌደራል ስልጣን ማንሳቱን ይፋ ቢያደርግም ህዝባዊ ተቋውሞው ግን ይህ እስከተጠናቀረበት ድረስ ቀጥሏል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞ መቀጠሉን ተከትሎ መንግሥት በቅርቡ የካቲት 16 ቀን 2008 ዓ.ም ሌሊት በምዕራብ ሸዋ ዞን ቶኬ ኩታዬ ወረዳ ጎሮሶሌ ከተማ ውስጥ ሞቱማ ፈዬራ የተባለ የ20 ዓመት ወጣትና የ10ኛ ክፍል ተማሪን ጨምሮ የተለያዩ ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡

ለአራት ወራት የዘለቀውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ በፀጥታ ኃይሉ የሚወሰደው የኃይል እርምጃዎች እንዳሳሰበቸው የገለፁ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ባለፈው የካቲት 30 ቀን 2008 ዓ.ም. “እኛ ሽብርተኞች አይደለንም ፤ የኦሮሞ ሕዝብን መግደል አቁሙ” የሚሉ መፈክሮችን በመያዝ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ 6 ኪሎ ዋናው ግቢ አካባቢ ተነስተው ወደ አሜሪካ ኤምባሲ ሲያቀኑ የነበሩ ተማሪዎች በፖሊስ ድብደባ ሰልፉ እንደተበተነ እና በርካታ ተማሪዎችም ታፍሰው መታሰራቸው ተጠቁሟል፡፡ ተማሪዎችም ሰላማዊ መሆናችንን ለመግለፅ ነጭ ጨርቅ እያውለበለብን ነበር ያሉ ሲሆን መንግሥት ለምን ሰልፉን እንደበተነ እና ተማሪዎችን እንዳሰራቸው እስካሁን የገለፀው ነገር የለም፡፡

የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ሁለት የስራ ሀላፊዎችን ከሃላፊነታቸው አነሳ

OPDO

የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ኦህዴድ/ ማዕከላዊ ኮሚቴ ከየካቲት 25 ጀምሮ ለአምስት ቀናት በአዳማ ከተማ ባካሄደው ጉባኤ ሁለት የስራ ሀላፊዎችን ከሀላፊነታቸው እንዲነሱ በማድረግ እና የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቋል።

የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ የስራ ሃላፊዎቹ ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ የተደረገው በአመራር ችግር መሆኑን አስታውቋል።

በዚህም 1ኛ የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሞቴ የስራ አስፈጻሚ አባል እና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባል እንዲሁም የኦህዴድ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ዳባ ደበሌ ሲሆኑ፥ በታየባቸው የአመራር ችግር ምክንያት ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ መወሰኑን እና ከኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባልነት ተነስተው ነገር ግን የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ወስኗል።

2ኛ የኦህዴድ እና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባል እና የኦሮሚያ ክልል የእርሻ እና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ሃላፊ አቶ ዘላለም ጀማነ ሲሆኑ፥ እስከ ቀጣዩ የድርጀቱ ጉባኤ ድርስ ከማንኛውም የድርጅት እንቅስቃሴ መታገዳቸውን ድርጅቱ ማስታወቁን ፋና ቢሲ ዘግቧል፡፡
ምንጭ፡ http://www.fanabc.com/index.php/news/item/1428