የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበር ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ይፋ አደረጉ
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሊቀመንበር ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ይፋ አደረገ፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ራሳቸውን ለማንሳት የተገደዱት፤ በትምህርት ክፍሉ ከ28 ዓመታት በላይ በፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ውል በዩኒቨርስቲው አስተዳደር መቋረጡን ተከትሎ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ዶ/ር ካሳሁን የዶ/ር መረራ የጡረታ ጊዜ እንዲራዘም ያስገቡት ጥያቄ በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ውድቅ መደረጉ እና ከዚያም የትምህርት ክፍሉ ስለሚፈልጋቸው በራሱ የኮንትራት ውል አስፈርሞ ለሰባት ወራት ያሰራበት ክፍያ አለመፈፀሙን ተከትሎ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለዩኒቨርስቲው አስተዳደር ማስገባታቸው ታውቋል፡፡
በተለይ እንደ አሜሪካ ድምፅ ዘገባ ከሆነ፤ ዶ/ር ካሳሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል በዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ የተወሰደውን ርምጃ ተከትሎ “ የዩኒቨርስቲው አስተዳደር ለትምህርት ክፍሉ ጥያቄና ፍላጎት ምላሽ ባለመስጠቱ፤ የትምህርት ክፍሉን እያስተባበርኩ መቀጠል ከሞራልም አኳያ ተቀባይነት እንደሌለው ይሰማኛል፡፡” በማለት ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ለመልቀቅ መወሰናቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡ ዶ/ር መረራ በበኩላቸው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስዱት አስታውቀዋል፡፡ በአሁን ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጡረታ ጊዜያቸው እንዲራዘም ጠይቀው የተፈቀደላቸውና እየሰሩ የሚገኙ በርካታ መምህራን እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ባልተገለፀ ምክንያት የዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ጥያቄ ብቻ ተቀባይነትን ሊያገኝ አለመቻሉ ታውቋል፡፡
ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደም ለሙሉ ፕሮፌሰርነት የሚያበቃ በርካታ ጥናቶችን አጠናቀው ማዕረጉን ለማግኘት ያቀረቡት ማመልከቻ በሚመለከተው የመንግሥት አካል ተቀባይነት እንዳላገኘ የሚታወቅ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደምም ሆነ አሁን የተወሰደባቸው እርምጃ በተቃውሞ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ እንደሆነ የተጠቆመ ሲሆን፤ በአሁን ወቅትም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ ሊቀመንበር እና የአራት ፓርቲዎች ግንባር የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ምክትል ፕሬዘዳንት እና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡
ምርጫ ቦርድ ከ200 በላይ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ሰረዘ
- “ምርጫ ቦርድ ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ እንዲቆይ አይፈልግም” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
ሰማያዊ ፓርቲ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ በምርጫ ቦርድ ትዕዛዝ እንደተሰረዙበት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በመላ አገሪቱ በተለይም በደቡብ ወሎ፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወላይታ፣ በቤንች ማጅ፣ በምዕራብ ጎጃም፣ በሲዳማ፣ በከምባታ፣ በጋሞጎፋ፣ አዲስ አበባ፣ በደቡብ ጎንደርና ጉጅን ጨምሮ በሌሎችም የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ አንድን ዕጩ ለመሰረዝ የሚያበቃ ምንም አይነት ህጋዊ ምክንያት ሳይኖር “ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደብዳቤ ታዘናል” በማለት ለህዝብ ተወካዮች ምክርቤትና ለክልል ምክር ቤቶች ያስመዘገብናቸው ዕጩ ተወዳዳሪዎቹን በመሰረዝ ከምርጫው ውድድር ውጪ እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሆነ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት አስረድተዋል፡፡
በየክፍለ ሀገሩ የተሰረዙት ዕጩዎች “ፓርቲው ትብብር የሚባል ህገ ወጥ አደረጃጀት መስርቷል፣ የሌሎች ፓርቲዎች አባላት ናችሁ” የመሳሰሉ ምክንያቶችና ደብዳቤ የተሰጣቸው ሲሆን በአንጻሩ በአዲስ አበባ የተሰረዙት ዕጩዎች ከምርጫ አስፈጻሚዎች ምንም አይነት ምክንያትና ደብዳቤ እንዳልተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዕጩዎቹ “የተሰረዝንበትን ምክንያት ንገሩን፣ ደብዳቤ ልትሰጡን ይገባል” ቢሉም የምርጫ አስፈጻሚዎቹ “እኛ እናንተን ለመመዝገብ ችግር የለብንም፡፡ ግን ከበላይ አካል እንዳንመዘግብ ተነግሮናል፡፡ ደብዳቤም ልንሰጣችሁ አንችልም፡፡” የሚል መልስ እንደሰጧቸው ገልፀዋል፡፡
በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች መሰረዛቸውን ተከትሎ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የቦርዱን ሰብሳቢ ፕ/ር መርጋ በቃናን ለማግኘት ቢጥሩም “ከከተማ ውጭ ናቸው፡፡ አሁን አታገኟቸውም” የተባሉ ሲሆን ፕ/ር መርጋ የህወሓትን 40ኛ አመት ለማክበር መቀሌ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በትናንትናው ዕለት በጉዳዩ ላይ ከቦርዱ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ነጋ ዱፌሳ ጋር የተነጋገሩ ሲሆን አቶ ነጋ “ማመልከቻ አስገቡ” ከማለት ውጭ ዕጩዎቹ ለመሰረዛቸው ተጨባጭ ምክንያት መስጠት እንዳልቻሉ ኢ/ር ይልቃል ገልጸውልናል፡፡
“የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ያለ አግባብ የሚሰርዙት ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ ጫና መፍጠር ስለሚችል በሂደቱ እንዲቆ ስለማይፈልጉ ነው” ያሉት ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፤ ሆኖም ይህ የምርጫ ቦርድ ውሳኔ ለነጻነት የሚያደርጉትን ትግል ትክክለኛ እንደሆነ እንዳስረገጠላቸው፣ ይህን የነፃነት ትግልም አጠናክረው እንደሚቀጥሉና የካቲት 22 ፓርቲያቸው ከትብብሩ ፓርቲዎች ጋር በ15 ከተሞች በተመሳሳይ ጊዜ በ15 ከተሞች የሚያደርገው ሰልፍ የዚሁ የነጻነት ትግል አካል እንደሆነ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በ15 ከተሞች የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጠራ
“ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚልመርህ የሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ የካቲት 22 ቀን 2007 ዓም በ15 ከተሞች እንደሚካሄድ ትብብሩ አስታውቋል።
“የሙስሊም ማህበረሰቡ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም በኑር መስጂድ ፣ የካቲት 6 ቀን 2007 ዓም ደግሞ በአንዋር መስኪድ ያደረገው ተቃውሞ እንዲሁም የባህርዳር ከተማ ህዝብ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም ያሳየው ህዝባዊ እምቢተኝነት ትግል በሃይል ሊዳፈን ቢችልም እንደማይጠፋ ትምህርት ሰጥቷል” ሲል በመግለጫው አስታውቋል፡፡ ትብብሩ፣ ገዢው ፓርቲ እያደረሰ ያለው የመብት ረገጣ፣ የሙስና መስፋፋትና የመልካም አስተዳደር እጦት የህዝቡን የለውጥ ፍላጎትና የትግል ተነሳሽነት እንዳሳደገው ገልጿል።
ትብብሩ ገዢው ፓርቲ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ከቃላት ያለፈ እምነትም ሆነ ቁርጠኝነት እንደሌለው በመግለጽ፣ ምርጫ ቦርድን በቁጥጥር ስር በማዋል ጠንካራ ፓርቲዎችን ከመጪው ምርጫ ለማግለል እየሰራ መሆኑን የአንድነትና መኢአድን ጉዳይ በመግለፅ አብራርተዋል።
ከሰሞኑ ኢቢሲ ያቀረበው የተቃዋሚ ፓርቲዎችን የመኖር ትርጉም ዋጋ የሚያሳጣው ‹‹መንግስትንና የመንግስት አስፈጻሚዎችን ከተቻችሁ፣ ካላከበራችሁ ወይም ጸጥ ለጥ ብላችሁ የምርጫ አጃቢ ካልሆናችሁ እስከ 15 ዓመት ትታሰራላችሁ›› የሚል አንድምታ ያለው በ ‹‹ባለሙያዎች ትንታኔ ›› ሥም የተላከው የማስፈራሪያ መልዕክትና የሌሉ የፈጠራ ክሶችን ለመፈብረክ በአባል ፓርቲዎቻችን ላይ ‹‹የሞተ ጉዳይን ከመቃብር በመቀስቀስ›› እና በአዲስ መልክ የተጀመረው የሚዲያ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ በግልጽ ያስተላለፈው ገዢው ፓርቲ የመድብለ ፓርቲ ስርአት እንዳይኖር መፈለጉን ነው ሲል አክሏል።
የእኛ፣ የአገራችንና ዜጓቿ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ በሁለት አማራጮች ላይ የተንጠለጠለ ነው የሚለው ትብብሩ አንድም ያለውን አምባገነናዊ ሥርዓት ተቀብለን፣የአገራችን ሉዓላዊነት በጥያቄ ውስጥ ባለበት፣ የጭቆና ቀንበር ተሸክመን በከፋ ውርደት ሥር ሰጥ ለጥ ብሎ መገዛት፤ አሊያም አምባገነንነትና ጭቆናን “በቃ” በማለት በሕዝባዊ የተቀናጀ ሰላማዊ ትግል ለአገራችን ሉዓላዊነትና የዜግነት ክብራችንን ለማስመለስ በህገ መንግስታዊ መብታችን ተጠቅመን ትግላችንን እስከማይቀረው ለውጥ/ ድል ደጃፍ ድረስ በቆራጥነት መቀጠል፣ ናቸው ብሏል፡፡
ሁሉን አቀፍ የነፃነትና ክብርን የማስመለስ ሰላማዊ ትግል ለ9ኙ ፓርቲዎች ብቸኛ አማራጭ መሆኑም ትብብሩ አስምሮበታል፡፡
ፓርቲዎቹ በመጨረሻም በሚደረገው አገራዊ፣ ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል በማይቀረው የሥርዓት ለውጥ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር በአንድነትና በቆራጥነት ህዝቡ እንዲነሳና በየካቲት 22 የተቃውሞ ሰልፍ ላይ እንዲገኝ በመግለጫቸው ጥሪ አቅርበዋል።
ፍርድ ቤቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አቤቱታ ላይ ቀጠሮ ሰጠ
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘላለም ወርቃገኘው ክስ መዝገብ የተከሰሱት የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በማረሚያ ቤት አስተዳደር ላይ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጠ፡፡ በዛሬው ችሎት የተከሳሾቹ ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ‹‹ህዳር 12 ለ 13 ቀን 2007 ዓ.ም አጥቢያ ድንገተኛ ፍተሻ ተደርጎ የተጠርጣሪዎቹ ንብረት ተወስዶባቸዋል፣ የሰብአዊ ጥሰት ተፈጽሞባቸዋል፣ ድንገተኛ ፍተሻው ህገ ወጥ ነው›› በሚል በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ላይ ላቀረቡት አቤቱታዎች ማረሚያ ቤቱ የሰጠውን መልስ ሰምቷል፡፡
የማረሚያ ቤቱ መልስ በጽሁፍ ከቀረበ በኋላ በቃልም እንዲቀርብ በታዘዘው መሰረት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የቀጠሮ ማረፊያ አስተዳደር አስተዳዳሪ ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አምባዬ ክቡር ፍተሻው መካሄዱን አምነው ነገር ግን፤ ‹‹ፍተሻው የተከናወነው በፍርድ ቤት ትዕዛዝ ከጠዋቱ 12 ሰዓት በኋላ ነው፡፡ ፍተሸውም በአቤቱታው ላይ እንደቀረበው ባልታወቁ ሰዎች ሳይሆን በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ጥበቃዎች ነው የተከናወነው›› ሲሉ መልስ ሰጥተዋል፡፡ የፍተሻውን አላማም ‹‹የታራሚዎችን ደህንነት ለመጠበቅ ሲባል የተከለከሉ ነገሮችን ፈትሾ ለማስወገድ ነው፡፡ በፍተሸውም ሚስማር፣ ስለት ነገሮች፣ እንዲሁም ብጥብጥ የሚቀሰቅሱ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡›› ብለዋል፡፡
ባለፈው የአብዛኛዎቹ ተከሳሾች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ሲደረግ የ7ኛ ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞን፣ እንዲሁም 8ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማ የተወሰኑ የክስ ማሻሻያዎች እንዲያደርግ ትዕዛዝ ሰጥቶ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በዚህ መሰረት በዛሬው ዕለት በሁለቱ ተከሳሾች ላይ አሻሽየዋለሁ ያለውን ክስ አቃቤ ህግ ይዞ ቀርቦ በንባብ አሰምቷል፡፡
በመጨረሻም በፍተሻው ወቅት ተፈጽሟል በሚል በተከሳሾቹ ጠበቃ የቀረበውን አቤቱታና ማረሚያ ቤቱ የሰጠውን መልስ አገናዝቦ ውሳኔ ለመስጠት እንዲሁም፤ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የቀረበው ማሻሻያ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ‹‹ተሸሽለዋል ወይንም አልተሸሻሉም›› የሚለውን ለመወሰን ለየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ጠዋት 3 ሰዓት ላይ ቀጠሮ መሰጠቱን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የመድረክ እጩ ተወዳዳሪ በትግራይ ተምቤን በፖሊስ ተደበደበ
የወርቃ ኣምባ ምርጫ ክልል መድረክን ወክሎ ለክልል ምክርቤት በእጩነት የቀረበው ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ በፖሊስ ተደብድቦ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶታል።
ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ ትናንት ቅዳሜ የካቲት 7 ቀን 2007ዓ.ም ከቀኑ 11 ሰዓት የወርቃ ኣምባ ከተማ ኣስተዳዳሪ ተስፋይ ሃይሉ “..ይዛቹ ኣምጡት ብሎናል..” በማለት ሃፍተ ኪሮስ የተባለ ፖሊስና ገብረተኽለ ወለቸኣልና ገብረጀወርግስ ሙሉ የተባሉ ሚሊሻዎች ወደ ፖሊስ ኮሚኒቲ እየደበደቡ ወስደውታል። በወቅቱ በርካታ ህዝብ እየተመለከተ የነበረ ሲሆን ድብደባው በህዝቡ እርዳታ እንዲቆምና ወደ ዋና ፖሊስ ጣብያ ወስደው እንዲያስሩትና ድብደባው እንዲያቋርጡት ተቃውሞው በማሰማቱ ድብደባው ተቋርጧል።
ተደባዳቢው ፖሊስና ሚልሻዎቹ ለምን እንደደበደቡት ሲጠየቁ “..ወደ ፖሊስ ጣብያ ስንወስደው ቀስ እያለ ሲሄድ ፈጠን በል ስንለው ቀስ እያለ በመሄዱ ነው..” ሲሉ መልሰዋል።
ፖሊስ ኣዛዡ ያለ ምንም ምክንያት እንደተደበደበ ካረጋገጠ በሗላ “..ፖሊሱ ሰካራም መሆኑና ቅር ሊለው እንደማይገባው..” ነግሮ ማታ ሰዎስት ሰዓት ከእስር ቤቱ ኣስፈትቶታል።
ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ ከእስር ከተለቀቀ በሗላ በጤና ኬላ የህግምና እርዳታ ተደርጎለታል።
ማታ 5 ሰዓት ኣከባቢ ፖሊስ ሃፍተ ኪሮስ ከ3 ሚልሻዎች በመሆን ወዳረፈበት ቤት በመሄድ ለባለ ቤቱ ማስፈራራት ኣድርሰዋል።
የህወሓት መንግስት በሑመራና ሽረ የሚገኙ ኣባሎቻችንም ተመሳሳይ ድብደባ ኣድርሰዋል ሲል በመቀሌ የመድረክ አመራር አባል ገልፀዋል፡፡






