Monthly Archives: April, 2013

ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?

”ጎዳና ቤቴ’

ሰኔ 25/2012 እአአቆጣጠር  በቢቢሲ ድህረ ገፅ ላይ በወጣ አንድ ዘገባ መሰረት ኢትዮጵያ በአመት 5ሺህ በላይ ሕፃናት በማደጎነት ወደ አሜሪካ  ብቻ እንደሚሄዱ  እና አሜሪካ ከዓለም ላይ በማደጎነት ከምትወስደው ሕፃናት ኢትዮጵያውያን ሕፃናት ከ አምስቱ አንዱ እንደሆኑይገልፃል።(http://www.bbc.co.uk/news/world-africa-18506474)

አዲስ አበባ ብቻ ዛሬ ከ አንድ መቶ ሺህ በላይ መግብያ ያጡ ”ጎዳና ቤቴ” ብለው አንቅልፍ በጣላቸው ቦታ ክልውስ ብለው የሚተኙ ሕፃናት ይኖሩባታል።ይህ የሆነው የኢትዮጵያ መንግስት ግዴለሽነት የመነጨ እንጂ ከድህነታችን ብቻ የሚመስለው ካለ ለመሳሳቱ እማኝ ላቅርብ።
ሕፃናት አሳዳጊ የሚያጡት ባብዛኛው የርስበርስ ጦርነት ሲኖር ወይንም ሰላም በተናጋበት ጊዜ ነው።ኢትዮጵያ ግን ጎዳና የወጡት ሕፃናቶቿ የበዙት በአንፃሩም ቢሆን ጦርነቱ ከቆመ ጊዜ ጀምሮ ነው ለምን?
በ 1969 ዓም በዚያድባሬ ሱማሌ ወረራ ሳቢያ ብዙ ሕፃናት አባት እናታቸውን አጡ።ሀገሪቱ በወቅቱ ገንዘብ የላትም።ምዕራባውያን ፊታቸውን አዙረውባት ነበር።ግን ሕፃናት ጎዳና አልተጣሉም ይልቁንም ኃላፊነት የተሰማቸው ኮለኔል መንግስቱ በ 16 ወራት ውስጥ የሕፃናት አምባ እንዲገነባ አድርገው በአንድ ጊዜ ከአምስት ሺህ ሕፃናት በላይ የሚይዝ ትልቅ የሕፃናት ማሳደግያ በአፍሪካ በግዙፍነቱ (በውቅቱ) እና በአቅሙ ቀዳሚ  ሆኖ ተገንብቷል። ኢህአዲግ መንግስት ከሆነበት ጊዜ  ጀምሮ ሲያዳክመው ቆይቶ በ 1990 ዓም ተዘጋ። ኢህአዲግ ወያኔ የነበረውን አስፋፍቶ ሕፃናትን ከጎዳና ኑሮ ከማዳን ይልቅ ሕፃናትን በማደጎነት እየሸጠ በአንድ ሕፃን በትንሹ 25ሺህ ዶላር መሰብሰብ እና ወደኪሱ  ማስገባቱን መረጠ።

ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?

ዛሬ ኮለኔል መንግስቱ እንደጀመሩት ቢቀጥል ኖሮ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሕፃናት በተማሩበት እና ከጎዳና ኑሮ በዳኑበት ነበር። ሃቁ ይህ ነው።አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ላይ የተሰቀለው ቢል ቦርድ እና ኢቲቪ በአቶ መለስ የሞቱ ሰሞን ከዜና አንባቢው ጀርባ አቶ በለስ ጣታቸውን ወደ ሕፃናት ሲዘረጉ ያሳያል።ግን  እንዴት ነው አቶ መለስ የኢትዮጵያ ሕፃናት አባት የሚባሉት? በምን መስፈርት? ሕፃናቱን ጎዳና ወድቀው እሳቸው በሚያልፉበት መንገድ በወታደሮቻቸው ስለገፏቸው ነው?ወይንስ የሕፃናት አምባን ስለዘጉላቸው? ነው ወይንስ በአስር ሺዎች በማያውቁት ባእዳን እጅ እንዲያድጉ ስለሸጧቸው። ‘መሸጥ’ የሚለው ቃል ለቀረበው ዕቃ ወይም ሰው አልያም ሕፃናት ገንዘብ ከፍሎ ሕፃኑን መውሰድ የሚለውን ትርጉም እስከያዘ ድረስ መሸጥ ከሚለው ቃል የትሻለ ሊገኝ አይችልም።

ቅዳሜ ጧት

ከአምስት አመት በፊት በ 2001ዓም አንድ ቅዳሜ ጧት ወደ ዝዋይ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም 45 ሰዎችን አሳፍሮ አንድ መለስተኛ አውቶቡስ መመናንን ይዞ መንገድ ላይ ነበር።በመንገድ ላይ በእድሜ ጎልማሳ ካህን ስለገዳሙ ታሪክ ይናገራሉ።በአንክሮ በመገረም ነበር የምንሰማው።እውነተኛ ታሪኩ ይህ ነበር።

555833_4741247050817_2127754364_n

” አቡነጎርጎርዮስ የዝዋይ ገዳም መስራች አንድቀን የመንፈስ ልጆቻቸውን እያስተማሩ ኮለኔል  መንግስቱ ከአዋሳ ሲመጡ ጎራ ይላሉ።ወደ ገዳሙ ውስጥ ሳይገቡ ገና አጥሩን ሲመለከቱ በረጅሙ ታጥሮ ይመለከቱ እና ‘ይሄ መነኩሴ ይህን ይህል ቦታ አጥሮ አገሩ ታድያ ምን ተረፈ’ ይሉ እና አንዱን ወታደር አቡነ ጎርጎርዮስን እንዲጠራቸው ይልኩታል። አቡነ ጎርጎርዮስ መልክቱ እንደደረሳቸው ‘አሁን ትምህርት ላይ ነኝ ደግሞስ ፈላጊ ይመጣል እንጂ ተፈላጊ እንዴት ይሄዳል?’ ብለህ ንገረው ብለው መልሰው ይልካሉ።ኮለኔል መንግስቱ እንዲህ አይነት ድፍረት በመስማታቸው ምንም ሳይሉ ወደ አዲስ አበባ ይመለሳሉ። በቀጣዩ ቀናት አቡነ ጎርጎርዮስ ኮለኔል መንግስቱን ቅሬታቸውን ለመንገር ይመጣሉ።ቅሬታቸው ሌላ ነበር።እንደገቡ አቡነ ጎርጎርዮስ በቁጣ ”ለመሆኑ ሕፃናት አምባ የምታሳድጋቸው ልጆች አምላካቸውን ካላወቁ አውሬ እንደሚሆኑ ታውቃለህ?” ይሉታል ይደነግጣል። ”ምን ይደረግ?” ይላቸዋል።”ለእኔ ፍቀድልኝ እኔ የማደርገውን አውቃለሁ ” ይሉታል። ከድጋፍ ደብዳቤ ጋር ይልካቸዋል።

አቡነ ጎርጎርዮስ በህፃናት አምባ ውስጥ የቅዱስ ሚካኤል ታቦት አስይዘው በግቢው ውስጥ ለሕፃናቱ ቤተክርስቲያን ሰሩላቸው።ብዙ በስነምግባራቸው የታነፁ ሕፃናትን አፈሩ። በቀን በሚልዮን ብር ለጦርነት ታወጣ የነበረች ሀገር እንዲህ ልጆቿን ታሳድግ ነበር። ዛሬ የጎዳና ተዳዳሪ ሲበዛ መንግስት ኃላፊነት አይወስድም።ሕፃናቱን ለመሸጥ ግን ቢሮዎችን በየቦታው ባእዳን እንዲከፍቱ አርጎ የውጭ ምንዛሪ ማስገኛ አደረጋቸው። ቢቢሲ ከላይ በጠቀስኩት ቀን ላይ ባወጣው ዘገባ ላይ እንዲህ ይላል።
”International adoption is big business in Ethiopia and the country accounts for almost one in five international adoptions in the US, but how ethical is the process?” http://www.bbc.co.uk/news/world-africa-18506474
”በኢትዮጵያ የማደጎ ሕፃናትን ወደውጭ መላክ የንግድ ሥራ ሆኗል።ይህም ወደአሜሪካ ከመላው አለም ከሚገቡት ውስጥ ከአምስቱ አንዱን እጅ ይይዛሉ።ነገር ግን ይህ እንዴት ሞራላዊ ሂደት ሊሆን ይችላል?” በማለት ይጠይቃል። እውነት እንዴት ሞራላዊ ሂደት ሊሆን ይችላል?
ግን ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?
ይህንን በ ኮለኔል  መንግስቱ የተመሰረተውን ታሪካዊ የሕፃናት አምባ እንቅስቃሴ የሚያሳይ ፊልም ይመልከቱ እና ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት ስጠን በሉ።

ምንጭ ፡- ከጉዳያችን ብሎግ የተወሰደ

የነ አቶ አንዱዓለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ክስ ውሳኔ በድጋሚ ተቀጠረ

በእነ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ለፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ የጠየቁት የአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እንዲሁም  እውቁ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን፣ አቶ አንዱዓለም አያሌው፣ ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለም፣አቶ ዮሐንስ ተረፈ፣አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ እና አቶ ምትኩ ዳምጤ ውሳኔ ለዛሬ መጋቢት 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ተቀጥሮ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ 6 ኪሎ የሚገኘው የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የይግባኙን የመጨረሻ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ቢጠበቅም ውሳኔውን ሳይሰጥ ለአምስተኛ ጊዜ ለሚያዚያ 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ተቀጠረ፡፡

ፍርድ ቤቱም ውሳኔውን ሊሰጥ ያልቻለበትን ምክንያት ሲገልፅ የክሱን ሂደት ገና መርምሬ አልጨረስኩም በሚል ተጨማሪ ቀነ ቀጠሮ መስጠቱን አስታውቋል፡፡ በወቅቱ የፍርድ ቤቱ ዳኞች ሽመክት አሰፋ፣ በላቸው አንሺሶ እና ዳኜ መላኩ ተሰይመው ሲሆን ከከሳሽ በኩል አቃቤ ህግ ብርሃኑ ወንድማገኝ እንዲሁም ከተከላካይ ጠበቆች አቶ አበበ ጉታ፣ አቶ ደርበው ተመስገን እና አቶ ሳሙኤል አሰፋ ተገኝተዋል፡፡ ተከሳሾችም በሰዓቱ የቀረቡ ቢሆንም የነበረው በበርካታ ያልተለመደ የጦር መሳሪያ አጀብ አዲስ ያልተለመደ ክስተት ቢሆንም በተለይ የአቶ አንዱዓለም አራጌ በከፍተኛ ደረጃ መጎሳቆል የችሎት ታዳሚዎችን ሐዘን ውስጥ ከቶ ተከሳሾቹ የውሳኔ ፍርዱ ሳይሰጥ ከቀኑ 6፡30 ሰዓት ወደ የመጡበት እስር ቤት ተመልሰዋል፡፡   

 

ማፈናቀሉ እስከመቼ?

ብስራት ወልደሚካኤል

ህወሓት/ኢህአዴግ በህይወቱ ከሚፈራውና ከሚጠላው ነገር አንዱ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚል ዜጋ ማየትና መስማት ነው፡፡ ምክንያቱም የድርጅቱ አባላት በባህሪያቸው በውሸት፣ በተንኮልና በዕውቀት አስተሳሰብ አድማስ ደካማ ስለሆኑ የዜጎችን አንድነትና ብሔራዊነት ስሜትን አጥብቀው ይጠላሉ፤ ይህንንም በማሰራጨት የማሃይሞችን ርካሽ ፖለቲካ አራምደውበታል፣እያራመዱም ይገኛሉ፡፡ የዚህ ዋነኛ ተባባሪ ደግሞ በህወሓት የሚነዱት ብአዴን፣ ኦህዴድ እና ደኢህዴን ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የሀገሪቱን አንድነትና ደህንነት አደጋ ላይ በመጣላቸው ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በዝምታ ሊያልፍ ስለማይገባ እስካሁን ለፈፀሙት ሁሉ አስፈላጊውን ሰነድ በእጃችን ማስገባት፣ ድርጊቱን የፈፀሙትንና ተባባሪዎቹን ስም ዝርዝር ከነ ሙሉ አድራሻቸው መያዝ፣ ጉዳት የደረሰባቸውና ሚደርስባቸው ዜጎችን መርዳትና መንከባከብ እንዲሁም ወንጀለኞችን በተለያዩ ማኀበራዊ ሚዲያዎች(Facebook, blog, twitter,….) ጨምሮ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በማጋለጥ ለህግ እንዲቀርቡና ተጠያቂ እንዲሆኑ ማድረግ የሁላችንም ኢትዮጵያዊያን የውዴታ ግዴታ መሆን ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም ዛሬ በሰፊው የአማርኛ ተናጋሪ ወገኖቻችን ላይ በህወሓት/ኢህአዴግ  እየደረሰ ያለው ግፍ በተመሳሳይ መልኩ ነገ በሌሎችም ላይ ይደርሳል፤ ከዚህ በፊትም ደርሷልና፡፡

ስለዚህ በቅርቡ በደቡብ ክልል ቤንች ማጂ ዞን ጉራፈርዳ ወረዳ ለረጅም ጊዜ ሀብት ንብረት አፍርተውና ተዋልደው የኖሩ የአማርኛ ተናጋሪዎችን የማፈናቀል ስራ የተሰራውን መረጃ በሚመለከት ፣

አሁን ደግሞ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያሶ ወረዳ እንዲፈናቀሉ የተደረጉት የአማርኛ ተናጋሪ ወገኖቻችን ለሞት.ለስቃይና ለመከራ እንዲደረጉ የተደረገበትን ምክንያት በዝርዝር በማጣርት መረጃውን ይፋ በማድረግ ሁሉም ዜጋ በጋራ ሊያወግዝና የተፈናቀሉትም ወደነበሩበት ስፍራ በክብር እንዲመለሱ ለማድረግ በሀግር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን በጋራ መስራት ይጠበቅብናል ብዬ አስባለሁ፡፡ ለዚህም በሀገር ውስጥ ያሉ የሚዲያ ባለሙያዎች፣ ፖለቲከኞች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ወደስፍራው በመሄድ አስፈላጊውን ጥናት በማድረግ መረጃውን ለህዝብ ይፋ ማድረግና የድርጊቱ ፈፃሚዎችም በአስቸኳይ ለህግ እንዲቀርቡ አስፈላጊውን ሁሉ ማድረግ፣

በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ይህን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ለዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ በማጋለጥ ለኢህአዴግ የሚደረገው የለጋሾች ድጋፍ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚውል ማረጋገጥና ድጋፉ እንዲቋረጥ ከማድረግ በተጨማሪ መረጃውን ለሚሰበስቡ  ሀገር ውስጥ ላሉ ሀገር ወዳድ ሰባዓዊ ባለሙያዎች የገንዘብ፣ የቁሳቁስና የሙያ ድጋፍ ማድረግ፣

በተለይ ወንጀሉ የሚፈፀምባቸው የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ወገኖቻችን ወኪል ነኝ የሚለውን ብአዴን/ኢህአዴግ አባላት ጉዳዩን አጥብቀው በመጠየቅ ለድርጅቱ የሚያደርጉትን ድጋፍ ሙሉ ለሙሉ በማቋረጥ ለህዝብ እና ለሀገር ያላቸውን ወገንተኝነት ማረጋገጥ፣ ከፓርቲውም በይፋ በመልቀቅ ህዝባዊ ዓላማ ያለውን ትግል መቀላቀልና የወንጀል ተባባሪ አለመሆናቸውን በተግባር በማሳየት ከነገ ተጠያቂነት እራሳቸውን ነፃ ማድረግ፣

የሌላው ማኀበረሰብ ኢትዮጵያዊያን ድርጊቱን በጋራ በማውገዝ አሁን እየተፈፀመ ያለው ዘግናኝና አሰቃቂ ወንጀል ወደ ሌሎችም መዛመቱ ስለማይቀር “ማፈናቀሉ እስከመቼ?” በሚል ሁሉም በጋራ በመንቀሳቀስ በራሱ ተስፋ የቆረጠውን ዘረኝነት አገዛዝ እርቃኑን በማስቀረት ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን በማፅናት የዜጎች ሰብዓዊ መብት በሙሉ መከበሩን ለማረጋገጥ የዜጎች ከሀገራቸው መፈናቀል፣ መሰደድ፣ በግፍ መታሰርና መገደል ማብቃት አለበት እላለሁ፡፡ አለበለዚያ ነገ ሁላችንም ከሀገራችን መፈናቀላችን አይቀሬ ስለሆነ ዛሬውኑ ቆም ብለን በማሰብ ማድረግ ያለብንን መወሰን ያለብን ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ማንም ኢትዮጵያዊነታችንን ሲፈልግ ወስዶ እንካችሁ፤ ሳይፈልግ ዜግነታችሁን እኔ የምሰጣችሁ ስፍር ብቻ ነው ሲሉ መፍቀድ ባርነትን ከመምረጥ ውጭ  ምን ትርጉም ልንሰጠው እንችላለን? እኔ በበኩሌ ባርነትን በፍፁም አልመርጥም፣ አልደግፍምም፡፡

! …. የኢህኣዴግ ኣጀንዳና የኣማራ ተወላጆች መፈናቀል …..!

 

አብርሃ ደስታ

(ከመቀሌ)

ህወሓት/ኢህኣዴግ ከሚከተለው ‘ኣብዮታዊ ዴሞክራሲ’ የተሰኘ የፖለቲካ ኣቅጣጫ (እነሱ ‘ርእዮተ ዓለም’ ይሉታል) ኣንፃር ‘የቡድን መብት’ ከ’ግል መብት’ ይቀድማል። በብዱን መብት እሳቤ መሰረት (በኣንቀፅ 39 የ’እስከመገንጠል መብት’ ታግዞ) ብሄሮች በየክልላቸው ያለ ሃብት (ለምሳሌ መሬት) በዋናነት እንዲቆጣጠሩ ያስችላል።

በዚ መሰረትም ‘የሌላ’ ክልል ተወላጆች በ’ሌላ ክልል’ መሬት የማግኘት መብታቸው ሲነፈጉ ይታያል። የኣማራ ተወላጆች ብዙ ግዜ ኑሮኣቸው ከመሰረቱበት ቀያቸው በኃልና በግፍ ሲፈናቀሉ እያየን ነው። በቡድን መብት መሰረት የኢትዮዽያ ሕጋዊ ዜጎች በገዛ ሀገራቸው መኖርያ መሬት ሲከለከሉ ማየት እጅግ ያሳዝናል። በሌላ በኩል በስልጣን ያለ ድርጅት (የራሱን ዜጎች እያፈናቀለ) መሬ ታችን ተቀባይነት በሌለው መንገድ ለዉጭ ዜጎች ሲቸረችር ይታያል። ዜጎቻችን በገዛ መሬታቸው ባዕድ ሁነዋል ።

የሚገርመው ደግሞ ‘መሬት ኣይሸጥም ኣይለወጥም’ ከሚል ግራ የተጋባ ፍልስፍና መሬታችን ለውጭ ዜጎች የሚሰጠው በነፃ ሊባል በሚችል ሁኔታ መሆኑ ነው። (በነፃ የሚሰጥበት ምክንያት መሬት ተሸጠ እንዳይባል ነው)። የኣማራ ተወላጆች ከቀያቸው መፈናቀል የገዢው ፓርቲ የተሳሳተ ፖሊሲና ለህዝብ ያለው ንቀት የሚያሳይ ነው። ዜጎችን በማባረር (‘ሕጋዊ ያልሆኑ ኗሪዎች’ በሚል ስም) መሬት ለውጭ ዜጎች ሲሰጥ እነዚህ የሌላ ሀገር ዜጎች እንዴት ‘ሕጋዊ’ ሆኑ???

ሰዎች ከቀያቸው በሃይል (በግፍ በዘርሓረጋቸው እየተለዩ) ሲፈናቀሉ (ሲባረሩ) የከፋ የሰብኣዊ መብት ጥሰት ነው። ዜጎቻችን (ወገኖቻችን) ሲፈናቀሉ የሚደርሳቸው ኢኮኖሚያዊ፣ ማሕበራዊና ስነልቦናዊ ቀውስ (Helplessness) መገመት ኣይከብድም። ሁሉም ኢትዮዽያ ሊተባበራቸው ይገባል፤ መንግስት ይህን ተግባሩ እንዲያቆም ተፅዕኖ ማድረግ ኣለብን።

እኛም እየተፈናቀሉ ካሉ ሰዎች ጎን መሰለፍ ያለብን ይመስለኛል። ምክንያቱም (1) ወገኖቻችን ናቸው። እኛ ኢትዮዽያውያን ያልደረስንላቸው ማን መጥቶ ይረዳቸዋል? (2) ዛሬ በኣማራ ተወላጆች እየተፈፀመ ያለው ግፍ (ኣሁንኑ ካልቆመ) ነገ በእያንዳንዳችን እንደሚፈፀም ማወቅ ይኖርብናል። (3) የማፈናቀል ተግባሩ የብሄር ፖለቲካ ችግር ኣባብሶ የጥላቻ ፖለቲካ ስር ሰዶ የኢትዮዽያ ሀገራችን ኣንድነት የሚፈታተን ይሆናል።

የስርዓቱ ደጋፊዎች ይህንን ችግር ተረድታቹ በገዢው ፓርቲ Pressure ፍጠሩ ፤ ኣለበለዝያ ግን ችግሩ ሁሉም ዜጋ ይነካል። በተለይ የትግራይ ተወላጆች በግልፅ ተቃውሞኣችንን ማሰማት ኣለብን። ህወሓት /ኢህኣዴግ ከተግባሩ እንዲቆጠብ ማድረግ ወይ ተግባሩ እንዲያቆም በመቃወም ከነዚህ ተፈናቃዮች ጎን መሰለፍ ኣለብን። ምክንያቱም እነዚህ ተፈናቃዮች ብዙ ችግር እንደሚደርስባቸው የታወቀ ነው። ቂም መያዛቸው (በገዢው ፓርቲ ቅር መሰኘታቸው) ኣይቀርም። ገዢው ፓርቲ (ኢህኣዴግ) የህወሓት ስራ መሆኑ ይታወቃል። ህወሓት ስልጣን መያዝ የቻለው በትግራይ ህዝብ ትግል ነው (ህወሓት ህዝቦች ማፈናቀል ወይ መጨቆን እንዲችል ለማብቃት ባይሆንም)።

ስለዚ የኣማራ ተፈናቃዮች በህወሓት ተግባር ምክንያት በትግራይ ህዝብ ቅር ሊሰኙ ይችላሉ። እንዲህ ከሆነ ደግሞ ዛሬ በኣማራ ህዝብ እየተፈፀመ ያለው ግፍ ነገ በትግራይ ህዝብ መደረጉ ኣይቀርም። ግለሰዎች በስልጣን ለማቆየት ሲባል በሰለማዊና ንፁህ ዜጎች ግፍ እየተፈፀመ ዝም ብሎ መመልከት ተገቢ ኣይደለም።

ስለዚ ተቃውማችን ማሰማት ኣለብን። ደሞ የትግራይ ተወላጆች በኣማራ ክልል የሉም? የደቡብ ክልል ወይ ኦሮምያ ወይ ሌላ ክልል ተወላጆች በኣማራ ክልል የሚኖሩ የሉም ? የማፈናቀሉ ተግባር ካልቆመ መጨረሻው ምን ሊሆን ነው? ስለ ሌሎች ስናስብ ስለራሳችን እያሰብን ነው፤ ሌሎችን ስንተባበር ራሳችን እየተባበርን ነው። ተግባራችን ስንቃችን ነው።

ለዜጎች ቅድምያ እንስጥ!

It is so!!!

ከቤንሻንጉል አማርኛ ተናጋሪ ዜጎችን በግፍ የማፈናቀሉ ሂደት ተጠናክሮ ቀጥሏል

-ጥቃቱ ህፃናትና አረጋውያን ላይም እየደረሰ ነውአማርኛ ተናጋሪውን ከየቦታው የማፈናቀሉ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የመረጃ ምንጮቻችን አስታወቁ፡፡ የፍኖተ ነፃነት ምንጮች እንደሚሉት በዚህ ሳምንት ውስጥ ብቻ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከማይ ዞን ያሶ ወረዳ 25 ሺህ አማርኛ ተናጋሪዎች እየተደበደቡ በጭነት መኪና ተጭነው ከመኖሪያቸው ተባረዋል፡፡ የአካባቢው የዓይን ምስክሮችም ተጧሪ አረጋዊያንና ህፃናት “ውሃ፣ አምባሻ እያሉ በየመንገዱ ሲለምኑ ያለርህራሄ እየደበደቧቸው ወስደዋቸዋል፡፡” ሲሉ በቅሬታ ያስረዱሉ፡፡
ፍኖተ ነፃነት ያነጋገረቻቸው የዓይን ምስሮች እንደሚሉት መንታ የተገላገለች እመጫት ሳትቀር አስር ቀን ሳይሞላት በጭነት መኪና ላይ ወርውረዋት አከባቢውን ለቃ እንድትሄድ ተደርጓል፡፡ የዝግጅት ክፍላችን ለመረዳት እንደቻለው አብዛኞቹ ተፈናቃዮች ከ96 ዓ.ም ጀምሮ በባዶ መሬት ላይ ሠፍረው አካባቢውን ያለሙ የነበሩ ናቸው፡፡ የዘሩትን እህል ሳይሰበስቡና ንብረታቸውን ሳይዙ እየተባረሩ የሚገኙት እነዚህ የአማርኛ ተናጋሪ ዜጎች የተለያዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችም እየደረሱባቸው እንደሚገኝ ፍኖተ ነፃነት ከአይን እማኞች ለማረጋገጥ ችላለች፡፡ ምንጮቻችን አክለውም “ሰው መሆን እስከሚያስጠላ ድረስ በጭካኔ እየደበደቡ መሬት ለመሬት እየጎተቱ መኪና ላይ ይወረውሯቸዋል፡፡ በአካባቢው ኦሮሚኛ እና ሌላ ቋንቋ ተናጋሪዎች በተመሳሳይ ጊዜና ከዚያ ወዲህ በቅርብ ጊዜ ሠፍረው የሚኖሩ አሉ፡፡ እነሱን የሚነካቸውና የሚጠይቃቸው የለም፡፡” በማለት አማርኛ ተናጋሪዎች ላይ ያነጣጠረ ዘር የማፅዳት ዘመቻ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡
ፍኖተ ነፃነት ያነጋገረቻቸው በአካባቢው በንግድ ስራ የተሰማሩ ግለሰብ እንደሚናገሩት አማርኛ ተናጋሪዎቹን ከስፍራው ለማፈናቀል ከሚሰጡት ምክንያት አንዱ “ከዚህ በፊት በክልላችሁ በነበራችሁበት ቦታ የማዳበሪያ ዕዳ አለባቸው” የሚል ነው፡፡ ግለሰቡ አክለውም “ዕዳ ካለባቸው ባሉበት በህግ መጠየቅ እየተቻለ ሁሉንም ወንጀለኞች ናቸው እየተባለ መደብደብና ማባረር ወንጀል ነው፡፡” ብለዋል፡፡ አያይዘውም ብአዴን በአማራ ህዝብ ስም ሥልጣን ላይ ተቀምጦ በአማራ ህዝብ ላይ የሚፈጸመውን እያየ እንዳላየ ዝም ብሎአል፡፡ አቤቱታ እየቀረበላቸው አንድም ነገር አላሉም፡፡ ብአዴን የአማራ ህዝብ ወኪል አለመሆኑን ሙሉ በሙሉ ያረጋገጠበት ወቅት ላይ ደርሷል፡፡” ሲሉ እጅግ አዝነው ተናግረዋል፡፡
ጉዳዩን እያስፈጸሙ ናቸው የተባሉትን የወረዳውን አስተዳዳሪ አቶ ታደሰ ሻምበልን በስልክ አግኝተናቸው ነበር፡፡ እራሳችንን አስተዋውቀን ጥያቄያችንን ልንጀምር ስንል አቶ ታደሰ ስልካቸውን ጆሮአችን ላይ በመዝጋታቸው ዜናው ሚዛናዊ ለማድረግ አልቻልንም፡፡
በዚህ ሳምንት ከወረዳው ተባረው በመጓጓዝ ላይ የነበሩ ዜጎችን ጭኖ የነበረው አንዱ መኪና ተገልብጦ 59 ሰዎች ህይወታቸው ሊያልፍ ችሏል፡፡ ህይወታቸው ካለፈው ውስጥ አብዛኞቹ ህጻናት፣ሴቶችና አረጋውያን መሆናቸውን በስፍራው የተገኙ የዓይን ምስክሮች ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡
ምንጭ ፍኖተ ነፃነት