Daily Archives: December 3rd, 2014

የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ላይ ተሻሽሎ ቀርቧል የተባለው ክስ ተሰማ

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው እየታየ ያሉት የዞን 9 ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ ማህሌት ፋንታሁን እና ናትናኤል ፈለቀ እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ ላይ የተመሰረተው ክስ ተሻሽሎ ቀርቧል የተባለው የክስ ዝርዝር ዛሬ በልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ተሰምቷል፡፡

zone9ዛሬ ህዳር 24 ቀን 2007 ጠዋት በዋለው ችሎት፣ በብሎገሮቹ እና ጋዜጠኞች ላይ ተሻሽሎ የቀረበው የክስ ዝርዝር በንባብ የተሰማ ሲሆን በክስ ወረቀቱ ላይ ከተመለከቱት ነጥቦች መካከል ግልጽ ያልሆኑ ነጥቦችን አካትቶ እንዲሰጥ ለአቃቤ ህግ ትዕዛዝ ተሰጥቶታል፡፡ ስለሆነም ሙሉ የክስ ወረቀቱ አርብ ለጠበቆቹ እንደሚደርስ ይጠበቃል፡፡

በጠቦቆቹ በኩል ክሱ ቀደም ብሎ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት መሻሻሉን ለማረጋገጥ ያለፈው የፍርድ ቤቱ ብይን ግልባጭ እስካሁን እንዳልደረሳቸው በመግለጽ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲደርሳቸው ጠይቀዋል፡፡ በዚህም የተነሳ የብይኑ ግልባጭ ሳይደርሰን ተሻሻለ የተባለው ክስ መሰማት የለበትም ብለው የነበር ቢሆንም፣ ክሱን አይታችሁ መቃወሚያ ካላችሁ አስተያየት እንድትሰጡበት እድል እንሰጣለን ያለው ፍርድ ቤቱ ክሱ እንዲሰማ አድርጓል፡፡

ፍርድ ቤቱ ጠበቆቹ ያላቸውን አስተያየት ይዘው እንዲቀርቡ ለታህሳስ 7 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱን የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ከ3 ወር በፊት የታፈነው የመኢአድ አመራር የት እንደደረሰ አልታወቀም

aeupየሶስቱ ፓርቲዎች አመራሮች ለታህሳስ 21 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጥሮባቸዋል
የገዥው ፓርቲ የደህንነት ኃይሎች የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችን ከየ ክፍለ ሀገሩ ማሰር በጀመሩበት ወቅት በደህንነትና ፖሊሶች የታፈነው የመኢአድ አመራር የት እንደደረሰ እንደማይታወቅ ቤተሰቦቹ መግለፃቸውን የነገር ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡ የሰሜን ጎንደር አመራር የሆነው አቶ ችሎት ባዜ መስከረም 2 ቀን 2007 ዓ.ም በገዥው ፓርቲ የደህንነት ኃይሎች የታፈነ ሲሆን፤ በወቅቱ ቤተሰቦቹ ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንደተዛወረ መረጃ ደርሷቸው እንደነበር መግለፃቸው ተጠቁሟል፡፡ ሆኖም በተደጋጋሚ አቶ ችሎት ወደ ማዕከላዊ መዛወር አለመዛወሩን ቢጠይቁም እንዳልመጣ ተነግሯቸዋል፡፡

የታፈነው የመኢአድ አመራር ማዕከላዊ እንደሌለ የተነገራቸው ቤተሰቦቹ ፍርድ ቤት ቀርቦ ከሆነ በሚል ሪጂስትራል ስሙ እንዳለ ቢያስጠይቁም እስካሁን ፍርድ ቤት እንዳልቀረበ አረጋግጠናል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል ከየ ክፍለ ሀገሩ በገዥው ፓርቲ የደህንነት ኃይሎች ታፍነው በአሁኑ ወቅት ማዕከላዊ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነት እና የመኢአድ አመራሮች በትናንትናው ዕለት አራድ ምድብ ችሎት ቀርበው ለታህሳስ 21 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጥሮባቸዋል፡፡

የ9ኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች ትብብር በወቅታዊ የጋራ እንቅስቃሴያቸው ዙሪያ መግለጫ ሰጥተዋል

የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የፊታችን ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ስላዘጋጁት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ወቅታዊ እንቅስቃሴ ዙሪያ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡፤

ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ ዕለታዊ መግለጫ

ዝግጅታችን ተጠናክሮ ቀጥሏል! እርስዎም ይዘጋጁ!
‹‹ነጻነት ለፍትሓዊ ምርጫ›› በሚል የአንድ ወር መርሃ ግብር ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ ስርዓቱ መርሃግብሮቻችን በማጨናገፍ ለነጻነት የምናደርገውን የትግል ጉዞ ለማደናቀፍ ሌት ተቀን እየሰራ ይገኛል፡፡ ሆኖም የነጻነት ትግሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚያስከፍል መሆኑን የተረዳው ትብብሩ ለገዥው ፓርቲ አፈና ሳይንበረከክ ስራውን ቀጥሏል፡፡ በተለይ ከመርሃ ግብሮቻችን መካከል ስርዓቱን ያስፈራውን የ24 ሰዓት የአደር ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅታችን አጠናክረን ቀጥለናል፡፡ ለዚህ የአዳር ሰልፍ የትብብሩ አባል ፓርቲዎች ሰው በሰው በመቀስቀስ፣ ወረቀት በመበተን እንዲሁም በየ ፓርቲዎቻችን ስም የታተሙ ቲሸርቶችን በመልበስ ህዝቡን እያነቃቃን እንገኛለን፡፡ ሰልፉ እስከሚደረግበት ህዳር 27/28 2007 ዓ.ም ድረስም ዝግጅታችን አጠናክረን እንቀጥላለን፡፡

ይህን መርሃ ግብር ስንነድፍ ለነጻነት የሚከፈለው መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅተንና የቀድሞ አባቶቻችን ካሳዩት ቆራጥነት ተምረን ነው፡፡ በዚህ ለቀጣይ የትግል ጉዞአችን ጭላንጭል ለምናይበት መርሃ ግብር የኢትዮጵያ ህዝብ ከጎናችን እንዲቆም ጥሪ እናደርጋለን፡፡ በውጭም ሆነ አገር ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለነጻነት ለምናደርገው ጉዞ የጀመርነውን የሰው በሰው ቅስቀሳ በመደገፍ፣ በገንዘብ፣ በሞራልና በሌሎች ለመርሃ ግብሩና ለአጠቃላይ ትግሉ ይጠቅማል ባሉት መንገድ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ እናቀርባለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ መርሃ ግብሩ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ በሞራልና በተለያየ መንገድ መልዕክቶቻችን ለህዝብ እንዲደርሱ ድጋፍ ያደረጋችሁልን በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ልባዊ ምስጋናችን ማቅረብ እንፈልጋለን፡፡ አሁንም ድጋፋችሁን አጠናክራችሁ በመቀጠል ታሪካዊ ግዴታችሁን እንድትወጡ እንጠይቃለን፡፡

በ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በኩል ለሰላማዊ ሰልፉ የሚያስፈልገው ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ህዝቡ በዝግጅቱ ከሚያደርገው ድጋፍ ባሻገር በመስቀል አደባባይ በሚኖረን ቆይታ የሚያስልጉት ቁሳቁሶች በተለይም ደረቅ ምግብና ውሃ ከአሁኑ እንዲያዘጋጅ ማስታወስ እንፈልጋለን፡፡ ህዳር 27/28 2007 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ የሚደረገው የ24 (አዳር) ሰልፍ ኢትዮጵያውያን ላይ የተጫነውን የፍርሃት ድባብ በመስበር ለነጻነት የምናደርገው ወሳኝ ጉዞ ጅማሬ በመሆኑ በሁሉም የማህረሰብ ክፍል የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ራሳቸውንና አገራቸውን ነጻ ለማውጣት የትግሉ አካል እንዲሆኑ ጥሪያችን እያቀርባለን፡፡

ያለ መስዋዕትነት ድል የለም!

ህዳር 23/2007 ዓ.ም

አዲስ አበባ

%d bloggers like this: