24 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በየመን ባህር ሰጥመው ሞቱ
ባለፈው ሰኞ ታህሣሥ 20 ቀን 2007 ኣ.ም. በጀልባ ወደ የመን ሊገቡ የሞከሩ 24 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ሞቻ በምትባል የየመን ወደብ ከተማ አቅራቢያ በደረሰባቸው የጀልባ መስጠም አደጋ መሞታቸውን የየመን የሀገር ውስጥ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ እንደሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ገለፃ ከሆነ በጀልቧ ተሳፍረው ከነበሩት ውስጥ በህይወት የተረፉ ስለመኖራቸውም ሆነ በአደጋው የሞቱትን በለመለየት ወደ ሀገራቸው ለመመለስ የተደረገ ጥረት አለመኖሩንም ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡
በቅርቡ ህዳር 28 ቅን 2007 ዓ.ም. በተመሳሳይ ሁኔታ በዚሁ በየመን የወደብ ከተማ በሆነችው ሞቻ አቅራቢያ 70 ኢትዮጵያውያን በሚጓዙበት ጀልባ በደረሰ አደጋ ህይወታቸው ማለፉ አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን ባህር አቋርጠው የምን ሊገቡ ሲሉ ህይወታቸው ላለፈው 94 ኢትዮጵያውያን ጉዳይ የኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ በአቅራቢያው ያሉ የኢትዮጵያ ኤምባሲና ቆንፅላ ፅህፈት ቤት አምባሳደሮች ያሉት ነገር የለም፡፡ በየ ዓመቱ የህንድ ውቅያኖስን እና ቀይ ባህርን በጀልባ አቋርጠው ወደ የመን ሊገቡ የሚሞክሩ በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች እየሞቱ ቢሆንም አደጋውን ለመቀነስ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል የተደረገ ጥረት አለመኖሩን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡
አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመንን ወደ ሌላ ሶስተኛ ሀገር ለመሸጋገር የሚጠቀሙባት በመሆኑ የስተኞች ጣቢያ እንደማይመዘገቡና እገዛም እንደማይደረግላቸው ተጠቁሟል፡፡ የመን ባህር አቋርጠው ከሚገቡ አብዛኞቹ ስደተኞች መካከል ጥቂቶች ብቻ በተለይም በፈረንጆቹ 2014 መጨረሻ የመን በሚገኘው በተባበሩት መንግስታት ከፍተኛው የስደተኞች ኮሚሽን እገዛ የተደረገላቸው 9,500 ኢትዮጵያውን እነደነበሩ የድርጅቱ መረጃ አመልክቷል፡፡
ከመንግስት በሚደርስባቸው የፖለቲካ ጫና እና በሀገሪቱ ከተከሰተው የኢኮኖሚ ችግር በተፈጠረው የኑሮ ውድነት የተነሳ የሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ዜጎች ቁጥር በየ ዓመት እየጨመረ መሄዱ ይታወቃል፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና ስራቸውን ለመቀጠል የሚያስችል ውል መጨረሻው የሚወሰነው በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ሲፀድቅ እንደሆነ ገለፁ
ታዋቂውና ስመ ጥር የምስራቅ አፍሪካ የፖለቲካ ሳይንቲስትና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና በመንግስት መደበኛው በስራ በቆያ ዕድሜያቸው በመጠናቀቁ ስራቸውን በሚታደስ ውል ስራቸውን እንዲቀጥሉ የትምህርት ክፍሉ ፈቃደኝነታቸውን በጠየቀው መሰረት ውል ፈርመው በስራ ገበታቸው ላይ እንደሆኑ አስታወቁ፡፡
ዶ/ር መረራ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ እንደገለፁት ከሆነ፤ በዩኒቨርስቲው በማስተማርና በምርምር ከ25 ዓመታት በላይ እንዳገለገሉና አሁን ዕድሜያቸው 60 ዓመት ስለሞላቸው የጡረታ ጊዜያቸው በመሆኑ፤ በእሳቸውና በዩኒቨርስቲው መካከል በሚታደስ አዲስ የኮንትራት ውል ስምምነት መሰረት ስራቸውን ለመቀጠል ከዚህ ቀደም ከሚያስተምሩበት ትምህርት ክፍል እና ከዩኒቨርስቲው ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ ጋር መፈራረማቸውን እና ስራቸውንም መቀጠላቸውን አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ በየጊዜው በኮንትራት መልክ የሚታደሰው አዲሱ የውል ስምምነት ሊፀና የሚችለው በእሳቸውና በትምህርት ክፍሉ ስራውን ለመቀጠል የሚያስችል ፈቃደኝነት ስምምነት በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል ሲፀድቅ መሆኑንም ሳይገልፁ አላለፉም፡፡
አዲስ ሚዲያም በቅርቡ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ዶ/ር መረራ ከሚሰሩበት አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተባረሩ የሚል ዜና ተሰምቷልና እውነት ነው ወይ ሲል ላቀረበላቸው ጥያቄ “እኔ እስካሁን የደረሰኝ መረጃ የለም፣ መደበኛ ስራዬን እየሰራሁ ነው፣ ነገር ግን አንዳንድ ወሬ እኔም እሰማለሁ እንጂ እሳካሁን የደረሰኝም የእግድ ደብዳቤም ሆነ መሸኛ የለም፣ አዲስ ነገር ካለ ወደፊት አብረን የምንሰማው ነው ሚሆነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ለዶ/ር መረራ ስራ ጋር በተያያዘ ስለተወራው ነገር ለማጣራትና ምላሽ ለማግኘት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ክፍል ተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም ለጊዜው አልተሳካም፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ትግል ውስጥ ጉልህ ሚና ያላቸው ሲሆን፤ በአሁን ወቅት የኦፌኮ ሊቀመንበርና በፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ የሚመራው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) የውጭ ጉዳይ ኃላፊ መሆናቸው ይታወቃል፡፡