Daily Archives: April 25th, 2016

አቃቤህግ እነ ኦኬሎ አኳይ በከባድ ወንጀል ክስ እንዲቀጡ ጠየቀ

በሰኔ 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ የሽብር ክሰ ተመስርቶባቸው ክሳቸው በከፍተኛው ፍርድቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ አኳይ(ሰባት ሰዎች) መጋቢት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ጥፋተኛ ስለመሆናቸው ፍርድቤቱ ውሳኔ ካስተላለፍ በኃላ ከሁለቱም ተከራካሪዎች የቅጣት አስተያየት ለመስማት ለዛሬ ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቶ ነበር፡፡

Okello Akuay

ተከሳሾችም ሆኑ አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ለፍርድቤቱ ያቀረቡ ሲሆን አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
ከአንደኛ አስከ ሶስተኛ ያሉ ተከሳሾች የወ/ህ/ቁ 27/1/፣ 32/1/ሀ፣ 38 እና 241 በመተላለፍ ወንጀል ለመፈፀም በተቋቋመ ቡድን አመራር፣ አባል፣የደህንነት ዘርፍ እንዲሁም የውጭ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን፣ ገንዘብ በማሰባሰብ እና አባላትን በመመልመል ፣ የቡድኑ አባላት ወታደራዊ ስልጠና የሚያገኙበትን ሁኔታ በማመቻቸት፣ መሳሪያ በመግዛት፣የጦር መሳሪያ ድጋፍ ለማግኘት ከኤርትራ መንግስት ጋር እና ከኦነግ እና ግንቦት ሰባት ከተባሉ ቡድኖች ጋር በመደራደር በከፍተኛ አመራርነት ሲንቀሳቀስሱ የነበረ መሆኑን አቃቤህግ ጠቅሶ ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን ፍርድቤቱ የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት እንዲመድብ ጠይቋል፡፡

የቡድኑን አላማ አውቀው፣ በቡድኑ ወታደራዊ ስልጠና በመውሰድ ጥቃት ለመፈፀም በዝግጅት ላይ ነበሩ ያላቸውን ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች የወንጀል አፈፃፀማቸው በመካከለኛ ይመደብልኝ ሲል የጠየቀው አቃቤህግ ሁሉም ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አመልክቷል፡፡

ተከሳሾች በበኩላቸው በጠበቃቸው አማካኝነት ጥፍተኛ የተባሉት ከ2006 ዓ.ም በፊት ፈፅማቹኃል በተባለው ድርጊት መሆኑ ከቀረበባቸው ክስም ሆነ ፍርድቤቱ በሰጠው ውሳኔ እንድሚታወቅ አስረድተው፣ ለጥፋተኝንት ውሳኔው መሰረት የሆኑት ድርጊቶች ተፈፀሙ በተባለበት ጊዜ በስራ ላይ በነበረው እና በ2002 ዓ.ም በወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ፍርድቤቱ እንዲወስንላቸው ጠይቀዋል፡፡

የወንጀል ህጉ አንቀፅ241 ስር በተደነገገው እና ተከሳሾች ጥፋተኛ በተባሉበት የወንጀል ድርጊት በየትኛውም አካል ላይ ስለመድረሱ የተረጋገጠ የገንዘብም ሆነ የአካል ወይም የህይወት አደጋ የለም ያሉት ተከሳሾቹ ፈፀሙ በተባሉት ወንጀል የደረሰ ጉዳት ባለመኖሩ የወንጀሉ አፈፃፀም ቀላል በሚል ሊያዝ ይገባል ሲሉ አመልክተዋል፡፡ ተከሳሾች የቅጣት ማቅለያዎንም ፍርድቤቱ እንዲቀበላቸው ጠይቀዋል፡፡

ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው እንዲሆም አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ በመሆኑ እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው አመልክተዋል፡፡

ፍርድቤቱ የቅጣት አስተያየቶቹን ተመልክቶ የቅጣት ፍርድ ለመስጠት ለረቡዕ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡
ምንጭ፡-ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (EHRP)