የፍርድ ቤት ችሎት ትዝብት
ማህሌት ፋንታሁን
የጥቅምት 16 ቀን 2010 ዓ.ም. የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ትዝብት። ብዙ መዝገቦች በቀጠሯቸው መሰረት ሳይሰሩ ተለዋጭ ቀጠሮዎች እየተሰጠባቸው ነው። የሚሰጠው ምክንያት ‘ለችሎቱ አዲስ ዳኞች በመሆናችን’ የሚል ነው። ተከሳሾችም በጉዳያቸው አላግባብ መራዘም እና በማረሚያ ቤት በሚደርስባቸው በደል ተማረው አቤቱታቸውን እያሰሙ ነው።
የዛሬዎቹን አቤቱታዎች በስሱ እነሆ!
� አቤቱታ አንድ። በእነ ክንዱ ዱቤ መዝገብ 2ኛ ተከሳሽ ዘመነ ጌቴ ፤ “ማእከላዊ እያለሁ አካላዊ እና ስነልቦናዊ ግፍ እና በደል ደርሶብኛል። በድቅድቅ ጨለማ ለ6ወር ተቀምጫለሁ። በድብደባ ብዛት የግራ አይኔ ማየት አይችልም። ዘሬን እንዳልተካ የዘር ፍሬዬን መተውኛል። አማራነታችን እየተጠቀሰ ይሰድቡናል። እኛ ስንወለድ አማራ ሆነን ወይም ኦሮሞ ሆነን መወለድ ፈልገን አይደለም። የተፈጥሮ ነገር ሆኖ ነው። አማራ አህያ ነው። አማራ ጅብ ነው። አህያውን በጅቡ እናስበላዋለን ይሉናል። በማእከላዊ የነበረው ስቃይም ተከትሎኝ ቂሊንጦ መጥቷል። የማረሚያ ቤቱ ፖሊሶች እየጠሩ ይደበድቡኛል። ምንም አይነት የመኖር ህልውና የለንም።” ዘመነ ጌቴ ይህን እያለ ዳኞቹ እንዲያበቃ/እንዲያቆም ሲነግሩት አብዛኞቹ እስረኞች ‘ይናገር! የሆነውን ነው ሚያወራው’ በማለት መናገሩን እንዲቀጥል ጠይቀዋል። ዘመነ ጌቴ ይህን ብሎ አቤቱታውን አጠቃሏል። “ስቃዬን እየተናገርኩ ነው። ስነልቦናዊ እና አካላዊ ጉዳት ደርሶብኛል፤ እየደረሰብኝም ነው። ፍርድ ቤቱ መፍትሄ ይሰጥልኝ ዘንድ ነው የምናገረው።”
�አቤቱታ ሁለት። በእነ ተሻገር ወ/ሚካኤል መዝገብ አባ ገ/እየሱስ ፤ “ማእከላዊ የደረሰብንን ግፍ ከዚ ቀደም ተናግረናል። ቂሊንጦ ከገባሁ በኋላ ችግር እየተከሰተብኝ ነው። ከወንድሞቼ ጋር እንዳልገናኝ እና አብሬ እንዳልበላ ይከለክሉኛል። ኦፊሰር ካሱ የሚባለው የዞን 3 ሃላፊ ነው የሚከለክለኝ። እኔ አዲስ አበባ ዘመድ ስላለኝ በሰሃን ተቋጥራ የምትመጣልኝን ምግብ ከሌሎች ጋር ተካፍዬ እንዳልበላ ተደርጌአለሁ። ማውራትም መጫወትም አልቻልኩም። ተፅእኖ እየተደረገብኝ ነው። ይሄን ክረምት የከረምኩት ክራሞት እ/ር የቁጠረው።”
�አቤቱታ ሶስት። 5ኛ ተከሳሽ አባ ” እሳቸው[አባ ገ/እየሱስ] የተናገሩት በደልና ግፍ በኔ ላይም ደርሷል። እኔ ወገን የለኝም። በልጅነቴ ነው ወገኔን ትቼ ገዳም የገባሁት። በገዳሙ[ዋልድባ] የነበሩትን አፅመ ቅዱሳን አፈራርሰው ዛፎቹን ቆርጠው ክሰል እያወጡበት ነው። ይህን ተቃውመን ብንናገር አሸባሪ ተባልን።” አባ ይህን ሲናገሩ ዳኞቹ በፊት ስለተከሰተ ነገር ሳይሆን በማረሚያ ቤት ስለሚደርስባቸው በደል ብቻ መናገር ገልፀውላቸዋል። ሆኖም አባ “ስለበፊቱም ስለአሁኑም መናገር እችላለሁ” ብለው የነበረ ቢሆንም ዳኛው ስነስረአቱ እንደማይፈቅድላቸው ከገለፁላቸው በኋላ አባ በማረሚያ ቤቱ ስለሚደርስባቸው በደል ማሰማት ቀጥለዋል። ” በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ 3ቴ እና 4ቴ ቢሮ እየጠሩ ያንገራግሩናል (ያስፈራሩናል ፤ ይዝቱብናል)። ፀሎት እንድንፀልይ አይፈቀድልንም። መንግስት ነው እንዴ ይቺን ሃገር የሚጠብቃት?! እ/ር ነው የሚጠብቃት! አበበ የሚባል ፖሊስ እና ካሱ የሚባል ኦፊሰር ‘አመፅ እያነሳሳችሁ ነው ጨለማ ቤት እናስገባችኋለን’ እያሉ ያስፈራሩናል። ከ2004 ጀምሮ እየተሰቃየን ነው። ገዳም እንዳንቀመጥ ተከለከልን። እናንተስ ለምንድነው እውነት ማትፈርዱልን? ለምን ፀሎት እንዳንፀልይ ተከለከልን?”
�አቤቱታ አራት። በእነ ተሰኢድ ኑርሁሴን ኑሩ ” የታሰርኩት አማራ ስለሆንኩ ነው። ጎንደሬ ስለሆንኩ ነው። ማእከላዊ ጥፍሬን ነቅለውኛል። ማእከላዊ የዘር ፍሬ ሚኮላሽበት የሶት ልጅ ጡት አስረው የሚጎትቱበት የስቃይ ቦታ ነው። እዚህ ያለነው ሁላችንም በማእከላዊ ስቃይ አሳልፈናል። በአደባባይ መናገር የቻልነው እና የደፈርነው ብቻ እንናገር ብለን ነው። እኔ የኪነጥበብ ሰው ነኝ። የዜማ እና የግጥም ደራሲ ነኝ። ያሰሩኝ ‘ላባ’ የተሰኘ ባለ መቶ ገፅ የግጥም መድብሌን ለማሳተም እየሄድኩ ሳለ ነው። እና የግጥም መድብሉ አልተመለሰልኝም። የጣሱት የሰብአዊ መብት እንኳን ሊመለስልኝ የሚቻል አይደለም። የግጥም መድብሌን ይመልሱልኝ። ከክሱ ጋር ግንኙነት የለውም። በማስረጃነትም አልተያያዘም። እያዝናና የሚያስተምር የስነፅሁፍ ስራ ነው። በተጨማሪም ፀሎት እንዳላደርግ ተከልክያለው። እኔ ሙስሊም ነኝ። እንዳልሰግድ ይከለክሉኛል። ክርስቲያኖችም እንዳይፀልዩ ተከልክለዋል። ከዚህ የመጣችሁ ቤተሰቦች ይህን በደላችንን ለሚዲያዎች ሁሉ ንገሩልን። ” ዳኞች የሰይድን አቤቱታ ከሰሙ በኋላ በማእከላዊ መርማሪዎች ተወሰደብኝ ያለውን የግጥም መድብል በተመለከተ ለማጣራት ከማእከላዊ የመጣ ፖሊስ መምጣቱን ጠይቀው ሲቪል የለበሱ እና ከአቃቤ ህግ ጎን ቁጭ ብለው ከነበሩ 3ት የማእከላዊ ፖሊሶች አንዱ በመቆም ከማእከላዊ መምጣቱን ለዳኞቹ መልስ ሰጥቷል። ፖሊሱ ስለጉዳዩ ሲጠየቅ የሚያቀው ነገር እንደሌለ የገለፀ ሲሆን ዳኞች በቀጣይ ቀጠሮ አጣርቶ ምላሽ ይዞ እንዲመጣ ካዘዙት በኋላ ስሙን ሲጠይቁት በችሎት ስሙን ለመናገር ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል። ዳኞች ከመታወቂያው ላይ ስሙን እንዲገለብጡም መታወቂያውን በማውጣትም በችሎት አስተባባሪ በኩል ለዳኞቹ ልኳል።
�አቤቱታ አምስት። በእነ ተሻገር ወ/ሚካኤል መዝገብ 28ኛ ተከሳሽ አራጋው፤ ” በማእከላዊ ድብደባ ያደረሱብን መርማሪዎች እዚሁ ቁጭ ብለዋል። ግፍና በደል ያደረሱብን እነሱ ናቸው። ያልሆነ ነገር ፤ ያላልነውን ፤ ያላደረግነውን ፅፈው በግዳጅ ያስፈረሙን እነሱ ናቸው። መርማሪው ስሙን ሲጠየቅ በግልፅ ያልተናገረበት ምክንያት ይታወቃል። የሰራውን ስለሚያውቅ ነው። ህግ ካለ በህግ እንዳኝ። እነዚህ [ወደ ማእከላዊ መርማሪ ፖሊሶች እየጠቆመ] መርማሪዎች ናቸው፤ ደብዳቢዎች ናቸው እንደገና እዚህ መጥተው ደግሞ ይከታተሉናል። ምስክርም የሚሆኑት እነሱ ናቸው። ብዙ ነገር ሆነው ነው የሚሰሩት። ” ዳኞች የአራጋውን አቤቱታ ሰምተው ከማእከላዊ የሚመጡ ፖሊሶች እንደማንኛውም ሰው መጥተው ችለቱን መከታተል እንደሚችሉ እና የመከልከል ስልጣን እንደሌላቸው ተናግረዋል።
�አቤቱታ ስድስት። በእነ ተሻገር ወ/ሚካኤል መዝገብ ተከሳሽ ሙላቱ ተሰማ ፤ ” ማእከላዊ በነበርኩ ጊዜ አሁን ልገልፀው በማልችለው አካሌ ላይ ድብደባ ደርሶብኛል። ከተፈቀደልኝ ልብሴን አውልቄ አሳያለሁ። እኔ የአንድነት የፍትህ እና ዲሞክራሲ ፓርቲ አባል ነኝ እንጂ አሸባሪ አይደለሁም። ካሸባሪም ጋር የምገናኝ አይደለሁም። ቂሊንጦ ጠባብ ክፍል ውስጥ አርባ እና ሃምሳ ሆነን ነው የምንኖረው። በ90ሳሜ ፍራሽ ላይ ለሁለት ነው ምንተኛው የሚቀርብልን ምግብ ተመጣጣኝ አይደለም። ቤተሰቡ ቅርብ ያለ የሚቋጥርለትን ይበላል። እኛ ሚጠይቀን የሌለ በቂ ምግብ አናገኝም። የክልላችን ፍርድ ቤት ስልጣን ስላለው ክሳችን ወደ ክልላችን ይዙርልን።”
�አቤቱታ ሰባት። በነተሻገር ወ/ሚካኤል መዝገብ ተከሳሽ ተስፋሁን ማኔ ፤ ” ማእከላዊ እያለሁ መርማሪው ተምረሃል ወይ ብሎ ጠየቀኝ። አዎ ስለው ፤ ስንት ጊዜ ወደቅክ አለኝ። አልወደቅኩም ስለው፤ አማራ ደደብ አይደለ እንዴ እንዴት አልወደቅክም? አለኝ። በቂሊንጦም ግንባታ እያስፋፉ ነው። ለግንባታው የሚሆን ድንጋይ በግዳጅ እንድሸከም እየተደረኩ ነው። ጀርባዬ ተላልጧል። ጉዳያችን በክልላችን ይታይልን።”
ለይቅርታ ያመለከተችው ‘ዘማሪት’ ምርትነሽ ጥላሁን: በምልአተ ጉባኤው ፊት ቀርባ አስረዳች፤ በይቅርታ ተቀበላት፤ በቡራኬ አሰናበታት
• በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አስተባባሪነት የሚዲያ መግለጫ ትሰጣለች፤
• ለሌሎችም መመለስ ጥረት እንድታድርግ ብፁዓን አባቶች አሳሰቧት፤
• “ቤተ ክርስቲያን የይቅርታ ቤት ናት፤ጥፋታቸውን አምነው ከመጡ እንቀበላቸዋለን፤” /ብፁዓን አባቶች/
†††
ፎቶ፡ ዘማሪት ምርትነሽ ጥላሁን እና የኢ.ኦ.ተ.ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ
የቅዱስ ሲኖዶስን የምሕረት ጥሪ በመቀበል፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮና ሥርዓት ከሚገዳደረው የእነበጋሻው ደሳለኝ ሕገ ወጥ ቡድን፤ ራሷን ለይታ፣ ይፋዊ የይቅርታ ጥያቄ ያቀረበችው ‘ዘማሪት’ ምርትነሽ ጥላሁን፣ የምልአተ ጉባኤውን ይቅርታ አገኘች፡፡
የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮችን በተመለከተ፣ ለጥፋተኞችና ለበደለኞች እንደጥፋታቸው መጠን ምሕረት የመስጠት፣ ይቅርታ የማድረግና አስፈላጊ ከኾነም በቀኖና የመቅጣት ሥልጣን ያለው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ በዛሬ፣ ጥቅምት 16 ቀን 2010 ዓ.ም. የቀትር በኋላ ውሎው፣ የ‘ዘማሪት’ ምርትነሽን ማመልከቻ ተቀብሎ ይቅርታ አድርጎላታል፡፡
የይቅርታ ማመልከቻዋ፣ በምልአተ ጉባኤው ፊት በንባብ ሲሰማ፣ ከሕገ ወጥ ቡድኑ ጋራ በአባሪነት ትንቀሳቀስ እንደነበር የጠቀሰችው ‘ዘማሪት’ ምርትነሽ፣ ጥፋት መፈጸሟን አምና ይቅርታ እንዲደረግላት ጠይቃለች፡፡
“ከእነርሱ ጋራ የነበርኩ ቢኾንም፣ የዓላማቸው ተከታይ አይደለሁም፤” ያለችው ‘ዘማሪት’ ምርትነሽ፣ ሕገ ወጡ ቡድኑ ቤተ ክርስቲያንን የሚጎዳ እንቅስቃሴ በማድረጉ ለመለየት መወሰኗን ገልጻለች፡፡ “እነርሱ ወደ ሌላ እምነት ቢሔዱም የእኔ እምነቴ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ነው፤ ወዳሳደገችኝ ቤተ ክርስቲያኔ ተመልሻለሁ፤ አስተምህሮዋንና ሥርዓቷን ጠብቄ እኖራለሁ፤” በማለት ውሳኔዋን ለምልአተ ጉባኤው አረጋግጣለች፡፡
በይፋ ለመመለስ መወሰኗን አድንቀው ምክር የሰጡ ብፁዓን አባቶች፣ “ተቀብለንሻል” ብለዋታል፡፡ እንደ እርሷ፣ ጥፋታቸውን አምነው የሚመለሱ ሌሎችም ካሉ፣ የይቅርታ ቤት የኾነችው ቤተ ክርስቲያን እጆቿን ዘርግታ እንደምትቀበላቸው አስታውቀዋል፤ የበኩሏን ጥረት እንድታደርግም አበረታተዋታል፡፡
በመጨረሻም፣ ቡራኬ እንድትቀበል የታዘዘችው ምርትነሽ ጥላሁን፣ ከርእሰ መንበሩ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ፊት ወድቃ መስቀል ከተሳለመች በኋላ በይቅርታና ቡራኬ መሰናበቷ ተገልጿል፡፡
በቅርቡም፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤቱ አስተባባሪነት፣ የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ቴሌቪዥንና ጋዜጣ ጨምሮ ለብዙኃን መገናኛዎች መግለጫ እንደምትሰጥ ተጠቁሟል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤው፣ የምርትነሽ ጥላሁንን የይቅርታ ጥያቄ ተቀብሎ ምሕረት ያደረገላትና በቡራኬ ያሰናበታት፣ የተሐድሶ ኑፋቄ ተላላኪ በጋሻው ደሳለኝን አውግዞ ከቤተ ክርስቲያን በለየበት ማግሥት መኾኑ ትኩረት ያሰጠዋል፡፡
ከሕገ ወጥ ቡድኑ ተለይታና የምሕረት ጥሪውን ተቀብላ ለመመለስ ለወሰነችው ምርትነሽ ጥላሁን፣ በዛሬው ዕለት የተደረገላት ሲኖዶሳዊ ይቅርታና አቀባበል፣ ብዙዎች፣ ራሳቸውን ከኑፋቄው ተጽዕኖ ቶሎ በማላቀቅ፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ የሚያበረታታ አብነታዊ እንደ ኾነ አያጠያይቅም፡፡
ምንጭ፦ ሐራ ተዋሕዶ
የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን አባል የ”ሽብር” ክስ ቀረበበት
በጌታቸው ሺፈራው
አዴኃን የአርበኞች ግንቦት 7 ክንፍ ነው ሲል አቃቤ ህግ ክስ አቀረበ
• የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን አባል የ”ሽብር” ክስ ቀርቦበታል
የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ (አዴኃን) የአርበኞች ግንቦት 7 ክንፍ ነው ሲል ክስ አቅርቧል። ዛሬ ጥቅምት 6/2010 ዓ•ም የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል መከላከል አባል በነበረ ግለሰብ ላይ በቀረበው የ”ሽብር” ክስ አዴኃን የአርበኞች ግንቦት 7 ክንፍ ነው በሚል ተጠቅሷል። አቃቤ ህግ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን አባል የነበረው ኮንስታብል ብርሃን በላይ ቸኮል ላይ ባቃረበው ክስ አዴኃንን የአርበኞች ግንቦት ሰባት ክንፍ ከማለቱም ባሻገር የ”ሽብር ቡድን” ሲል በ”ሽብር” ፈርጆታል።
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ በተነበበው ክስ ኮንስታብል ብርሃን አማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም ዞን ጃቢጠና ወረዳ አውንት ጎንቻ ጫካ ውስጥ ከሚንቀሳቀሱት ቄስ ደመቀ ዓለሜ፣ አበባው መኮንን፣ አበራ ምናሉ፣ ልቅናው ምህረት፣ ምትኩ ፀጋዬ፣ ዮናስ ጋሻው እና ደሳለኝ የተባሉ የአዴኃን ታጣቂዎች ጋር አብሮ እንዲሰራ ተልዕኮ ተሰጥቶት ተስማምቷል የሚል ክስ ቀርቦበታል።
በተጨማሪም ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ውስጥ ያሉና የከዱ ጠንካራ አባላትን ለመመልመል ተስማምቷል፣ አባላትን መልምሎ ወደ ኤርትራ ልኳል፣ ባህርዳር አካባቢ ሆኖ ለአዴኃን ለመስራት ተስማምቷል፣ ስለ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽንና አመራሮቹ ጠቃሚ መረጃ ለአዴኃን ሰጥቷል የሚል ዝርዝር ክስ ቀርቦበታል።
አቃቤ ህግ “በኢፌዲሪ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል መከላከል ዘርፍ አባል ሆኖ ሲሰራ ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለመጠበቅ የገባውን ቃል ኪዳን በማፍረስ እራሱን የአርበኞች ግንቦት 7 በማለት በሚጠራው የሽብር ቡድን ክንፍ በሆነው የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ በማለት በሚጠራው የሽብር ቡድን” አባል ነው በሚል ባቀረበው ክስ ኮንስታብል ብርሃንን የአርበኞች ግንቦት 7፣ እንዲሁም የአርበኞች ግንቦት 7 ክንፍ የሆነው አዴኃን አባል ነው የሚል ክስ አቅርቦበታል። አባላትን በመመልመል፣ በማደራጀት፣ ለአዴኃን አባላትና አመራሮች መረጃ በማቀበል ” በሽብርተኛ ድርጅት ውስጥ አባል መሆን በማንኛውም መልኩ በመሳተፍ ወንጀል” ክስ የቀረበበት ኮንስታብል ብርሃን የክስ መቃወሚያ ለማቅረብ ለጥቅምት 29/2010 ቀጠሮ ተሰጥቶታል።
የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ በፀረ ሽብር አዋጁ ከተፈረጁት የፖለቲካ ቡድኖች ውስጥ እንዳልሆነ የሚታወቅ ሲሆን በፀረ ሽብር አዋጁ ባልተፈረጁት የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ (አዴኃን)፣ የጋምቤላ ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ ( ጋህነን)፣ የቤኒሻንጉል ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ቤህነን)፣ የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ትህዴን)፣ የሲዳማ አርነት ንቅናቄ (ሲአን) አባልነት በ”ሽብር”የተከሰሱና የተፈረደባቸው ኢትዮጵያውያን እንዳሉ ይታወቃል።
በአዋጁ በ”ሽብርተኝነት” ያልተፈረጁ ድርጅቶች ከአርበኞች ግንቦት 7 እና ኦነግ ጋር ግንባር ፈጥረዋል፣ አብረው ስራ እየሰሩ ነው እንዲሁም በ”ሽብር” የተፈረጁት ድርጅቶች ክንፍ ናቸው በሚል በድርጅቶቹ ስም ክስ የሚቀርብባቸው ተከሳሾች አቀቤ ህግ የሚያቀርብባቸውን ክስ በሀሰት እና ሆን ተብሎ ለማጥቃት የቀረበ ነው ሲሉ ተደምጠዋል።
የአርበኞች ግንቦት 7 አባል ናችሁ ተብለው ክስ የተመሰረተባቸው በአርባምንጭ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ፍርድ ቤት ቀረቡ
የአርበኞች ግንቦት 7 አባል ናችሁ ተብለው ክስ የተመሰረተባቸው በአርባምንጭ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት እነ ሉሉ መሰለ ዛሬ ጥቅምት 9፣ 2010 ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ችሎት ቀርበው ነበር።
★በመዝገቡ ክስ የተመሰረተባቸው 13 ሰዎች ሲሆኑ በብይን አንዱ ነፃ ሲወጣ (መሃመድ ዳና) 12ቱ እንዲከላከሉ ተበይኖ ነበር።
★ እንዲከላከሉ ከተባሉት ውስጥ 5ቱ (አለም ክንፈ፣ በረከት ተገኔ፣ ደረጄ አደመ፣ ሲሳይ አምባው እና አጥናፉ አበራ) አንከላከልም በማለታቸው መጋቢት 29 ቀን 2009 አራት አመት ከአምስት ወር ተፈርዶባቸዋል።
★እንከላከላለን ያሉት የተቀሩት ሰባቱ (ሉሉ መሰለ፣ አየለች አበበ፣ በጋሻው ዱንጋ፣ ዘኪዎስ ዘሪሁን፣ ጌታሁን ቃፃ፣ መርዶኪዮስ ሽብሩ እና ያረጋል ሙሉአለም) በግንቦት ወር 2009 ውስጥ መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰምተው አጨርሰዋል።
★በባለፈው አመት በተደጋጋሚ ለፍርድ ተቀጥረው የነበረ ቢሆንም የምስክሮች ቃል አልተገለበጠም እየተባለ ተለዋጭ ቀጠሮ ሲሰጣቸው የነበረ ሲሆን የዛሬውም ቀጠሮ ፍርዱን ለማሳወቅ ነበር።
★ሆኖም ዳኞች ፍርዱን ሰርተው እንዳልጨረሱ በመግለፅ “ለጥቅምት 28 ለማድረስ እንሞክራለን” ብለዋል።
★ በተደጋጋሚ በሚሰጠው ቀጠሮ የተማረሩት ተከሳሾቹን በመወከል 1ኛ ተከሳሽ ሉሉ መሰለ ይህን ብለዋል። “2008 የተከፈተ መዝገብ ነው። ባለፈው አመት ግንቦት ላይ ነው መከለከያ ምስክር አሰምተን የጨረስነው። ከኛ በኋላ መከላከያ ምስክር ያሰሙ ፍርድ ተሰርቶላቸዋል። የኛ በምን ምክንያት እንደዘገየ አላቅም። ቤተሰቦቻችን ከ500 ኪሜ ርቀት ነው ሚጠይቁን። እየተንገላቱ ነው። ጠያቂም የለንም።”
★እነ ሉሉ መሰለ በጥቅምት ወር 2008 በፖሊስ ተይዘው ማእከላዊ 4ት ወር ቆይተው የካቲት ወር 2008 ላይ ነው ክስ የተመሰረተባቸው።
ምንጭ፦ የፍርድ ቤት ውሎዎች
የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ
በጌታቸው ሺፈራው
የአቶ በቀለ ገርባ የይግባኝ ክርክር ተሰማ
“ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” አቃቤ ህግ
የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝ አቃቤ ህጉ “ፊልድ ወጥቷል” በሚል ሰበብ ሳይሰማ ቀርቷል
ፎቶ፦ አቶ በቀለ ገርባ
ተከሰውበት ከነበረው የ”ሽብር ክስ” በብይን ወደ መደበኛ ወንጀል ህግ ተቀይሮላቸው ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የዋስትና ጥያቄ አቅርበው ውድቅ የተደረገባቸው የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ የዋስትና ይግባኝ ክርክር ዛሬ ጥቅምት 9/2010 በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተሰምቷል።
የአቶ በቀለ ገርባ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን በአቶ በቀለ የተጠቀሰው አንቀፅ በመርህ ደረጃ ዋስትና እንደማያስከለክል፣ የእስር ፍርድ ቤቱም አቶ በቀለ በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ስለነበር በእነዚህ አካላት በኩል ወደ ውጭ ይወጣሉ እንዲሁም የዋስ መብት ተፈቅዶላቸው ቢፈቱ ግዴታቸውን አክብረው ላይቀርቡ ይችላሉ በሚል አቃቤ ህግ ባቀረባቸው ነጥቦች የዋስትና መብታቸውን መከልከሉ ትክክል እንዳልሆነ በመግለፅ ክርክራቸውን በዝርዝር አቅርበዋል።
አቶ አምሃ አቃቤ ህግ ለዋስትና መከልከያነት ያቀረበው መቃወሚያ እና የእስር ፍርድ ቤቱም ዋስትና የከለከለበት ጉዳይ የሽብር ክሱ በብይን ሲወድቅ የወደቀ መሆኑንም አስረድተዋል። በውጭ ከሚገኙ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ጋር ግንኙነት ያደርጉ ነበር የተባለውም በብይን በውጭ ከሚገኙ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ማድረግ ወንጀል አይደለም ተብሎ እንደተበየነ አስረድተዋል። በመሆኑም ወንጀል ያልሆነ ነገር መሰረታዊ የዜጎች መብት የሆነውን የዋስትና መብት ሊያስከለክል አይገባም ሲሉ ክርክራቸውን አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ካቀረበው ነጥብ ውጭ የዋስትና መከልከያ ነጥብ ሳያገኝ የዋስትና መብት የከለከለ ከመሆኑም ባሻገር አቶ በቀለ ዋስትና የተከለከሉበት ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ በመጥቀስ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ጠይቀዋል።
አቃቤ ህግ በበኩሉ አቶ በቀለ የሽብር ክሱ ውድቅ ሳይደረግ ዋስትና ተከልክለው ስለነበር የእስር ፍርድ ቤቱ ለሁለተኛ ጊዜ የዋስትና መብት ሊያይ አይገባውም ብሎ ለልደታ ፍርድ ቤት አቅርቦት የነበረውን መቃወሚያ በማስታወስ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ክርክሩን እንዲያግደው ጠይቋል። ” ፍርድ ቤቱ ወደ ክርክር መግባቱ አግባብ አይደለም” ሲልም ተቃውሞ አቅርቧል። ይሁንና ፍርድ ቤቱ ክርክሩን እንዲቀጥል ከወሰነ በሚል ከአሁን ቀደም ለእስር ፍርድ ቤት ያቀረባቸውን የዋስትና መቃወሚያዎች ደግሞ አቅርቧል። አቶ በቀለ ይከላከሉ የተባሉበት ወንጀል ከባድና እስከ 10 አመት የሚያስቀጣ ነው በሚል የእስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲፀና ጠይቋል።
አቶ አምሃ በበኩላቸው እነሱ በጠየቁት ይግባኝ አቃቤ ህግ ” ክርክሩ መደረግ የለበትም!” ብሎ ተቃውሞ ማቅረብ እንደማይችል፣ እስከ 10 አመት ያስፈርዳል የሚባለው በተጠቀሰው ወንጀል ከፍተኛ ጉዳት ሲደርስ መሆኑን፣ አቶ በቀለ ይከላከሉ ተባለ እንጅ ጥፋተኛ እንዳልተባሉ በመግለፅ የደንበኛቸው የዋስትና መብት እንዲከበር ለአቃቤ ህግ መቃወሚያ በሰጡት መልስ አስረድተዋል። የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክርክሩን መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለጥቅምት 20/ 2010 ዓም ቀጠሮ ሰጥቷል።
በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት የነበረው እና 6 አመት ከ6 ወር የተፈረደበት የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ይግባኝም ዛሬ ጥቅምት 9/2010 ቀጠሮ ተይዞለት የነበር ቢሆንም ለአቶ በቀለ ገርባ ክርክር መልስ የሰጠው አቃቤ ህግ “ለዮናታን ጉዳይ መልስ የሚሰጠው አቃቤ ህግ ፊልድ ወጥቷል። ፍርድ ቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን” የሚል ጥያቄ አቅርቧል። የአቶ ዮናታን ተስፋዬ ጠበቃ “መልስ መስጠት ያለበት ተቋም እንጅ ግለሰብ አይደለም” ሲሉ በአቃቤ ህግ በኩል የቀረበውን ምክንያት አሳማኝ እንዳልሆነ አስረድተዋል። ፍርድ ቤቱም እንዲህ አይነት አሳማኝ ያልሆነ ምክንያት መቅረብ እንደሌለበት ገልፆ ለጥቅምት 24/2010 ቀጠሮ ሰጥቷል።