በሽብር የተከሰሰው ወጣት ህክምና ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ
በጌታቸው ሺፈራው
• ‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል!›› 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ
• ‹‹ይህን የሚያደርገው መንግስት ከሆነ ቁርጡን አውቀነው እንሞታለን!›› 4ተኛ ተከሳሽ ይማም መሃመድ

አቶ አየለ በየነ
በእነ መልካሙ ክንፈ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሶ ቂሊንጦ እስር ቤት ታስሮ የነበረው ወጣት አየለ በየነ ነገሰ ህክምና እንዳያገኝ ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ፡፡ ወጣት አየለ በየነ ህክምና ተከልክሎ ለሞት እንደተዳረገ በአባሪነት የተከሱት ዛሬ ሀምሌ 18/2009 ዓ.ም ለከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4 ወንጀል ችሎት ገልፀዋል፡፡
ተከሳሾቹ የፀረ ሽብር አዋጁ ከሚፈቅደው አራት ወር በተጨማሪ 5 ወር በአጠቃላይ 9 ወራትን ማዕከላዊ ታስረው እንደቆዩ የተገለፀ ሲሆን ሟች ለረዥም ጊዜ ታሞ ህክምና ቢጠይቅም ህክምና ሳይገኝ ቀርቷል ተብሏል፡፡ ህመሙ ከጠናበት በኋላም ከ10 ቀን በላይ ምግብ መብላት ባለመቻሉ ለእስር ቤቱ አስተዳደሮች በቀን ከሶስት ጊዜ ባላይ ህክምና እንዲያገኝ ጥያቄ ቢያቀርቡም መልስ ሳያገኙ መቅረታቸውንና በመጨረሻ ከእስር ቤቱ ውጭ እንዲታከም ቢታዘዝለትም በተቋሙ ቶሎ ህክምና ማግኘት ባለመቻሉ ህይወቱ ማለፉን ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡
ቀሪዎቹ ተከሳሾችም ህክምና ሊያገኙ ባለመቻላቸው ለህይወታቸው እንደሚሰጉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታቸው አሰምተዋል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ ታሞ በየወሩ ህክምና እየወሰደ የነበር ቢሆንም መርማሪዎች የፈለጉትን መረጃ ስላልስጠ ህክምና መከልከሉንና የሟች እጣፈንታ ሊደርስበት እንደሚችል ስጋቱን ለፍርድ ቤት ገልፆአል፡፡ ‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል፡፡›› ያለው 1ኛ ተከሳሽ ንፁህ በመሆናቸውና መረጃ ስላልተገኘባቸው ህጉ ከሚፈቅደው ውጭ ለ9 ወራት ማዕከላዊ መቆየታቸው ይህም ለንፁህነታቸው ማስረጃ እንደሆነ ገልፆአል፡፡ ማች ንፁህ በመሆኑም ክሱ እንዳይቋረጥ፣ ምስክሮችም ተሰምተው የፍርዱን ሂደት ማወቅ እንደሚፈልጉ ገልጾአል፡፡
ሌሎች ተከሳሾም ተመሳሳይ ችግር እንደገጠማቸው የተገለፀ ሲሆን 4ኛ ተከሳሽ ይማም መሃመድ ‹‹ይህን የሚያደርገው መንግስት ከሆነ ቁርጡን አውቀነው እንሞታለን›› ሲል ገልፆአል፡፡ ‹‹አየለን ሞተ ማለት አልችልም፡፡ ተቀጠፈ ነው የምለው፡፡ የሞተው ዘመድ አጥቶ አይደለም፡፡ ጓደኛና ቤተሰብ አጥቶ አይደለም፡፡ የሞተው ህክምና የሚሰጠው አጥቶ ነው›› ሲልም አክሏል፡፡
ባለፉት ቀጠሮዎች ሟችን ፍርድ ቤት ሳያቀርብ የቀረውን ቂሊንጦ እስር ቤት ፍርድ ቤቱ ተከሳሹን የማያቀርብበትን ምክንያት እንዲገልፅ ወይንም ተከሳሹን እንዲያቀርብ በጻፈለት ትዕዛዝ መሰረት ሀምሌ 17/2009 ዓ.ም ተከሳሽ መሞቱን ቢገልጽም በምን ምክንያት እንደሞተ እንዳልገለፀ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ቂሊንጦ ሟች በምን እንደሞተና ለሞቱ ማረጋገጫ ባልላከበት ሁኔታ ግለሰቡ መሞቱን እርግጠኛ መሆን ስለማይቻል እስር ቤቱ ለሀምሌ 26/2009 ዓ.ም ተከሳሹ ስለመሞቱ የሚያሳይ ማረጋገጫና የሞተበትን ምክንያት እንዲያመጣ ሲል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
አየለ በየነ በመዝገቡ ስር 2ኛ ተከሳሽ የነበር ሲሆን ከኦነግ መሪ ዳውድ ኢብሳ ጋር ግንኙነት በመፍጠር እና ሀገር ውስጥ ያሉ መረጃዎችን ሪፖርት አድርጓል የሚል ክስ ቀርቦበት ነበር፡፡ የሟች ታናሽ ወንድም ቦንሳ በየነም በዚሁ ክስ መዝገብ ስር ክስ ተመስርቶበታል፡፡ በመዝገቡ ስር፡-
1.መልካሙ ክንፉ ተፈሪ
2. አየለ በየነ ነገሰ
3. ቦንሳ በየነ ነገሰ
4. ይማም መሃመድ ኬሮ
5. ለሜሳ ግዛቸው አባተ
6. ኩመራ ጥላሁን ዴሬሳ
7. መያድ አያና አቶምሳ
8. ሙሉና ዳርጌ ሩዳ የተከሰሱ ሲሆን ተመሳሳይ ችግር እየደረሰባቸው እንደሆነ ተገልፆአል፡፡
በኢትዮጵያ ወቅታዊ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ
1. የመሬት መብት ተሟጋቹ ኦሞት አግዋ ቀሪ መከላከያ ምስክራቸውን ያሰሙት ባሳለፍነው ሰኔ ወር ነበር፡፡
የመሬትና አካባቢ ጥበቃ አክቲቪስት ኦሞት አግዋ ሰኔ 05 ቀን 2009 ዓ.ም ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው ቀሪ ሁለት የመከላከያ ምስክሮችን አስደምጠዋል፡፡ ምስክሮቹ በእስር ላይ የሚገኙት የቀድሞው የጋመቤላ ክልል ፕሬዝዳንት ኦኬሎ አኳይ እና አቶ ሳምሶን አባተ የተባሉ ምስክር ናቸው፡፡
ምስክሮቹ በዋናነት ኦሞት አግዋን የሚያቋቸው በ1996 ዓ.ም ጋምቤላ ክልል በተነሳ ግጭት በክልሉ መንግስት በተቋቋመ የሰላም ኮሚቴ ውስጥ አባል ሆነው ግጭቱን ለማብረድና ግጭቱን በመሸሽ የተሰደዱ ዜጎችን ለማስመለስ መልካም ስራ መስራታቸውንና ተከሳሹ “የጋምቤላ ሰለምና ልማት ጉባኤ” የሚባል ምግባረ ሰናይ ድርጅትም መስርተው ሲሰሩ እንደሚያውቁ አስረድተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ቀሪ ሦስት የተከሳሽ መከላከያ ምስክሮችን ከዝዋይ እና ሸዋ ሮቢት የፌደራል እስር ቤቶች ሲቀርቡ ለመስማት በሚል ለሐምሌ 20 ቀን 2009 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
2. የኦፌኮ አባላትና አመራሮች እነ ጉርሜሳ አያና ላይ ይሰጣል የተባለው ብይን አሁንም በቀጠሮ መጓተቱ ቀጥሏል
የሽብር ክስ በቀረበባቸው የኦፌኮ አመራሮችና አባላት እነ ጉርሜሳ አያኖ (በቀለ ገርባ) መዝገብ ላይ ሰኔ 9 ቀን 2009 ዓ.ም ብይን ለማሰማት የመጨረሻ ቀጠሮ ተሰጥቶ የነበር ቢሆንም ብይኑ ‹‹ተሰርቶ አላለቀም›› በሚል ሌላ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
ለብይን በሚል ቀጠሮ እየተሰጠባቸው አራት ወራት ያህል ያስቆጠሩት እነ ጉርሜሳ አያኖ (22 ሰዎች)፣ ብይኑን ትሰማላችሁ ተብለው ለሰኔ 15 ቀን 2009 ቀጠሮ ቢሰጣቸውም በዕለቱ ቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ተከሳሾቹን ፍርድ ቤት ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ እንደገና ተከሳሾች ባልቀረቡበት ሁኔታ ለሐምሌ 06 ቀን 2009 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
3. በእነ ንግስት ይርጋ መዝገብ የአቃቤ ህግ ምስክሮች ባለመቅረባቸው ተከሳሾች በቀጠሮ እየተጉላሉ ነው
በአክቲቪስት ንግስት ይርጋ የክስ መዝገብ በሽብር የተከሰሱት ተከሳች ላይ አቃቤ ህግ አሉኝ የሚላቸውን ምስክሮች ባለማቅረቡ በተደጋጋሚ ቀጠሮ ተከሳሾች መጉላላት ላይ ይገኛሉ፡፡ ሰኔ 20 ቀን 2009 ዓ.ም ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ችሎት ቀርበው የነበሩት ተከሳሾች ምስክር ሳይሰማባቸው እንደገና ምስክር ለመጠባበቅ ለሐምሌ 11 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ተከሳሾች በተደጋጋሚ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ መሰጠቱን በመቃወም አቤቱታ አሰምተዋል፡፡ በዚህም 5ኛ ተከሳሽ የሆነው በላይነህ አለምነህ “እኛ የታሰርነው እና ድርጊቱ ተፈፀመ የተባልነው ባህርዳርና ጎንደር ቢሆንም ምስክር እየተጠበቀ ያለው ግን ከአዲስ አበባ ነው፡፡ ይህ እንዴት ይሆናል? በባለፈው ቀጠሮ ምስክር ረጅም ቀጠሮ እየተሰጠን ያለው አቃቤ ህግ ምስክሮችን እስኪያሰለጥን ድረስ ነው ወይ ብለን አስተያየት ሰጥተን ነበር፡፡ ፍርድ ቤት አቃቤህ ግን ማዘዝ ከቻለ ለምንድነው ሃይ የማይለው?” ሲል ተናግሯል፡፡
4. ዶ/ር መረራ ጉዲና ያቀረቡት የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል
*የምስክሮች ማንነት ይገለጽ በሚለው መቃወሚያ ላይ ብቻ ብይኑ አልተሰራም፤ ጉዳዩ ለህገ-መንገስታዊ ትርጉም ለፌደሬሽን ምክር ቤት ተልኳል ተብሏል፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ ሦስት የተለያዩ ክሶች የቀረቡባቸው የኦፌኮ ፕሬዚደንት ዶ/ር መረራ ጉዲና በቀረቡባቸው ክሶች ላይ ያቀረቡት የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያዎች አብዛኞቹ ውድቅ ሲደረጉ አንዱ ብቻ ለህገ-መንግስታዊ ትርጉም ለፌደሬሽን ምክር ቤት መላኩን ሰኔ 30 ቀን 2009 ዓ.ም ጉዳዩን ለማየት የተሰየመው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት አስታውቋል፡፡
ዶ/ር መረራ መቃወሚያቸው ውድቅ መደረጉን ከችሎቱ ከሰሙ በኋል፣ ‹‹የተከሰስሁት ፖለቲካዊ ክስ ነው፡፡ እኔ የተከሰስሁት ለኦሮሞ ህዝብ፣ ለኢትዮጵያ ህዝቦች በመከራከሬ ነው፡፡ ይህንን እናንተ ዳኞችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብም ያውቃል፡፡ እኔ የተከሰስሁት በሀገራችን ሀቀኛ ፌደራላዊ ስርዓትና ፍትህ እንዲሰፍን በመከራከሬ ነው›› ሲሉ አስተያየታቸውን አሰምተዋል፡፡
ችሎቱ የፌደሬሽን ምክር ቤት የተላከለትን የትርጉም ስራ ሰርቶ መላኩን ለመጠባበቅ በሚል ለሐምሌ 25 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
5. ጋዜጠኞችና አርቲስቶች ሙዚቃና ግጥሞችን ዩ ቲ ዩብ ላይ ጭነዋል በሚል የሽብር ክስ ቀርቦባቸዋል
ሁከትና አመጽ የሚያስነሱ ዜና፣ ግጥምና ሙዚቃ በማዘጋጀት ዩ ቲ ዩብ ላይ እንዲጫን አድርገዋል በሚል ሰባት ሰዎች የሽብር ክስ የቀረበባቸው ባሳለፍነው ሰኔ ወር ነበር፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ ክሱ የተመሰረተባቸው ተከሳሾች ኦሊያድ በቀለ፣ ኢፋ ገመቹ፣ ሞይቡሊ ምስጋኑ፣ ቀነኒ ታምሩ፣ ሃይሉ ነጮ፣ ሴና ሰለሞን እና ኤልያስ ክፍሉ ናቸው፡፡ አቃቤ ህግ ተከሳሾችን የጸረ-ሽብር አዋጁን አንቀጽ 4 መተላለፍ ክስ ያቀረበባቸው ሲሆን፣ ተከሳሾቹ ሰኔ 23 ቀን 2009 በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19 ወንጀል ችሎት ቀርበው ክሱ ተነቦላቸዋል፡፡
6. ሁለት ጋዜጠኞች የእስር ጊዜያቸውን ጨርሰው ባሳለፍነው ሰኔ ወር ከእስር ተፈተዋል
የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እና የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ አዘጋጅና ባለቤት ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የተበየነባቸውን የእስር ቅጣት አጠናቀው ከእስር ተፈተዋል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው አመጽ በማነሳሳት ጥፋተኛ ተብሎ የተበየነበትን የአንድ አመት ከስድስት ወር እስሩን ጨርሶ ከቃሊቲ እስር ቤት የተፈታው ሰኔ 16 ቀን 2009 ዓ.ም ሲሆን፣ በስም ማጥፋት ክስ የአንድ አመት እስር ተበይኖበት የነበረው ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ደግሞ በአመክሮ ከሸዋሮቢት እስር ቤት የተፈታው ባሳለፍነው ሳምንት ነው፡፡
ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት
የዶ/ር መረራ ጉዳይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ትርጉም እንዲሰጥበት ትእዛዝ ተሰጠ
የእነ ዶ/ር መረራ ጉዲና መዝገብ ለዛሬ የተቀጠረው ከዚህ ቀደም በቀረበው መቃወሚያ ላይ ብይን ለመስጠት ነበር። በመሆኑም ዛሬ – ሰኔ 30/2009 – ዶ/ር መረራ ጉዲና በተመሰረተባቸው 3ት ክሶች ላይ ያቀረቧቸው መቃወሚያዎች ላይ 19ኛው ወንጀል ችሎት ከፊል ብይን ሰጥቶበታል። ችሎቱ፣ ዶ/ሩ ያቀረቡትን ክሱ እንዳይንጓተት ከሌሎቹ በሌሉበት ከተከሰሱት ሶስት ተከሳሾች ይነጠልልኝ የሚለውን መቃወሚያ ጨምሮ ሌሎቹን መቃወሚያዎች በሙሉ ውድቅ ሲያደርግ አንዱን ግን ለትርጉም ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ለትርጉም መላኩን ተናግሯል።

ዶ/ር መረራ ጉዲና
በእነዶ/ር መረራ መዝገብ የተከፈተው ክስ ላይ አቃቤ ህግ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን በመጥቀስ፣ የምስክሮች ሥም ሳይጠቀስ የቀረ ሲሆን፣ ይህ በሥራ ላይ ያለው የሥነ ስርዓት ሕግ ተከሳሾች የሚቀርብባቸውን ማስረጃ እና ምስክር የማወቅ መብት አላቸው ከሚለው ጋር የሚጋጭ በመሆኑ እንዲተረጎም ወደፌዴሬሽን ምክር ቤት ተልኳል። የተከሳሹ ጠበቃ አቶ ወንድሙ ኢብሳ በበኩላቸው “እኛ የጠየቅነው፣ ደንበኛችን ባልተከሰሱበት የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ የምስክር ጥበቃው አንቀፅ ሊጠቀስባቸው አይገባም ብለን እንጂ ትርጉም ያስፈልጋል ብለን አይደለም” ብለው ቅሬታቸውን አቅርበዋል።
ዶ/ር መረራም መልእክት አለኝ በማለት የሚከተለውን ለዳኞች ተናግረዋል፣ “የተመሰረተብኝ ፖለቲካዊ ክስ ነው። መንግስት ይዞ የተነሳው ተቃዋሚዎችን በራሱ የተበላሸ አስተዳደር ጥፋት ጉዳይ መወንጀል ስለሆነ እንጂ መንግሥት የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ በጠየቀበት ጉዳይ ነው የተከሰስኩት። የተከሰስኩት፣ ለኦሮሞ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለኢትዮጵያ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለእኩልነት እና ሁላችንንም እኩል ለሚመለከት ስርዓት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ሀቀኛ የፍትህ ስርዓትና የፌዴራል ስርዓት እንዲኖር በመታገሌ ነው። ዳኞች እስካሁን ካላነበባችሁ፣ የአቤ ጉበኛን አልወለድም እና የበአሉ ግርማን ኦሮማይ አንብቡ። ሊወድቅ እየደረሰ መንግስት የሚሰራውን ሥራ የሚያስረዱ መፅሃፍት ናቸው።”
ዳኞች መዝገቡን ለሐምሌ 25/ 2009 የተቀጠሩ ሲሆን፤ በሚቀጥለው ቀጠሮ ችሎቱ የምስክሮች ዝርዝር መገለፅ አለበት በሚል ክሱ እንዲሻሻል ወይም የለበትም በሚል የቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ይይዛል ተብሎ ይጠበቃል።
EHRP
እነ ኦሞት አግዋ ካቀረቡት አሰራ አንድ የከስ መቃወሚያ አስሩን ፍርደቤቱ ውድቅ አደረገው
ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያ አቃቤህግ ከሰጠው ምላሽ ጋር መርምሮ ምላሽ ለመስጠት ለዛሬ ጥር 2 ቀን 2008 ዓ.ም የቀጠረው ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያዎች ከአንዱ በሰተቀር ሁሉንም አለመቀበሉን እና ውድቅ ማድረጉን የመሃል ዳኛው ታረቀኝ አማረ በንባብ ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡

እነ አቶ ኦሞት አግዋ አዲስ አበባ በሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ታስረው ሲቀርቡ
በፍርድ ቤቱ ከአንድ መቃወሚያ በሰተቀር መቃወሚያዎቹ ውድቅ እንዲሆኑ እና ተቀባይነት እንዳያገኙ ምክኒያት የሆነው አቃቤ ህግ በማስረጃ ማሰማት ሂደት ላይ በዝርዝር እንድንሰማቸው ያደረጋል የሚል ነው፡፡
ተከሳሾች ክሳችን በእያንዳዳችን በተናጠል ቀርቦብን ሳለ አቃቤ ህግ በጋራ የከሰሰን ክስ ተነጣጥሎ ለየብቻ እንድንከሰስ ይደረግ የሚለውን የተከሳሾች መቃወሚያ ፍርድ ቤቱ የወንጀል ህጉን አንቀፅ 211 ቁጥር 7/3 በመጥቀስ ወንጀሎቹ የተለያዩ ቢሆንም የጋምቤላ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋሕነን) የጠራው ስብሰባ ላይ ኬንያ ፣ናይሮቢ ለመሳተፍ ሲሄዱ በቁጥጥር ስር የዋሉ መሆናቸውን ጠቅሶ ተከሳሾቹ በአንድ መዝገብ ሊከሰሱ ይችላሉ በማለት ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን መቃወሚያ አልተቀበለም፡፡
ተከሳሾች አባል ሆነውበታል በሚል የተጠቀሰው የጋምቤላ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋሕነን) ቡድን ህልውና እንዳለው አቃቤ ህግ በክሱ እንዲያስርዳ በተቃውሞቸው የጠየቁት ተከሳሾች፣ ቡድኑ በፍርድ ቤትም ሽብርተኛ ተበሎ አለመሰየሙን ጠቅሰው ከክሱ ላይ እንዲሰረዘላቸው ላቀረቡት መቃወሚያ ፍርድቤቱ የቡድኑን ህልውና እና ዝርዝር ማሰረጃ በክሱ ሂደት የሚሰሙ ናቸው በማለት ተቃውሞውን አለተቀበለም፡፡
በኢሜል አና በስካይፒ የተለያዩ ግንኙነቶችን ፈጥረዋል ብሎ አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ያሰቀመጠውን ተከሳሾች ከማን ጋር ግንኙነት እንዳደርጉ ሰላልጠቀሰ በክሱ ከማን ጋር ግንኙነት እንደነበራቸው በዝርዝር እንዲጠቀስ በክስ ተቃወሞው ላይ ያቀረቡትንም ተቃውሞ እንድሌሎቹ የክስ መቃወሚያዎች በተመሳሳይ ፍርድ ቤቱ የክሱ መሰረታዊ ስህተት አይደለም፣በማሰረጃ ማሰማት ሂደት ላይ እምንሰማቸው ዝርዝሮች ናቸው በማለት ተቃውሞውን ውድቅ አድርጓል፡፡
በመጨረሻም ተከሳሾች ካቀረቡት አስራ አንድ መቃወሚያዎች ፍርድቤቱ የተቀበለው በክሱ ላይ አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ አሰቀጠራቸው የተባሉት የፖሊስ አባላት ስም ዝርዝር በክሱ ተካቶ ይቅረብልን በለው ያቀርቡትን ተቃውሞ ሲሆን ፍርድቤቱ አቃቤህግ ለጥር 17 ቀን 2008 ዓ.ም. በክሱ ላይ የተጠቀሱትን የፖሊስ አባላት ስም ዝርዝር በክሱ አካቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥል፡፡
EHRP
ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ የይግባኙን ጉዳይ በተመለከተ ለሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታ አቀረበ
የቀድሞው የአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በ2003ዓ.ም. ሰኔ ወር ላይ ከሌሎች 4 ሰዎች ጋር (ጋዜጠኛ ኤልያስ ክፍሌ፣ ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ፣ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሄር እና ወ/ሮ ሂሩት ክፍሌ) የፀረ ሽብርተኝነት ህጉን ተላልፈሃል ተብሎ ክስ ተመስርቶበት የነበረ ሲሆን፤በዚህም የ14 አመት የእስር ቅጣት እንደተወሰነበት የሚታወስ ነው።

ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ
ቅጣቱ ከተላለፈበት በኋላ ጥፋተኛ መባሉን በመቃወም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ቢልም መዝገቡ በይቅርታ ጉዳይ እየታየ መሆኑ ተገልፆለት በወቅቱ ይግባኝ ማለት ሳይችል ቀርቷል። ከእርሱ ጋር የይቅርታ ጥያቄ ያቀረቡ የስዊድን ጋዜጠኞች እና በተመሳሳይ መዝገብ የምትገኘው ሂሩት ክፍሌ ከእስር የተለቀቁ ሲሆን፤ የጋዜጠኛ ውብሸት የይቅርታ ጉዳይ ግን እስካሁን ድረስ ተፈፃሚ አልሆነም።
በመሆኑም በቅርቡ በወንጀለኛ መቅጫ ስነስረዓት ህጉ አንቀፅ 191 ስር በተመለከተው መሰረት የይግባኝ ጊዜ ካለፈ በኋላ ይግባኝ ለማቅረብ ፈቃድ ለማግኘት የሚቀርብ ማመልከቻ በማስገባት ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኙን አቅርቦ ነበር። የወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህጉ አንቀፅ 196 (1) እና (2)፤ የተፈረደባቸው ብዙ ሰዎች ሆነው አንዱ ብቻ ይግባኝ ያቀረበ እና የተጠቀመ [ከእርሱ ጋር አብራ የተከሰሰችው ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ከጋዜጠኛ ውብሸት ጋር ተመሳሳይ የቀረበባት እነወዲሁም የስር ፍርድ ቤት 14 ዓመት ከፈረደባት በኋላ በይግባኝ ወደ 5 አመት እንደተቀነሰላት ይታወቃል።] እንደሆነ ሌሎቹም ይግባኝ እንዳሉ እንደሚቆጠር እንደሚደነግግ በመጥቀስ ነው ይግባኙን ያቀረበው። ይግባኙን የተመለከተው ይግባኝ ሰሚ ችሎት የይግባኙን አቤቱታ ሳይቀበለው ውድቅ አድርጎበታል። ጋዜጠኛ ውብሸትም ይግባኝ ሰሚ ችሎት መሰረታዊ የህግ ስህተት በመጣስ ይግባኙን እንዳልተቀበለው በመግለፅ ያቀረበው አቤቱታ ዛሬ ሰበር ሰሚ ችሎት ቀርቦ ነበር። ዳኞች ጉዳዩን መርምረው ብይኑን ሰኔ 12 ቀን 2009 ዓ ም ቀን እንደሚያደርሱ እና ውሳኔውን ከመዝገብ ቤት ከማግኘት እንደሚቻል ተናግረዋል።
ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በ2007 ዓ. ም. “የነፃነት ድምፆች” እና “ሞጋች እውነቶች” የተሰኙ መፅሐፍት ለንባብ ያበቃ ሲሆን በመጪው ሰኞ ሰኔ 12/2009 ቀን ከታሰረ 6ዓመት ይሞላዋል።
EHRP