በሞያሌ 10 ያህል ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተገደሉ
(ዳጉ ሚዲያ)ትናንት ቅዳሜ መጋቢት 1 ቀን 2010 ዓ.ም በደቡብ ኢትዮጵያ፥ቦረና ዞን የሞያሌ ከተማ በገዥው መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት የፀጥታ አባላት 10 ሰላማዊ ዜጎች ሲገደሉ 11 ያህሉ መቁሰላቸውን የዓይን እማኞችን እና የከተማውን ከንቲባ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል።
ግድያውን በተመለከተ በአስቸኳይ አዋጁ መሰረት የመላ ሀገሪቱን አጠቃላይ የጠጥታ እና የተፈጥሮ ሃብትን በበላይነት እየተቆጣጠረ ያለው የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያት በበኩሉ በተፈጠረ የመረጃ ስህተት ምክንያት 9 ሰላማዊ ዜጎች በስሩ ባሉ የፀጥታ ኃይሎች 9 ሰላምዊ ዜጎች መገደላቸውን እና 12 ያህል መቁሰላቸውን አስታውቋል።
ግድያው የተፈፀመው በከተማው በተለምዶ ሸዋበር በሚባል ሰፈር ሲሆን፤ በወቅቱ በአካባቢው ምንም ዓይነት ህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ባልነበረበትና ዜጎች በተለመደ ሰላማዊ መደበኛ ዕለታዊ እንቅስቃሴ እያሉ ግድያው በጅምላ መፈፀሙን የከተማው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በተለይ ጥቃቱ በሚፈፀምበት ወቅት በመዝናኛ ስፍራ የነበሩ፥ በምግብ ቤትና በሱቅ ግብይት ላይ የነበሩና መንገድ ላይ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል።
በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ ም የታወጀው እና ለ6 ወራት የሚቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ክልል ባሉ የተለያዩ ከተሞች በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በኮማንድ ፖስቱ የፀጥታ አባላት መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ የሞያሌው የጅምላ ግድያ ተጨማሪ ጥቃት መሆኑ ታውቋል። የጅምላ ጥቃቱን ተከትሎም በርካታ የከተማው ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሀገር ኬንያ ተሰደዋል።
ቀደም ሲል የመብት ተሟጋች ኢትዮጵያውያን፥ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፥ ዓለም አቀፍ ይሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት፥ የአሜሪካ መንግሥትና የአውሮፓ ህብረት አባላት እና የገዥው መንግሥት አካል የሆኑ በርካታ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተግባራዊ እንዳይደረግ ተቃውመውት እንደነበር አይዘነጋም። ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየተፈፀመ ያለው ግድያ እና እስር ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል።
በኢትዮጵያ የፖለቲካ ውጥረት ተባብሷል፤ መንግሥት በሰላማዊ ዜጎች ላይ እወሰደ ያለው የኃይል ርምጃም ቀጥሏል
(ዳጉ ሚዲያ) የኢትዮጵያ መንግሥት ሀገሪቱን በመደበኛው ህግ ስርዓት ፀጥታ መጠበቅም ሆነ ማስጠበቅ አልቻልኩም በማለት ከባለፈው የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ ም ጀምሮ ለ6 ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ህግ ተግባራዊ አድርጓል። ይሁን እንጂ አርብ የካቲት 23 ቀን 2010 ዓ ም በተደረገው ድንገተኛ የአስችኳይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ አዋጁ በአወዛጋቢ ሁኔታ መፅደቁን ፓርላማው አስታውቋል።
አፈ ጉባዔው አቶ አባዱላ ገመዳ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይፋ እንዳደረጉት ከሆነ 547 መቀመጫ ካሉት የፓርላማው አባላት መካከል 8ቱ በህይወት እንደሌሉ በመግለፅ፤ ቀሪዎቹ “539” የፓርላማ አባላት እንዳሉ አስታውቀዋል። ከነዚህ ውስጥ አዋጁ በህገ መንግሥቱ ድንጋጌ መሰረት እንዲፀድቅ ከፓርላማው 2/3 ኛ ድምፅ ድጋፍ ማግኘት እንዳለበት በመጠቆም፥ አዋጁን ለማፅደቅ 2/3ኛ ድምፅ 339 ድምፅ ብቻ እንደሚያስፈልግ፥ የተሰጠው የድጋፍ ድምፅ ግን 346 እንደሆነና ይህም ከሚጠበቀው በላይ ድምፅ ድጋፍ እንደተገኘ፥ በ88 ተቃውሞ እና በ7 ድምፀ ተዓቅቦ አዋጁ መፅደቁን አስታውቀው ነበር። ይሁን እንጂ አፈ ጉባዔው በርካታ የተሳሳቱ መረጃዎችን ለፓርላማ አባላቱና ለህዝቡ እንደገለፁ በዕለቱ የወጡ መረጃዎች አመልክተዋል።
በአፈ ጉባዔው ከተላለፉአት የሐሰት መረጃዎች መካከል በዕለቱ በፓርላማ የተገኙ አባላት ቁጥር 539 ሳይሆን 441 እንደሆነ የፓርላማው ህዝብ ግንኙነት ክፍል ወዲያውኑ በድህረ ገፁ በሰጠው እርማት ያጋለጠ ሲሆን፤ በዕለቱ የኦህዴድ/ኢህአዴግ ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር አብይ አህመድን ጨምሮ በርካታ የፓርላማ አባላት በዕለቱ ያልተገኙ እንደነበር፥ ከፓርላማው 2/3ኛ ድምፅ ለማግኘት ቢያንስ 365 ድምፅ ድጋፍ ማግኘት የሚገባ ሲሆን በዕለቱ የተገኘው የድጋፍ ድምፅ 346 ብቻ መሆኑ ቀድሞ በአፈጉባዔው መገለፃቸው አዋጁ በህጉ አግባብ እንዳልፀደቀ መረጃዎች አመልክተዋል። ይሄንንም የፓርላማው አባላት ከተበቱ በኋላ የነበረውን ስሀተት ለማረም የገዥው ስርዓት ደጋፊ የሆኑትን ጨምሮ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃንም ተደጋጋሚ የቁጥር መሰረዝና ማስተካከል ሲሞክሩ ተስተውሏል።
ይህንንም ተከትሎ አዋጁ ባለፈው ዓመት ምስከረም 2009 ዓ ም ጀምሮ ለ10 ወራት ከቆየው የአስቸኳይ አዋጅ በባሰ ህገ መንግሥቱን የሚፃረሩ፥ የዜጎችን የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚጥሱ አፋኝ ድንጋጌዎችን ይዟል በሚል በህዝቡ ዘንድ ተቃውሞ ቢደረግበትም፤ አዋጁ ከህግ አግባብ ውጭ በአወዛጋቢ ሁኔታ ፀድቆ ስራ ላይ መዋሉ ታውቋል። ይህንንም ተከትሎ በተለይ በምዕራብ ኢትዮጵያ የዋጁ አስፈፃሚ ተደርጎ ሙሉ ሥልጣን የተሰጠው ወታደራዊ ዕዝ “ኮማንድ ፖስት” በጥቂቱ ከ8 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል።
በተለይም በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋና ቄለም ወለጋ ዞን፥ ደንቢ ዶሎ፥ ጊንቢ፥ ሻምቡ፥ነጆ፤ ነቀምት፥ በምዕራብ ሽዋ አምቦ፥ ጊንጪ ከተገደሉት በተጨማሪ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በተተኮሰባቸው ጥይት መቆሰላቸውን ከስፍራው የተገኙ የዓይን እማኞች ገልፀዋል። ከተገደሉ ዜጎች መካከልም በኃይማኖት የአምልኮ ሥፍራ የነበሩ የኃይማኖት ሰባኪ “ፓስተር” እና በ80 ዎቹ የዕድሜ ክልል ያሉ አዛውንት ይገኙበታል።
መንግሥት እየወሰደ ያለውን የኃይል ርምጃ ተከትሎ ህዝባዊ ቁጣው ከምዕረብ ኢትዮጵያ ወሌሎች አካባቢዎች እየተዛመተ ይገኛል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አዋጁን እና የመንግሥትን ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በሚቃወሙ አካላት ከነገ ሰኞ የካቲት 26 እስከ ረቡዕ የካቲት 28 ቀን 2010 ዓ ም ከቤት ያለመውጣት፥ የንግድና የሥራ እንቅስቃሴ እቀባ መጠራቱ ታውቋል። ከነገ የካቲት 28 ቀን 2010 ዓ ም ጀምሮ ለተከታታይ 3 ቀናት በተለይ በኦሮሚያ ክልል ምንም ዓይነት መደበኛ የትራንስፖርት እና ንግድን ጨምሮ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳይኖር፥ ህዝባዊ እቀባውን ጥሶ የሚገኝ አካልም በየ አካባቢው በሚገኙ የተቃውሞ አስተባባሪዎች ርምጃ ሊወሰድበት እንደሚችል ተጠቁሟል። ነገር ግን የጤና ተቋማትና አምቡላንሶች የተለመደ ሥራቸውን መስራት እንደሚችሉና በተቃውሞ አስተባባሪዎቹ ጥበቃ እንደሚደረግላቸው ተጠቁሟል። የአስቸኳይ አዋጁ ውድቅ እስካልተደረገ ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል በተለያየ መንገድ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተጠቁሟል። ይሁን እንጂ በመንግሥት በኩል ግን አዋጁን በተግባር ከማስፈፀም ውጭ የተሰጠ ሌላ ምላሽ የለም። ስለሆነም ይህ እስከተዘገበበት ድረስ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ውጥረት ተባብሶ ቀጥሏል።
በኢትዮጵያ ለቀጥይ 6 ወራት የሚቆይ አስቸኳይ አዋጅ ታወጀ
(ዳጉ ሚዲያ) መንግሥት የፖለቲካ እስረኞች የነበሩት ጋዜጠኞችን፥ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችን እና የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችን መፈታት እና የጥቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን ተከትሎ፤ ከትናንት የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ የተደረና በሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደፀደቀ የተነገረለት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁን ገዥው መንግሥት አስታውቋል።

የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ
አዋጁም ለቀጣዮቹ 6 ወራት የጸና መሆኑን የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ ዛሬ የካቲት 10 ቀን 2010 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል። አዋጁም እንደ አስፈላጊነቱ ታይቶ ለተጨማሪ 4 ወራት ሊራዘም እንደሚችልም ተገልጿል።
የአስቸኳይ አዋጁ የመሰብሰብ፥ የመደራጀት፥ መረጃዎችን የመለዋወጥ፥ የመፃፍ፥ የተለያዩ ምልክቶችን ማሳየት፥ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ብርበራ፥ ፍተሻ እና የመሳሰሉ መብቶችን የገደበ መሆኑን ሚኒስትሩ አስታውቀዋል። እንደ እዋጁ ከሆነ፤ የጊዜ ገደብን ጨምሮ መንግሥት የመገናኛ ብዙኃንን ከማገድ እስከመዝጋት የሚደርስ ርምጃን እንዲወስድ የሚፈቅድ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።
ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መውጣት በመንግሥት የተገለፀው፤ በሀገሪቱ የተፈጠረው አለመረጋጋት እንደሆነ ተጠቅሷል። አዋጁንም ከ15 ቀናት በኋላ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት እንደሚፀድቅ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ቢናገሩም፤ የምክር ቤቱ አባላት ካልተቀበሉት ውድቅ ሊደረግ እንደሚችል አሊያም ሌላ አማራጭ ስለመኖሩ ከመግለጽ ተቆጥበዋል።
እነ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱና ንግስት ይርጋ ክሳቸው ተቋርጦ ፤ እነ ብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞ እና አሳምነው ጽጌ በይቅርታ እንዲፈቱ መወሰኑ ተገለፀ
(ዳጉ ሚዲያ) ከወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ ህዝባዊ ተቃውሞ በእስር ላይ ከነበሩት ሰዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፥ አቶ ጌታቸው አደመ፥ አቶ አታላይ ዛፌ፥አቶ ተሻገር ወልደሚካኤል እና ንግስት ይርጋ ጨምሮ የ 101 እስረኞቸ ክሳቸው እንዲቋረጥ መደረጉን ለመንግሥት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።


ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ እና ወ/ት ንግስት ይርጋ
ክሳቸው እንዲቋረጥ ከተወሰነላቸው እስረኞች መካከል 56 በግንቦት ሰባት፥ 41 እንዲሁም ከኦነግ ጋር ተባብራችኋል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው ነበሩ።


ብ/ጄነራል ተፈራ ማሞ እና ብ/ጄነራል አሳምነው ጽጌ
በተያያዘ ዜና፤ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የሚል ክስን ጨምሮ በተለያየ ጉዳይ ተከሰው የተፈረደባቸውና በይቅርታ ከእስር እንዲለቀቁ ከተወሰነላቸው መካከል ብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞና ብርጋዴር ጀነራል አሳምነው ጽጌን እንደሚገኙብት ተጠቁሟል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥራ መልቀቂያ አስገቡ
ጠቅላይ ሚኒስትር እቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሥራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን ዛሬ የካቲት 8 ቀን 2010 ዓ. ም. በፅህፈት ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አረጋግጠዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥራ መልቀቂያቸውን በቅድሚያ በስልጣን ላይ ያለው የገዥው ፓርቲ አባል ለሆነውና ተወክለው ለመጡበት ለደኢህዴን እና ኢህአዴግ ከሊቅመንበርነት ለመልቀቅ ያስገቡት ጥያቄ ተቀባይነቱን ማግኘቱን አስታውቀዋል። ይህንንም ተከትሎ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ኃላፊነት ለመነሳት ለገዥው ኢህአዴግ ምክር ቤት ጥያቄ ማስገባታቸውንና ውሳኔያቸው ተቀባይነት አግኝቶ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲፀድቅላቸው እንደሚንሱ ይጠበቃል።

አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ
ለረጅም ጊዜ በሥላጥን ላይ ቆይተው በሞት የተለዩት አቶ መለስ ዜናዊን በመተካት ከነሐሴ 2004 ዓ. ም. ጀምሮ በሥልጣን ላይ ያሉት አቶ ኃይለማርያም፤ ዛሬ በፅህፈት ቤታቸው በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በሰጡት ይፋዊ የሥራ መልቀቂያ መግለጫ እንዳስታወቁት ከሆነ በእርሳቸው ምትክ በፓርላማው ሌላ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር እስኪሾም ድረስ ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ አስታውቅዋል። የሥልጣን መልቀቃቸውም በሀገሪቱ ያለውን ችግር ለመፍታት የመፍትሄ አካል አድርገው እንዳሰቡትም አስታውቀዋል።