ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ተፈታች፤ መንግሥት የተወሰኑ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችን እና ተማሪዎችንም መፍታት ጀመረ
በፍትህ ሚኒስቴር በፌደራሉ አቃቤ ህግ በ”ሽብርተኝነት” ወንጀል ክስ ከተመሰረተባቸው በርካታ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች፣ ፖለቲከኞች እና ተማሪዎች መካከል ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙን ጨምሮ ጥቂቶች ተለቀዋል፡፡
ከእስር ከተለቀቁት መካከል የእርስ ጊዜዋን የጨረሰችው ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ፣ በሚያዚያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በጅምላ ከታሰሩት ጋዜጠኞች እና የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮጊስ፣ኤዶም ካሳዬ፤ እንዲሁም የዞን 9 ብሎገሮች ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን ይገኙበታል፡፡
ከእስር ከተለቀቁት ተማሪዎች መካከል ከአዲስ አበባ አዲስ ማስተርፕላን ማስፋፊያ ጋር በተያያዘ ከኦሮሚያ ክልል ከታሰሩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች መካከል የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የነበሩት አዱኛ ኬሶ፣ ቶፊቅ ራሺድ፣ሌንጂሳ አለማየሁ፣ አብዲ ከማል፣ መገርሳ ወርቁ፣ ቤሊሱማ ዳመነ እና ተሻለ በቀለ ክሳቸው ተቋርጦ ከእስር መለቀቃቸው ታውቋል፡፡
ይህን እንጂ አሁንም ሆን በስፋት ከታወቁት የህሊና እስረኞች መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ, ውብሸት ታዬ እና የዞን 9ኙ በፈቃዱ ኃይሉን ጨምሮ 13 ጋዜጠኞችና ብሎገሮች፣ እነ አንዱዓለም አራጌ፣ ኦልባና ሌሊሳ ፣አብርሃ ደስታን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት እንዲሁም የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በእስር ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ ምንም ክስ ሳይመሰረትባቸው ከአንድ ዓመት በላይ በእስር ላይ ከነበሩት የኦሮሚያ ተማሪዎች መካከል ተማሪ አስላን ሐሰን በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዳለ በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ማለፉም ተጠቁሟል፡፡
መንግሥት ቀደም ሲል ጋዜጠኞችን፣ ብሎገሮችን ፣ ፖለቲከኞች እና የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተማሪዎችን በተመሳሳይ “የሽብር ክስ ወንጀል” ቢመሰርትባቸውም ከተከሳሾች ጀምሮ በሀገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፉ ማኀበረስ፤ የተመሰረቱት ክሶች የፖለቲካ ውሳኔ እንጂ ከወንጀል ጋር የተያያዘ እንዳልነበር በመጠቆም ከፍተኛ ተቃውሞ ያስከተለ ሲሆን፤ ተቃውሞው አሁንም እንደቀጠለ ይገኛል፡፡
ሰበር ዜና፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ሶስት ጋዜጠኞችን እና ሁለት የዞን 9 ብሎገሮችን ከእስር መልቀቁን አስታወቀ
ከሚያዚያ አጋማሽ 2007 ዓ.ም. በፌደራሉ አቃቤ ህግ በ”ሽብርተኝነት” ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ እየታየ ከነበረው የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች መካከል፤ ሶስቱን ጋዜጠኞች እና ሁለቱን ብሎገሮች ክሳቸው በፍትህ ሚኒስቴር ውድቅ ተደርጎ መፈታታቸውን የገዥው መንግሥት ደጋፊ የሆነው ሬዲዮ ፋናን ዋቢ በማድረግ አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡
ዛሬ ሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ከእስር የተፈቱት ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ፤ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን እንደሆኑ ታውቋል፡፡
እንደሬዲዮ ፋና ዘገባ ከሆኑ ቀሪዎቹ የዞን 9 ብሎገሮች መካከል በእስር ላይ የሚገኙት በፍቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ የክስ ጉዳዩን እንደሚቀጥል የፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ ማስታወቁን ጨምሮ ዘግቧል፡፡
ጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮች ቀደም ሲል በፍትህ ሚኒስቴር አቃቤ ህግ በ”ሽብር ወንጀል” ተከሰው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ለብይን ተቀጥሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡
የህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት በተመሰረተባቸው ክስ ጥፋተኛ ተባሉ
ከ35 ወራት የፍርድ ሂደት ቆይታ በኋላ ዛሬ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ የወንጀል ችሎት በእስር ላይ ባሉት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት በሆኑት በእነ አቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ የአቃቤ ህግን እና የመከላከያ ምስክሮችን ቃል በንባብ አሰምቶ ማጠናቀቁን ተከትሎ ዛሬ በ18 ተከሳሾች ላይ ፍርድ ሰጥቷል።
ከ1ኛ እስከ 9ኛ ያሉት ተከሳሾች በተከሰሱባቸው በፀረ ሽብር ህጉ አንቀፅ አራት ላይ በተዘረዘሩት መቀስቀስ፣ ማነሳሳት እና ማሴር በሚሉ ወንጀሎች ጥፋተኛ ተብለዋል።

ቀሪዎቹ ተከሳሾች በፀረ ሽብር ህጉ አንቀፅ አራት ላይ በተጠቀሰው በመሳተፍ ወንጀል ጥፋተኛ ተብለዋል።
ፍርድ ቤቱ በተከሳሾቹ ላይ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለሀምሌ 27 ቀን 2007 ዓመተ ምህረት ቀጠሮ ሰጥቷል።
ተከሳሾቹ እና አቃቤ ህግ ከሀምሌ 27 ቀደም ብለውም የቅጣት ማቅለያ እና ማክበጃ አስተያየታቸውን እንዲያቀርቡም አዟል።
ፍርድ ቤቱ ዛሬ ጠዋት ከከሳሽና ከተከሳሽ በኩል በተካሄዱ ክርክሮች አምስት ጭብጦችን መመርመሩ ነው የተመለከተው።
ከአምስቱ ጭብጦች መካከል መንግስት በእስልምና ሃይማኖት ጣልቃ ገብቷል አልገባም? የሃይማኖቱ ተከሳሾችን ከፋፍሏል አልከፋፈለም? እና የመጅሊሱ ምርጫ ከህገ መንግስቱ ጋር ተጋጭቷል? አልተጋጨም? የሚሉት ተጠቃሾች ናቸው።
ችሎቱ እነዚህን ጭብጦች ሲመረምር በተለያዩ ሃገራት ከሃይማኖት ጋር በተያያዘ የሚራመዱ አሰራሮችን ማየቱን በችሎት መግለፁ ተጠቁሟል፡፡
ከዚህ ሰፊ ሃተታ በኋላ መንግስት በሃይማኖት ጣልቃ አለመግባቱን፣ ተከታዮችን አለመከፋፈሉንና የመጅሊሱ ምርጫ ከህገ መንግስቱ ጋር ሳይቃረን በሃይማኖታዊ ስርአት መካሄዱን ከምስክሮችና ከማስረጃ ቃል በማገናዘብ አረጋግጫለሁ ማለቱን ተከትሎ ነው ከሰዓት በኋላ ፍርድ መስጠቱን ኤቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ወደ ሳሙኤል አወቀ መኖሪያ ቤት ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ
• ከአዲስ አበባ ወደ ጎጃም ለሌላ ለቅሶ በመሄድ ላይ የነበሩ ዜጎች ተደብድበው ተመልሰዋል
የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ሰኔ 8/2007 ዓ.ም ደብረማርቆስ ከተማ የተገደለው የሳሙኤል አወቀ ለቅሶ እንዳይደርሱ ታገዱ፡፡ አመራሮቹና አባላቱ ዛሬ ሰኔ 13/2007 ዓ.ም በጠዋት ከአዲስ አበባ ተነስተው የሳሙኤል አወቀ ቤተሰቦች ወደሚገኙበት ምስራቅ ጎጃም ዞን ግንደወይን እያቀኑ በነበረበት ወቅት አባይ ድልድይ ላይ በፌደራል ፖሊስ ታፍነው ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ጎሃ ፂዮን ከተማ ውስጥ እስከ ምሽቱ 2 ተኩል ድረስ ታግተው ውለዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን ወደ ለቅሶ እንዳይሄዱ ያገዱት ከአዲስ አበባ የሄዱና ከቦታው ተዘጋጅተው ሲጠብቁ የነበሩ የፌደራል ፖሊሶች እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አመራሮቹና አባላቱ ለፖሊስ ቃል ሲሰጡ ከሳሙኤል አወቀ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት፣ በፓርቲው ውስጥ ያላቸውን ኃላፊነት፣ ሳሙኤልን ማን እንደገደለው የሚመለከቱ ጥያቄዎች ቀርበውላቸዋል፡፡ ለቅሶ እንዳይደርሱ ከተከለከሉትና ታተው የዋሉት
1. ኢ/ር ይልቃል ጌትነት/ የፓርቲው ሊቀመንበር
2. ይድነቃቸው ከበደ/ የፓርቲው የህግ ጉዳይ ኃላፊ
3. ወሮታው ዋሴ /የፓርቲው የፋይናንስ ጉዳይ ኃላፊ
4. ሀብታሙ ደመቀ/ የኦዲትና ኢንስፔክሺን አባል
5. ጌታቸው ሺፈራው/ የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ
6. ጋሻው መርሻ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
7. እምላሉ ፍስሃ/ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል
8. ሜሮን አለማየሁ/ አባል
9. ጥላሁን አበጀ/ አባል
10. ጠና ይታየው/ አባል
11. እስጢፋኖስ በኩረጽዮን /አባል
12. ኃይለማሪያም ተክለ ጊዮርጊስ/ አባል
13. ጋሻነህ ላቀ/ አባል
14. ግርማ ቢተው አባልና
15. የመኪናው ሾፌር ናቸው
ከምሽቱ 2 ሰዓት ተኩል ከአዲስ አበባ በመንገድ ትራንስፖርት ሰራተኞችና ትራፊክ ፖሊሶች ህጋዊ መሆኑ ተረጋግጦ ያለፈው እንዲሁም ለአራት ቀን ከፓርቲው ጋር ውል የያዘው መኪና እንዳይንቀሳቀስ ተከልክሎ ከፍተኛ አመራሮቹና አባላቱ ከእስር ተለቀዋል፡፡ በተጨማሪም የሰማያዊ ፓርቲ ልዑካን ይዘዋቸው የነነበሩ ቁሳቁሶች ለምርመራ በሚል በፖሊስ ተይዘዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ከአዲስ አበባ ተነስተው ምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወደ ሌላ ለቅሶ ሲሄዱ የነበሩ ዜጎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ከታፈኑ በኋላ ደጀን ላይ ተይዘው ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸው በግዳጅ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ተመልሰው ወደ ለቅሶው ቢሄዱ እስከ 10 ሺህ ብር ሊቀጡ እንደሚችሉ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል፡፡ እነዚህ ዜጎች በተያዙበት ወቅት ሰማያዊ ፓርቲ ደብረማርቆስና ባህርዳር ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ሊያደርግ እንደሆነ እንደተገለጸላቸው፤ እነሱም የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ላይ ትገኛላችሁ ተብለው ተጠርጥረው እንደሆነ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ከምርጫው ጋር በተያያዘ 4ኛ ሌላ የመድረክ አባል ተገደሉ
ባለፈው ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ምርጫን ተክትሎ የሚገደሉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 2፡00 ሰኣት ላይ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) አመራር አካል የነበሩት አቶ ብርሃኑ ኤረቦ መገደላቸውን መድረክ አስታውቋል፡፡ አቶ ብርሃኑ በደቡብ ክልል ሀዲያ ዞን በሚገኘው ሶሮ ወረዳ በዳና ቶራ ቀበሌ የፓርቲው የኮሚቴ አመራር አባልና በምርጫው ቅስቀሳም ላይ ንቁ ተሳትፎ እንደነበራቸውም ፓርቲው በመግለጫው አስታውቋል፡፡

በወቅቱ ግድያውን የፈፀሙት ብርሃኑ ደቦጭ እና ታዲዮስ ጡምቦ የተባሉ ፖሊሶች እንደሀኑ እና ከዛ በፊትም እነኚህ ፖሊሶች የመድረክ አመራሮች እና አባላቱን ሲያስፈራሩና ሲዝቱባቸው እንደነበርም ተጠቁሟል፡፡ በተለይ አቶ ብርሃኑ ኤረቦ በሁለቱ ፖሊሶች መኖሪያ ቤታቸው ደጅ ተይዘው ከተደበደቡና ከተገደሉ በኋላ አስከሬናቸው ባካባቢው ባለ ወንዝ ተጥሎ እንደተገኘ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ አቶ ብርሃኑ ኤረቦ የተገደሉበት ሶሮ ወረዳ በምርጫ ዋዜማ መምህር ጌታቸው የተባሉ የመድረክ ዕጩ በኢህአዴግ በደረሰባቸው ጫና እና አስተዳደራዊ በደል በወረዳው አስተዳደር ፊት ራሳቸውን አቃጥለው ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ ወረዳው የኢህአዴግ ተወካይ እና የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሆኑት ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም የተወዳደሩበት ወረዳ መሆኑ ታውቋል፡፡
መድረክ ከግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አቶ ብርሃኑ ኤረቦን ጨምሮ የተገደሉት የክልል አመራሮቹ ቁጥር አራት የደረሰ ሲሆን፤ እነኚህም በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ አቶ ጊዲሳ ጨመዳ፣ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ አርሲ ዞን ቆራ ወረዳ አቶ ገቢ ጥቤ፣ ከትግራይ ክልል ምዕራብ ትግራይ ዞን ማይካድራ ከተማ አቶ ታደሰ አብርሃ እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በምርጫው ወቅት ከፍተኛ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበሩ የመድረክ አባላትና ደጋፊዎች በተለይም በደቡብ፣ በኦሮሚያ እና በትግራይ በርካታ ሰዎች እንደታሰሩ፣በጥይት ተደብድበው እንደቆሰሉ እና ቤቶቻቸው እንደተቃጠለ ከፓርቲው የተገኘ መረጃ አመልክቷል፡፡ በተመሳሳይም በአማራ ክልል ምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረማርቆስ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ አመራርና የህዝብ ተወካዮች ዕጩ የነበረው ወጣት ሳሙኤል አወቀም ተደብድቦ መገደሉ ይታወቃል፡፡ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ አባሎቻቸው የተገደሉት በኢህአዴግ መሆኑን እንደሚያምኑ ገልፀዋል፡፡



