ቃና ቴሌቭዥን-በይ ደስም አላልሽኝ
ሀብታሙ ስዩም
እና ባጭሩ የምትሉኝ በሃገሪቱ የሚሰሩ ፊልሞች ጥራት እና የታሪክ ፍሰት እምብዛም ስላልሆነ የቱርክ ፊልም እያየን እንቆይ ነው? በይ ደስም አላልሽኝ አለ ሙዚቀኛው፡፡የሀገራችን ፊልሞችና ድራማዎች ጥራትና ብቃት ከፍ እንዲል ሺ ዓመት የለፋን እንመስላለን አነጋገራችን፡፡ወገኖቼ በአስር ወር የፊልም ትምህርት ቤት የተማርኩት የመጀመሪያው ነገር የኛ ሀገር ፊልም ለውዝግብ መብቃቱ ራሱ ታላቅ ስኬቱ መሆኑን ነው፡፡

የፊልም ዕቃዎችን ለማስገባት ያለውን ጣጣ፣ጥበቡን የሚደግፍ ሁነኛ የመንግስት አካል ዕጦት፣ የትምህርትና ስልጠና ተቋማት እጥረት ፤ታሪኮች የተገደቡ እንዲሆኑ የሚደረገው የእጅ አዙር ጫና ፣ሲኒማ ቤቶችን ከሚያስተዳድሩት ግልገል መንግስቱ ሃይለማሪያሞች ጋር ሁሌ የሚላተመው የኛ ፊልም የራሱን ተመልካቾች መፍጠሩ አፈር ህይወትን ፈጠረ እንደሚለው እሳቤ እጅግ የሚገርም ነው፡፡እንዲህ እየሆነ የብዙሃን የእንጀራ ቤት የሆነውን ዘውግ በአንድም ሆነ በሌላው የሚጓዳ አሰራርና ትግበራ ለኔ ምኑም አይስማማኝም፡፡
በዕቁብና በቤተሰብ ብድር ከተሰሩ ፊልሞች ውስጥ የሚገርሙ ተዋናያንን፣ተስፋ ያላቸው የቴክኒክ ባለሙያዎችን፣ መንገድ ላይ ስናያቸው ፈገግታችንን የሚያገዝፉ አዘጋጆች ተፈጥረው መገኘታቸው ሁሉ ለኔ እጡብ ነው፡፡በኢንተርናሽናል ደረጃም ሆነ በሀገር ቤት አምራቾች የተሰሩ ፊልሞችን አሰራርና ሂደት ለመታዘብ ዕድሉ ነበረኝ፡፡ጎበዛዝስት የፊልም ሰሪዎቻችን ሄሎሄ በታዘብክ ቁጥር ጉዳዩ እን የሚሊየን ብር ፊልምን በሁለት ብር እስኪርቢቶ( በትችት) ድራሹን አጥፍቶ ዞር በማለት የሚጠገን ነገር አላገኘሁበትም፡፡
ከዓመታት መውደቅ መነሳት በኃላ ቴሌቭዥኖቻችንም የአማረኛ ፈልሞችና ድራማዎችን ሀገራዊ ተፈላጊነት በማየት ከሰዓታቸው ሙዳ ሙዳውን ማከፈል ጀመሩ፡፡ይሄ ጅማሮ ደራሲያን ፣ተዋናያን የቴክኒክ ባለሙያዎች በገቢ የሚያድጉበትን ዕድል አስፍቶ ባልበላ ጎናቸው ያሳዩትን መፍጨርጨር በበላ ሆዳቸው አሳድገው እንደሚመጡ ተስፋ ሆኖኝ ነበር፡፡ይሄን መሰል ጥረታቸውን ተጨማሪ ዕድል በመስጠት እኒህ ወገኖች ለተጨማሪ ሰዎች የመንፈስም ሆነ የስጋ ጥግ እንዲሆኑ መጣር አስፈላጊም ነበር፡፡አሁን እንደሰማሁት ግን ለምዕታ ዐመት ተለፍቶበት እንዳልተወጠ ጉዳይ ‹‹ የሀገራችን ፊልም ጉዳይ በቅቶናል›› ተብሎ የቱርክና የቴሌሙንዶ ሀብታሞችን ግዛተ አጤ በሀገሬ ፊልመኞች ጉሮሮ ላይ መትከል በእጅጉ ያልታሰበበት የወጠጤ ነጋዴ ሀሳብ ሆኖብኛል፡፡
ፊልመኞቻችን ችግር የለባቸውም የሚል ክርክር አልወጣኝም፡፡አሁን ያለው የፊልመኞቻችን ችግር በጊዜ ውስጥ በባለሙያዎች መካከል በሚደረግ ውድድር እና የተማሩ ፊልም ሰሪዎች እየበዛ መምጣት ፤ሀገሪቱ በፊልም ስራ ዙሪያ የያዘቻቸው የእጅ አዙር ገደቦችና መሰናክሎች ሲከስሙ የሚቀረፍ ነው፡፡
እንኳን የኛ ሀገር ፊልም ይቅርና ሆሊውድ እንኳ አንዳንዴ እህል ውሃ የማይሉ ፊልሞች ይሰራሉ፡፡ነገር ግን ውሃ ስለጠማን እሳት እንሙቅ አይነት ውሳኔ በዚያ ሀገር የተለመደ አይደለም፡፡
የቱርክ ፊልሞችን ለናሙና ማየት ችግር የለውም፡፡ይሄን በሚያክል ምጥጥን ሰዐታቱን መሙላት ግን ለኔ መንስኤው ግልጽ ያልሆነ የስድ ውሳኔ ነው፡፡ደሞ እናውራ ከተባለ ፊልሞችን አስተርጉሞ የማሳየት ዕቅድ የሌሎችን ሀገራት ፊልሞች ለሀገራችን ተመልካች ከማቃመስ መልካም እሳቤ ብቻ የሚነሳ አይደለም፡፡ከሀገራቱ ኤምባሲዎች፣የሀገራቱን ልዕልና ለማጉላት ከሚሰሩ ድርጅቶች የሚገኘውን ፈንድና ጥቅማጥቅም ከመጠቅለል ፍላጎት የሚነሳ የትርፍ ጥረትም ነው፡፡
ከምንም በተጀመረ ጥበብ ውስጥ ሞካሪ እስካለ ድረስ የሚሞክረውን ሰው እስትንፋስ ለማርዘም ማናቸውም ከለላዎች መደረግ አለባቸው፡፡ቢያንስ ያ ሰው ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ያ ሰው የእኔና የአንተን ቋንቋ ተጠቅሞ በዓለም ውስጥ ትንሽም ቢሆን ዐይንና ጆሮ እንድናገኝ እየለፋ ያለ ሰው ነው፡፡ፊልም እና ሙዚቃ የእንጀራ ጉዳይ ብቻም አይደሉም ዐለምን በእጃዙር የምታማልልበትና የሀገርህን እሳቤ በሌላ ዐለም ላይ የምትጭንባቸው ህመም አልባ መሳሪያዎች ናቸው፡፡አሜሪካ የዓለምን ልብ ያስከፈተችው በኒኩሌር ይመስልሃል፡፡እኔና አንተ አሜሪካ ሳንረግጣት ያወቅናት የጠንቋይ ዘር ስለሆን ይመስልሃል? ጥበበኞቿን ይዛ አሜሪካዊነት የተጠቀጠባቸው ሁነኛ ፊልሞችን በማስንጨፍ ነው፡፡እና ለቱርክ ፊልም ይሄን ሁሉ ጊዜ መስጠት ሀሊት እና ሀዛል ሲላቀሱ ከማየት ወዲያ የማይዘል የሞራል ልዕልናን የመጫን እርሾ የሌለበት ይመስልሃል?
ለማንኛውም ፊልሞቻችን እንከነ ብዙ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡የአንዳንድ ፊልም ሰሪዎች የዕውቀት ማነስን ሰበብ አድርጎ በማንሰራራት ላይ ያለውን ጥበብ በብላሽነት መጠቅለል የማይገናኝ አመክኒዮ ነው፡፡ስላበሳጩን ሳይሆን ስላስገረሙን የፊልም ታጋዮች ክብር ውሳኔያችንን ማጤን ግድ ይላል፡፡ ምንም ይሁኑ ምንም እንድናያቸው ጉጉት የተውልን መልካም ውጥኖችም ናቸው፡፡ለመራመድ እዳለመ – ነገር ግን እንደሚወድቅ እንደሚነሳ ልጅ እየተከተልን እየደጋገፍን እራሱን ችሎ እንዲቆም ማብቃት ይኖርብናል እንጂ እንደሞተ ሁሉ ገሸሽ አድርገነው በጉዲፈቻ ሌላ ጠብደል ከእልፍኝ ማስገባቱ ዘረሰናይ ብርሃነ ማሪያምን የሚያክል የዓለም ፊልሞችና ቴሌቭዥን የጀርባ ውስጠ ባህሪ ይገባቸዋል ከሚባሉ ሰዎች የሚጠበቅ አይደለም፡፡
ቀድሞ ነገር የጣቢያው ዓላማ የሶስተኛ ዓለም ሚዲያዎች ሊኖራቸው የሚገባውን እና ህዝቡ በድህነቱና በአለማወቁ ሰበብ የገጠሙትን የኑሮ ትንቀንቆች ድል የሚያደርግበትን መላ መጠቆም አይመስልም፡፡የጣቢያው ዓላማ የየለት ኑሯችንን የሚያፈኩ ከአንጀት ጠብ የሚሉ መሰናዶዎች ማድረስ አይመስልም፡፡ተዝናኑ ነው-በባዶ ሆድ-በባዶ ጭንቅላት ተዝናኑ-አይነት ነው፡፡
አፈር ስሆን ከማብቃቴ በፊት ዘረሰናይ፡፡አንጀሊ ረድታህ የሰራኸው ፊልም ይዘቱን ታስታውሰዋለህ? እየውልህ እሱን እና እሱን መሰል ድሃውን ህዝብ በየለቱ የሚነኩ ችግሮች በተንሰራፉበት ሀገር ነው አንተ ችግሩ ሁሉ ተቀርፎለት የመዝናኛ ያለህ ብሎ እንደለመነህ ሁሉ ለዚህ ህዝብና ሀገር የቱርክና የቴሌሙንዶ ግሳንገስ ይዘህለት የመጣህ፡፡
ከጎበዝ ዳይሬክተርነት ወደ ግደቢስ ነጋዴነት –ይሄ ነው መርመጥመጥ፡፡እንኳን ወደ ማደንዘዙ ዘመቻ በሰላም ተቀላቀልክ፡፡
ፓትርያርኩ፡- ለኢትዮጵያ የደኅንነት፣ ለምእመናን የድኅነት ሥጋት
ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

‹የክርስቶስ አንዲት በግ መከራን ስትቀበል ከማይ እኔ የበጉ እረኛ መከራ መቀበልን እመርጣለሁ›
ይህንን የተናገረው ዮሐንስ አፈወርቅ ነበር፡፡ የቁስጥንጥንያዋ ንግሥት አውዶቅስያ የአንዲት ክርስቲያን ምእመንን መሬት ወስዳ ባሰቃየቻት ጊዜ ለተግሣጽ የተናገረው ነው፡፡ እንዳለው አልቀረም አውዶቅስያ ባደረሰችበት መከራ ተግዞ በዚያው ሞትን ተቀብሏል፡፡ እውነተኛ አባት ስለ በጎቹ ራሱን አሳልፎ ይሰጣል እንጂ በጎቹን ለራሱ ክብርና ጥቅም ሲል አሳልፎ አይሰጥም፡፡ ፓትርያርክ ማለት በግሪክ ‹ታላቅ አባት› ማለት ነው፡፡ የታላቅ አባት ተግባር የልጆቹን ሥራ ማፍረስ አይደለም፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፤ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን መክሰስ አይደለም፤ ለዚህማ ሰይጣን እንጂ አባት አያስፈልግም፡፤ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን ጠርቶ መውቀስ እንጂ በር መዝጋት አይደለም፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፡፡ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን ማቀፍ እንጂ ማባረር አይደለም፤ ለዚህማ ሰይጣን አለ፡፡
ፓትርያርኩ እንጨት የሚሸጡ እናቶች ካወጡት የእንጦጦ ኪዳነ ምሕረት ገንዘብ ግማሽ ሚሊዮን ብር እንደዋዛ በአንድ ሙሰኛ ሲነጠቅ ተኝተዋል፤ በመሐል ከተማ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የተሠሩ ሕንጻዎች በጎጆ ቤት ዋጋ በሙስና ለዐሠርት ዓመታት ሲከራዩ ተኝተዋል፤ ከመንበረ ፕትርክናቸው ሥር ባለች አጥቢያ የቤተ ክርስቲንን ገንዘብ አናስበላም ያሉ ካህናትና ምእመናን ሲባረሩ ተኝተዋል፡፡ በሕዝብ ጥያቄ ሽፋን ጽንፈኛ አቋምን በሚያራምዱ ሰዎች አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ ይተኛሉ፤ የስልጤ ዞን ምእመናን በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ እየተቀበልን ነው ሲሉ ይተኛሉ፤ ቤተ ክህነቱ የኑፋቄ ማኅደር ሲሆን ይተኛሉ፤ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ሲዘጉ፣ ገዳማትና አድባራት ሲፈርሱ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች ሲበተኑ ይተኛሉ፤ በመሥዋዕትነት የተመሠረቱት የደቡብ አፍሪካ አብያት ክርስቲያናት በሙሰኛ አመራሮች አደጋ ላይ ሲወድቁ ይተኛሉ፣ ይሄ ሁሉ ዘለፋና ኑፋቄ በቤተ ክርስቲያን ላይ ሲዘንብ ይተኛሉ፡፡
መናፍቃንን የሚተች ጽሑፍ በኦርቶዶሳውያን ተጻፈ ሲሏቸው፤ ምእመናንን የሚያጸና ጉባኤ ሊዘጋጅ ነው ሲሏቸው፤ ሕዝቡ ወደ ቤተ ክርስቲያን እየመጣ ነው ሲሏቸው፤ ወጣቱ ትውልድ ቤተ ክርስቲያኑን ለማገልገል እየተጋ ነው ሲሏቸው፤ ዲያስጶራው ሕዝብ በእናት ቤተ ክርስቲያን ሥር ሆነ ሲሏቸው፤ ቤተ ክርስቲያንን የሚገልጥ ዐውደ ርእይ ሊዘጋጅ ነው ሲሏቸው፤ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን ፕሮግራም ሊቀርብ ነው ሲሏቸው ያን ጊዜ ብዕራቸውን ይዘው ለማገድና ለመክሰስ ይነቃሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ‹ድንግል ሆይ የአንቺን ምስጋና ለመጻፍ ምንጊዜም ብእሬ ቀለም እንደያዘ ነው› ነበር ያለው፡፡ የፓትርያርኩ ብእር ግን ምእመናንን የሚያጽናና ጦማር ለመጻፍ ወይም ድንግልን የሚያመሰግን ድርሳን ለመድረስ የሚጨበጥ አይደለም፡፡ እንደ ጠንቋይ ብዕር ለማፍዘዝና ለማደንገዝ እንጂ፡፡
የፓትርያርክ ዋናው ሥራው የሀገር ደኅንነት እንዲጠበቅ ‹ዕቀብ ሕዝባ ወሠራዊታ ለሀገሪትነ ኢትዮጵያ› እያለ መጸለይ፤ የምእመናን ድኅነት እንዲረጋገጥም ሃይማኖት ማስተማር፣ በጎችን መሠማራትና ቀኖናን መጠበቅ ነበረ፡፡ ለቅዱስ ጴጥሮስ ‹በጎቼን ጠብቅ፣ አሠማራ› ነበር የተባለው፡፡ መጠበቅ- ከክህደት፣ ከኑፋቄ፣ ከኃጢአት ከበደል፤ ማሠማራት – በትምህርት፣ በምግባር፣ በትሩፋት፣ በአገልግሎት፣ በጽድቅ መስክ ላይ፡፡

‹ባለሞያ ሴት የሠፋችውን ወራንታ፣ ጅል ትተረትረዋለች› እንደተባለው በደኅና ጊዜ ትጉኃን አበው የሰበሰቧቸውን ወጣቶች ካልበተንኩ ብሎ እንዴት አንድ ፓትርያርክ ይነሣል፡፡ ወጣቶቹ ሊሳሳቱ፣ ሊያጠፉም ይችላሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ግን ለዚህም መንገድ ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት ሳይቀሩ የገዛ ልጆችዎን ያወያዩ ሲሏቸው በራቸውን ጠርቅመው የሚዘጉ ፓትርያርክ በታሪክ የሚጀመሪያው መሆን አለባቸው፡፡ በሱራፊ ነበልባል የተዘጋች ገነት ስትከፈት በፓትርያርክ የተዘጋች የቤተ ክህነት በር ልትከፈት አልቻለችም፡፡ ሰይጣንን ከእግዚአብሔር ጋር ለማነጋገር የደከሙ እነ ክርስቶስ ሠምራን የመሰሉ ቅዱሳን ባሉባት ቤተ ክርስቲያን እረኛው ከመንጋው ጋር መነጋገር አቃተው፡፡ ኢየሱሳውያንን በዐደባባይ ሳናነጋግራቸው መሄድ የለባቸውም ብለው የተሟገቱ እነ እጨጌ በትረ ጊዮርጊስ በነበሩባት ቤተ ክርስቲያን የገዛ ልጆቹን ለማነጋገር በር የሚዘጋ እጨጌ ተፈጠረ፡፡ የመካ ቁራይሾችን አሳልፈን ለጠላቶቻቸው አንሰጥም የሚሉ አበው በነበሩባት ቤተ ክርስቲያን የገዛ ልጆቹን አሳልፎ የሚሰጥ አባት መጣ፡፡
የኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናት በ1972 እኤአ ካይሮ ላይ ባደረጉት ጉባኤ ከተስማሙባቸው ነገሮች አንዱ የኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት ተልዕኮ ነበረ፡፡ እንዲህ ይላል ‹ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት አምስት ተልዕኮ አላቸው፡፡ እነዚህም
1. ወንጌልን መስበክ(Preach the Gospel)
2. ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መፈጸም(Administer the Sacraments of the Gospel.)
3. የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ አንድነትና ቀኖና መጠበቅ(Guard the faith, unity, and discipline of the church.)
4. ለካህናትና ለምእመናን የቅድስና ምሳሌ መሆን(Be a moral example of holiness and wholesomeness.)
5. በእረኛውና በበጎች መካከል ያለውን ክፍተት ማጠበብ(Diminish the distance between bishops and their flock.)
ለመሆኑ የእኛ አባት የቱን ነው እየፈጸሙ ያሉት? ወይስ ከኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር ውጭ ሆነናል?
ዐውደ ርእዩ የማይደረግበት በቂ ምክንያት ከነበረ ቢያንስ ከሳምንት በፊት መግለጥ ይቻል ነበር፡፡ ዓላማው ግን ማበሳጨት፣ ዐመጽ ማስነሣት፣ ተሥፋ ማስቆረጥና ምእመናንን ወደማይፈልጉት መሥመር መውሰድ ነው፡፡ ለዚህ ነው ፈያታዊ ዘየማን ገነት በገባባት ሰዓት ዐውደ ርእዩ እንዲዘጋ የተደረገው፡፡ የዚህች ሀገር ሰላም አይፈለገም? ምእመናን ሀገር እንደሌላቸውና መብት እንደሌላቸው ራሳቸውን እንዲቆጥሩ ይፈለጋል? ‹ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል› እንዲል ሀገሪቱ ያለባት ችግር አይበቃትም? ተጨማሪ ችግር ማምረት ይፈለጋል?
ችግሩ ሁሉ እየተፈጠረ ያለው በመንግሥት ስም ነው፡፡ ‹መንግሥት አዞናል፤ እገሌ የተባለ ባለ ሥልጣን ብሎናል፤ ፖሊስ እንጠራለን፤ ደኅንነት እናዛለን› ነው በቤተ ክህነቱ ዘንድ የሚባለው፡፡ እውነት መንግሥት በስሙ የሚሠራውን ያውቀዋል፤ ካወቀውስ ዝም ይላል? ቤተ ክህነቱ በሚያመጣው ዳፋ መከራ ለመቀበልስ ዝግጁ ነው? ይህ አካሄድስ ለሀገሪቱ ደኅንነት የሚበጅ ነው? ዐውደ ርእዩ እንዲዘጋ ያዘዘውስ የትኛው መንግሥት ነው? አንዱ የሚፈቅድ ሌላው የሚዘጋ ስንት መንግሥት ነው ያለው? ወይስ ‹ደብዳቤ መጻፉ አላዋጣምና ዝጋልኝ› ተብሎ እጅ የተሰነዘረለት አካል ያደረገው ነው? መጽሐፉ እንደሚል ‹የማይገለጥ የተሠወረ› አይኖርምና ዐውቀነዋልም፣ እናውቀዋለንም፡፡
የገዛ ፓትርያርካችን ለእኛ ለምእመናን ድኅነትን እንዳናገኝ ሥጋት ሆነውብናል፡፡ የታገሡትን ሁሉ ለክፋት በማነሣሣት ደግሞ ለሀገሪቱ ደኅንነት ሥጋት እየሆኑ ነው፡፡ የምእመናኑን ሥጋት ሲኖዶሱ፤ የሀገሪቱንም ሥጋት መንግሥቱ ሊያስቡበት ይገባል፡፡ ከቤተ መቅደስ የተነሣ ችግር መጀመሪያው እንጂ መጨረሻው አይታወቅምና፡፡ እንዲህ ያሉ ነገሮች የምእመኑን የአስተሳሰብ ቅርጽ ይቀይራሉ፡፡ የሐበሻን ሥነ ልቡና ለሚረዳ ደግሞ ሲረገጥ እንደሚጠክር ጭቃ ያጠነክራሉ፡፡ ሲሞረድ እንደሚሳል ቢላዋ፣ ሲቀረጽ እንደሚሾል እርሳስ ያደርጋሉ፡፡
በዐውደ ርእዩ የሚማሩት የሚያዩት ብቻ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ያላዩትም እንዲማሩ አድርገዋል፡፡ ሐሳብና ርእዮት ሊያስተባብረው የማይችለውን ተጠቂነት ያስተባብረዋል፡፡ ተጠቂነት ክርክርና ውይይት፣ ማስረጃና መረጃ አይጠይቅም፡፡ መጠቃቱን ያወቀ ሁሉ ራሱ ገብቶት ይተባበራልና፡፡ ምናልባትም ምእመናንን ከገድል ተራኪነት ወደ ገድል ሠሪነት ያሻግራቸው ይሆናል፡፡ ‹እዚያም ቤት እሳት አለ› አሉ አለቃ፡፡
እንደ ሶምሶን ከአንበሳ ሬሳ ማር ለማውጣት ግን በሳል አመራር ይጠይቃል፡፡ የማኅበሩ አመራርም ቢሆን ጊዜውን አይቶ የሚሣለጥ አመራር እንጂ የተቸከለ አመራር መሆን የለበትም፡፡ የፓትርያርክ ማትያስ ዘመን እንደ ፓትርያርክ ጳውሎስ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምም ዘመን እንደ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ አይደለም፡፡ አሁን የሆነው ነገር ሊሆን እንደሚችል ቀድሞ እየታወቀ ከግንቡ ጋር እስኪጋጩ ድረስ ቆሞ መጠበቅ ብልህነት አይደለም፡፡ አሁንም ‹እገሌ የተባለ ባለሥልጣንን አናግረናል፤ እገሌ የተባሉ አባት አይዟችሁ ብለውናል› እያሉ መጓዝ የሚያዋጣ አይደለም፡፡ ለጉባኤ ተሰብስቦ ‹ ለፓትርያርኩ የተጻፈው ደብዳቤ አንጀት አርስ ነው› ብሎ አጨብጭቦ የሚበተን አመራር ጊዜው ሊያልፍበት ይገባል፡፡ ከዲሚትሪ ሆቴል እስከ ፌዴራል ጉዳዮች የተደረጉትን ውይይቶች ገምግሞ አዲስ አቅጣጫ መያዝ ይገባ ነበር፡፡ የሚሰበሰብ ብቻ ሳይሆን የሚተነብይ አመራርም ያስፈልጋል፤ ካልሆነ ግን
‹ከክምር ድንጋይ ላይ ይበቅላል ደደኾ
የፈራሁት ነገር መጣ ድኾ ድኾ› የተባለው ይደርሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የደረሰውን የሰብዓዊ ጉዳት አስመልክቶ በ33 ወረዳዎች ብቻ 103 ዜጎች መገደላቸውን የሚገልፅ ገለልተኛ የምርመራ ሪፖርት ይፋ ሆነ

ከህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ተጀምሮ በነበረው እና መላው ኦሮሚያ ክልልን ያዳረሰው ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ የደረሰው ሰብዓዊ ጉዳት ልዩ የምርመራ ሪፖርት መግለጫ ይፋ ሆነ፡፡ ልዩ መግለጫው ይፋ የሆነው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሰመጉ ዋና ጽህፈት ቤት ሲሆን፤ መግለጫውም የ103 ዜጎች ህይወት መጥፋቱን አስታውቋል፡፡
ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ይባል የነበረውና በኋላም የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ(ሰመጉ) እየተባለ የሚጠራው ብቸኛው ሀገር በቀል መነግሥታዊ ያልሆነ ገለልተኛ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት ሲሆን፤ ባለፉት አራት ወራት በተጀመረውና እስካሁንም በቀጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ የሰብዓዊ ጉዳት ቀዳሚውን ልዩ መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡ ሰመጉ በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም ጠቁሟል፡፡

ሰመጉ 34 ገፅ ባለው ልዩ መግለጫው እንዳስታወቀው ከሆነ፤ የደረሰው የሰብዓዊ ጉዳት ምርመራ የሚያካትተው ከህዳር 2 ቀን እስከ የካቲት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሱ የሰብዓዊ ጉዳቶች ብቻ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በተለይ በምርመራ ወቅት ድርጅቱ የጋጠሙትን ችግሮችም የጠቀሰ ሲሆን በተለይም የገንዘብ ፣ የሰው ኃይልና የምርመራ መሳሪያ እጥረት፣ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ሁኔታ ውጥረት የተሞላበት በመሆኑ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተው ቀውስ እንደልብ ተዘዋውሮ ለመስራት አለመቻል፣የመንግሥት የደህንነት እና የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ጫና እና ክትትል ማድረጋቸው፣ ሕዝቡ ከፍተኛ ፍርሃት ውስጥ በመግባት ማንንም ሰው አለማመን እና መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆን ዋነኞቹ መሆናቸው ጠቅሷል፡፡
በክልሉ አሁንም በተለያዩ ቦታዎች ተቃውሞች መቀጠላቸውንም በመጥቀስ፣ ማንኛውም የሰብዓዊ መብት የሚመለከተው አካል የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን ሰብዓዊ መብት እንዲያከብር፣ እንዲያስከብርና እንዲያስጠበቅ ጫና እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡
ሙሉ መግለጫውን ከዚህ ቀጥሎ ያለውን መስፈንጠሪያ (ሊንክ) በመጠቀም ያገኙታል፡- http://ehrco.org/wp-content/uploads/2016/03/The-Human-Rights-Council-HRCO-140th-Special-Report-Amharic-Scanned-March-14-2016.pdf
የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ…
ከዚህ ቀደም በቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት የነበሩና ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የትግራይ ክልል ስር ያሉት የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ “እኛ አማራ ነን፣ ያለፈቃዳችን ተገደን ነው ወደ ትግራይ የተካለልነው፣ የአማራ ማንነት ጥያቄያችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አማራ እንጠቃለል” የሚል ጥያቄን ቢያነሱም፤ ከመንግሥት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ አባላት ተገደው ያለፈቃዳቸው ወደ ትግራይ እንድንጠቃለል ተደርገናል ከሚለው ጥያቄ በተጨማሪ አማራ በመሆናችን ብቻ በትግራይ ክልል አስተዳደር ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብና፤እየተፈፀመብንም ይገኛል በማለት የቀደመው የአማራ ማንነታችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አስተዳደር አማራ ክልል ለመጠቃለል አንዱ ምክንያታቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ይስተዋላል፡፡

እንደ ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴዎች አገላለፅ፤የነበረው የወልቃይት ጠገዴ አስተዳደር ወሰን ክልልም በሰሜን ተከዜ ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ ኤርትራ፣ በምስራቅ የቀድሞው ትግራይ ጠቅላይ ግዛት ፣ በምዕራብ ሱዳን በደቡብ የቀድሞው ቤጌምድር (የአሁኑ ጎንደር) አስተዳደር አካል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አካባቢውም በአሁን ወቅት በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በሚል አስተዳደር ስር በ3 ወረዳዎች የተዋቀሩት ቃፍታ ሁመራ፣ ወልቃይት እና ጠገዴ ወረዳዎች በቀድሞ ቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት ወልቃይት ጠገዴ አውራጃ አስተዳደር እንደነበርም ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ቀደምት የአስተዳደር ሰነዶችን እና የአማራ ማንነትን ያረጋግጣሉ የሚሏቸው መረጃዎችን አያይዘው በሕገ-መንግሥቱ መሰረት ጥያቄ ቢያቀርቡም ከሚመለከተው አካል እስካሁንም ምላሽ አለማግኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
በተለይ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ ተወካዮች የአማራ ማንነት ጥያቄ ይዘው ላለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ ጥያቄ ያቀርቡ እንደነበር እንደሚያውቁ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲአዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አስታውሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ይህን ያስታወሱት ባለፈው ከኦሮሚያ እና በሌሎች ሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ በተያያዘ መድረክ በዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ላይ ነበር፡፡
የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላቱም በተለያየ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ከሆነ፤ አማራ ሆነው ሳለ ሳይወዱ በግድ ወደ ትግራይ መጠቃለላቸውን፣ ልጆቻቸውም ከአፍ መፍቻ አማርኛ ውጭ ተገደው በትግርኛ እንዲማሩ መደረጉን፣ የአካባቢው ህዝብ ከአማርኛ በተጨማሪ አረብኛ እና ትግርኛም ባላቸው የድንበር ግንኙነት አማካኝነት መናገር ቢችሉም፤ ባህላቸውን እና ማንነታቸውን የሚገልፁበት ቋንቋ አማርኛ መሆኑን እና የማንነት ስነ ልቦናቸውም አማራ እንደሆነ፤ ይህንንም ላለፉት 25 ዓመታት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማት ጥያቄ ሲያነሱ ግድያ፣ እስራት፣ ድብደባ፣ ማስፈራራትና ስደት እንደደረሰባቸው፣ ከጥያቄው ጋር በተያያዘ የትግራይ ክልል መስተዳደር ግድያን ጨምሮ የተለያዩ በደሎችንም ይፈፅም እንደነበርና አሁንም እየፈፀመ እንደሆነ ሲያነሱ ይደመጣል፡፡
የአማራ ማንነት ፈቃዳችን ሳይጠየቅ ተገደን እንድንጠቃለል ተደርገናል ለሚሉት የትግራይ ክልል መስተደዳደርና በፌደራሉ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄን የሚያቀርቡ ተወካዮች በአዲስ አበባም ለተወሰኑ ቀናት በፖሊስና ደህንነት አባላት ታግተው መለቀቃቸው የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን ጨምሮ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን የተዘገበ ሲሆን፤ በተለይ የትግራይ ክልል አስተዳደርና እና የክልሉ ምዕራባዊ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎች አሁንም ከፍተኛ ማስፈራሪያ እና ዛቻ እየፈፀሙ መሆኑን የኮሚቴው አባላት ገልፀዋል፡፡ አዲሱን የአስተዳደር ክልል መዋቅር የመሰረተው ኢህአዴግ መንግሥት እና የትግራይ ክልል መስተዳደር ቀድሞ የነበረውን የአማራ ስነ ህዝብ ስብጥር፣ ባህል እና ማንነትን ለማጥፋትና መቀየር ላለፉት 25 ዓመታት ሙሉ ሲሰሩ ተቃውሞ ብናቀርብም ሰሚም አላገኘንም፣ እንደወንጀለኛም ተቆጥረናል ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ከዛ በተጨማሪ የእኛ የአማራ ማንነት እንደሌለ ተቆጥሮና ተክዶ ልጆቻችን በአማርኛ እንዳይማሩና እንዳይናገሩ፣ በአማራ ማንነታቸው እንዲያፍሩና የነበረውን የአማራ ማንነት ባህል እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ በግድም የትግርኛ ቋንቋ እንዲነገሩ፣ የትግራይ ማንነት ባህልን ብቻም እንዲያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ይህም ህገ-መንግሥቱን እንደሚፃረር ብናነገርም የከፉ በደሎች ተፈፅመውብናል ይላሉ፡፡
በተለይ አካባቢውን በተመለከተ በአጼ ኃይለስላሴ ዘመን የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩትና የአጼ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል መንገሻ ስዩም ወልቃይት ጠገዴ በሳቸው ዘመንም ሆነ ከዛ በፊት ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ አስተዳደር ስር እንዳልነበር እንደሚያውቁ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ገልፀው ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሃላፊ በኩላቸው ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ እንደሆነ እና ከዛ ጋ ተያይዞ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ የህዝቡ እንዳልሆነ ከመግለፃቸው በተጨማሪ የአማራ ማንነት ጥያቄ የሚያነሱ ተወካዮች የሚቃወም ሰልፍም በአካባቢው ተደርጎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአማራ ማንነት ጥያቄን ለሚያነሱ ማኀበረሰብ አባላትና ተወካዮች ጥያቄያቸው መፍትሄ አሊያም ህዝባዊ ውሳኔ ያገኝ ዘንድ ባሉበት ወልቃይት ጠገዴ ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፍ ቢጠይቁም በትግራይ ክልልም ሆነ በክልሉ ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሊፈቀድ ባለመቻሉ የማኀበረሰቡ ተወካዮች ህዝባዊ ስብሰባዎቻቸውን በአጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች ለማድረግ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለ ኦሮሚያው ተቃውሞ እና ስለ ጎንደር የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ቢገልፁም፤ ስለ ወልቃይ ጠገዴ አማራ ማንነት ጥቄን ግን ሳያነሱት ከማለፋቸው በተጨማሪ በጥቅሉ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንነት ጋር በተያያዘ ያልተመለሰ ጥያቄ የለም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ አዲስ ሚዲያ ባለው መረጃ መሰረት የብሔረሰብ ማንነት እና የራስ አስተዳደር ጋ በተያያዘ በትግራይ ወልቃይት ጠገዴን እና በኣማራ ክልል ምላሽ አግኝቷል ከተባለው የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጥያቄ በተጨማሪ በኦሮሚያ፣ በደቡብ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ከክልሎቹ እስከ አዲስ አበባው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ እስካሁንም ምላሽ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡
የበዕውቀቱ ስዩም ወጎች
ከተስፋዬ ገብረአብ

በዕውቀቱ ስዩም “ከአሜን ባሻገር” በሚል ርእስ ያሳተመውን መፅሃፍ አነበብኩት። እንደተለመደው ጥሩ ተራኪ ነው። በዚህ ባዲሱ መፅሃፉ በዕውቀቱ ስለማንነቱ ያሰፈረው አዲስ መረጃ ግን ቀደምት ስራዎቹን ወደ ሁዋላ ተመልሼ እንዳገላብጥ አስገድዶኛል። በዕውቀቱ ባለተሰጥኦ ነው። ተፈጥሮ ብእረኛነትን ያለስስት ያስታቀፈችው ድንቅ የዘመናችን ገጣሚ ነው። በተለይ በአጫጭር ስነግጥሞቹ የሚያነሳቸው ጭብጦች አስደማሚ ስለመሆናቸው ብዙ ተነግሮለታል። ለአብነት ሙስናን በአምስት መስመሮች ብቻ የገለፀበት መንገድ የቅኔ ችሎታውን ፍንትው አድርጎ ያሳያል፣
እልፍ ከሲታዎች – ቀጥነው የሞገጉ
“ስጋችን የት ሄደ?” – ብለው ሲፈልጉ
በየሸንተረሩ – በየጥጋጥጉ
አስሰው አስሰው – በምድር በሰማይ
አገኙት ቦርጭ ሆኖ – በአንድ ሰው ገላ ላይ
የእነዚህ ስንኞች ገጣሚ እኔ ብሆን ኖሮ ፑሽኪንን እንቀው ነበር። በዕውቀቱ በእነዚህ ስንኞች ከህዝብ የዘረፉትን በቢሊዮን የሚገመት ዶላር ባንክ ውስጥ ስለደበቁ ባለስልጣኖች በቀላል መንገድ ነበር የነገረን። በዕውቀቱ ድፍረቱ የበረታ ነው። ገጣሚነቱ ቃላት አሳክቶ ቤት መምታቱ አይደለም። ነባር አስተሳሰቦችን የመሞገትና በተለየ መንገድ የማየት ልዩ ችሎታ አለው። በተለይም በሃይማኖት ጉዳይ ላይ ትኩረት ያደርጋል። ኢአማኒ መሆኑ ሃይል ሆኖ ሳያግዘው አልቀረም። “ከአሜን ባሻገር” ላይ እንደነገረን ለፈጣሪ ከመስገድ የተላቀቀው ሲግመንድ ፍሮይድን ካነበበ በሁዋላ ነው። ሆኖም የአክራሪ ህብረተሰብ ባልደረባ መሆኑን በመዘንጋቱ ዋጋ ከፍሎበታል። የመፅሃፍ ቅዱስን ትረካዎች እያነሳ ከሚተርብባቸው ግጥሞቹ መካከል “ዳዊትና ጎልያድ” ይጠቀሳል።
እግዜርና ዳዊት – አብረው ተቧደኑ
ብቻውን ታጠቀ – ጎልያድ ምስኪኑ
አንዳንዱ ተገዶ – ለሽንፈት ሲፈጠር
በጥቅሻ ይወድቃል – እንኳንስ በጠጠር
ተቀባይነት አጊኝተው የቆዩ እምነቶችን ገልብጦ በማሳየት ረገድ በዕውቀቱ የተሳካለት ገጣሚ ነው። “ትንሹ ዳዊት ግዙፉን ጎልያድ አሸነፈው” ብለን እናምን ነበር። ከዳዊት ጀርባ ተሸሽጎ ጎልያድን የገነደሰውን አምላክ በፍልሚያው ውስጥ በማስገባት ነባር እምነታችን ላይ ጥያቄ ምልክት እንድናስቀምጥ ያደርገናል። ቀላል አቅም አይደለም። ሌሎች ብእረኞችም በእየሱስ ታሪክ ላይ ተመሳሳይ ጥያቄዎችን ያነሳሉ። ካህሊል ጊብራን ለይሁዳ ወገናዊ ሆኖ ፅፏል። እየሱስ ወደ ምድር ሲመጣ በምናውቀው መንገድ እንዲሞት ተወስኖ ከነበረ፣ ይሁዳ አሳልፎ እንዲሰጠው ተወስኖ ከነበረ ለምንድነው ይሁዳን አንደከሃዲ የምንቆጥረው? በዕውቀቱ እንዲህ ያሉ ተገላቢጦሽ እውነቶችን በኮሚክ አቀራረብ በመተረክ ረገድ የተሳካለት ገጣሚ ነው። ለአብነት ዲዮጋንን የተቸባቸው ስንኞች አስደማሚ ናቸው።
ውሻው ዲዮጋንን – እዩት ተጃጅሎ
በከንቱ ይጮሃል – “ሰው የት አለ?” ብሎ
ሰው ሰራሹን ፀሃይ – በጣቱ አንጠልጥሎ
በዕውቀቱ “ከአሜን ባሻገር” የሚል መፅሃፍ ፅፎ እስኪያሳትም ድረስ የጎጃም አማራ ይመስለኝ ነበር። “ስምና ማንነት” የምትለውን ምእራፍ ሳነብ ግን በዕውቀቱ መሰረቱ ኦሮሞ መሆኑን አወቅሁ። በመግቢያዬ እንደገለፅኩት የዚህን ወጣት ገጣሚ ስራዎች መለስ ብዬ ለማየት የተገደድኩት ከዚሁ ማንነቱ ጋር በተያያዘ ግጥሞቹን ለመመርመር ነበር። በርግጥም ከዚህ ቀደም ትርጉም አጥቼላቸው ለነበሩ ከጥቂት በላይ ስንኞቹ አሁን ምክንያት አገኘሁላቸው። ወደ ግጥሞቹ ከመግባቴ በፊት ግን በዕውቀቱ ስለማንነቱ የገለፀውን ባጭሩ ልጠቃቅስ።
አያቱ አቶ በዳዳ ይባላሉ። ጅባት እና መጫ (አምቦ) ተወልደው ጋርዱላ የተባለ አካባቢ ኖረዋል። አያቱ ጥቂት ልጆች ወልደው ሲሞቱ አባቱንና ወንድሞቹን የማሳደግ እጣ እናቱ ቀደም ሲል ከሌላ ከወለዱት ወንድማቸው እጅ ላይ ወደቀ። የአያቱ ስም የተቀየረው በዚህ ጊዜ ነበር። በዕውቀቱ ይህን ሁኔታ ሲገልፅ፣
“አባቴ በመጀመሪያ አባቱን አጣ። ቀጥሎ የአባቱን ስም አጣ።” ሲል አስፍሮአል።
በዕውቀቱ ስለ ዘር ጉዳይ አንስቶ በመፅሃፉ ከማካተቱ በፊት ከራሱ ጋር ጥቂት ሳይሟገት አልቀረም። አጎቱ አቶ አማረ፣ “ስለዘርና ስለሃይማኖት በመፃፍና በመከራከር ጊዜህን አታጥፋ” ብሎ ቢመክረውም ምክሩን ባለመቀበል ይህንን ምእራፍ ለመፃፍ እንደበቃ አስፍሮአል።
አባቱ አቶ ስዩም “በዳዳ” የሚለውን የአባታቸውን ስም ለመቀየር ፈቃደኛ እንዳልነበሩ ለበዕውቀቱ ነግረውታል። የአሳዳጊ ግማሽ ወንድማቸውን ፍላጎት መጋፋት ግን አልቻሉም። በርግጥ “በዳዳ” የሚለው ቃል በኦሮምኛ ትርጉሙ፣ “የበለፀገ ወይም ሃብታም” ማለት ነው። ይህ ቃል ግን በአጋጣሚ በአማርኛ መዝገበ ቃላት ውስጥ ብልግና ተብለው ከተመዘገቡ ቃላት ጋር ይቀራረባል። ስለዚህ ይህንን ስም ይዞ አማሮች ወደ በዙበት ትምህርት ቤት መሄድ የሚያደርሰውን ጉዳት የአቶ ስዩም አሳዳጊ ተገንዝበውት ሊሆን ይችላል። በዕውቀቱ ግን በዚህ አይስማማም። ጉዳዩን ቀለል አድርጎ “ህያውነት ነው” ይለዋል። በዕውቀቱ በኢትዮጵያዊነቱ ብቻ መጠራት እንደሚፈልግ ከፅሁፎቹ ተረድቻለሁ። ለነገሩ በመፅሃፉ የአያቱን ጉዳይ ማንሳቱ በአስረጅነት እንጂ ስለዘር ጉዳይ ለመነጋገር አይደለም።
በዕውቀቱ የአያቱ ስም “ከበዳዳ ወደ መሰለ” የተለወጠበትን ምክንያት ለማወቅ ጥቂት ጉዞዎችን አድርጎአል። “በዳዳ የሚለው ስም ከአባቴ አባትነት ለምን እንዲቀየር ተፈለገ? በዘመኑ የፖለቲካ ጫና ወይስ በህያውነት” ሲል ቢጠይቅም ለዚህ ጥያቄ ግን ምላሽ አያገኝም። አዲሳባ ኗሪ የሆነ አማረ የተባለ አጎቱ ስቆ ብቻ ዝም አለው። የአጎቱ ስቆ ዝምታ በዘር ፖለቲካ ላይ ለመነጋገር ባለመፈለግ ይመስላል። አጎቱ፣ “ሰዎች በውይይት የሚግባቡበበት ዘመን እስኪመጣ አርፈህ ግጥምህን ፃፍ” ሲል ይመክረዋል።
በዕውቀቱ ግን የአጎቱን ምክር አልሰማም። በዳዳ የሚለው የአያቱ ስም ለምን እንደተቀየረ ለማወቅ ፍለጋውን ቀጠለ። ስም ቀያሪ ትልቅ አጎቱን ለመጠየቅ እስከ አለታ ወንዶ ቢጓዝም ምክንያቱን አልነገሩትም። በመቀጠል አባቱን ለመጠየቅ መንኩሳ ሄደ። አባቱ ግን ሸፋፈኑበት። ዝምታን መረጡ። በዕውቀቱ አልተዋቸውም። በዳዳን ትቶ መሰለ የሚለውን ስም ይዞ አባይን መሻገሩ ለተቀባይነቱ ጠቅሞት እንደሆን በቀጥታ አባቱን ጠየቀ። አባቱ መልስ ከመስጠታቸው በፊት ውጥረቱን ለማርገብ አክስቱ ጣልቃ ገብታ ተቆጣች። ኦሮሞ በጎጃም የተከበረ መኳንንት መሆኑን ተናግራ ጉዳዩን ቋጨችው። በመግቢያዬ እንደገለፅኩት የበዕውቀቱ ሽሽግ ማንነት በቀደምት ስነግጥሞቹ ውስጥ ተንፀባርቀው እንደሆን ለማየት መለስ ብዬ ስራዎቹን ፈታትሼ ነበር። ከምስጢራዊ ስንኞቹ መካከል ጥቂት አገኘሁ፣
በነፍሴ ሰማይ ላይ
ቢሰርቅ ጣምራ ፀሃይ
አንዱን ጋርጃለሁ
ሌላው ደምቆ እንዲታይ
“ምን ማለቱ ነው?” ብዬ ሳስብ “የአቶ በዳዳን ኦሮሞነት ሸሽጎ አያቱ ባልሆነ ስም እየተጠራ መቀጠሉን እየተቃወመ ይመስላል” አልኩ። “አንዱን ጋርጃለሁ – ሌላው ደምቆ እንዲታይ” የሚለው ኦሮሞነቴን ደብቄ ሌላ መስዬ እየታየሁ ነው የሚል ትርጉም የያዘ መሰለኝ። እንግዲህ እኔ እንደገባኝ ነው። በእውቀቱ ቢጠየቅ ግጥሞቹን የቋጠረበትን ሌላ ምክንያት ሊሰጥ ይችላል። ስለዚህ የኔን አስተያየት ስታነቡ የአንባቢ መብቴን ተጠቅሜ እንጂ የበዕውቀቱ ልብና አንጎል ውስጥ ገብቼ ያሰበውን ለማወቅ እንደማልችል ከወዲሁ ላሰምርበት እፈልጋለሁ። በዕውቀቱ በዚህ አላበቃም፣
ቀንድ አውጣ ሆይ!
ውብ ዛጎልህ አማለለኝ
ከጎጆህ ላስወጣህ ነው (ይቅር በለኝ)
‘በዝግ አለም – ሰማይ ጣራ ነው’ ይባላል
ያለውበት ነውንጂ – ያለቤት መኖር ይቻላል
እነዚህ ስንኞች ለኔ የሰጡኝ ትርጉም፣ በዕውቀቱ አቶ በዳዳን ከተሸሸጉበት ዛጎል ጎትቶ ለማውጣት መወሰኑን ነበር። በርግጥም እንደፎከረው ፈፅሞታል። ያለ ውበት መኖር እንደሚቻል ለማሳየት ሞክሮአል። አያቱ በዳዳ መሆናቸውን ሲገልፅ በከበበው ማህበረሰብ አመለካከት ውበቱ እንደሚቀንስ የግድ ያውቃል። ከዚህ በሁዋላ ሌሎች ወገኖች በዕውቀቱ ባለበት ስለ ኦሮሞ ለማንሳት ቃላት መምረጥ ሊኖርባቸው ነው። በዕውቀቱ አያቱን ከተሸሸጉበት አውጥቶ ለነፃነት ከማብቃቱ በፊት በዚሁ ቁጭት የፃፋቸው የሚመስሉ ስንኞችን ማስተዋል ችዬ ነበር። ለአብነት በአንድ ግጥሙ ኦሮሞ – አማራንና ትግሬን በገፀባህርይነት ያመጣና እንዲህ ሲል ያላግጣል፣
በታሪክ ሜዳ ላይ
አሉላ ጎበና
ወንዱን አስከትለው – ሲገድሉ ሲሞቱ
አባ ገብረሃና
እርስዎ ባይኖሩ – ምን ይውጠው ሴቱ?
ጨመረልኹ መሰል – ባባ ነፍሶ ፈንታ
እንደ አንደበትዎ – እንትንዎ መንታ
አንዱ ለቀን ሲሆን – አንደኛው ለማታ
“ባባ ነፍሶ ፈንታ” ማለቱ ባልቻ አባነፍሶ ስልብ ነበሩ ስለሚባል ሲሆን፤ “እንትንዎ መንታ” ማለቱ ደግሞ አለቃ ገብረሃናን እንደ ምላስዎ መሾል (የቀጣፊነት ችሎታ) ሁለት ብልት ይዘዋል ማለቱ ነው። ሌሎች ጦር ሜዳ ሲሞቱ እርስዎ ውሎና አዳርዎ ከሴት ጋር መዳራት ነው ማለቱ ነው። በዕውቀቱ እንዲህ በመረረ ሁኔታ ሊሳለቅ የቻለው ምን ተሰምቶት እንደሆን ባውቅ በጣም ደስ ባለኝ ነበር። በተለይ ገዢዎች ላይ ቅሬታና ቂም እየያዘ እንደመጣ የሚጠቁሙ ከጥቂት በላይ ስንኞቹን ታዝቤያለሁ። አንዷ እንዲህ ትላለች፣
አልወጣም ተራራ – ደመናውን ላብስ
ቀስተደመናውን – ሽቅብ ልቀለብስ
አልዋስም እኔ – ካቡነ ተክሌ ክንፍ -ከያ’ቆብ መሰላል
እኔ መውጣት ሳስብ – ሰማዩ ዝቅ ይላል
ዝቅ ይላል ያለው ሰማይ ስልጣን ነው። የትኛው ስልጣን እንደሆነ ግን አልገባኝም። የወያኔን ማለቱ ይሆን? ወይስ የወደቀውን የፊውዳል ስርአት አመለካከት? በእውነቱ አልገባኝም። ቁልቁል ይቀለበሳል ያለው ቀስተደመና ግን የኢትዮጵያ ባንዴራ ነው። የአቡነ ተክሌ ክንፍና የያእቆብ መሰላል ያላቸው ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያንን ሊሆን ይችላል። በዕውቀቱ ከሁሉም ለይቶ ተክልዬ ላይ መቀለድ ይወዳል። ምክንያቱን አላውቅም። በዚህ ግጥሙ ግን በባንዴራው፣ በቤተክርስትያን እና ከፍ ባለው የአመለካከት ስልጣን ላይ ርግማኑን ያወረደ ይመስላል። ርግጥ ነው፤ ስነግጥሞች ብዙውን ጊዜ ለትርጉም ክፍት ስለሆኑ አንባቢ በራሱ መንገድ የመረዳት መብት አለው።
የበዕውቀቱ ቀደምት ግጥሞች “ከአሜን ባሻገር” ላይ ከተጠቀሱት አቶ በዳዳ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማየት ሞክሬያለሁ። በዕውቀቱ የመፅሃፉን ርእስ ለምን “ከአሜን ባሻገር” ሲል እንደሰየመው ምስጢር አልነበረም። በቀጥታ ከአያቱ ከአቶ በዳዳ ጋር ይያያዛል። እሱም በዚያው ምእራፍ ላይ እንዲህ ሲል ገልፆ ነበር፣
“የተለያዩ ባህሎችን በአንድ በገና ውስጥ እንደተወጠሩ አውታሮች ማስተናገድ በማይታወቅበት ጥንታዊ ማህበረሰብ ውስጥ ግለሰቦች የገናና ባህሎችን ምልክት አሜን ብለው ከመቀበል ያለፈ ምርጫ አልነበራቸውም።”
እና “ሉአላዊነት” የሚል ግጥሙ ብሶት ያዘለ ነበር፣
የጋራችን አለም – የጋራችን ሰማይ
የብቻችን ህመም – የብቻችን ስቃይ
ደመናው እንዴት ይታይ
ሸፍኖት ሰንደቅ አላማው
ሸፍኖት ብሄራዊ መዝሙሩ
ብሄራዊ ልቅሶውን ማን ይስማው?
ከእናቴ፣ ከአባቴ፣ ከወንድም ከእህቴ
ከወዳጅ ጠላቴ
የእንባ ጡብ ሰብስቤ
ሽቅብ ደራርቤ
የሰራሁት ህንፃ – መቸም አልፈረሰ
ሚፈርስም አይመስለኝ – ምፅአት ካልደረሰ
“ከአሜን ባሻገር”ን ሳነብ ገጣሚው ውስጡ የሚቃጠል ባህር ሆኖ ተሰማኝ። ባህሩ የእንባ ጥርቅም መሆኑን ራሱ ነው የነገረን። ምን ቢሆን ነው በዕውቀቱ ልቡ ውስጥ የእንባ ኩሬ ያጠራቀመው? ምንድነው ከውስጡ የሚጮኸው? ምንድነው በቀጥታ መናገር ያልቻለው? በአንድ ሰማይ – በአንድ አገር ስር ዜጎች አብረው እየኖሩ፤ ላንደኛው ወገን ስቃይ እንደሆነበት ሲነግረን አልገባ ብሎን ይሆን? የኦሮሞ ህዝብ ላይ ሚዛን ያጣ ወቀሳ ከሚያዥጎደጉዱ ሰዎች መሃል ተቀምጦ የውሸት ሳቅ መሳቅ ሰልችቶት ይሆን ማንነቱን ይፋ ለማድረግ የተገደደው? የትልቅ አጎቱና የአባቱ ዝምታ አስጨንቆት ይሆን የሚከተለውን ግጥም የፃፈው?
አዳኝ በንስሃ – ሰይፉ አልዶለዶመም
ታዳኝ በፀሎቱ – ካራጆች አልዳነም
ተኳሹ ቢዋልል – አልመታ ቢል ተኩሱ
ካፈሙዝ ይጠጋል – ኢላማው እራሱ
“ከአሜን ባሻገር” ላይ በዕውቀቱ ልጅነቱን በተመለከተ ጥቂት ያነሳል።
“…ከተወለድኩበት ቤት ግርጌ የሚንቆረቆረው፤ ቀይ አቧራዬን ከእግሬ ላይ ያስለቀቅሁበትን ደቦሆላ የተባለው ወንዝ የአማርኛም ሆነ የግእዝ ትርጉም እንዳለው ለማረጋገጥ ሞክሬ አልተሳካልኝም። ለካ ደቦሆላ በኦሮምኛ Daboolaa (የተከደነ) ማለት ኖሮአል?…” ሲል አስፍሮአል።
የበዕውቀቱ የትውልድ መንደር መንኩሳ ትባላለች። መንኩሳ ራሱ ቃሉ ኦሮምኛ መሆኑን አልደረሰበትም መሰለኝ አላነሳውም። “መና” ማለት “ቤት” ማለት ነው። “ኩሳ” ደግሞ “ማከማቻ” ነው። “ማከማቻ ቤት” ወይም “መጋዘን” እንደ ማለት ነው።
በዕውቀቱ በመፅሃፉ አንዳንድ ታሪካዊ ሁኔታዎችን እያነሳ ለመሞገት ሞክሮአል። አብዛኛው ጥናታዊ እና የታሪክ ትንተና ጉዳይ ነው። ፕሮፌሰር መሃመድ ሃሰን እና ፕሮፌሰር አስመሮም ለገሰ ስለ ኦሮሞ የሰሩትን የተከበሩ ስራዎች እያጥላላ፣ ‘ይሄ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ እገሌ የተባለው ፈረንጅ በመፅሃፉ ይጠቅሰው ነበር’ ብሎ ሊሞግት ይሞክራል። ይህን መሰል ሙግት መቸም ፈረንጅ የፃፈውን የበለጠ የሚታመን ማመሳከሪያ የማድረግ የአበሻ ፀሃፊያን ልማድ ሆኖአል። የባለታሪኩ ማስታወሻ በእጅ እያለ አንድ ፈረንጅ ከአስጎብኚው የሰማውን የበለጠ ማመን ያስተክዛል።
በዕውቀቱ አጤ ምኒልክ የፈፀሙትን በጎም ሆነ ክፉ ተግባር ከጊዜው ጋር እንዲታይ፣ እርሳቸው የፈፀሙትን ሌሎችም የወቅቱ ነገስታትና መሪዎች እንደፈፀሙት ለማሳየት መሞከሩ በርግጥ ለአብሮ መኖር የሚበጅ በመሆኑ ተገቢ ነው። ‘የአኖሌ የጡት ቆረጣ ታሪክ እውነት አይደለም’ ሲል ማስተባበሉ ግን መረጃ የለውም። እንደተለመደው ‘ጡት ተቆርጦ ቢሆን ኖሮ እገሌ ይፅፈው ነበር።’ አይነት ክርክር ነው። የፕሮፌሰር መሃመድ አባስን መፅሃፍ እንኳ ያነበበ አይመስለኝም። “የቡርቃ ዝምታ” ታሪክ ቀመስ ልቦለድ እንደመሆኑ ገፀባህርያት የሚናገሩትን እንደ ደራሲው አቋም መውሰድ ልክ አለመሆኑን በዕውቀቱ አያጣውም። መቸም ችግር ነው፤ የከበበውን ስሜታዊ ማህበረሰብ ለማስደሰት ያደረገው ይሆናል።
“የጁገል ልባዊ ወግ” በሚል ርእስ የፃፍኩትን ትረካም በዕውቀቱ ይጠራጠረዋል። ለማረጋገጥ ግን ቀላል ነው። ጁገል ሄጄ ያነጋገርኳቸው እናት አመቱላ ሻሽ አቦኝ ሞተው ከሆነ ዘመዶቻቸው ይኖራሉ። የሃረሪ አዛውንቶች ታሪካቸውን ሲናገሩ ከአንድ ምንጭ እንደሚቀዳ ውሃ ይዘቱ አንድ ነው። የሃረሪ የታሪክ አባት ብዬ የጠቀስኩት አብዱሰመድ እድሪስ ተራ ሰው አይደለም። በዕውቀቱ ሊያናንቀው ሞክሯል። ስለማያውቀው ነውና አልፈርድበትም።
ይልቁን በእውቀቱ ስለ ጎጃም ነባር ጌቶች የተረከው ተነባቢ ነው። የጎጃም መስራች አባት ኢቢዶ የሚባል የቦረና ኦሮሞዎች መሆናቸውን የተሻለ ምንጭ አጣቅሶ ተንትኖአል። ኢቢዶ ከወለጋ ከብት እየነዳ ወደ ጎጃም ከገባ በሁዋላ ለጎጃም ስርወ መንግስት መሰረት መጣሉን ያብራራል። በዕውቀቱ በትረካው ደጃዝማች ጎሹ ኦሮሞ መሆናቸውን ጠቅሶ ሲያበቃ፤ የጎሹ ልጆች ኤሌምቱ፣ ዶሪ፣ ተሰማ ይባሉ እንደነበር ይገልፃል። ሁዋላ ንጉስ ተክለሃይማኖት የተባሉት እንግዲህ የተሰማ ጎሹ ልጅ ‘አዳል ተሰማ’ ናቸው። ኦሮሞ በጎጃም “መኳንንት” የመሆኑ ጉዳይ በሰነዶች የተረጋገጠ መሆኑን አብራርቶአል። በእውቀቱ በትረካው፣ ጎጃም ውስጥ የሚገኙ ወረዳዎችን በመዘርዘር ግዛቱ በኦሮሞዎች እንደተመሰረተ ያብራራል። ካሰፈራቸው ስሞች መካከልም ባሶ፣ ሊበን፣ ጂጋ፣ ቡሬ፣ ሶማ፣ ዲማ፣ ኢልማና ዴንሳ፣ መጫ ይጠቀሳሉ። ባህርዳር ራሷ መጫ ስር መሆኗን ግን አልጠቀሰም። የበዕውቀቱ ትንተና ዶክተር መረራ ጉዲና “ጎጃም ኦሮሞ ነው” ከሚለው ጋር ይመሳሰላል። በእርግጥ እንዲህ ያለ ወግ ወያኔ ፊት ማውራት ጥሩ አይመስለኝም። ያላሰቡትን ማሳሰብ ይሆናል። “እንኳን ባሩድ ሸቶሽ፤ እንዲያውም ጠርሙስ አረቄ ትጨርሺያለሽ” እንዲሉ እንዳይሆን።
እንግዲህ በዕውቀቱ ስዩም በነገረን አዲስ ማንነቱ መሰረት በተለይ በአማራና በኦሮሞ ህዝቦች መካከል የሰላምና የትብብር ወንዝ እንዲፈስ አስተዋፅኦ ማድረግ ይጠበቅበታል። ዳር ላይ በመቆም “እገሌ ሊያጋጨን ይህን ፃፈ” እያሉ ሌላው ላይ ጣት ከመቀሰር ተላቀው እንደ ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ በር ከፋች ሚና መጫወት የበለጠ ውጤት ያስገኛል። በዕውቀቱ አቡነ ተክልዬን በመተረቡ የደረሰበትን የቡጢ አደጋ በማስታወስ መስጋት ያለበት አይመስለኝም። መቸም በአንክል ሳም አገር ህግ መሰረት በአያት መጠራት ደንብ ስለሆነ “ኢጆሌ በዳዳ” ማለት ቢጀምር፤ የአድናቂዎቹ ቁጥር ከግራም ከቀኝም ይጨመርለታል። ቀልዳዊ ፅሁፎች ቀልቡን ከሚስቡት “ከአሜን ባሻገር” ላይ እንደጀመረው ለአገርና ለህዝብ የሚጠቅም ስራ ቢሰራ መንፈሱን የሚያረካው ይመስለኛል።
በመጨረሻ የዘመናችን ገጣሚ በዕውቀቱ ስዩም በቋጠራት አንዲት አስቂኝ ቅኔ ልቋጭ። አስቂኝ እንኳ አይደለችም። እንደ ካራሜላ ጣፋጭ ናት። “ፍካሬ እውነት” በሚል ርእስ የቋጠራት ስትሆን፤ እንዲያው ሳስባት የኢትዮጵያን ሚዛን ያጣ ታሪክ አፃፃፍ ለማሳየት የተቋጠረች የ’ሳትዳር ወግ ትመስለኛለች።
“ሰማዩ!
እንዲህ እንደዛሬው ርቆ ሳይወረወር
ሁሉ ‘ንዳሻው ሚቆርሰው
ሁሉ ‘ንዳሻው የሚጎርሰው
ግዙፍ እንጀራ ነበር”
ብለሽ የነገርሺኝን እውነት ነው ተቀብያለኹ
ምክንያቱም ወድሻለኹ
“አያቴ
ሶስት መቶ አመታት ኖሩ
የመቶ አመት ሰው እያሉ
ብርቱ ፅኑ ነበሩ
ዝሆን በጥፊ ጣሉ
አንድ ጥይት ተኩሰው ሶስት ነብሮች ገደሉ”
ብለሽ የነገርሺኝን እውነት ነው ተቀብያለኹ
ምክንያቱም ወድሻለኹ
“አባቴ
ከሰዎች ሁሉ ይለያል
ባይኖቹ ብቻ ሳይሆን በማጅራቱም ያያል”
ብለሽ የነገርሺኝን እውነት ነው ተቀብያለኹ
ምክንያቱም ወድሻለኹ
ግና ጅል እንዳልመስልሽ አይደለሁም ተላላ
በርግጥ በጄ ብላሻለች ነፍሴ ሁሉን ተቀብላ
እውነት ማለት ከሚወዱት መስማማት‘ንጂ
አይደለምና ሌላ…
Source:- https://www.facebook.com/ttgebreab/posts/10205493725844203