Category Archives: Social and Culture

በኢትዮጵያ የጥራት ጉድለት የተገኘባቸው 69 ሚሊየን ኮንዶሞች ተገኙ

በያዝነው 2008 ዓ.ም. ሁለተኛ አጋማሽ የጥራት ጉድለት የተገኘባቸው 69 ሚሊየን ኮንዶሞች ሊወገዱ ነው።
ከግሎባል ፈንድ በተገኘ ከ2 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር የተገዙት ኮንዶሞች፥ በኢትዮጵያ የምግብ መድሃኒትና ጤና አጠባበቅ ቁጥጥር ባለስልጣን ፍተሻ የጥራት ችግር እንዳለባቸው ተጋግጧል።

Condoms

ኮንዶሞቹ ከሁለት ወራት በፊት በተደረገ ፍተሻ መያዛቸው ነው የተገለጸው። የመድሃኒት ፈንድና አቅርቦት ኤጀንሲ ዋና ዳይተሬክር አቶ መስቀሌ እንደተናገሩት፥ የኮንዶሞቹ አቅራቢ ድርጅት ለግዢ የወጣውን ገንዘብ እንዲተካ የማድረግ ስራ እየተሰራ ይገኛል።
ኮንዶሞች ለገበያ ከመቅረባቸው በፊት ጥብቅ የጥራት ፍተሻ እንደሚደረግላቸው ያነሱት ዳይሬክተሩ፥ ይህ ስራም ጥራቱ ተረጋግጦ ገበያ ላይ ከዋለ በኋላ በአያያዝ ምክንያት ሊደርስ የሚችል ችግርንም እስከ መፈተሽ ድረስ የሚከናወን ነው ብለዋል ሲል ፋናቢሲ ዘግቧል፡፡
ጥራት የጎደላቸው 69 ሚሊዮን ኮንደሞች በአንድ የህንድ ኩባንያ አማካኝነት በኢትዮጵያ መሰራጨታቸውን በተመለከተ ቀደም ሲል ዋዜማ ሬዲዮ መዘገቡ ይታወሳል፡፡

የተሰራጩት ኮንዶሞች ጫፋቸው የተቀደዱ፣ ፈሳሽ እና አየር ማሳለፍ የሚችሉ፣በላዩ ላይ ያለው ማለስለሻ ቅባት ከሰውነት ፈሳሽ ጋር ሲደባለቅ የጤና ችግር የሚፈጥር እንደሆነ በተደረገ ምርመራ መረጋገጡ ተጠቁሟል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በነበረው ተቃውሞ ከ400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ሂውማን ራይትስ ዎች ይፋ አደረገ

ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች ከ400 በላይ የሚሆኑ ሰልፈኞችን የገደሉ ሲሆን ከአስር ሺህ በላይ የሚቆጠሩትን ደግሞ ማሰራቸውን አስታውቋል፡፡ የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ “የኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ እስራቶችንና ሌሎች የመብት ጥሰቶች በአስቸኳይ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኛ የሆነ ማጣሪያ እንዲካሄድ ድጋፍ ማድረግ አለበት።” ሲል ባለ 61 ገፅ ሪፖርት ይፋ አድርጓል፡፡

HRW logo

ድርጅቱ ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው ባለ 61 ገጽ ሪፖርት “ጭካኔ የተሞላበት አፈና’ – የግድያ እና የእስራት ምላሽ፤ ለኢትዮጵያ የኦሮሞ ተቃውሞ” የሚል ነበር፡፡ መንግሥትም በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ ርምጃ መውሰዱን በመግለፅ ድርጊቱን አውግዟል፡፡ ሪፖርቱ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ እንዲሁም ሀሳባቸውን በነጻነት በሚገልጹ ዜጎች ላይ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን፣ ከ125 በላይ የሚሆኑ የተቃውሞ ሰልፎች ተሳታፊዎችን፣ ጉዳዩን በአንክሮ ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦችን፣ በተለያዩ ጊዜያት የመብት ጥሰት የተካሄደባቸውና ጉዳት የደረሰባቸውን ግለሰቦች ያካተተ ቃለ መጠይቅ ማድረጉንም አስታውቋል፡፡

በመንግሥት የተቋቋም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮምሽን ይህንን የኦሮሚያ ክልል ተቋውሞ ተከትሎ በተወሰደ ርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 173 ብቻ መሆናቸውን እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃም “ተገቢና ተመጣጣኝ” ነው ሲሉ ኮሚሽነሩ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ሰኔ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. “ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት” እና ለጋዜጠኞች ገልፀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ተገቢና ተመጣጣኝ ያሉት ርምጃ የተወሰደው በመከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል መሆኑንም ለጋዜጠኞች ጠቁመዋል፡፡

Oromo Protest_Ethiopia

መንግሥታዊ ያልሆነው ሀገር በቀል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፤ በኦሮሚያ ክልል በነበረው ተቃውሞ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃ ተገቢና ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ቀደም ሲል ይፋ ባደረገው ዝርዝር ሪፖርት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በነበረውን ተቃውሞ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ፤ ሀገር በቀል የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ባለፈው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም በመግለፅ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

ሙሉውን የሂውማን ራይትስ ዎች ሪፖርት እዚህ https://www.hrw.org/news/2016/06/15/ethiopia-protest-crackdown-killed-hundreds  ያገኙታል፡፡

የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ወደ ሐምሌ 4 ተራዘመ

(አዲስ ሚዲያ)  ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ተራዘመ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር ባለፈው ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ሊሰጥ የነበረው ፈተና መከካከል ሁለት የትምህርት ዓይነቶች ቀድመው በማኀበራዊ ሚዲያ ከነመልሶቻቸው መለቀቃቸውን ተከትሎ እንዲቋረጥ የተደረገው ፈተና ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ለመስጠት ትምህርት ሚኒስቴር መርሃ ግብሩን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ቅሬታና ተቃውሞ አስከትሎ ነበር ፡፡

Ethiopian Minstry of education
በተለይ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. መካከል የረመዳን ፆም ፍቺ በዓል ላይ የሚውል ተቃውሞ በመቅረቡ፣ ትምህርት ሚኒስቴርም ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ቅሬታ በመቅረቡ ፈተናው በአንድ ሳምንት ተራዝሞ ከሐምሌ 4-7 ቀን 2008 ዓ.ም. እንደሚሰጥ አስታውቋል ፡፡

ቀደም ሲል ግንቦት ሊሰጥ የታሰበውን መርሃ ግብር እንዲቀየር ያስገደዱት የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎችም ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚሰጠው አዲሱ መርሃ ግብር ላይ ሌላ ተቃውሞ እንደማያስነሱና ከባለስልጣናቱ ጋር እልህ መጋባቱ አላስፈላጊ መሆኑን በመጥቀስ፣ ተማሪዎች ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚሰጠውን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተረጋግተው እንዲፈተኑ ጠይቀዋል፡፡

ትምህርት ሚኒስቴር እና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች በየበኩላቸው በየአካባቢው ያሉ መምህራን፣ ወላጆች፣ አስተዳደሮች እና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ ለተማሪዎች እንዲያደርጉላቸው የትብብር ጥያቄ አቅርበዋል፡፡

 

የሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አል-ሸባብ 43 የኢትዮጵያ ወታደሮች መግደሉን አስታወቀ

(አዲስ ሚዲያ) አል-ሸባብ ጥቃቱን የፈፀመው ከዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ በስተሰሜን 300 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሃልገን ከተማ፤ የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ልዑክ( አሚሶም) አባል በሆኑ የኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ መሆኑን ሮይተርስ እና አል-ጀዚራን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡

Ethiopian troops in Somalia

በተለይ የታጣቂ ቡድኑ ወታደራዊ ክንፍ ቃል አቀባይ ሺክ አብዱዓሲስ አቡ ሙሳብ ለሮይተርስ እንደገለፁት ከሆነ፤ ትናንት ሐሙስ ሰኔ 2 ቀን 2008 ዓ.ም. በማዕከላዊ ሶማሊያ ሂራን ክልል ከተማ በሆነችው ሃልገን በፈፀሙት ጥቃት 43 የኢትዮጵያ ወታደሮችን መግደላቸውን፣ ቁጥሩን በይፋ ባይገልፁም በነበረው ውጊያ ከራሳቸው ከታጣቂ ቡድኑም የተገደሉ እንዳሉ አረጋግጠዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ በቃል አቀባዩ በኩል በኢቢሲ በኩል ባስተላለፈው መግለጫ 245 የአልሸ-ሸባብ ታጣቂዎችን መግደሉን ቢያስታውቅም፤ በውጊያው ምን ያህል የኢትዮጵያ ወታደር እንደተገደለ የገለፀው ነገር የለም፡፡

የኢትዮጵያ ጦር በኢህአዴግ ውሳኔ ወደ ሶማሊያ ከገባ ጀምሮ በርካታ ወታደሮች እንደተገደሉና ጉዳት እንደደረሰባቸው በተወሰነ ደረጃ ታጣቁ ቡድኑ በተለያየ ጊዜ ካሰራጨው የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ወታደሮች ስም እና ማንነት በስተቀር፤እስካሁን በኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ ስለደረሰ ጉዳት በመንግሥት በኩል ለህዝብ የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ የለም፡፡ ይሁን እንጂ ለተመሳሳይ ተልዕኮ በአፍሪካ ህብረት አሚሶም የተሰማሩ የኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ጅቡቲ ወታደሮች ከአል-ሸባብ ጋር በተደረጉ ውጊያዎች የደረሱ ጉዳቶችንም ሆነ ድሎች በተለያየ ጊዜ ለህዝባቸው ሲገልፁ ተስተውሏል፡፡

የኢህአዴግ መራሹ መንግሥት በይፋ ወታደሮቹን ወደ ሶማሊያ ካዘመተ ከ7 ዓመታት በላይ ቢሆንም፤ እስካሁን በኢትዮጵያ ወታደሮች ላይ ስለደረሰው ጉዳት በመንግሥት በኩል ይፋ ተደርጎ ባያውቅም፤ የስርዓቱ ደጋፊ ብሎገሮች በትናንትናው የአል-ሸባብ ጥቃት 9 ያህል የኢትዮጵያ ወታደሮች ሞታቸውን እና 248 የታጣቂው ቡድንም በኢትዮጵያ ወታደሮች እንደተገደሉ ገልፀዋል፡፡

በሐሙሱ የአል-ሸባብ ጥቃት በሶማሊያ ውስጥ ስለተገደሉ የኢትዮጵያ ወታደሮች የኢትዮጵያ መንግሥት ምን የገለፀው ነገር ባይኖርም፤ ጥቃቱን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባን ኪ ሙን በይፋ አውግዘዋል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የቀረበበት ክስ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት አመልክቷል

ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ክሱ ተሰርዞለት በነጻ እንዲሰናበት በክስ መቃወሚያው አምልክቷል፡፡

Getachew Shiferaw_Addismedia

ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው አራት ገጽ ያለው የክስ መቃወሚያውን ለችሎቱ አስገብቷል፡፡

ተከሳሹ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀጽ 7(1)ን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበበት ክስ “በማናቸውም መልኩ በሽብር ተግባር መሳተፍ” የሚለው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመን ድርጅት ስም መጥራት፣ የሽብር ድርጅቱ በሚጠቀምበት ሚዲያ መጠቀም ወይም የሽብር ድርጅት አባል ነው የተባለን ሰው ለሽብር ድርጅቱ አንዳችም ፋይዳ በሌለው ነገር ላይ ማነጋገር ሁሉ ይጨምራል በሚል ተለጥጦ መቅረብ እንደሌለበት በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡

ተከሳሽ አቃቤ ህግ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ስለነበሩ ክስተቶች የሽብር ድርጅት አመራር ናቸው ላላቸው ሰዎች መረጃ ማስተላለፍን በሽብር ድርጅቱ ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ስህተት ብቻ ሳይሆን ከህጉ አላማም በእጅጉ የራቀ ነው ሲል ተከሳሹ ተቃውሟል፡፡

ስለሆነም የአዋጁን አንቀጽ 7(1) ጠቅሶ ክሱን ማቅረብ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕጉ አንቀጽ 112 ላይ በወንጀል ጉዳይ በሚቀርብ ክስ ስለ ወንጀሉ እና የወንጀሉ ሁኔታ ስለሚሰጠው ዝርዝር ወንጀለኛው የፈጸመውን ተግባር ወንጀል ከሚያደርገው ሕግ አነጋገር ጋር የተቀራረበ መሆን አለበት የሚለውን አስገዳጅ ድንጋጌ የሚጥስ በመሆኑ የአዋጁ አንቀጽ መጠቀሱ አግባብ አይደለም ተብሎ ክሱ እንዲሰረዝለት አመልክቷል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው በሁለተኛነት ያቀረበው መቃወሚያ የህጋዊነት መርህን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ ህገ-ወጥነቱ በህግ ያልተደነገገን ድርጊት ወይም ግድፈት እንደወንጀል ሊቆጥረውና ቅጣት ሊወስንበት እንደማይገባ በማስታወስ በክሱ ዝርዝር ላይ የተመለከቱ በህግ ወንጀል ናቸው ተብለው ያልተደነገጉ ድርጊቶችን ጠቅሶ ክሱ እንዲሰረዝለት የሚጠይቀውን መቃወሚያ አስገብቷል፡፡

ተከሳሹ በሦስተኝነት ያቀረበው የመቃወሚያ ነጥብ የተከሰሰበትን ወንጀል ለይቶ በማወቅ መልስ ለመስጠት እንዲያስችለው ግልጽ ሊሆኑለት የሚገቡ ነጥቦችን በመጥቀስ ነው፡፡ በዚህ መቃወሚያ ስር ተከሳሹ ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ እንደተቀበለ ከመጠቀሱ በቀር ተልዕኮው ምን እንደሆነ፣ መቼ፣ ከማን እና በምን አይነት መንገድ ተልዕኮውን እንደተቀበለ ከሳሽ ግልጽ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡ ተከሳሹ ‹‹የሽብር ቡድኑ በሚጠቀምበት ሚዲያ›› በሚል የቀረበበት ክስ በህግ ቋንቋ ምን ማለት እንደሆነም አልተገለጸም ሲል ጠቃውሟል፡፡

በመሆኑም ከሳሽ እነዚህና ሌሎች በመቃወሚያው ላይ የተመለከቱ ነጥቦችን ግልጽ እንዲያደርግ፣ ይህን ማድረግ የማይችል ከሆነ ግን ክሱ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት ተከሳሹ ለችሎቱ በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡
ችሎቱ አቃቤ ህግ ተከሳሹ ያቀረበውን የክስ መቃወሚያ ተመልክቶ መልስ እንዲሰጥበት ለመጠባበቅ ለሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡-EHRP