የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል
ትናንት ቅዳሜ ነሐሴ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በምስራቅ ጎጃም ደብረማርቆስ ከተማ እና ዛሬ እሁድ ነሐሴ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. በሰሜን ወሎ መቄት ከተማ ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ ህዝቡም በነበረው የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ወልቃይት ጠገዴ የአማራ ነው፣ የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ መንግሥት ምላሽ እንዲሰጥ፣ ወልቃይት ጠገዴ ወደነበረበት አማር መመለስ አለበት፣ የህወሓት የበላይነት ይቁም፣ የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች ይፈቱ፣ መብትን መጠየቅ አሸባሪነት አይደለም፣በኦሮሚያ የሚፈሰው ደም የእኛም ደም ነው፣ ፍትህ ለወገኖቻችን፣ ጭቆና በቃን፣…..የሚሉ መፈክሮች በስፋት ተደምጠዋል፡፡

የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ እንዳይደረግ መንግሥት ቀደም ሲል በደህንነቱ እና የፀጥታ ኃይሉ አማካኝነት ከፍተኛ ጥበቃና ማስፈራሪያ ቢያደርግም፤ በተለይ የደብረ ማርቆስ እና አካባቢው ነዋሪ መነሻውን ከከከተማዋ የተለያየ አካባቢ በማድረግ መዳረሻው ወደ ንጉስ ተክለኃይማኖት አደባባይ ሲያደርግ ተስተውሏል፡፡ ይሁን እንጂ መንግሥት የተቃውሞ ሰልፉ መዳረሻ ጋ ከመድረሱ በፊት በህዝቡ ላይ በወሰደው ወታደረዊ ርምጃ 4 ሰዎችን በፅኑ መቁሰላቸው ታውቋል፡፡ መንግሥት ሰልፉን ለመበተን በወሰደው የኃይል ርምጃ የተበሳጩ ሰዎች በሁለት የፀጥታ ኃይሉ ላይ የአፀፋ ርምጃ መውሰዳቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
እሁድ ነሐሴ 8 ቀን በወሎ እና ሰሜን ሸዋ ከተሞች አጠቃላይ የአማራ ተጋድሎ ተቃውሞ ጥሪ መተላለፉን ተከትሎ በሰሜን ወሎ መቄት ከተማ ተመሳሳይ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተደርጓል፡፡ በሌሎች ከተሞችም በተለይ በደሴ፣ ወልዲያ፣ ከሚሴ፣ ኮምቦልቻ፣ ላሊበላ፣ ደብረ ብርሃን፣ ሸዋ ሮቢትን ጨምሮ በሌሎችም የወሎና ሴመን ሸዋ ከተሞች ተመሳሳይ የተቃውሞ ሰልፍ ጥሪ የነበረ ቢሆንም ፤መንግሥት በወሰደው ጥብቅ ወታደራዊ ቁጥጥርና አፈና ምክንያት ህዝቡ መውጣት እንዳልቻለ ተጠቁሟል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውችን ከተክትሎም በአማራ ክልል ባሉ የተለያዩ ከተሞች በርካታ ወጣቶች ከቤታቸውና ከስራ ገበታቸው ላይ እየታፈኑ በመታሰር ላይ መሆናቸውን የአዲስ ሚዲያ ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
የተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ የመጣው የአማራ ተጋድሎ ህዝባዊ ተቃውሞ ባለፈው ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. መነሻውን በሰሜን ጎንደር ያደረገው የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ፣ ወደ ደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር እና ጋይንት ከዚያም ወደ ምዕራብ ጎጃምና የአማራ ክልል መዲና ወደሆነችው ባህርዳር ከተማ መደረጉ አይዘነጋም፡፡ ዘጠነኛ ወሩን ያስቆጠረው የኦሮሚያም ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች እንደቀጠለ ሲሆን፤ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እየጠወሰደ ባለው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ የሚገደሉ፣ የሚቆስሉ እና የሚታሰሩ ዜጎች ቁጥርም እየጨመረ መሄዱ ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ በሁለት ቀናት ብቻ በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ዜጎች ተገደሉ
(አዲስ ሚዲያ) በኢትዮጵያ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እና አማራ ክልል በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል ርምጃ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ በርካታ ሰላማዊ ንፁሃን ዜጎች ተገደሉ፡፡ በተለይ እንደ መብት አራማጆች እና የአካባቢው ምንጮች መረጃ ከሆነ በሁለቱ ቀን የኦሮሚያ እና አማራ ክልል የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ንፁሃን ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡
በተለይ እንደ መብት አራማጆች መረጃ ከሆነ፤መነሻውን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን በማድረግ ወደ ጠቃላይ ሀገራዊ ይዘት የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የኦሮሞ ተቃውሞ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል ባሉ ከተሞች አጠቃላይ በተጠራው የረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ 67 ያህል ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደራዊ ርምጃ ሲገደሉ፤ ከ500 ያላነሱ በፅኑ ቆስለው በክምና ላይ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ትናንት በነበረው የኦሮሚያ ክልል እና የአዲስ አበባ ተቃውሞ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎች መታሰራቸውም ተጠቁሟል፡፡

በትናንትናው ተቃውሞ በኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ ግድያ ከተፈፀመባቸው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች መካከል በምዕራብ አርሲ አሳሳ፣ በምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ እና ሐረማያ እንዲሁም በምስራቅ ወለቃ ነቀምት ከተሞች ዋነኛ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በነበረው የኦሮሚያ ተቃውሞም የህወሓት መንግሥት በቃን፣ የኦሮሞን ህዝብ መግደል ይቁም፣ የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ፣አሸባሪ አይደለንም፣ አማራ የእኛ ነው፣ የጎንደር አማራዎችን መግደል ይቁም፣ የወልቃይት ጥያቄ ሕገ መንግሥታዊ ነው፣ወያኔ ሌባ፣…የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡ በነበሩ የተቃውሞ ሰልፍ ከተሞች እና አካባቢዎች በርካታ ሰዎች መሳተፋቸውን ከኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ፣ ማኀበራዊ ሚዲያ እና ከተለያዩ አካባቢዎች ያገኘናቸው የዓይን እማኞች መረጃ ማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሳሳይም በአማራ ክልል በተለይም በደቡብ ጎንደር ዞን ደብረ ታቦር ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. በተጠራው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ ላይ መንግሥት በወሰደው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ ከ6 ያላነሱ ሰዎች ወዲያው ሲገደሉ በርካቶች በመቁሰላቸው፣ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች እና በደቡብ ጎንደር ጋይንት ጨምሮ የተለያዩ ወረዳቸዎች ነዋሪዎች በመቆጣት በድንገት የተቃውሞ ሰለፍ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ መነሻውን የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ በማድረግ ወደ አጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የአማራ ተቃውሞን ተከትሎ መንግሥት ከደብረ ታቦር በተጨማሪ የተቃውሞ ሰልፎች በነበሩበት ስፍራዎች ሁሉ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በመወሰዱ የህዝቡ ቁጣ ተባብሱ የህወሓት ደጋፊና ተባባሪ ናቸው የተባሉ የንግድ ተቋማት፣ የመንግሥት ተሸከርካሪዎች እና ተቋማት ላይ እንዲሁም በጎንደር አዘዞ የሚገኘውን የመከላከያ ወታደራዊ ካምፕ ከጥቅም ውጭ ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡
በሰሜን ጎንደር ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በሰሜን ጎንደር ሳንጃ፣ ቆላ ድባ፣ ዳባት፣ አርማጭሆ፣…በመሳሰሉ ቦታዎች በመንግሥት ወታደሮች እና በህዝቡ መካከል ውጊያ መኖሩን እና የመንግሥት ወታደሮችን እና ከህዝቡም በርካታ ሰዎች መሞታቸውን እና መቁሰላቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በባህርዳር ከተማ በነበረው የአማራ የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ከ30 ያላነሱ ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ታውቋል፡፡ በአማራ ክልል ዛሬ የተገደሉ 30 ያህል እና ትናንት ደብረ ታቦር ከተገደሉ 6ቱ በተጨማሪ ሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች በተደረገ የትናንት እና የዛሬ ተቃውሞ 29 ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡ ህዝቡም በባህርዳር የተለያዩ ህዝባዊ ተቋማት ሰንደቅ ላይ የብአዴን እና በኢህአዴግ የፀደቀውን የፌደራሉን ሰንደቅ ዓላማ በማውረድ የቀድሞውን አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቅሉ እና ሲያውለበልቡ ተስተውሏል፡፡ በአጠቃላይ በሁለቱ ቀን የአማራ ክልል ተቃውሞ 65 ያህል ዜች ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎችም መቁሰላቸውን እና የህክምና ርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡

በተለይ በደብረ ታቦር እና ባህርዳር በተደረገው የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ፤ ወልቃይት የአማራ እንጂ የትግሬ አይደለም፣ ወልቃይት አማራ ነው፣ ለሱዳን የተሸጠው መሬታችን ይመለስ፣ የታሰሩት ይፈቱ፣ በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ የሚደረገው ግድያ ይቁም፣ በቀለ ገርባ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ ኢትዮጵያዊነት አሸባሪነት አይደለም፣በኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ አንደራደርም፣ወያኔ ሌባ፣አንዳርጋቸው ጽጌ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ የህወሓት አገዛዝ በቃን፣ ግድያ ይቁም፣….የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡
በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እየተካሄደ ባለው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ በርካታ መረጃዎች በመታፈናቸው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደረዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ እና የቆሰሉ ዜጎች ቁጥር ከተጠቀሰው ሊጨምር እንደሚችል ይገመታል፡፡
በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል በነበሩ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በጠፋው የሰው ህይወት እና በወደሙ ንብረቶች ዙሪያ እስካሁን ከገለልተኛ አካል የተጣራ ይፋ ማብራሪያም ሆነ መግለጫ የለም፡፡ ይሁን እንጂ በሁለቱም ክልሎች ባሉ በርካታ ወረዳዎችና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ አለመረጋጋቱ እንደቀጠሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በጎንደር ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ
(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ እሁድ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ መዳረሻውን በጎንደር ፋሲለደስ መስቀል አደባባይ ያደረገ ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ፡፡ የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ምክንያት ባለፈው ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የማዕከላዊ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አንሺ ኮሚቴ አባላት ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ በሌሊት አፍኖ ወስዶ በማሰሩ፣ ከኮሚቴ አባላት መካከልም ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ እቤታቸው ሊያፍኑ የሄዱትን የፀጥታ አካላት ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፣ በሌሊት ህገወጥነት በሚል በተፈጠረ አለመግባባት የ11 የፅጥታ ኃይሎች እና 3 ሲቪሎች መገደላቸው ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢዎችን እና የፀጥታ ኃይሉ ላይ የአፀፋ ርምጃ የወሰዱትን ጨምሮ የመንግሥትን ርምጃ በማውገዝ እና ተቃውሞ ያቀረቡ የአካባቢውን ህዝብ ወንጀለኛ አድርጉ በሚዲያ በማቅረቡ የተቆጣው ህዝብ፤ ተቃውሞውን በአደባባይ ለማቅረብ ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ ህዝቡ በራሱ ተነሳሽነት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲወጣ እንዳደረገው ከአስተባባሪዎቹ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከጎንደር ፋሲለደስ ከተማ በተጨማሪ በደቡብ ጎንደር በእስቴ ወረዳ መካነ ኢየሱስ ከተማ፣በምዕራብ በለሳ እና ማክሰኝት ከተማ ተመሳሳይ ጥያቄ መነሻ ያደረገ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ታውቋል፡፡ በተለይ በጎንደሩ ሰልፍ የተለያዩ የኃይማኖት አባቶች በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ማድረጋቸውን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡
በዛሬው ተቃውሞ ሰልፍም የተለያዩ መፈክሮች የተደመጡ ሲሆን፤ በዋናነትም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ ሕገ-መንገሥታዊ መብት ነው፣ የሻዕብያ ተላላኪ ህወሃት እንጂ ወልቃይት አይደለም፣ በግፍ የታሰሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በአስቸኳይ ይፈቱ፣…የሚሉትን ጨምሮ በርካታ መፈክሮች እንደተሰሙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተቃውሞ፤ ታሪክ ምስክር ነው ወልቃይት አማራ ነው ፣ አማራ ለኢትዮጵያ የግዛት አንድነትና ሉአላዊነት የተዋደቀ ታላቅ አርበኛ ሕዝብ ነው ፣ ዘረኝነትን አጥብቀን እናወግዛለን ፣ የትግራይን ሕዝብ እናከብራለን፤የህወሓትን አፋኝ የአገዛዝ ፖሊሲ አጥብቀን እናወግዛለን፣አማራነት ይከበር፣ በኦሮሞ እህት ወንድሞቻችን ላይ የሚደርሰውን ግፍና በደል አጥብቀን እንቃወማለን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ይፈልጋል፣ በኦሮሚያ የሚደረገው በወንድምና እህቶቻችን ላይ ግድያ ይቁም፣ ኢቢሲና ሌሎች መንግስታዊ ሚዲያዎች የጎንደርንና አካባቢውን ህዝብ ይቅርታ ይጠይቁ የሚሉ መሪ ቃሎች ተደምጠዋል፡፡
በተጨማሪም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ እስኪመለስ ድረስ ትግሉ ይቀጥላል፣አማራነት ወንጀል አይደለም፣ የትግራይ ወሰን ተከዜ ነው፣ ወልቃይት የአማራ ነው ፣ የሐብታሙ አያሌዉ ከአገር የመዉጣት እግድ በአስቸኳይ ይነሳለት፣ ዜጎችን በፖለቲካ አመለካከታቸዉ ማሰርና ማሰቃየት ይቁም፣ በፖለቲካ አመለካከታቸዉ የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ እና የህወሓት የበላይነት ይቁም የሚሉ መፈክሮች ጎልተው ተሰምተዋል፡፡
ይህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከሳምንት በፊት እውቅና ተጠይቆ በመንግሥት ተከልክሎ የነበረ ሲሆን፤ በድጋሚ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ቢገባም፤ መንግሥት ለህዝባዊ የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና አለመስጠቱን ከማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት ጋር በኢቢሲ እና ኤፍቢሲ ቢያሳውቅም ህዝቡን ለተቃውሞ ከመውጣት ማገድ አልቻለም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ እውቅና መንፈጉን በስሩ ባለ መገናኛ ብዙኃን ከመግለፁ በተጨማሪ በጎንደር ከፍተኛ የመከላከያ፣ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና የከተማው ሚሊሻ አባላት በበብዛት በከተማው እንዲሰፍሩ መደረጉ ታውቋል፡፡
ተቃውሞ ምንም እንኳ የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ ያድርግ እንጂ፤ ለዓመታት በአማራ ማኀበረሰብ ላይ በመንግሥት በተለይም በህወሓት/ኢህአዴግ አማራ ክልልን ጨምሮ በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍል እየተፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ የመብት ጥሰት ተባብሶ መቀጠሉ አንዱ የተቃውሞ አካል መሆኑን የሰልፉ ታዳሚዎች ሲያስተጋቡ ተስተውሏል፡፡
በነበረው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍም፤ በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያስከትል በሰላም መጠናቀቁን የተሳታፊዎችን ጨምሮ ዓይን እማኞች እውቅና የነፈገው የመንግሥት አካል አስታውቀዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በ25 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ አረንጓዴ፣ ቢጫ ቀይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በብዛት ሲውለበለብ ታይቷል፡፡