እንደኔ ቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰውራችኹ!
አቤል ዋበላ

“እያዩ ፈንገስ” ወይም “ፌስታሌን” የተሰኘውን ትያትር ብዙዎቻችኹ አይታችኹታል ብዬ ገምታለው አልያም ስለ ማኀበራዊ እና ፖለቲካ ቀመስ ትችቶቹ በወሬ በወሬ ሰምታችኃል፡፡ እኔ ዝናውን የሰማኹት እስር ቤት ሳለኹኝ ነበር፡፡ ወያኔ እግዜር የስራዋን ይስጣትና እኔ ከወህኒ እስክወጣ ድረስ መድረክ ላይ አቆየችው፡፡ በትያትር ቤት ታድሜ እንደተዋራለት ሆኖ አገኘኹት፡፡ ይህን ጥበብ ለመድረክ እንዲበቃ ያደረጉትን እና በመድረክ እንዳይታይ ለማስተጓጎል ያልሞከሩትን አመስግኛለው፡፡
የትያትሩ አንድ ገቢር ግን እስካኹን ድረስ ውስጤ ቀርቷል፡፡ የተነሳኹበትን ሐሳብ ለማስረዳት ይረዳኛልና ይህንን ክፍል እንድተርከው ይፈቀድልኝ፡፡ እያዩ ፈንገስ ውድ ንብረቶቼ የሚላቸው ዕቃዎቹን የያዘ አንድ ፌስታል እንደጠፋበት ይናገር እና ለፍለጋ ይሰማራል፡፡ በሚኖርበት ሰፈር አቅራቢያ በሚገኙ ገንዳዎች፣ ቆሻሻ መጣያ ስፍራዎች ፈልጎ ያጣዋል፡፡ የክፍለ ከተማው ቆሻሻ መጣያ ስፍራ ሄዶ ቢፈልግም እንዳላገኘው ለተመልካቹ በሞኖሎግ ያስረዳል፡፡ በመጨረሻም የአዲስ አባባ ቆሻሻ በሙሉ “ቆሼ” እንደሚጣል እንደሰማ ተናግሮ ለፍለጋ ወደ መድረክ በስተጀርባ (ወደ ቆሼ) ይሄዳል፡፡ ከዚያ ሲመለስ የተናገረው ነገር ነው የኔን ቀልብ የማረከው፡፡ እያዩ አንዲት ፌስታሉን ፍለጋ ቆሼ ቢሄድ እራሱን ተራራ ከሚያክለው ቆሻሻ ጋር አወዳድሮ ወደተመልካቹ ተንበርክኮ “ዛሬ በቆሻሻ ፊት አነስኩላችኹ፤ እንደ እኔ በቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰወራችኹ” ሲል ሲቃ በተመላበት ድምጽ ተናገረ፡፡
ይህንን እንደተናገረ እኔ ከዚያ ትያትር ቤት ወጣኹኝ፡፡ በሐሳብ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ማዕከላዊ፣ አዲስ አበባ የቀጠሮ እስረኛ ማረፊያ ቤት ቂሊንጦ እና ልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አስራ ዘጠነኛ ወንጀል ችሎት ሄጃለው፡፡ ለአንድ አመት ከስድስት ወር በቆሻሻ ፊት ያነስኩባከቸውን ጊዜያት አስታውስኩኝ፡፡ እየታመመኩኝ ውስጤ የሚሰማኝን ነገር አውጥቼ እንዳልናገረው የመግለጽ አቅም እያነሰኝ እያለ እያዩ ፈንገስ ደረሰልኝ፡፡
በቆሻሻ ፊት ማነስ እንዲህ ነው በሀገርህ እንደሁለተኛ ዜጋ ስለምትታይ የመብት ጥያቄዎችን አታነሳም ስለዚህ ከስርዓቱ አገልጋዮች ጋር ያለህ ግንኙነት የተገደበ ነው፡፡ ነገር ግን ሰው ነንና መሰረታዊ፣ ሰብዓዊ ፍላጎቶች ይኖሩናል፡፡ እነዚህን ለማግኘት ከማንም ጋር ይሁን መነጋገር፣ እርዳታን መጠየቅ እንገደዳለን፡፡ ለምሳሌ ሳይቤሪያ እያለን ከእስረኞቹ መሀል አንድ ሰው ይታመማል፡፡ አንዳንዴ ህመሙ እንደአተት(የሆድ ህመም) የሚደርግ ይሆንና እንቸገራለን፡፡ በር ደብድበን ይህ ሰው ሽንት ቤት ደርሶ እንዲመጣ ካላደረግን ማታ መጥተው ለአስር ደቂቃ ሽንት ቤት እንድንሄድ እስኪፈቅዱልን ድረስ የማይሆን ነገር እያየን እና እያሸተትን መቆየታችን ነው፡፡ በር ስንደበድብ ሰላማዊ ዋርድያ ካጋጠመን ታማሚውን “ቶሎ ደርሰህ ተመለስ” ይለውና ለእኛ ደግሞ ትንሽ ንጹህ አየር እንዲገባ በሩን ከፈት አድርጎት ይቆማል፡፡ ሁልጊዜ ግን ሰላማዊ ሰው ላያጋጥም ይችላል፡፡ “እዛው ቁጭ ይበል” ብሎ የሚል ይኖራል፡፡ ውጤቱ የከፋ ስለሚሆን ‘አረ ባክህ እረዳን . . . እና ሌሎች ኢትዮጵያዊ የልመና ዘዴዎችን’ ተጠቅመን ልቡን ለማለስለስ እንሞክራለን፡፡ ብዙ ጊዜ አይሳካም፡፡ ከዚህ በታች ከቆሻሻ በታች ማነስ ከየት ይመጣል፡፡ ባለ ማዕረግ ከሆነ ደግሞ ኮማንደር ወይም ሳጅን ማለትም ይጠበቅብናል፡፡
ቅሊንጦም እንዲሁ በቆሻሻ ፊት ሳንስ ከርሜ ነው የወጣኹት፡፡ ታመህ ቤተሰብ መድሃኒት እንዲያስገባልህ ለመጠየቅ ወይም ለሌላ በጣም አስፈላጊ ሰብዓዊ ጉዳይ አጋጥሞህ ሱፐር ኢንቴንዳንት፣ ኦፌሰር ምናምን ብለህ ያልተከበረውን አክብረህ መጥራት ይጠበቅብሃል፡፡ ሌላው ይቅርና “ካቴናው እጄን አጥብቆ ይዞታል ትንሽ አላላልኝ” ማለት በራሱ ለስድብ እና ማንጓጠጥ ሊዳርግ ይችላል፡፡ አንዳንድ በቆሻሻ ፊት ማነስን እና ንትርኩን የጠሉ ወዳጆቼ ካቴናው እጃቸውን እየሰረሰረው ችለው ይቀመጣሉ፡፡
ፍርድ ቤት ደግሞ ሌላው መተናነሻ ቦታ ነው፡፡ እንደኔ እንደኔ ጠበቃ ባላቆም፣ ባልከራከር እና የተውኔቱ አካል ባልሆን እመርጥ ነበር፡፡ ነገር ግን በጓደኛ እና ቤተሰብ ግፊት የማልሆነውን ሆኜ ነው የከረምኩት፡፡ የዐቃቤ ህግ በሬ ወለደ ክስ እና ሙያዊ ብቃት ማነስ አእምሮ ሊገምተው ከሚችለው በላይ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ያለህ ብቸኛ ምክኒያታዊ ድርጊት ከት ከት ብሎ መሳቅ ነው፡፡ ነገር ግን ችሎት በመድፈር እስከስድስት ወር እስራት ስለሚፈረድብህ ከቆሻሻ አንሰህ ሰብዓዊነትህን ለቀህ ምንም እንዳልተገረመ ሰው ለመሆን ትሞክራለህ፡፡ ለማይረባ ጉዳይ አንድ ወር ወይም ሁለት ወር ሲቀጥርህ የተከበረ ዳኛ እና ፍርድ ቤት እንደሌሉ እያወቅክ “የተከበረው ፍርድ ቤት፣ ክቡር ዳኛ ይህ ነገር ትንሽ አልዘገየም? በማረሚያ ቤት ሆነን እየተንገላታን ስለሆነ ቀኑን አጠር ቢያደርጉት” ልትል እጅህን ብታነሳ አይተው እንዳላየ ያልፉሃል፡፡ እንድትናገር ዕድሉን እንዲሰጡህ ድምጽህን ስታሰማ ስነ ስርዓት የጎደላቸው ሰዎች “ስነ ስርዓት፣ ስነ ስርዓት” ብለው ይገስጹሃል፡፡
እያዩ ተራራ በሚያክል ቆሻሻ ፊት ማነሱን ሲናገር እነዚህን እና ሌሎች በርካታ ህሊናን የመፈታተኑ ቅጽበታቶችን ነው ያስታወስኩት፡፡ ነገም ቆሼ መውረድ አልቀረልኝም፡፡ ነገ ከጓደኞቼ BefeQadu Z. Hailu, Natnail Feleke, Atnaf Brhane እና Soleyana Shimeles Gebremichael (በሌለችበት) ጋር ጠቅላይ ፍርድ ቤት እቀርባለው፡፡ ያው እያዩ ከክፍለ ከተማ ወደ ከተማ ሲሄድ የቆሻሻ ተራራው ግዝፈት እንዳስደነገጠው እኔም እንዲሁ ክው ብያለው፡፡ ክርክር ተሰምቶ ስላለቀ የመጨረሻውን ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ወይ ቂሊንጦ አለያም ፒያሳ እንገናኝ፡፡ ምንም እንኳን አረጋዊ ሁኜ ለምርቃት ባልበቃም መልካም ምኞቴን ትቼላችኹ ልሂድ፡- እንደኔ በቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰውራችኹ!
አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው
ባለፈው ሚያዝያ 2006 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ታስረው ፣ጉዳያቸው ለአንድ ዓመት ከ5 ወር በላይ ሲታይ ቆይቶ ከበፈቃዱ ኃይሉ በስተቀር ቀሪዎቹ “መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ” ተብሎ ከሁለት ወራት በፊት የተወሰነላቸው አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው፡፡
የፌደራል ዐቃቤ ሕግ በአምስት የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ላይ ባቀረበው ይግባኝ መሠረት ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲቀርቡ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የወንጀል ችሎት ማዘዙ ተሰምቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለሚከራከሩት አምስት የዞን ዘጠኝ አባላት መጥሪያውን ያወጣው ታህሣሥ 4 ቀን 2008 ዓ.ም ሲሆን፤ ለቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ የሰጠው ለፊታችን ታህሣሥ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 2፡30 መሆኑን መጥሪያው ያስረዳል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ መጥሪያው የደረሰው ለበፍቃዱ ኃይሉ ብቻ ሲሆን፤ በተሰጠው የቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ እንዲቀርቡ መጥሪያ የወጣላቸው በፈቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ከዚህ ቀደም፤ በፍቃዱ ኃይሉ የተቀየረለትን “አመፅ የማነሳሳት” የወንጀል አንቀፅ ለመከላከል ለጥር 30 ቀን 2008 ዓ.ም. መቀጠሩ አይዘነጋም።
የዞን9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ቃል
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡
ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ ተሰሙት ምስክሮች
7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡
8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡
9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡
10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)
11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡
12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡
በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡
ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡
ምንጭ፡- ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ
የማያዳምጥና የማያነብ መንግስት እድሜው ስንት ነው?
ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ
“መንገዱ በዚህ ወር ይጠናቀቃል፤ ባቡሩ በዚህ ወር ስራ ይጀምራል” ይሉናል፡፡ መንገዱ ወዴት ያደርሳል? ባቡሩ ወዴት ይወስዳል? ልጆቻችን ወጥተው የማይገቡበት መንገድ፣ የማይሳፈሩበት ባቡር ምን ያደርጋል? መንገዱ ሲሰፋ፣ መጓጓዣው ሲበረክት የልጆቻችን ፍርሀት፣ የእኛ የወላጆች ጭንቀት ከመበርከቱ በቀር ትርፉ ምንድነው?
ቁሳዊ ልማት ብቻውን ማህበረሰባዊ እድገት አያመጣም፤ ቀውስ ካልሆነ በቀር፡፡ የማህበረሰብህን . . . የነገ ወራሽህን. . የወጣቱን አስተሳሰብና አሰራር ሳታለማ (ሳትለውጥ) ታክሲ ብታመጣ፣ ወንዝ ውሀ ስትቀዳ፣ ጫካ እንጨት ስትለቅም ትደፈር የነበረችውን ልጃገረድ፣ ታክሲ ውስጥ ታስደፍራታለህ፤ ነገም ባቡር ውስጥ (ዛሬ በህንድ ሀገር ባቡር ማለት ብዙ የማያስከፍል ፔንሲዮን ነው)፡፡ እኛ ሀገር ብዙ መንገድ ብዙ ወንጀል፣ ሰፊ ኢንቨስትመንት ሰፊ ዝርፊያ፣ ትልቅ ባለስልጣን ትልቅ ዘራፊ ከማለት የተለየ ፍቺ የሚኖረው መቼ ነው?
“ልማታዊ መንግስት ነን፣ ኒዎ ሊብራሊዝምን እንቃወማለን” ይሉናል፡፡ በልማት ስም ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብታችንን አንጠፍጥፈው ወሰዱት፡፡ ይበጃል ያልነውን ስንጽፍና ስንናገር ጸረ ልማት ይሉናል፡፡ ደፈር ብለን መብታችንን ከጠየቅን አሸባሪ ይሉናል፡፡ በየእስር ቤቱ ያጉሩናል፤ ድንበር አሻግረው ያሰድዱናል፡፡ መብታችንንና የመናገር ነጻነታችን ልማታዊ ላሉት መንግስት ጭዳ አደረጉት፡፡
“ልማታዊ አይደላችሁም! ኒዎ ሊብራል ናችሁ አንላቸዋለን፡፡ የምትኖሩበት ቤት፣ የምትነዱት መኪና፣ ልጆቻችሁ የሚማሩበት ትምህርት ቤት (ሀገር)፣ የምትገበያዩበት ሱፐር ማርኬት፣ የምትዝናኑበት ሪዞሪት. . . የልማታዊነት ሳይሆን የኒዎ ሊብራሎች መገለጫ ነው፡፡” እንላቸዋለን፡፡
“ዝም በሉ! የምንላችሁን አሜን ብላችሁ ተቀበሉ” ይሉናል፡፡ ማተሚያ ቤቱ የእነሱ ነው፤ ራዲዮና ኢቲቪው የእነሱ ነው፤ አዋጅና መመሪያ የሚጥልብን ፓርላማ የእነሱ ነው፡፡ አዋጅ ጣሳችሁ፣ አሸበራችሁ፣ እራለ የሚይዘን ፖሊስ የእነሱ ነው፤ ከፖሊሶቹ ተቀብሎ የሚፈርድብን ፍርድ ቤት የነሱ ነው፡፡ ያለ ወንጀሉ ተከስሶ የሚፈረድበት ዜጋ እሱ ራሱ የራሱ አይደለም፡፡ ራሳችንም የእነሱ ነን፡፡ የእኛ የሆነው ተስፋችን ብቻ ነው! ለሀገራችንና ለወገናችን ያለንን ብሩህ ተስፋ ምንም ሊያስረው አይችልም፡፡ የኔ ተስፋ ልጆቼ ውስጥ፣ ያልተወለደው የልጆቼ ልጆች . . . . . ውስጥ አለ፡፡ ተስፋ የሚታሰረው፣ የሚሞተው እርኩስ፣ ለሀገርና ለወገን የማይበጅ ሲሆን ብቻ ነው፡፡
ዛሬ አትጻፉ ተብለናል፡፡ አትናገሩ ተብለናል፡፡ አንጽፍም፡፡ አንናገርም፡፡ ከተማው ጭር ብሏል፡፡ ሀገሩ ጭር ብሏል፡፡ መንግስትም ጭርታው ተስማምቶታል፡፡ እኛ ግን አንጽፍም እንጂ እንነበባለን፤ አንናገርም እንጂ እንደመጣለን፡፡ የማያነበንና የማያዳምጠን የኢህአዴግ መንግስት ብቻ ነው፡፡ አንድ መንግስት ህዝቡን ሳያዳምጥና ሳያነብ ምን ያህል እድሜ ይኖራል? እንጃ! . . . . . አንድ ቀን መንግስት ህዝብን ማንበብ፣ ህዝብን ማዳመጥ ግዴታው ይሆናል፡፡ አቤት ታዲያ ያኔ የሚያነበው መአት! የሚያዳምጠው ቁጣ! ያኔ ማንም መንግስትን መሆን አይመኝም፡፡ እውነቴን እኮ ነው፣ አሁን 1983 ዛሬ ቢሆን ደርግን መሆን የሚመኝ አለ?
ጋዜጠኞቹ እና የዞን 9 ብሎገሮቹ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው
- ኤዶምና ማህሌት የመብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸው ቅሬታ አቅርበዋል
የዞን 9 ብሎገሮቹና ሶስቱ ጋዜጠኞች ያቀረቡት መቃወሚያ ‹‹ተቀባይነት የለውም›› ተብሎ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጠረባቸው፡፡ ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ የተከፈተባቸው ክስ አግባብ አለመሆኑን የሚገልጽ ስምንት ገጽ የክስ መቃወሚያ አቅርበው የነበረ ቢሆንም አቃቢ ህግ ‹‹ክሱ ምንም ችግር የለበትም፣ የሚሻሻል ነገር የለውም፡፡›› በሚል መቃወሚያውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡
ቃሊቲ እስር ቤት ታስረው የሚገኙት ኤዶም ካሳዬና ማህሌት ፋንታሁን ማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥሰት እንደሚፈጸምባቸው ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡ ሁለቱ ታሳሪዎች በፍርድ ሂደት ላይ ያሉ ቢሆንም እስር ቤቱ ውስጥ ‹‹አሸባሪ›› የሚል ስም እንደሚሰጣቸው ቅሬታ ያቀረቡ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ‹‹ቤተሰብ ብቻ ነው የሚጠይቀን፡፡ ከቤተሰብ ውስጥም የምንጠየቅው ስማቸውን ባስመዘገቡት ብቻ ነው፡፡ ያም ሆኖ የምንጠየቀው ለ10 ደቂቃ ነው፡፡ ለመጠየቅ የሚመጡ ቤተሰቦቻችንም ድብደባ ይፈጸምባቸዋል፡፡›› በሚል ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡
ባለፈው ችሎቱ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ኃላፊ ታሳሪዎቹ ይደርስብናል በሚሉት በደል ዙሪያ ለዛሬ ቀርበው እንዲያስረዱ ተጠይቀው የነበር ቢሆንም ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡ ዛሬ ያልተገኙት የማረሚያ ቤቱ ኃላፊ ለጥቅምት 25/2007 ዓ.ም ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ የነበር ቢሆንም ኤዶምና ማህሌት ‹‹ይህ የመብት ጉዳይ ስለሆነ አጭር ቀጠሮ ሊሰጥልን ይገባል፡፡›› በማለታቸው ማረሚያ ቤቱ ውስጥ እየተፈጸመብን ነው ያሉትን በደል ብቻ ለማየት ጥቅምት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ኃላፊው ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ኤዶምና ማህሌት ለዋናው ክስም ጥቅምት 25 ደግመው ይቀርባሉ፡፡
በዛሬው ችሎት የታሰሪዎቹ ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች፣ የኤምባሲና የተቋማት ተወካዮችን ጨምሮ በርከት ያለ ታደሚ ተገኝቶ ተከታትሏል፡፡ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም አቃቢ ህግ ያቀረበው ክስና ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ ያቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ ምርመራ ተደርጎ ሌላ የፍርድ ሂደት ይጀመራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ ጋዜጣ

