Tag Archives: Ethiopian Justice

የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና (ክፍል 2)

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
(ከዝዋይ እስር ቤት)

temesegen dበዚህ አውድ ለማቅረብ የተገደድኩበትን ዘግናኝ ታሪክ፣ ወደር በሌለው አስከፊነቱ የተነሳ ለንባብ ባላበቃው በወደድኩ ነበር፡፡ ግና! ይህ መንግስታዊ የጭካኔ ተግባር፣ ዛሬም በምስኪን ዜጎች ላይ እየተፈፀመና ብዙዎችን ሰለባ እያደረገ በመሆኑ ህዝቡ ይህን ሊሸሸግ እየተሞከረ ያለውን መከራ ተረድቶ ሥርዓቱን በአደባባይ ዓመፅ “ሃይ!” ይል ዘንድ ትርክቴን ለማጠናቀር ተገድጄያለሁ፡፡ ለእስር ያበቃኝ የጋዜጠኝነት ሙያዬም ተጨማሪ ዕዳ ጭኖብኛል፡፡

“ጄል-ኦጋዴን”

ጄል ኦጋዴን በሱማሌ ክልል ርዕሰ-መዲና የሚገኝ፤ ለ800 እስረኞች ታቅዶ በ1992 ዓ.ም የተገነባ እስር ቤት ነው፡፡ የግቢውን ዙሪያ ከከበበው አጥር በግምት 15 ሜትር ፈንጠር ብሎ ሌላ ተደራቢ የድንጋይ አጥር ተበጅቶለታል፡፡ እስከ ሚያዝያ 24 1999 ዓ.ም ድረስ እስር ቤቱ በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች ካሉ መሰል ማጎሪያዎች ብዙም የተለየ አልነበረም፡፡ በዚህ በተጠቀሰው ቀን የኦጋዴን ነፃ አውጭ ግንባር (ኦብነግ) ታጣቂዎች፣ አቦሌ እና ሰንደሬ ወታደራዊ ካምፖችን ጨምሮ፣ በነዳጅ ዘይት ፍለጋ ላይ የተሰማሩ ቻይናውያን ባለሙያዎች መኖሪያ ሰፈር ላይ የሰነዘሩትን ከባድ ጥቃት ተከትሎ የፖለቲካ እስረኞች ብቻ የሚታጎሩበት እስር ቤት ከሆነ ወዲህ ግን በዋይታ የሚናወፅና በደም ጅረት የሚጥለቀለቅ ምድራዊ ሲኦል ለመሆን በቅቷል፡፡ መንግስት በጥቃቱ ከዘጠኙ ቻይናውያን ጋር 74 ሲቪል ዜጎችና ወታደሮች መገደላቸውን ቢያምንም፤ የአካባቢው የአይን እማኞች ከሰራዊቱ ብቻ እስከ 300 እንደተሰዉ ይናገራሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኦብነግ እንደ አል-ቃይዳ እና አል-ሸባብ የአባላቱን አስከሬን ትቶ የመሸሽ ልምድ ስለሌለው በቡድኑ ላይ የደረሰውን ጉዳት በትክክል ለማወቅ አዳጋች እንደሆነ ቀጥሏል፡፡

የሆነው ሆኖ ከዚህ ጥቃት በኋላ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ የሚመራ አምስት ከፍተኛ ባለስልጣናትን ያካተተ የደህንነትና (ጄነራል ሳሞራ የኑስ እና ጌታቸው አሰፋ ያሉበት) የፀጥታ ኮሚቴ ተቋቁሞ የሚከተሉትን (ዛሬም ድረስ እየተተገበሩ ያሉ) አስቸኳይ ውሳኔዎችን አስተላልፏል፡፡ ‹‹ከጅጅጋ ውጭ ባሉ በክልሉ ማንኛውም የመንግስትም ሆነ የግል ተሽከርካሪ እንዳይንቀሳቀስ፣ ትዕዛዙን ጥሶ የተገኘ ከነጭነቱም ሆነ ተሳፋሪዎቹ በከባድ መሳሪያ እንዲመታ፤ አብዛኛውን ህዝብ በፍጥነት ከመኖሪያ ቀዬው በማፈናቀል ለቁጥጥር ወደሚያመቹ ከተሞች ማስፈር (በ2006 ዓ.ም መጀመሪያ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ካሳ ተክለብርሃን 2300 መንደሮችን ወደ ተመረጠ ቦታ ማስፈሩ እንደተሳካ መናገሩን ልብ ይሏል)፤ ወታደራዊ መኪና ላይ ምንም አይነት የደፈጣ ጥቃት ከደረሰ በአቅራቢያው የሚገኝ መንደርን ያለርህራሄ ማውደም (ለማሳያ ያህልም ፍልቼ፣ ቃሙዳ፣ ሳስባኒ፣ ሁለሌ፣ ለንካይርተ፣ ቻለሌን… የመሳሰሉ ከተሞች ወደ ፍርስራሽነት መቀየራቸውን መጥቀስ ይቻላል) እና ከአንድ ሻምበል ያነሰ ኃይል ለአስቸኳይ ጉዳይም ቢሆን ከቦታ ቦታ እንዳይንቀሳቀስ›› የሚል እንደነበር ይታወሳል፡፡ ከዚህ በኋላም ኤታማዦር ሹሙ ጄነራል ሳሞራ የኑስ በክልሉ የሚገኘውን የደቡብ ምስራቅ ዕዝ ወታደራዊ አዛዦችን በቪዲዮ ኮንፈረንስ ሰብስቦ ማብራሪያ ሰጥቶ ሲያበቃ ውሳኔውን ያለምንም ማቅማማት ተግባራዊ እንዲያደርጉት በጥብቅ አሳስቧል፡፡

ደቡብ ምስራቅ ዕዝ ከኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት (ከ1993 ዓ.ም) በኋላ በምስራቅ ኢትዮጵያ የሰፈረ ሲሆን እስከ ታህሳስ 1999 ዓ.ም ድረስ በሜ/ጀነራል ባጫ ደበሌ ሲመራ ቆይቷል፡፡ ከታህሳስ 1999 እስከ 2000 ዓ.ም ደግሞ ብርጋዴር ጄነራል ስዩም አስተዳድሮታል፤ በዚሁ ዓመት ከጥቅምት እስከ ሚያዚያ ድረስ ባሉት ጊዜያትም በብ/ጄነራል ሙሉጌታ በርሄ ስር የቆየ ሲሆን፤ ከሚያዚያ 2000 ዓ.ም አንስቶ አሁን ድረስ እየተመራ የሚገኘው በሌ/ጄነራል አብርሃም ወ/ማርያም (ቅፅል ስሙ ‹‹ኳርተር››) እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ከዚህ ዕዝ ውስጥ በዋናነት ሶስት ክፍለ ጦሮች (12ኛ፣ 13ኛ እና 32ኛ) ክልሉን ሶማሊያ ድንበር ድረስ እንዲቆጣጠሩት ተመድበዋል፡፡ ሰፈራቸውን ነገሌ ቦረና ያደረጉት 43ኛ እና 44ኛ ክፍለ ጦሮችም፣ ኦጋዴን ድረስ እንዲንቀሳቀሱ ትዕዛዝ ተሰጥቷቸዋል፡፡ በአናቱም የአግአዚ ኃይል በቀድሞ ምክትል አዛዡ ብ/ጄኔራል ገ/መድህን ፈቀደ (‹‹ወዲ ነጮ››) ስር ሆኖ አልፎ አልፎ በተደራቢነት እየተላከ በነዋሪዎቹ ላይ በደረሰው ጅምላ ጭፍጨፋ እና ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የተሳተፈ ስለመሆኑ ከወታደራዊ መረጃ ምንጮቼ ሰምቻለሁ፡፡ ይህም ሆኖ ለደረሱ እልቂቶችና ጭፍለቃዎች በግንባር ቀደምትነት ተጠያቂ ተደርገው የሚጠቀሱት ከጄነራል ሳሞራ፣ ከጀኔራል ‹‹ኳርተር›› እና ከክልሉ ፕሬዝዳንት በተጨማሪ በብ/ጄነራል በየነ ገ/እግዚአብሔር (‹‹ወዲ አንጥር››) የተመራው 12ኛ ክ/ጦር እና በብ/ጄነራል ፀጋዬ ገ/ጨርቆስ (‹‹ጀብጀብ››) ዕዝ ስር የነበረው 13ኛ ክ/ጦር እንደሆነ ይነገራል፡፡ ኦብነግ በስፋት ይንቀሳቀስባቸዋል ተብለው የሚታሰቡት፡- ደገሃቡር፣ ቀብሪደሃር፣ ዋርደር፣ ጎዴ እና ቪቅ ከተሞች መደበኛ የጦር ቀጠናዎች ከሆኑ 15 አመት ያለፋቸው በመሆኑ፣ ከሌሎች የክልሉ አውራጃዎች በተለየ ሁኔታ የችግሩ ቀጥተኛ ተጠቂ ሆነዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትም የሚፈፅማቸውን ኢ-ህገ መንግስታዊ ድርጊቶች ለመሸፈን እንደ ቀይ መስቀል፣ ዓለም-አቀፍ ሚዲያዎች፣ ግብረሰናይ ድርጅቶችና መሰል ተቋማት ከጅጅጋ ውጪ እንዳይንቀሳቀሱ በኃይል አግዷል፡፡ ይህ ኩነትም በ ዙ-23 እና በሌሎች ከባድ መሳሪያዎች ተደብድበው ከምድረ-ገፅ የጠፉ መንደር ነዋሪዎች፣ የቤት እንስሳት እና ቁሳዊ ንብረቶች በአንድነት ተቃጥለው መውደማቸውን ዛሬም ድረስ በምስጢርነት ሸሽጎ ለማቆየት አስችሎታል፡፡

የሆነው ሆኖ የመከላከያ ሰራዊቱ እና በክልሉ ከ70-80 በመቶ በሚሆኑ አካባቢዎች ላይ መንቀሳቀስ የቻለው ኦብነግ፣ ቢያንስ በሳምንት አንድ ጊዜ ከባድ ውጊያ እንደሚያደርጉ ይታወቃል፡፡ በእርግጥ ግጭቱ አሁንም ሳያበራ የመቀጠሉ ምክንያት አማፂው ቡድን ያን ያህል ከመንግሥት አቅም በላይ ሆኖ አይደለም፤ ይልቁንም የጄነራሎቹ እጅ በዘወርዋራ ስላለበት መሆኑን ወታደራዊ ምንጮቼ ያስረግጣሉ፡፡ ‹‹የኦብነግ ህልውና በተለይም ለከፍተኛ መኮንኖች ዋነኛ ንግድ (ቢዝነስ) ነው›› ይላሉ፡፡ የክልሉ መንግስት ‹‹የመረጃ እና ፀጥታ ባጀት›› በሚል ሽፋን በዓመት የሚመድበውን ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ የህዝብ ሀብት እንዲያወራርዱ አዛዦቹ አይገደዱም፡፡ መከላከያ ራሱም ‹‹የመረጃ እና የበረሃ ፍሳሽ›› በሚል የሚበጅተው አመታዊ ወጪ በብዙ ሚሊዮን ብሮች የሚቆጠር እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይህ በጀት እስከ ኃይል አመራሮች ድረስ ወርዶ እንደየድርሻቸው መጠን የሚመዘበርበት አሰራርም ተዘርግቶለታል፡፡ እናም ጀነራሎቹ ኦብነግ ሙሉ በሙሉ ተወግዶ የገቢ ምንጫቸው እንዳይደርቅም ሆነ፤ ከአቅም በላይ ተጠናክሮ በብቃት ማነስ እንዳያሳጣቸው (እንዳያስወቅሳቸው) ተቆጣጥረው ለመዝለቅ የቻሉበትን ቀመር እንዲከተሉ ይህ የገቢ ምንጭነት ገፊ ምክንያት መሆኑ ይነገራል፡፡

ሌላው ቀርቶ ከመከላከያ ሠራዊቱ እና ከፌዴራል ፖሊስ በተጨማሪ በቀጥታ የክልሉ አስተዳደር የሚያዝዘውና ‹‹ልዩ ኃይል›› ተብሎ የተቋቋመው ታጣቂ ቡድን ዛሬም ድረስ የሎጅስቲክ አቅርቦቱን ያለጨረታ ጠቅላላ የያዘችው የሜ/ጀነራል ዮሐንስ ወ/ጊዮርጊስ (በአሁኑ ወቅት ጀነራል አበባውን ተክቶ የማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ ነው) ባለቤት ሃዋ መሆኗ በራሱ የሚነግረን ነገር አለ፡፡ (በነገራችን ላይ ክልሉን የሚያስተዳድሩት በህዝብ የተመረጡት ሳይሆኑ ‹‹የፀጥታ አማካሪ›› በሚል በየወረዳው የተመደቡ የሻለቃ ወይም የሻምበል አዛዦች ከጀርባ ሆነው ነው፡፡ ለነርሱ ያልተመቸ ኃላፊን በሌላ እስከመቀየር ድረስ የሚንጠራራ ስልጣን አላቸው፡፡ የፕሬዚዳንት አብዲና እና የጄነራል ‹‹ኳርተር››ን የ‹‹ሥራ ግንኙነት›› መመልከቱ ጉዳዩን ፍንትው አድርጎ ለመረዳት ያስችላል፡፡ በርግጥም አስራ ሦስት ፕሬዚዳንቶች የተፈራረቁበት ክልል ዛሬ እንዲህ በጨካኙ አብዲ መርጋት መቻሉ እንቆቅልሽ ሊሆን አይችልም)፡፡

‹‹ጄል-ኦጋዴን›› ከደረቅ ወንጀለኞች ማረሚያነት፣ በኦብነግ አባልነት የሚጠረጠሩ ንፁሃንን ወደማሰቃያ እስር ቤት እንዲቀየር የተደረገበት መግፍኤ ከላይ የጠቀስኩትን (የ1999 ዓ.ም የኃይል ጥቃትን) ተከትሎ ሟቹ አምባ-ገነን ጠ/ሚኒስቴር በደህንነት ኮሚቴው ስም የሰጠው ትዕዛዝ ነው፡፡ መቼም ዕድል ፊቷን አዙራበት ወደዚህ ግቢ የተላከ ምስኪን፣ በቀን አንድ መናኛ እንጀራ እየተወረወረለት፣ በ‹‹ምርመራ›› ስም የተወለደበትን ቀን ከመርገም አልፎ ዘላለማዊ ዕረፍት የሚያጎናፅፈው መልአከ-ሞት ቶሎ መጥቶ እንዲገላግለው እስከመናፈቅ ለሚያደርስ ስቀየት (ቶርቸር) ይዳረጋል፡፡ እስር ቤቱ የተገነባው 800 ታሳሪዎችን ታሳቢ ተደርጎ ቢሆንም፣ ወደምድራዊ ገሃነም ከተቀየረ ወዲህ ግን ከ5000 በላይ ሰዎች የሚታጎሩበት የሰቆቃ ግቢ ሆኗል፡፡ ሁሉም ታሳሪዎች ከጠዋት 2፡30 እስከ 7፡00 ሰዓት ድረስ አንድ ቦታ ተሰብስበው ክብርን፣ ሞራልን እና ሰብዕናን የሚያጎድፍ ግፍ ይፈፀምባቸዋል፡፡

ogadenበተለይም ሴት እስረኞች በየተራ እንዲቆሙ ይደረግና ወንዱ አንድ በአንድ እየተነሳ ሴተኛ አዳሪ መሆኗን፣ እሱ እና ጓደኞቹ ከእርስዋ ጋር ግብረ-ስጋ ግንኙነት መፈፀማቸውን፣ ወዘተ እንዲናገር ይገደዳል፡፡ ይህንን ለማድረግ ፈቃደኛ ሆኖ ካልተገኘም በጨካኝ ታጣቂዎቹ ፍዳውን ይበላል፡፡ ሁኔታውን መራር የሚያደርገው ደግሞ ‹‹ስብሰባው›› ሲጠናቀቅ፣ ሰብሳቢው እስረኞቹ ወደየክፍላቸው እንዲገቡ ትዕዛዝ የማይሰጥ መሆኑ ነው፤ ይልቁንም ወፋፍራም ዱላ ጨብጠው ዙሪያውን ለከበቡት ፖሊሶች በአይኑ ምልክት ያስተላልፋል፤ ይሄኔ በያዙት ቆመጥ ከአቅራቢያቸው ያገኙትን ሁሉ መቀጠቀጥ ይጀምራሉ፤ እስረኛውም ከዱላው ውርጅብኙ ለማምለጥ ባገኘው አቅጣጫ ይተራመሳል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ድርጊት በየቀኑ የተለመደ በመሆኑ የዕለቱ ፕሮግራም ሊገባደድ በተቃረበ ቁጥር፣ ሁሉም ለመሸሽ ዝግጁ ሆኖ ይጠባበቃል፤ ከድብደባው ማምለጡ ግን ብዙም የሚሳካ አይሆንም፡፡

በ‹‹ጄል-ኦጋዴን›› ሴት እስረኞችን አስገድዶ መድፈር፣ ሙዝ ልጦ እንደመብላት ቀላል ከሆነ ሰነባብቷል፡፡ በዚህም በርካቶች በየጊዜው ለውርጃ ወደሆስፒታል ሲላኩ ይስተዋላል፡፡ አልፎ አልፎ እዚያው ለመውለድ የሚገደዱ እህቶችም አሉ፡፡ አብዛኞቹ ሴት እስረኞች ፀጉራቸውን ከማሳደግ ይልቅ መላጨትን ይመርጣሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ የሚፈፀምባቸው ስቅየት የበሰበሱ ቆሻሻዎችንና ፈሳሽ-ሰገራዎችን ፀጉራቸው ላይ መደፋትን ስለሚያካትት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ እዚህ ቦታ ሴቶች አንድ ላይ እንዲሰበሰቡ እና ልብሶቻቸውን እንዲያወልቁ ከተደረገ በኋላ እርቃናቸውን የሚገረፉበት ጊዜም እንዳለ ከአይን እማኞች ሰምቻለሁ፡፡ ከሁሉ የከፋው ደግሞ ንፅህናን ካለመጠበቅና በምግብ እጥረት የሚነዛው ወረርሽኝ ነው፡፡ በ2004ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ በሽታው ተከስቶ አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ብቻ 700 ያህል ሰዎች በሞት መቀጠፋቸው ይነገራል፡፡ በወቅቱ አስከሬን ቶሎ ስለማይነሳ እስረኞቹ ከአስከሬኑ ጋር እስከ 3 ቀን ድረስ ጋር ለመቆየት ይገደዱ ነበር፡፡

በ‹‹ጄል-ኦጋዴን›› ግቢ ከሚገኙ ማጎሪያዎች መካከል 3ኛ፣ 4ኛ፣ 7ኛ እና 8ኛ ክፍሎች ‹‹የቅጣት ቤት›› ሲሆኑ፤ አሰራራቸውም ሶስት በሶስት ሜትር የሆነ እጅግ በጣም ጠባብ፤ ውስጣቸውም ሃምሳ ሳንቲ-ሜትር ጥልቀት ባለው ውሃ የተሞላ ነው፡፡ እያንዳንዱ ክፍልም የግድ ከ25 እና ከዚያ በላይ እስረኞች እንዲይዝ ስለሚደረግ ለቅጣት ወደግቢው የተላከ እስረኛ ለሳምንት ያህል እንቅልፍ በዓይኑ ሳይዞር ለመሰንበት ይገደዳል፡፡ በአናቱም የመከላከያ ሰራዊት አባላት ወደዚህ ግቢ እየተላኩ ስቅየትም ሆነ ግድያ እንደሚፈፀምባቸው ሰምቻለሁ፡፡ በግቢው ለአራት ወራት ገደማ ያሳለፈው ሀሰን፣ በውል በማያስታውሰው በአንድ የተረገመ ቀን 3 ወታደሮች ሲረሸኑ ማየቱንና ከመካከላቸው አንዱም ‹‹እባካችሁ አትግደሉኝ! የ3 ልጆች አባት ነኝ!›› እያለ ሲማፀን መስማቱን ያስታውሳል፡፡

እስረኞቹ ላይ የጭካኔ ተግባር የሚፈፅሙት ደግሞ ከዚህ ቀደም ‹‹አል-ኢትሀድ አል-ኢስላሚያ›› በሚል ስም ተደራጅቶ ሲንቀሳቀስ፤ በኦብነግ ተሸንፎ ከኦጋዴን የተባረረው አማፂ ቡድን አባላት የነበሩ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች መንግስት ምህረት አድርጎላቸው ወደ ሰላማዊ ህይወት ከተመለሱ በኋላ የክልሉ ፕሬዝዳንት አብዛኛውን አሰባስቦ ‹‹ልዩ ኃይል›› ብሎ አደራጅቷቸው ሲያበቃ፤ ከኦብነግ ጋር ተያይዞ የሚጠረጠሩ እስረኞች ላይ ያሻቸውን እንዲፈፅሙ ባልተፃፈ ሕግ ስልጣን ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም የቀድሞ ሽንፈታቸውን ለመበቀል እንደ መልካም አጋጣሚ እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ ዛሬ በክልሉ ከተሞች በሚገኙ የተለያዩ የእስር ቤት ግቢዎች ውስጥ የጅምላ መቃብር መመልከት አስገራሚነቱም አስደንጋጭነቱም እየቀረ የመጣው ከዚህ አኳያ ይመስለኛል፡

ኢትዮጵያዊውን የገደለው ቻይናዊ “ለሁለቱ አገራት መልካም ግንኙነት” ሲባል ክሱ እንዲቋረጥ ተደረገ

በምዕራብ ጎጃም ዞን ሰሜን አቸፈር ወረዳ ውስጥ ኢትዮጵያዊውን የገደለው ዠንግ ቢንዥንግ የተባለ ቻይናዊ ‹‹በቸልተኝነት ሰው በመግደል›› ወንጀል ክስ ተመስርቶበት የነበር ቢሆንም ‹‹ለሁለቱ አገራት መልካም ግንኙነት›› በሚል ትዕዛዝ ክሱ መቋረጡን ከክልሉ ፍትህ ቢሮ የተገኘው ሰነድ አጋለጠ፡፡

የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ ለአቸፈር ወረዳ ፖሊስ ጽህፈት ቤት ተከሳሹ ካሳ ከፍሎ መውጣቱ ለሁለቱ አገራት መልካም ግንኙነት እንደሚበጅ በጻፈው ደብዳቤ ክሱ እንዲቋረጥ መደረጉን ‹‹በአማራ ፍትህ ቢሮ የምዕራብ ጎጃም ዞን የፍትሕ መምሪያ የወንጀል መዛግብት መርምሮ መወሰንና ተከራክሮ ማስወሰን የስራ ሂደት›› ለሰሜን አቸፈር ፖሊስ ጽህፈት ቤት በጻፈው ደብዳቤ ተመልክቷል፡፡ በትዕዛዙ መሰረትም ክሱ ቀሪ ሆኖ የምርመራ መዝገቡ ተመላሽ መደረጉን በደብዳቤው ላይ መገለፁን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

በ2004 ኣ.ም. በአርሲ በቻይና ኩባን ተቀጥረው የሚሰሩ ዘጎች በርካታ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በቻይኖች ተፈፅሞባቸው አቤቱታ ቢያቀርቡ የኢትዮጵያ መንግስት ተበዳዮቹንና አቤቱታ አቅራቢዎቹን ለመግደልና ለማሰር በመሞከሩ የሰራተኛ ማኀበሩ አመራሮች ሀገር ጥለው መሰደዳቸው አይዘነጋም፡፡news pic

የታሰሩት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት በመታወቂያ ዋስ ከእስር ተፈቱ

blueመንግሥት ያስተላለፈውን ጥብቅ ትዕዛዝ በመተላለፍ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለመጣስ ሙከራ አድርገዋል በሚል ተጠርጥረው ከታሰሩ በኋላ ከሰባት እስከ 14 ቀናት ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀባቸው ከዘጠኝ ፓርቲዎች የተውጣጡ አመራሮችና አባላት፣ ታኅሣሥ 1 እና 2 ቀን 2007 ዓ.ም በመታወቂያ ዋስ ከእስር ተፈቱ፡፡

የሰማያዊ ፓርቲና የዘጠኙ ፓርቲዎች ጥምረት ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነትን ጨምሮ፣ በአምስት ፖሊስ ጣቢያዎች ታስረው የሰባት፣ አሥርና 14 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ የተጠየቀባቸው 84 እስረኞች በሁለቱ ቀናት ውስጥ የተፈቱ ሲሆን፣ ከአንድ መቶ በላይ የሚሆኑ ለሰላማዊ ሠልፉ ወጥተው ታስረው የነበሩ ሰዎች ሁኔታቸው እየተጣራ ኅዳር 28 እና 29 ቀን 2007 ዓ.ም. መፈታታቸውም ታውቋል፡፡

ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ ስድስት ሰዓት ጀምሮ እስከ ኅዳር 28 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ ስድስት ሰዓት ለ24 ሰዓታት፣ የዘጠኙ ፓርቲዎች ጥምረት ሊያደርግ ለነበረው ሰላማዊ ሠልፍ ቅስቀሳ ወጥተው የታሠሩ ሦስት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ግን አለመፈታታቸው ታውቋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ጸሐፊ አቶ ማቲያስ መኩሪያ፣ የምርጫ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አባል አቶ ባህሩ እሸቱና አቶ ሲሳይ ዘርፉ ናቸው፡፡

ሦስቱ የፓርቲው አባላት የታሰሩት ለሰላማዊ ሠልፉ ቅስቀሳ ወጥተው በመሆኑ ሌሎቹ ሲፈቱ መፈታት ቢኖርባቸውም፣ ፖሊስ ለሁለተኛ ጊዜ የሰባት ቀናት ተጨማሪ ጊዜ ጠይቆባቸው አለመፈታታቸው ተገልጿል፡፡

የታሰሩት የፓርቲዎቹ አመራሮችና አባላት በወቅቱ ከፍተኛ ድብደባ እንደደረሰባቸውና እንደተጎዱ የተገለጸ ቢሆንም፣ የሰማያዊ ፖርቲ አባላት ከሆኑት አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድና ወ/ሪት እየሩስ ተስፋው በስተቀር፣ ሌሎቹ ደህና መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሰውነታቸው ጉዳት እንዳለውና ሕመም እንደሚሰማቸው ከመናገራቸው ውጪ የከፋ ጉዳት እንዳልደረሰባቸው የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርና የምርጫ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ስለሺ ፈይሳ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ምንጭ፡- ረፖርተር

የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

(ከዝዋይ እስር ቤት)

temesgen_desalegn መሐሙድ የሱፍ የተወለደው በ1980ዓ.ም ከሶማሌ ክልል ርእሰ-መዲና ጅጅጋ 500 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በምትገኘውዶሀን ከተማ ነው፡፡ ለቤተሰቡ ሰባተኛ ልጅ ሲሆን፤ አምስት እህቶችእና ሦስት ወንድሞች አሉት፡፡ በጅጅጋ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት እስከ አስረኛ ክፍል ድረስ መዝለቁቢሳካለትም፤ ከዚህ በላይ ግን ሊቀጥል አልተቻለውም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የኢትዮጵያመንግስት የደህንነት ሠራተኞች የ1999ዓ.ም የግንቦት ሃያ በዓል በጅጅጋ ከተማ ስታዲዬም በተከበረበት ዕለት፣ የኦጋዴን ነፃአውጪ ግንባር (ኦብነግ) በሰነዘረው የቦንብ ጥቃት ተሳትፈሃል በሚል ለእስር በመዳረጉነው፡፡ ይህንን ተከትሎምከምድራችን አስከፊ ማሰቃያዎች መካከል ግንባር ቀደም በሆነውና የክልሉ ነዋሪ “ጄል-አዳብ” (የገሃነም እስር ቤት) እያለ በሚጠራው ማጎሪያ ውስጥ እጅግ በጣም የከፋ ምድራዊ መከራ እንደተቀበለሀዘን በተጫነው ድምፅ ይናገራል፡፡ በሠውነቱ የተለያዩ ክፍሎች ላይ እንደ ፍም ቀልተው የሚታዩት ጠባሳዎቹም ያሳለፈውንሥቃይ አፍ አውጥተው ይመሰክራሉ፡፡

ለአራት ወራት ያህል አንድ ክፍል ውስጥ ለብቻው ተቆልፎበት፤ ሃያ አራት ሠዓታትሙሉ እጆቹ በካቴና ተቀፍድደው፣በቀን ከአምስት ጊዜ በላይ ለምርመራ እየተጠራ ያለዕረፍት ከባድ ስቅየት (ቶርቸር)ሲፈፀምበት ቆይቷል:፡ በመጨረሻም ለአንዲትም ቀን የፍርድ ቤት ደጅ ሳይረግጥ፣ ለኦብነግ አባላት አንድ ፓኬት ሲጋራሲያቀብል እጀ-ከፈንጅ ተይዟል በሚል ክስ የጅጅጋ ዞን ፍርድ ቤት በሞት እንዲቀጣ መወሰኑን እዛው እስር ቤት ሆኖከኢትዮጵያ ሬዲዮ የዜና እወጃ እና ከቪኦኤ ሶማሊኛ ፕሮግራም ሠምቷል፡፡

ከፍርዱ በኋላም በተመሳሳይ ወንጀል ከተከሰሰ አንድ እስረኛ ጋር በካቴና ተጠፍሮ በቀን አንድ እንጀራ ለሁለት ተካፍሎእንዲበላ እንደ ውሻ እየተወረወረለት 60 ቀናትን አሳልፏል፡፡ መሐሙድ በተለይም በእንቅልፍ ወቅት እርሱ ወይምየሰንሰለት ደባሉ የተገላበጠ እንደሆነ ካቴናው የሚያደርስበትን የመለብለብ ቃጠሎ ሲያስታውስ ዓይኖቹ በእንባ ይሞላሉ፡፡በአሁኑ ወቅት በዝዋይ ማጎሪያ ከባድ ጥበቃ ለሚደረግባቸው ብቻ በተመደበ ‹‹ዘጠነኛ ቤት›› ውስጥ አስራ አንድ ሶማሊኛተናጋሪዎችን ጨምሮ በድምሩ ሰላሳ አራት ሰዎች ጋር ከዛሬ ነገ የግፍ ፍርዱ ተፈጻሚ ሊሆንብኝ ይችላል በሚል ሰቀቀንእየባነነ በስጋት ተጠፍንጎ መኖር ከጀመረ እነሆ ሰባት ዓመት ሊደፍን ሦስት ወራት ብቻ ቀርተውታል፡፡

 የተዋረደው የፍትሕ ሥርዓት!. . .

ርግጥ ነው ይህ በጨረፍታ ያቀረብኩት አሳዛኝ ታሪክ የመሐሙድ የሱፍ ብቻ አይደለም፡፡ ሌሎች ሰባት ‹‹አባሪዎቹ››ስቃዩንም ሆነ የሞት ፍርዱን ይጋሩታል (በነገራችን ላይ በአንድ መዝገብ የተወነጀሉት እነዚህ ስምንት የሞት ፍርደኞች፡-መሐድ ኢብራሂም፣ አረብ ሰዋኔ ዱልባንቲ፣ ሐሰን መሐመድ ዑስማን፣ ሐሰን መሐመድ ዓሊ፣ ሙክታር መሐመድ ዓብዱላሂ፣ከድር ሽኩር ሙሳ እና ካሚል ዓብዱልናስር እንኳን በጋራ መንግሥት ላይ ሊያሴሩ ቀርቶ እርስ በርስም የተዋወቁት እስር ቤትውስጥ ነው፡፡ ከጅጅጋ ወደ ዝዋይ ‹‹ዘጠነኛ ቤት›› ተዘዋውረው በርካታ ዓመታትን ያሳለፉትም በጭካኔው ወደርእንደማይገኝለት የሚነገረው የክልሉ ፕሬዚዳንት አብዲ በአደራ እንዲቀመጡ በመተላለፋቸው መሆኑን ነግረውኛል፡፡) እንደ መሐሙድ ሁሉ እነርሱም ፍርድ ቤት ቀርበውአያውቁም፤ ምንም ዓይነት የሰውም ሆነ የሰነድ ማስረጃ አልተቆጠረባቸውም፡፡ እዚህ ጋ የማነሳው አሳዛኝ ገጠመኝከመካከላቸው አንዳቸውም ራዲዮ ስላልነበራቸው የተጣለባቸውን የሞት ፍርድ ውሳኔ የሠሙት፣ ዜናው ከተላለፈ ከበርካታቀናት በኋላ ሬዲዮ ካላቸው እስረኞች መሆኑ ነው፡፡

ይህ እጅግ አሳፋሪና አስደንጋጭ መንግሥታዊ ውንብድና በደንብ ይብራራ ዘንድ ለተከሳሶቹ ከተሰጣቸው ባለ አንድገፅ የክስ ቻርጅ የሁለቱን ብቻ በአዲስ መስመር እጠቅሳለሁ፡-‹‹በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ሕግና ፍትሕቢሮ በሶማሌ ክልላዊ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት ጅጅጋ የዐ/ሕግ/መ/ቁ 90/2000

ከሳሽ፡- ዐ/ሕግ

ተከሳሽ፡- ሐሰን መሐመድ ዑስማን (ሐንን መድቤ)

ዕድሜ፡- 21 ሥራ፡- ተማሪ አድራሻ፡- ጅጅጋ ከተማ፡- 06 ቀበሌ ወንጀል በ1996ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ.መ.ሥ.ሥ.ህ.ቁ. 240(3) እና 251(መ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀል ዝርዝር

ተከሳሽ ከመስከረም 1999 ዓ.ም. ጀምሮ እራሱን ኦ.ብ.ነ.ግ. እያለ ከሚጠራው ተቃዋሚና አሸባሪ ድርጅት ጋር በራሱፈቃድ በዚሁ በጅጅጋ ከተማ ከላይ በተጠቀሰው ዓመተ-ምህረት አባል በመሆን በጫካ በዚሁ አካባቢ ከሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች ጋርበከተማም

ሆነ በጫካ በመገናኘት በኢኮኖሚ ረገድ የሚያስፈልጋቸውን፡- ጫማ፣ ልብስ የመሳሰለውን እዚያው ድረስ ሄዶ በማቀበልአብሮ ሲንቀሳቀስ በመቆየቱ ተከሶ ቀርቧል፡፡››

ሁለተኛው የክስ ቻርጅ ደግሞ እንዲህ ይነበባል፡-

‹‹በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ሕግና ፍትሕ ቢሮ

በሶ/ክ/መ/ ጅጅጋ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት

ጅጅጋ

የዐ/ሕ/መ/ቁ 90/2000

ከሳሽ፡- ዐ/ሕግ

ተከሳሽ፡- መሐድ ሼክ ኢብራሂም

ዕድሜ፡- 28፣ሥራ፡- የለውም አድራሻ፡- ጅጅጋ ከተማ፡- ቀበሌ 05

1ኛ ክስ፣ወንጀሉ፡-

በ1996 ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ/መ/ህ/ ቁ. 241 እና 251(መ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀሉ ዝርዝር

ተከሳሹ በ1998 ዓ.ም. ወራትና ቀኑ በውል ካልታወቀ ጊዜ ጀምሮ እራሱን ኦ.ብ.ነ.ግ. እያለ ከሚጠራው ተቃዋሚ የፖለቲካ

ድርጅትና አሸባሪ ጋር በራሱ ፈቃድ አባል በመሆን ከዚህ ሕገ-መንግሥቱን ከሚፃረር ድርጅት በቀጥታ ፌዴሬሽኑእንዲከፋፈል፣ ክልሉን

የመገንጠል ዓላማ ለማሳካት ይህንኑ ድርጅት ከዚሁ በጅጅጋ ከተማ ለጊዜው ካልተያዘ ግብረ-አበሩ ጋር በመሆን ይህንኑአሸባሪ ድርጅት

በሚያስፈልገው ማቴሪያል ሁሉ፡- ጫማ፣ የፖሊስ የደንብ ልብስ፣ መድሃኒት. . . የመሳሰለውን በማቀበሉ፡፡

2ኛ ክስ፣ወንጀሉ፡-

በ1996ዓ/ም የወጣውን የኤ.ፌ.ዴ.ሪ የመ/መ/ህ/ ቁ. 36 (ለ) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣

የወንጀሉ ዝርዝር

ተከሳሹ ከ1996 ዓ.ም. ጀምሮ የተለያዩ መ/ቤቶች ማለትም፡- የክልሉ ት/ቢሮን፣ የቀብሪ-ደሐር ት/ቢሮን፣ እንዲሁም የMSF እና የተለያዩ መሥሪያ ቤቶችን እና የትምህርት ተቋማትን ማህተም በማስመሰል አትሞ እና የኃላፊዎችን ፊርማ ዓይነትአስመስሎ በማስፈር ሐሰተኛ ሰነድ አዘጋጅቶ በመገኘቱ ተከሶ ቀርቧል፡፡›› (ሁሉም የክስ ቻርጆች ማኅተም እና አንጋው አፈወርቅ ምንተስኖት የተባለ የክልሉ ዐቃቤ ሕግ ፊርማ አላቸው) እነሆም ያለአንድ ምስክር፣ ያለምንም የሰነድ ማሰረጃ፣ አንድም ቀን ችሎት ቀርበው የእምነት ክህደት ቃል ሳይጠየቁ እና ሳይከራከሩ (ያውም የዞን ፍርድ ቤት) በነዚህ በስም በጠቀስኳቸው በስምንቱ ኢትዮጵያውን ላይ የሞት ቅጣትን የመሰለየመጨረሻ ውሳኔ እንደቀልድ አስተላልፎባቸዋል፡፡ (በነገራችን ላይ ሌሎች 13 የኢትዮጵያ-ሶማሌ ተወላጆችም በተመሳሳይ የሐሰትውንጀላ የዕድሜ ልክ እስር ተፈርዶባቸው ዝዋይ ይገኛሉ፡፡ የሚገርመው ጉዳይ ደግሞ ም ቢሆኑ መጀመሪያ ተጠርጥረው በተያዙበት ወንጀልአይደለምየተጠየቁት፡፡ ጉዳዩ ጭራሽኑ በምርመራም ወቅት አልተነሳም) መቼም በዚህ መልኩ በተቀናበረ የውሸት ክስ ከ20-27 ዓመት የሚገኙ ወጣቶችን በሲኦላዊ እሳተ-ነበልባል ስቅየት ውስጥ እንዲያልፉ ከማድረግም በዘለለ፣ ብሩህ ቀናቸውን አጨልሞ ላይመለሱወደመቃብር የሚሸኝ ቅጣት ሲጣል ከመመልከት የበለጠ የትኛውንም ዜጋ የሕሊና ስቃይ ውስጥ ከትቶ፣ አንገት አስደፍቶ፣ በቁጣ ቀስቅሶ ወደአደባባይ የሚያወጣ ገፊ-ምክንያት አለ ብዬ አላምንም፡፡

ማነው ተጠያቂው?

በእነዚህ ንፁሃን ኢትዮጵያውያን ላይ ‹በጄል-አደብ› የደረሰባቸው በነውረኝነት የታጀለ ኢ-ፍትሐዊ ፍርድ እና ስቅየት፣ የሥርዓቱን እውነተኛ ማንነት ገሃድ የሚያወጣ ተጨባጭ ተግባር መሆኑ ባይካድም፡ ይህንን አረሜናዊ ድርጊት በፊት-አውራሪነት የመሩት፡- ኮሎኔል ሞኒ መንገሻ በጊዜው የክልሉ የፀረ-ሽብር ግብረ-ኃይል ዋና ኃላፊ የነበረ አሁን ወደአዲስ አበባ ተቀይሮ‹ሕገ-ወጥ የሠው ዝውውር ወንጀል መከላከል› ኃላፊ፣ ቢኒያም የተባለ የክልሉ የደህንነት ኃላፊ፣ ሻለቃ ዘገየ በክልሉ የፌዴራል ፖሊስኃላፊ፣

ወልደአራዌ የክልሉ ፖሊስ ም/ኮሚሽነር፤ እንዲሁም ሻለቃ ወንድሜ፣ ሻለቃ በለጠ እና ታሰረ የተባሉ ኃላፊነታቸውንለይተው የማያስታውሷቸው ግለሰቦች መሆናቸውን ግፉአኖቹ በተሰበረ ልብ፣ ምሬት በሞላው ድምፅ፣ ተስፋ በቆረጠ ስሜትሲተርኩልኝ ዓይኖቼ ላይ የተቋጠረው የእንባ ከረጢት ገንፍሎ እንዳይፈስ ብርቱ ትግል ማድረጌን አልሸሽግም፡፡

የሆነው ሆኖ እነዚህ የሥርዓቱ ሹማምንት የፍርድ ቤት ደጅ ሳይረግጡ፣ የሞት ቅጣት እንዲተላለፍባቸው ባደረጓቸው ምስኪኖች ላይ የማሰቃያ ጥበቦቻቸውን በሙሉ ከሞከሩባቸው በኋላ፡- ‹‹ሞት እንፈርድባችኋለን!!›› እያሉ ያስፈራሯቸውናይዝቱባቸው ነበር፤ እነርሱም፡- ‹‹እናንተ ፍርድ ቤት ናችሁ እንዴ?›› ብለው በግርምትና ባለማመን ሲጠይቋቸው፣ ማናአህሎኝነትያሳበጣቸው የፀጥታ

ኃላፊዎች እንዲህ በማለት አስረግጠው መልስ መስጠታቸውን ሰምቻለሁ፡-

‹‹አዎን! ፍርድ ቤት ማለት እኛ ነን!!››

በርግጥ ከዚህ ሁሉ መከራ በኋላ የተላለፈባቸው ውሳኔ፣ ያውም በሞት እንዲቀጡ የሚል መሆኑን ስናስተውል የዛቻውን መነሾ መረዳቱ አዳጋች አይሆንብንም፡፡ በአናቱም በምርመራ ወቅት ዕድል ፊቷን ያዞረችበትን ተጠርጣሪ እዛው እስረኛ ፊትበሽጉጥ ግንባሩን በርቅሰው እንደ መናኛ ነገር ሜዳ ላይ ይዘረጉት እንደነበረ የዓይን እማኞች ይመሰክራሉ፡፡

በጥቅሉ ይህ ሁነት በሀገሪቱ አለቅጥ የተንሰራፋውን የፍትሕ እጦት፣ የሠብአዊ መብት ጥሰት፣ ዳኞች ከሕግ ይልቅ ከቤተ- መንግሥት በሚላክላቸው የፍርድ ውሳኔ ንፁሃኑን ለምድራዊ ስቃይ ከመዳረግም አልፈው ተርፈው በጭካኔሕይወታቸውንም እንደሚነጠቁ በቂ ማስረጃ ይመስለኛል፡፡

‹‹ጄል-አዳብ››

የክልሉ ኗሪዎች ‹‹ጄል-አዳብ›› (የገሃነም እስር ቤት) እያሉ የሚጠሩት የጅጅጋው ማሰቃያ ቤት ክፍሎች የተሠሩት አራትመቶ ታሳሪዎችን እንዲይዙ ታስቦ ቢሆንም፣ አብዛኛውን ጊዜ ከአራት ሺህ በላይ ታሳሪዎች እንደሚታጎሩበት አረጋግጫለሁ፡፡ይህም አንድ ሰው ከአንድ ሰዓት በላይ በእንቅልፍ ማሳለፍ እንዳይችል አድርጎታል፡፡ ምክንያቱም ቦታውን ለተረኛው የመልቀቅ ግዴታአለበትና፡፡

ምናልባት እንቅልፍ ቢጥለው እንኳ ተረኞቹ ቀስቅሰው (ጎትተው) ያስነሱታል፡፡

ከ‹‹ጄል-አዳብ›› በሕይወት ተርፎ የሚወጣ ሰው ዕድለኛ ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ በዚህ ቦታ ከቤተሰብ ጋር መገናኘት ጭራሽ አይሞከርም፡፡ ማሰቡ እንኳ እንደ ቅንጦት ነው የሚታየው፡፡ በእስር ቤቱ አጥር ሦስት መቶ ሜትር ክልል ርቀት ዙርያ ውስጥመገኘትም ለከባድ ስቃይ (አንዳንዴም ለሞት ቅጣት) ይዳርጋል፡፡ በሃያ አራት ሰዓት አንዴ፣ አንድ እንጀራ ለሦስት እየተቃመሱለአምስት ዓመት በዛ እስር ቤት ያሳለፈ ምስኪን አጋጥሞኛል፡፡ ይህ ወጣት በ2004ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ ሦስት ዓይነት ተላላፊ  በሽታ (ተቅማጥ፣ ሰውነትን የሚያሳክክና ጉሮሮን አሳብጦ ለአዕምሮ መቃወስ የሚዳርግ) ተከስቶ በቀን እስከ አስራ አራት ሰው ድረስ ይሞትእንደነበር ያስታውሳል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ሕክምና ብሎ ነገር አልነበረም፡፡

እንዲያውም በግልባጩ የክልሉ አስተዳዳሪዎችጭካኔያቸውን (ኢ-ሠብአዊነታቸውን) ወለል አድርገው የሚያሳብቁ ድርጊቶች መፈፀማቸውን አላቋረጡም፡፡ ለማሳያ ያህልም እስረኛው ከሌሊቱስድስት

ሰዓት ላይ በአንድ ድምፅ እንዲህ የሚል መፈክር እንዲያሰማ መገደዱን እዚህ ጋ መጥቀስ ይቻላል፡-

‹‹መለስ ዜናዊ ሐኖላዶ!›› (መለስ ዜናዊ ለዘላለም ይኑር!)

‹‹አብዲ ሑመድ ዑመር ሐኖላዶ!››

‹‹ኢትዮጵያ ሐኖላዶ!››

ኦብነግ ሐዳኦዶ!›› (ኦብነግ ይውደም!)ሌላው አስገራሚ ጉዳይ ቤተሰብ ታሳሪ ልጁ በሕይወት ይኑር ይሙት የሚያውቀውከማጎሪያው በስንት ጊዜ አንዴ የሚፈታ ሰው ሲገኝ ብቻ የመሆኑ እውነታ ነው፡፡ እናም ድንገት በአንዲት ‹ዕድለኛ› ቀን አንድ ታሳሪ ከ‹‹ጄል-አዳብ›› የተለቀቀእንደሆነ ወሬው ከመቅጽበት ይዛመትና ለሳምንታት አሊያም ለወራት የእስረኛው ቤት በእንግዶች እስከ አፍ-ገደፉ ጢም ብሎ ይውላል፡፡የተለመደ ነውና እሱም ያለመታከት የቀረበለትን ጥያቄ በሚከተለው መልኩ ሲመልስ ይከርማል፡- ‹‹ኦ!… እገሌ ከሞተ እኮ ሁለት ዓመት አለፈው›› ፤ “እገሌማ ሲያሳዝን! ካረፈ ገና አንድ ወሩ ነው”፤ “ኦ! እገሌ ለወደፊቱ እግዜር ይጠብቀው እንጂ እስካሁን በሕይወት ይገኛል…” ወዘተ ወዘተ. . .

የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ላይ ተሻሽሎ ቀርቧል የተባለው ክስ ተሰማ

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው እየታየ ያሉት የዞን 9 ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ ማህሌት ፋንታሁን እና ናትናኤል ፈለቀ እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ ላይ የተመሰረተው ክስ ተሻሽሎ ቀርቧል የተባለው የክስ ዝርዝር ዛሬ በልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ተሰምቷል፡፡

zone9ዛሬ ህዳር 24 ቀን 2007 ጠዋት በዋለው ችሎት፣ በብሎገሮቹ እና ጋዜጠኞች ላይ ተሻሽሎ የቀረበው የክስ ዝርዝር በንባብ የተሰማ ሲሆን በክስ ወረቀቱ ላይ ከተመለከቱት ነጥቦች መካከል ግልጽ ያልሆኑ ነጥቦችን አካትቶ እንዲሰጥ ለአቃቤ ህግ ትዕዛዝ ተሰጥቶታል፡፡ ስለሆነም ሙሉ የክስ ወረቀቱ አርብ ለጠበቆቹ እንደሚደርስ ይጠበቃል፡፡

በጠቦቆቹ በኩል ክሱ ቀደም ብሎ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት መሻሻሉን ለማረጋገጥ ያለፈው የፍርድ ቤቱ ብይን ግልባጭ እስካሁን እንዳልደረሳቸው በመግለጽ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲደርሳቸው ጠይቀዋል፡፡ በዚህም የተነሳ የብይኑ ግልባጭ ሳይደርሰን ተሻሻለ የተባለው ክስ መሰማት የለበትም ብለው የነበር ቢሆንም፣ ክሱን አይታችሁ መቃወሚያ ካላችሁ አስተያየት እንድትሰጡበት እድል እንሰጣለን ያለው ፍርድ ቤቱ ክሱ እንዲሰማ አድርጓል፡፡

ፍርድ ቤቱ ጠበቆቹ ያላቸውን አስተያየት ይዘው እንዲቀርቡ ለታህሳስ 7 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱን የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡