Tag Archives: Ethiopian politics

በርካቶችን ለሞት የዳረገው የኦሮሚያ – ሶማሌ ግጭት እስከ ትናንት አለመቆሙን መንግስት አስታውቋል

አለማየሁ አንበሴ
Abdi,kassa & Lemma
አቶ አብዲ መሐመድ፥ እቶ ካሳ ተክለብርሃን እና አቶ ለማ መገርሳ

በኦሮሚያ እና በሱማሌ ክልሎች መካከል የተፈጠረው ግጭት እንደቀድሞ የወሰን ጉዳይ እንዳልሆነ የተጠቆመ ሲሆን፣ ትክክለኛ መንስኤው እየተጣራ መሆኑን ያስታወቁት የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ፤ ግጭቱ እስከ ትናንት አርብ ድረስ በተለያዩ ቀበሌዎች መቀጠሉንና በርካቶች ተገድለው፣ ከ20 ሺህ በላይ ዜጎች መፈናቀላቸውን አስታውቀዋል፡፡

ለበርካታ ቀናት በቀጠለ ግጭት፤ የሠው ሕይወት ጠፍቷል፣ ንብረት ወድሟል፣ ዜጎች ተፈናቅለዋል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ግጭቱ በቅርቡ እንዲገታ ይደረጋል፤ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎችም በመሃል ገብተው የማረጋጋት ስራ ይሠራሉ ብለዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለ ማርያም ደሣለኝ፤ ከሁለቱ ክልል አመራሮች ጋር በግጭቱ ላይ በስልክ ውይይት ማድረጋቸውንና ግጭቱ እንዲቆም ማሣሠቢያ መስጠታቸውንም ሚኒስትሩ አስታውቀዋል፡፡
በአካባቢው ለግጭቱ መባባስና ለሠው ህይወት መጥፋት ምክንያት የሆኑ ለህግ እንዲቀርቡ ይደረጋል ያሉት ሚኒስትሩ፤ የመሳሪያ ትጥቅ የማስፈታት ስራም ይሰራል ብለዋል፡፡

የመከላከያ ሰራዊትና የፌደራል ፖሊስ በግጭቱ መሃል ገብቶ ለማረጋጋት ለምን ዘገየ ተብለው የተጠየቁት ሚኒስትሩ፤ ክልሎቹ ችግሮቹን በራሳቸው ይፈቱታል የሚል እምነት በመጣሉ ነው ብለዋል፡፡
በግጭቱ የሶማሊያ ሪፐብሊክ ኃይሎችና የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል መሳተፋቸው ተጣርቶ ህጋዊ እርምጃ ይወስዳል ብለዋል – ሚኒስትሩ፡፡ ግጭቱ በታጠቁ አካላት የታገዘ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትሩ፤ እነዚህ የታጠቁ አካላት እነማን ናቸው የሚለው ግን እስካሁን ምላሽ አለማግኘቱንና በማጣራት ሂደቱ እንደሚታወቅ ተናግረዋል፡፡ ግጭቱ የህዝብ ለህዝብ አለመሆኑን ግን አስረግጠው በመግለፅ፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የሁለቱ ክልሎች የመንግስት ኮሚኒኬሽን ኃላፊዎች ጉዳዩን አስመልክቶ በየሚዲያው የሚያስተላልፏቸው መግለጫዎች፣ ግጭቱን ሊያባብሱ የሚችሉ በመሆኑ ከእንግዲህ በኋላ ግጭት አባባሽ መግለጫዎችን ከመስጠት እንዲቆጠቡ ዶ/ር ነገሪ አሳስበዋል፡፡

የኮሚኒኬሽን ኃላፊዎቹ ከዚህ ድርጊታቸው የማይቆጠቡ ከሆነ፣ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድም ሚኒስትሩ ጠቁመው፤ በሁለቱም የሚገለፁ አሃዛዊ መረጃዎችንም ገና ያልተጣሩ መሆናቸውንና መንግስት ሁኔታውን አጣርቶ እንደሚገልፅ አስታውቀዋል፡፡

የሶማሌ ክልል ግጭቱን አስመልክቶ ለቪኦኤ በሰጠው መግለጫ፤ በአወዳይ ከተማ 50 ሠዎች መገደላቸውን ሲገልፅ፣ የኦሮሚያ ክልል በበኩሉ፤ በአወዳይ ከተማ 18 ሰዎች መገደላቸውን፣ ከነዚህ ውስጥ 12ቱ የሶማሌ ተወላጆች፣ ቀሪዎቹ የኦሮሞ ጃርሶ ጎሣ አባላት መሆናቸውን አስታውቋል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋ ትናንት ምሽት ባሰራጩት መረጃ፤በሰሞኑ ግጭት ከተፈናቀሉት ከ22ሺ በላይ ዜጎች በተጨማሪ አጠቃላይ የድንበር ግጭቱ ከተከሰተበት ከ2009 ጀምሮ 416ሺ807 ዜጎች መፈናቀላቸውን አስታውቀዋል፡፡

በአወዳይ የደረሠውን ግጭት ተከትሎ፣ ከሶማሌ ክልል ከ21 ሺህ በላይ ዜጎች ተፈናቅለው በጭናቅሠን፣ ባቢሌና ሐረር ከተሞች ተጠልለው እንደሚገኙ የኦሮሚያ ክልል ቃል አቀባይ አቶ አዲሱ አረጋንና ምንጮቹን ጠቅሶ ቪኦኤ ዘግቧል፡፡

የሱማሌ ክልል የመንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ኢንድሪስ አህመድ በበኩላቸው፤ “ሰዎች ከአካባቢው የተፈናቀሉት በግዴታ ሳይሆን በፍቃዳቸው ነው፤ ጥቃት አልተፈፀመባቸውም” ብለዋል፡፡ ምንጮች በበኩላቸው፤ የግዳጅ ማፈናቀል መፈፀሙንና በዜጎች ላይ ድብደባና እንግልት እንደደረሰባቸው ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል፡፡

የሱማሌ ክልል መንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ኢንድሪስ አህመድ፤ በአወዳይ ከተማ የደረሰውን ግድያ ተከትሎ ባስተላለፉት መግለጫ፣ የኦሮሚያ ክልል መንግስትን “የአሸባሪነት አላማ አራማጅ” በሚል የፈረጀ ሲሆን የኦሮሚያ ክልል ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ ፍረጃውን አጣጥለው፣ ከአንድ ክልልን ከሚያስተዳድር አካል የማይጠበቅ ነው ብለዋል፡፡

የሶማሌ ክልል መንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊ ለቪኦኤ በሰጡት መረጃ፤ በአስራ አንድ የሶማሌ ወረዳዎች፣ ማንነታቸው ባልታወቀ አካላት በተሠነዘሩ ጥቃቶች፣ ከሁለት መቶ አስራ ሶስት ሰዎች በላይ ህይወት ማለፉን አስታውቀዋል፡፡ ይሄን ተከትሎም የሶማሌ ክልላዊ መንግስት፣ ለ5 ቀናት የሚቆይ ብሄራዊ የሃዘን ቀናት በክልሉ ማወጁንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ፣የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን የግጭቱን መነሻና የደረሰውን ጉዳት የሚያጣራ ቡድን ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ወደ አካባቢው መላኩንና ማጣራት መጀመሩን የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደምሰው በንቲ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡

ሰሞኑን የሁለቱ ክልሎች የመንግስት ኮሙኒኬሽን ኃላፊዎች በማህበራዊ ድረ-ገፆቻቸው የሚያሰፍሯቸው የእርስ በርስ ውንጀላዎች አስደንጋጭና ግጭቱን የሚያባብሱ መሆናቸውን አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡ ክልላዊ መንግስታቸውን ወክለው መልዕክት የሚለዋወጡ እንደማይመስሉና ኃላፊነት የጎደሏቸው እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ምንጭ፡ አዲስ አድማስ

የዶ/ር መረራ ጉዳይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ትርጉም እንዲሰጥበት ትእዛዝ ተሰጠ

የእነ ዶ/ር መረራ ጉዲና መዝገብ ለዛሬ የተቀጠረው ከዚህ ቀደም በቀረበው መቃወሚያ ላይ ብይን ለመስጠት ነበር። በመሆኑም ዛሬ – ሰኔ 30/2009 – ዶ/ር መረራ ጉዲና በተመሰረተባቸው 3ት ክሶች ላይ ያቀረቧቸው መቃወሚያዎች ላይ 19ኛው ወንጀል ችሎት ከፊል ብይን ሰጥቶበታል። ችሎቱ፣ ዶ/ሩ ያቀረቡትን ክሱ እንዳይንጓተት ከሌሎቹ በሌሉበት ከተከሰሱት ሶስት ተከሳሾች ይነጠልልኝ የሚለውን መቃወሚያ ጨምሮ ሌሎቹን መቃወሚያዎች በሙሉ ውድቅ ሲያደርግ አንዱን ግን ለትርጉም ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ለትርጉም መላኩን ተናግሯል።

dr-merera-gudina-aau

ዶ/ር መረራ ጉዲና

በእነዶ/ር መረራ መዝገብ የተከፈተው ክስ ላይ አቃቤ ህግ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን በመጥቀስ፣ የምስክሮች ሥም ሳይጠቀስ የቀረ ሲሆን፣ ይህ በሥራ ላይ ያለው የሥነ ስርዓት ሕግ ተከሳሾች የሚቀርብባቸውን ማስረጃ እና ምስክር የማወቅ መብት አላቸው ከሚለው ጋር የሚጋጭ በመሆኑ እንዲተረጎም ወደፌዴሬሽን ምክር ቤት ተልኳል። የተከሳሹ ጠበቃ አቶ ወንድሙ ኢብሳ በበኩላቸው “እኛ የጠየቅነው፣ ደንበኛችን ባልተከሰሱበት የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ የምስክር ጥበቃው አንቀፅ ሊጠቀስባቸው አይገባም ብለን እንጂ ትርጉም ያስፈልጋል ብለን አይደለም” ብለው ቅሬታቸውን አቅርበዋል።

ዶ/ር መረራም መልእክት አለኝ በማለት የሚከተለውን ለዳኞች ተናግረዋል፣ “የተመሰረተብኝ ፖለቲካዊ ክስ ነው። መንግስት ይዞ የተነሳው ተቃዋሚዎችን በራሱ የተበላሸ አስተዳደር ጥፋት ጉዳይ መወንጀል ስለሆነ እንጂ መንግሥት የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ በጠየቀበት ጉዳይ ነው የተከሰስኩት። የተከሰስኩት፣ ለኦሮሞ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለኢትዮጵያ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለእኩልነት እና ሁላችንንም እኩል ለሚመለከት ስርዓት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ሀቀኛ የፍትህ ስርዓትና የፌዴራል ስርዓት እንዲኖር በመታገሌ ነው። ዳኞች እስካሁን ካላነበባችሁ፣ የአቤ ጉበኛን አልወለድም እና የበአሉ ግርማን ኦሮማይ አንብቡ። ሊወድቅ እየደረሰ መንግስት የሚሰራውን ሥራ የሚያስረዱ መፅሃፍት ናቸው።”

ዳኞች መዝገቡን ለሐምሌ 25/ 2009 የተቀጠሩ ሲሆን፤ በሚቀጥለው ቀጠሮ ችሎቱ የምስክሮች ዝርዝር መገለፅ አለበት በሚል ክሱ እንዲሻሻል ወይም የለበትም በሚል የቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ይይዛል ተብሎ ይጠበቃል።

EHRP

አቶ ፈቃደ ሸዋቀና አረፉ

የቀድሞው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ስነ ምድራዊ ጤና መምህር የነበሩት አቶ ፈቃደ ሽዋቀና ባጋጠማቸው የጤና ችግር ምክንያት በህክምና ሲረዱ ቆይተው ግንቦት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. በስደት ይኖሩ ከነበረበት አሜሪካ ህይወታቸው አልፏል።

Fekade Shewakena

አቶ ፈቃደ ሸዋቀና ህወሓት/ኢህአዴግ ግንቦት 1983 ዓ ም አዲስ አበባ ገብቶ ስልጣን ከተቆጣጠረ በኋላ ወዲያ 42 የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህራን በሟቹ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜና ትዕዛዝ ከተባአረሩ አንዱ ነበሩ።

አቶ ሸዋቀና ከስራቸው እንዲባአረሩ ከተደረጉ ብሏላ ወደ አሜሪካ በመሰደድ በሙያቸው የአንድ SCG ኩባንያ የስነምድር ጤና ተንታኝ በመሆን ለ25 ዓመታት አገልግለዋል። ከሙያቸው በተጨማሪ በይበልጥ በተለያዩ ፅንፍና ጠርዝ ላይ ያለውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ ወደ መሐል ለማምጣት ባደረጉት የአስታራቂነት ሚና እና ጥረት በሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች እምነትና ከበሬታን ማግኘት የቻሉ እንደነበሩ ይነገርላቸዋል።

የቀብር ስነ ስርዓታቸውም በስደት ዓለም በቆዩባት አሜሪካ እንደሚፈፀም የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

አቶ አሰፋ ጫቦ አረፉ

ዮሐንስ ሞላ

አቶ አሰፋ ጫቦ ከአባቱ ከጫቦ ሣዴ ሃማ ያሬና ከእናቱ ከማቱኬ አጀን ከተራራ አናት ላይ ከሚገኝ ሜዳማ ቦታ ላይ ጨንቻ ከተማ ነው የተወለደው፡፡ከጋሞ ሰንሰለት ተራራዋች አንዱ ጫፍ ላይ የሚገኝ ጠረጴዛ ነው ይላታል ጨንቻን ሲገልጣት ከ2-6ኛ ክፍል እዚያው ጨንቻ የተማረ ሲሆን በዘጠኝ ዓመቱ የጨንቻ ገብርዔል ዲያቆን በመሆንም አገልግሏል በድቁናው ባገኘው ካፒታልም ጥቂት የዶሮና የበግ ግልገል ገዝቶበታል ሐሙስ ሐሙስን እየጠበቀ ኤዞ ገበያ ዶሮና እንቁላል አየነገደ ይውል ነበር ከእነሱም ውስጥ ት/ቤት ድረስ እየተከተሉ ያስቸግሩት የዶሮና የበግ ግልገልም ነበረው እንደፈረንጆቹ pet መሆናቸው ነው፡፡

Assefa Chabo
የ8ኛ ክፍል ትምህርቱን በሻሸመኔ በኃላ ታሪኩን ሲያውቅ ስሙን ካላስቀየርኩ ብሎ ከታገለበት ከአጼ ናኦድ ት/ቤት ከ39 ተማሪዎች አንዱ በመሆን ነበር የተከታተለው የተዋቀረበትን ዋልታና ካስማ ያየበት ቆይታው በጋሞ ውስጥ ካሉ 40 ከሚሆኑ ‹ካዎ›ች አንዱ በሆኑት በዘመዱ በቀኛዝማች ኢሌታሞ ኢቻ ቤት በኖረበት ወቅት ነበር፡፡

ሲገልጻቸውም ‹በኢሌታሞና በሰዋች መሀከል የግንኙነት አጥር የለም፡፡ወግ ሳያበዙ ለህዝብ አሳቢና ተቆርቋሪ ናቸው ነው› የሚላቸው የጋሞ ካዎ የሚፈራ ሳይሆን የሚከበር ነው ይለናል፡፡ ገና በልጅነቱ ለህዝብ በመስራት እርካታ ማግኘት እንደሚቻልም የተገነዘበው በጉሌታ-አንዱሮ ግብር ተቀባይ ተደርጎ በቀኛዝማች ኤሌታሞ ሲመደብ ነው ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ከአዲስ አበባ ከኮከበ ጽባህ አቋርጦ ሲቪል አቪዬሺን ተቀጥሮ ባህር ዳር ሄደ፡፡ ‹ሀ› ብሎ የመጀመሪያውን ስራውንና የመጀመሪያ ልጁንም ያገኘው ጎጃም ነበር፡፡ ‹ጎጃሜ ተነቀለ› ብሎ ፖሊስና እርምጃው ላይ ጽፎ ጠፍቶ እስከወጣ ድረስ እዚው ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ሕግ ት/ቤት LLB አግኝቶ የተመረቀ ሲሆን በዓለም አቀፍ የህግ ተማሪዋች ውድድር ከውጭ የምስክር ወረቀት ከንጉሱም የወርቅ ኦሜጋ ሰዓት ተሸልሟል፡፡

በ 1960 የህግ ተማሪ ሆኖ በአፍሪካ አዳራሽ የቀድሞ ተማሪዎች ማህበር ስብሰባ ላይ ከመጮህ ጀምሮ ይህው እስከእልፈተ ሞቱ ድረስ ለአገርና ለወገን ዋይታውን አላቋረጠም ነበር ፡፡ በአጠቃላይ የአጥቢያ ፍ/ቤት ጸሐፊ፤የበጅሮንድ ጽ/ቤት ተላላኪና ጸሐፊ የአየር መርማሪ (metrology) የህግ አማካሪ ሆኖ ሰርቷል፡፡በፖለቲካው መስክ ከተማሪዎች ንቅናቄ ባሻገር የሁለት ድርጅቶች መስራችና መሪ ሲሆን ከ 1966-1967 የልጅ እንዳልካቸው አዲሱ ካቢኔና የደርግ አውራጃ አስተዳዳሪ ሆኖ ጋርዱላ ሄዶ ነበር፡፡ በጄኔራል መብራቱ ፍስሃ ታስሮ እስከተባረረ ድረስ የፖለቲካ ድርጅት መስራችና መሪ፤የአውራጃ አስተዳዳሪ የመንግሰትና የባለስልጣን አማካሪ፤የህዝብ ተከራካሪ በመሆን በለውጡ ውስጥ ሰርቶእል፡ ፡

በኃላም በራሱ ከግቢ የመራቅ ጥያቄ አነሳሽነት ‹‹በችሎታው መጠን ሥራ ይሰጠው›› የሚለውን ሻምበል ፍቅረስላሴ ወግደረስ የፈረመበትን ደብዳቤ ይዞ መገናኛ ሚኒስቴር ወረደ፡፡ ከዚያ ነው እንግዲህ በየካቲት 1971 ዓ.ም መጀመሪያ ወደ ደርግ ጽ/ቤት ታፍኖ ተወስዶ ከዚያም በማዕከላዊ ታስሮ ከ 10 ዓመት ከ 6 ወራት ከ 6 ቀናት በኃላ የተፈታው፤ ማዕከላዊ እስር ቤት የሰው ገበያ ነበር ብሎ ሲገልፀው በ10 ዓመት የእስር ዘመኔ ውስጥ ከ100.000ሺ በላይ ሰው አይቼበታለው ይለናል ካያቸውም ውስጥ በባህርይ፣በቁመና፣በአለባበስና በስነምግባራቸው ጥሩ አድርጎ በመጻህፉ ውስጥ ይገልጻቸዋል፡፡

እንደተፈታም የአስኮ ጫማ ሱቅ የነበረበት ፎቅ ላይ የጥብቅናና የንግድ አማካሪ ቢሮ በመክፈት ሙግቱን አስረዝሞ ገንዘብና ጊዜ ከማባከን ይልቅ አስቀድሞ በድርድርና ከፍ/ቤት ውጭ ለመጨረስ ያደረገው ጥረትም ከዚሁ ከራሱ ማንነት የመነጨ ነው፡፡ በሽግግር መንግስቱ የምክር ቤት አባል በመሆንም በ 1983 አርባ ምንጭ ሄዶ ነበር ሁሉም አልሆን ሲለው ያለውዴታ በግድ አሜሪካ በስደተኝነት መጥቶ መኖሩን ጀመረ፡፡

በተፈጥሮው ሰው መጥላት የማይፈልገው አንጋፋው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች፣ ቀጥተኛው፣ ብዕረኛው አቶ አሰፋ ጫቦ የ 73 ዓመት ባለዕድሜው የአራት ልጆች አባትና የዘጠኝ ልጆች አያት ነበር ፡፡

‹የትዝታ ፈለግ› በሚል ርዕስ ለንባብ ያበቃውን መጽሐፉን በምናነብበት ወቅት ብዙ ወደማናቃቸው ጊዜያትና ግለሰቦች ከመውሰዱም ሌላ የአጻጻፍ ውበቱ እጅግ ያስደንቃል የባህሪይ አቀራረፅ ችሎታውና የአካባቢ ስዕላዊ መግለጫው ያረካል ‹‹ነፍጠኛ›› ማለት አማራ ብቻ ነው ማለት እምነት እንጂ እውነት አንዳልሆነና ‹‹ነፍጠኛ›› በሚል የሚበጠብጠንን ጥያቄ ለመመለስ ናችሁ የተባልነውን ሳይሆን ውስጣችን ገብተን ሆነን ያለነውን እንድናስተውል ይጎተጉተናል፡፡
ዋታካዳ እንደሚጠሩት ‹‹ጋንታይናው›› ‹ጋትዬ› አሰፋ ጫቦ ዛሬ አብዛኛው እየፈራ እየሸሸ ምክንያቱን በሚደረደርበት ወቅት እሱ ምን አቅብጦኝ ከደርግ ጋር ገጠምኩ; ብሎ አያውቅም አምኖ እንጂ ምናምን ፍለጋ ወይም ሰው ገፍቶት እንዳልገባ በግልጽ አስቀምጦልናል እንዲያውም ‹በመሸ በጠባ ቁጥር በጥሼ የምቀጥለው ማተብ› የለኝም ይል ነበር በንባብ የዳበረ የበሰለ መሆኑን ከማሳየቱም ሌላ ስለ አሜሪካ መምጣትና መኖር ያካፈለው ምክር በቀላሉ የሚታይ አይደልም ስለስደቱ ዓለም ችግርና ውጥንቅጥ ሲጽፍም ስደተኛው በሃብት ድህነትና በአእምሮ ድህነት መሃከል ያለው ልዩነት የጠፋበት መምሰሉን ፍንትው አድርጎ አቅርቧል በአጠቃላይ ጆሮ ጠገብነት ማወቅን አለመተካቱን ያሳውቀናል
ጀግና ፍለጋ ጦር ሜዳ መሪዋች አምባ የፖለቲካ ሰዋች አምባ እንሄዳለን፡፡

ሲገኝ አገር ያውቀዋል ፀሃይ ይሞቀዋል ያልታወቁ በየቤቱ የታጨቁ ተራሰው የሆኑ ያልተሰጣቸውን በመፈጸም የጀግኑ አሉ ይላል ጋሞ ይላል ፤ ጋሞ ግብር ገበረ እንጂ ሥርዓቱን አልገበረም በማለት ጥፋቱን ስህተቱን በማመን መቀበልና ባደባባይ ይቅርታ መጠየቅ የጋሞነት ገላጭ አብሮ የተወለደ የውሰጥ ባህርይ መሆኑን በመተንተን ለየት ስላለው የአገርና የህዝብ አስተዳደር ሥርዓት ሲያጫውተን አንዳንዶቻችን በአገራችን ውስጥ ይህ መኖሩን ባለማወቃችን እንቆጫለን ወደዛሬያችን ለማምጣት በምኞት እንጋልባለን
ሌላው የጋሽ አሰፋ ትልቅነቱ እንደአንዳንዶቹ ፀሃፊዋች በራሱ አራት ነጥብ ዘግቶ እመኑልኝ ሳይለን ያየሁትና የኖርኩት እንጂ ያጠናሁት አይደልም ይላል በትዝታዋቹ ውስጥ እየሾለከ የሁላችንንም ትዝታ የቆሰቆሰውን ያህል ዛሬ በአገራችን ስለተንሰራፋው ሥርዓትም በማዘን እየገለጸ ወደተሻለ እንድንጓዝ ይማፀነናል፡፡

በእስራት ብዛት የህዝብ ነጻነት ታፍኖ የቀረበት ዘመንም አገርም አለመኖሩን በማስረገጥ የጋራ ቤታችን የሚፈለገውን መጠነኛ ጥገና በማካሄድ ፈንታ መናድ የመረጡትን አውግዞአቸዋል፡፡አገራቸውን ባለማወቅ ወይም ለማወቅ ባለመፈለግ ነቀዝ የበላው ቤት እንድትሆን ስለማድረጋቸው በመውቀስ ወደምትፈለገዋ ከስህተቷ ልምድ የቀሰመች አዲሲቷ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጽያን እንድንገነባ ይጣራል፡፡

አብርሃም ሊንከን እንዳለውና ጋሽ አሰፋም በመጽሃፉ ላይ እንደጠቀሰው ‹‹ማንንም ያለቂም እንድንመለከት፣ሁሉንም በልግስና እንድናቅፍ፣በሃቅ ላይ እንድንጸና፣አምላክም ይህንን ሐቅ እንድናይ እንዲረዳን እንማጸን፡፡

ጋሽ አሰፋ ጫቦ ያመነበትን እንደተናገረና እንደሰራ ሃገርና ወገኑን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ እንደደከመ አለፈ፡፡ ይህን ታላቅ ሰው በህይወቱ እያለ በጣይቱ የትምህርትና የባህል ማህከል ጋብዘን በማስተናገዳችን ክብር ተሰምቶናል ፡፡ ብዕረⶉቻችን ጀግኖቻችን ጠበብቶቻችን ሳያልፉ ማክበር ግዴታችን መሆኑን እናምናለን፡፡

~ ጣይቱ የባህል ና የትምህርት ማህከል

ዶ/ር መረራ ጉዲና ያቀረቡት የዋስትና መብት ጥያቄ ውድቅ ተደረገባቸው

(አዲስ ሚዲያ) ባለፈው የካቲት 24 ቀን 2009 ዓ. ም. በነበረው ቀጠሮ ዶ/ር መረራ ጉዲና በጠበቃቸው አማካኝነት የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጥያቄ አቅርበው ነበር። በዚህም ምክንያት የካቲት 30 ቀን 2009 ዓ. ም. አቃቤ ህግ ባቀረበው የዋስትና ጥያቄ ላይ ያለውን ተቃውሞ አቅርቦ፤ ለመጋቢት 1 ቀን 2009 ዓ. ም. ተይዞ የነበረው ቀጠሮ በዋስትናው ጉዳይ ላይ መርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር።

Dr.Merera Gudina

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዳኞች በሁለቱም ወገን የቀረበውን ክርክር መመርመራቸውን ገልፀዋል፥ የዋስትና መብት በህገ መንግስቱ የተደነገገ ቢሆንም ፍፁም መብት ሳይሆን በህግ አግባብ ሊገደብ የሚችል እንደሆነ ጠቅሰው ዶ/ር መረራ ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ከዚህ አግባብ መታየት ያለበት ጉዳይ እንደሆነ ተናግረዋል።

ዳኞች በማስከተልም የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ስነ-ስርዐት አንቀፅ 63 ንዑስ አንቀፅ 1 ላይ “ማንኛውም የተያዘ ሰው የተከሰሰበት ወንጀል የሞት ቅጣትን ወይም አስራ አምስት አመት ወይም በላይ የሆነ ፅኑ እስራት የማያስቀጣ ከሆነ እና ወንጀል የተፈፀመበት ሰው በደረሰበት ጉዳት የማይሞት የሆነ እንደ ሆነ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ወረቀት አስፈርሞ መልቀቅ ይችላል፡፡” እንደሚል ጠቅሰው፤ ዶ/ር መረራ ላይ የቀረበባቸው የመጀመሪያ ክስ (ወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ 32፣ 38 እና 238) የሚያስቀጣው የእድሜ ልክ እስራት ወይም የሞት ቅጣት በመሆኑ የዋስትና መብት እንደማይፈቀድላቸው ገልፀው ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሆነው ክሳቸውን እንዲከታተሉ አዘዋል።

ዶ/ር መረራም የዋስትና መብት እንዳልተፈቀደላቸው ከሰሙ በኋላ

“1ኛ.ከእነ ጄኔራል መንግስቱ ንዋይና ጄኔራል ታደሰ ብሩ ዘመን ጀምሮ ከአንድ ትውልድ በላይ ገዳዮችን፣ ሟቾች፣ አሳሪዎችና ታሳሪዎች በበዙበት የሃገራችን የፓለቲካ አላማ ውስጥ በመቆየት አንድ ከሆዱ በላይ ለሃገሩ የሚያስብ ምሁር ማድረግ እንዳለበት ሁሉ ከአርባ አምስት ዓመታት በላይ ለሃገሬ የተሻለ ለውጥ እንዲመጣ መታገሌ እየታወቀ ወደ ጎን መገፋቱ ፤
2ኛ. ለሁላችንም የምትሆንና በእኩልነት የምታስተናግደን፣ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትፈጠር ነፃ የፍትህ ስርአት በሃገራችን እንዲሰፍን ላለፉት 25 አመታት በመታገሌ፤ መከሰሴ አንሶ የሃገሪቱ ፓርላማ አባል ጭምር የነበርኩ ሰው ለተራ ወንጀለኛ የሚፈቅድ የዋስ መብት በመከልከሌ የተሰማኝ ጥልቅ ሃዘን ለራሴ ብቻ ሳይሆን እኛም ሆነ ልጆቻችን በሰላም ይኖሩበታል ለምንለው መከረኛ ሃገራችን አላልፍለት ብሎ ሲታመስ ለሚኖረው መከረኛ ህዝባችን ጭምር መሆኑን እንዲታወቅልኝ ነው።” ሲሉ ተናግረዋል።

በመጨረሻም በክሱ ላይ የሚቀርብ መቃወሚያ ለመቀበል ለሚያዚያ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል። የተቀሩት ተከሳሾችን በተመለከተ በጋዜጣ እንዲወጣ የታዘዘው የጥሪ ማስታወቂያን ለማየት ለመጋቢት 29 ቀን 2009 ዓ. ም. የተያዘው ቀጠሮ እንደተጠበቀ መሆኑን በመግለፅ በዕለቱም ዶ/ር መረራ መቅረብ እንዳለባቸው ፍርድ ቤቱ ሲናገር ተደምጧል።