የ‹‹ደሃው›› አቶ መለስ 3 ቢሊዮን ዶላር የት ነው?
ቴዎድሮስ ባልቻ
አቶ መለስ ዜናዊ የእረፍታቸው ዜና ከተነገረ በኋላ በህይወት ሳሉ የሌላቸውን ባህርይ ሳይቀር በመግለፅ ደጋፊዎቻቸው ጣዖት ማምለክ እስኪመስል ድረስ እንዲመለኩ ይፈልጋሉ፡፡ እውነታው ግን አቶ መለስ የኢህአዴግ ደጋፊዎች የሚያወሩላቸውን ያህል ግለሰብ ስላለመሆናቸው የማይረሱ በርካታ ስራዎቻቸው ይናገራሉ፡፡ ይህ ማለት ግን አንዳችም ጥሩ ስራ የላቸውም ማለት ሳይሆን በንፅፅር ሲቀርብ ግን ጥሩ መሪ ነበሩ ማለት በገለልተኛ አካላት ሰፊ ጥናት መደረግ ያስፈልገዋል፡፡
አመራሮቹማ ከቤተ መንግስት እስከ ገጠር ቀበሌ የእሳቸውን ሞት ተከትሎ ምስላቸውን የያዙ ፖስተሮች መለጠፋቸው ሰውየውን ‹‹ቅዱስ›› ለማስመሰል ከመሞከር ባለፈ ለፖለቲካ ትርፍ እየተጠቀሙባቸው መሆኑን ያሳብቃል፡፡ ይህንን ለማርከስም ሆነ ህዝቡ ስለ እሳቸው ትክክለኛ ማንነት እንዲያውቅ አማራጭ የሀገር ውስጥ ነፃ ሚዲያ ያለመኖር በመጋረጃ ውስጥ ያሉት መለስ ተዘንግተዋል፡፡ ለዚህም በሀገሪቱ ስለሳቸው ትክክለኛ ማንነት የተወሰኑ ተግባራቸው የአደባባይ ምስጢር ቢሆንም እሳቸው ከሚያደንቋቸው የውጭ ሚዲያ መዳሰሱ የተሻለ ሳይሆን አይቀርም፡፡
በቅርቡ የዓለም መሪዎችንና ባለሃብቶችን ሃብትና የግል ታሪክ በማስነበብ የሚታወቀው ድህረ ገፅ ስለእሳቸው በአጭሩ ያስቀመጠውን እንመልከት፡፡ የመረጃው መረብ ሰውዬውን ከልደት ዘመን እስከሞታቸው ከመግለፁ በተጨማሪ አንድ አስደንጋጭ (ለኢህኢዴግዎች) መረጃም አክሎበታል፡፡ ይህም ያላቸውን የሃብት መጠን ከዓለም ጠቅላይ ሚኒስትሮች መካከከል ከጣሊያኑ ጠቅላይ ሚኒስትርና የታወቁ ባለሃብት ከሆኑት ሲልቪዮ በርሎስኮኒ በመቀጠል በ3 ቢሊዮን ደላር (56 ቢሊዮን ብር ገደማ) 2ኛ ደረጃን እንደያዙ www. therichest.org በግልፅ ተቀምጧል፡፡ ለዚህም http://www.therichest.org/celebnetworth/politician/minister/meles-zenawi-net-worth/ መጎብኘት ይቻላል፡፡
በተለይ ነገሩን አስደንጋጭና አሳፋሪ የሚያደርገው በህይወት ያሉት ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን በባህርዳሩ የኢህአዴግ ጉባዔ ሳይጠየቁ የአቶ መለስን ድህነት ሲናገሩ ነበርና፡፡ ያኔ ባለቤታቸው ከመንግስት መደበኛ 6 ሺህ ብር ደመወዛቸው ላይ ተቆራርጦ 4 ሺህ ብር ያህል እንደሚደርሳቸውና በዚህም ይተዳደሩ እንደነበር መግለጣቸው አይዘነጋም፡፡ በርግጥ ያኔ ባለቤታቸው የተናገሩትን ህዝቡ ተቀብሏቸዋል ለማለት ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም 21 ዓመታትን ሙሉ ያለመላከ ሞት ከቤተመንግስት አልወጣም ብለው የመሸጉትን የህዝብና የሀገርና የወገን ፍቅር ኖሯቸው እንዳልነበረ እንቅስቃሴያቸው ያሳብቅ ነበርና፡፡
‹‹ደሃው ›› አቶ መለስ
ዛሬ እንደጣዖት ፎቶአቸውን በየቦታው ተለጥፎ የምናገኛቸው አቶ መለስ ዝናዊ ምናልባት በመሪ አስተሳሰብ ካልሆነ በቀር በገንዘብ በኩል ደሃ ነበሩ ለማለት ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያን ያለባህርበር ከማስቀረት አልፈው በታሪክ የኢትዮጵያ እንደሆነ የሚታወቀውን አሰብ ወደብንና አካባቢውን ትውልዱ ያንን እንዳያስብ በማድረግ ሽንጣቸውን ገትረው ሲከራከሩ ተስተውለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ስንቶች የሞቱለትን የሀገሪቱን ሰንደቅዓላማ ‹‹ጨርቅ ነው›› ብለው አራክሰዋል፡፡ የአክሱም ሐውልት ለወላይታ ምኑ ነው ሲሉም ከመናገር ያለፈ የአስተሳሰብ ድህነት የለም፡፡
እሳቸውም በአንድ ወቅት በቴሌቪዥን መስኮት ቀርበው እንደድሮ (ጫካ ሳሉ) እንደማይርባቸውና የቆሸሸ እንደማይለብሱ ከማስታወስ ውጭ በገንዘብ በኩል ያኔ ደሃ እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡ እውነታው ግን ያ ስለመሆኑ ህዝቡ መርምሮ እንዲያውቅ ዕድል አልሰጡትም፡፡ ዛሬ ግን ተከታዮቻቸው ከእራሳቸው አልፈው መላው ህዝብ ንፁህና ቅዱስ አድርጐ እንዲመለከታቸው በየመድረኩ የሚነገረው አሰልቺ ወሬ ገመናቸውን ሊደብቅ እንደማይችል የተረዱት አይመስልም፡፡
በተለይ በገንዘብ ደረጃ ምንም ያልነበራቸውና ይሄንንም ራሳቸው የተናገሩ ቢሆንም ስለ እሳቸው ዝርዝር የህይወት ታሪክ በግልፅ በማስቀመጥ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ መሆናቸውን ግን በህይወታቸውም ሆነ በሞታቸው አላስተባበሉም፡፡ ስለዚህ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ በባዶ እጃቸው ጫካ ገብተው የወጡት አቶ መለስ ነግደው ሳያተርፉ ቢሊየነር ባለጠጋ የሆኑት ከህዝብ ሃብት ዘርፈው ካልሆነ ከየትም ሊያመጡ እንደማይችሉ እሙን ነው፡፡ ስለሆነም ሰውዬው ይወራ እንደነበረው ዓይነት እንዳልሆኑ ውሎ ሲያድር እየጠራ ነው፡፡
የግል ማኀደራቸው በአጭሩ
አቶ መለስ (ለገሰ) ዜናዊ በወርሃ ግንቦት 1947 ዓ.ም. በአድዋ ተወለዱ፡፡ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስም በአድዋ ንግስት ሳባ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲከታተሉ የሁለተኛ ደረጃን አዲስ አበባ በሚገኘው ጀነራል ዊንጌት ተከታትለው በመጨረስ የከፍተኛ ትምህርታቸውን በቀድሞ ቀዳማዊ ኃ/ስላሴ በአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ገብተዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲው ከአንድ ዓመት ቆይታ በኋላ በሁለተኛው ዓመት አቋርጠው ወደጫካ ከመግባታቸው ውጭ በኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የከፍተኛ ትምህርት ማጠናቀቃቸውን የሚገልፅ የምስክር ወረቀት የላቸውም፡፡
ነገር ግን የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በምን ዘርፍ፣ ከየትና መቼ እንዳገኙ የሚያሳይ ማስረጃ እስካሁን ባይገለፅም ከእንግሊዙ ኦፕን ዩኒቨርስቲ በህዝብ አስተዳደር ማስተርስ ዲግሪ ማግኘታቸው ተገልጧል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኔዘርላንድስ ሮተርዳም ከሚገኘው ኤራስመስ ዩኒቨርስቲ በኢኮኖሚክስ የማስተርስ ዲግሪ ባለቤት ከመሆን ውጭ በትምህርት ሌላ ደረጃ እንደሌላቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
አቶ መለስ ከወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር ጋብቻ በመመስረት ሰናይ፣ ሰመሃል እና ማርዳ የሚባሉ የሶስት ልጆች አባት እንደሆኑም በመካነ ድሩ የመረጃ መረብ ላይ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ በመጨረሻም ለ21 ዓመታት በስልጣን ላይ ከቆዩ በኋላ በተወለዱ 57 ዓመታቸው ነሐሴ 14 ቀን 2ዐዐ4 ዓ.ም (እንደ መንግስት ገለፃ) መሞታቸውን፤ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ እንደነበሩ ደግሞ http://www.therichest.org›› የተሰኘው ድህረ- ገጽ በግልፅ አስፍሯል፡፡
ሌላው ደቀመዝሙሩ ከመምህሩ እንደሚማር ሁሉ የታችኞቹ ሙሰኞች መሰረት የላይኞቹ ባለስልጣናት ልምድና ተሞክሮ መሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ‹‹ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን ውጭ ታሳድራለች›› እንዲሉ የታችኞቹ ሙሰኞች (ከቀበሌ እስከየ መስሪያ ቤቶች ባለስልጣን) ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስን እና መሰሎቻቸውን ፈለግ ተከትለው ባይተማመኑ እነ አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በቤታቸው የዶላርና የብር ክምችት ባልተገኘ ነበር፡፡
ስለዚህ በኢትዮጵያ ያለውን የሙስና ተግባር በእጅጉ ለመቀነስ ከተፈለገ ወኔውና ድፍረቱ ካላቸው አቶ ኃ/ማርያም ደሳለኝና የፌደራሉ የስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ምርመራ በ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ እንደሆኑ ከተነገረላቸው ከቀድሞው የቤተመንግስት የስልጣን ባህታዊ ከሆኑት ሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ እና ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን እስከ ሚኒስትሮችና የጦር ጀነራሎች መዝለቁ የግድ ይላል፡፡
ከላይ የተጠቀሰው አቶ መለስ አላቸው ከተባለው 3 ቢሊዮን ዶላር ውጭ የሃብት ምንጫቸው ያልታወቁ ጊዜ አመጣሽ ከበርቴዎችን መዳሰሱ ያላቸውን ቁርጠኝነት ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡ በዚህም አለ የተባለው ሃበት እውነትነት መርምሮ ለህዝብ የማሳወቅም ግዴታ አለበት፡፡ ለዚህም ይረዳ ዘንድ በሀገሪቱ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ እና የፕሬስ ነፃነት በወረቀት በህገመንግስቱ ከማስፈር ውጭ በተግባር የሚረጋገጥ ከሆነ በርካታ የሙስና ተግባራትንና ብልሹ አሰራሮችን በማጋለጥ የኮሚሽኑንና የሌሎች የፍትህ ተቋማትን ስራ ያቀላል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ከመካላከያ ሚኒስቴር፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት (ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች)፣ የከተማ መስተዳድሮች ውስጥን ጨምሮ በተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ያሉ የብልሹ አሰራሮች ምን ያህል ለሙስና እንደተጋለጡም የፌዴራሉ ኦዲተር መስሪያ ቤት የመረጃ ዘገባዎችን /ሪፖርቶቹን / እንደግብዓት መጠቀም አስፈላጊ ቢሆንም እስካሁን በተግባር የታየ እርምጃ ግን የለም አለበለዚያ እንደ ዳዊት ‹‹ሙስና›› እያሉ መደጋገሙና ትናንሾቹ ላይ ብቻ ጃስ ማለት የህዝብን የትኩረት አቅጣጫ ከማስቀየር ባለፈ ለሀገርና ለህዝብ ሃብት ተቆርቋሪነትን አያሳይም፡፡
እሳቸውስ ሞቱ 3 ቢሊዮን ዶላሩስ?
በተለይ ወደ ፖለቲካው የሀገር አስተዳደርነት ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት የሳይንሱን ትምህርት በርቀት ሳይሆን በመደበኛ ተከታትለው የህግ ምሁሩና ድምፃዊ የነበሩት የኤሲ ሚላኑ እግርኳስ ክለብ ባለቤት ከሆኑት ከ76 ዓመቱ የጣሊያኑ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲልቪዮ በርሎስኮኒ የ6 ቢሊዮን ዶላር ባለቤት ቀጥለው ከጫካ በትጥቅ ትግል ወደ ስልጣን የወጡት አቶ መለስ በ3 ቢሊዮን ዶላር ሁለተኛነትን ይዘዋል፡፡ በመቀጠልም የሊባኖሱ የሐርቫርድና የቤሩት ዪኒቨርስቲ ምሩቅና ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት የተለያዩ ኩባንያዎች ባለቤት የሆኑት የ57 ዓመቱ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ነጂብ አዝሚ ሚካቲ በ 3 ቢሊዮን ዶላር 3ኛነትን ይዘው ይከተላሉ፡፡
አቶ መለስ ግን ከጫካ ወደ ፖለቲካ ስልጣን ከመውጣት ውጭ የተጠቀሰው ሃብታቸው ከየት መጣ? የሚል ጥያቄን ያጭራል፡፡ ምክንያቱም ህዝብ ከሚያውቀው እውነታ ውጭ እሳቸውም ምንም እንደሌላቸው ከመሞታቸው በፊት ተናግረዋልና፡፡ በጣም የሚገርመው የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ዊሊያም ዶናልድ ካሜሩን እንኳ ያላቸው ሃብት ሲታይ 6 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብቻ እንደሆነ እና የዚህም ሃብታቸው ምንጭ ፖለቲካ እንደሆነ ድህረ-ገፁ ሲጠቁም የአቶ መለስ ዜናዊ 3 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ምንጭም ፖለቲካ እንደሆነ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ በዚህም ሟቹ አቶ መለስ ይህን ያህል ሃብት በፖለቲካ ስራ ባለቤት ከሆኑ የሌሎቹ ባለስልጣናት ቢጣራ ስንት ይሆን የሚል ጥያቄን ከማስነሳቱ በተጨማሪ ሀገሪቷ ምን ቀራት ያሰኛል፡፡
በርግጥ የአቶ መለስንና ባለቤታቸውን ከፍተኛ ባለጠግነትን (ቢሊየነርነትን) በተመለከተ ምስጢራዊ መረጃዎችን በመልቀቅ የሚታወቀው ‹‹wikleaks›› የተሰኘው ድህረ- ገፅ ‹‹Ethiopian Super rich persons›› ሲል የተለያዩ የቅርብ ወዳጆቻቸውን የቃለመጠይቅ ምስክርነት ማስረጃ ሳይቀር አስደግፎ ማስነበቡ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ‹‹therichest›› ድህረ – ገፅ ያላቸውን የገንዘብ መጠን 3 ቢሊዮን ዶላር ብሎ ባይገልፅም ከፍተኛ የሀገሪቱ ባለጠጋ መሆናቸውን አልሸሸገም ነበር፡፡
በአሁኑ ሰዓት አቶ መለስ ሞተዋል፤ አላቸው የባለው 3 ቢሊዮን ዶላርስ የት ገባ? ምን እየሰራስ ነው? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ቢሆንም እዚህ ላይ ቀን ከሌት ስለመለስ ሙገሳና አድናቆት አውርተው የማይጠግቡት የአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያ ደሳለኝ ከባድ የቤት ስራና ፈተና ነው፡፡ ከእሳቸው በተጨማሪ የፌደራሉ የሥነ – ምግባርና ፀረ – ሙስና ኮሚሽን ቁርጠኝነትንና ተዓማኒነት ለማረጋገጥ የአቶ መለስ አላቸው የተባለው 3 ቢሊዮን ዶላር የት እንዳለና ምን እየሰራ እንደሆነ ከነምንጩ ከመረጃ መረቦቹም ሆነ በራሳቸው ዘዴ አጣርተው የመግለፅ ትልቅ ፈተና ይጠበቅባቸዋል፡፡
የገንዘቡ መገኘት ከተረጋገጠ በኋላም ገንዘቡ ከድሃው የኢትዮጵያ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቆ የተዘረፈ ስለመሆኑ ማንም ሊጠራጠር አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከራስ በላይ ምስክር የለምና ሁለቱም የህወሐት ኢህአዴግ እና የሀገሪቱ የስልጣን ቁንጮዎች በገንዘብ አቅም ድሃ ስለመሆናቸው ተናግረዋልና፡፡ ስለዚህ እነኛ ታማኝ የመረጃ ምንጮች የገፁት በተለይ ‹‹therichest›› ያሰፈረው 57 ቢሊዮን ብር (3 ቢሊዮን ዳላር ) ወደ ተዘረፈው ህዝብ ተመልሶ ጥቅም ላይ ሊውል ይገባል፡፡
‹‹ ዓሳ የሚገማው ከጭንቅላቱ ነው››
አበው ሲተርቱ ‹‹ዓሳ የሚገማው ከጭንቅላቱ ነው ›› ይላሉ፡፡ ዓሳ ከምግቦች ሁሉ የተሸለና ሁሉንም ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን አሟልቶ የያዘ ተወዳጅ ምግብ ቢሆንም ለምግብነት ከመሰናዳቱ በፊት ከመኖሪያው ውሃ ውስጥ እንደወጣ የማይወደድ ሽታ አለው፡፡ የዚህ ‹‹መጥፎ ሽታ›› መነሻው ደግሞ ጭንቅላቱ እንጂ ሌላው አካሉ እንዳልሆነ ይነገራል፡፡ በዚህም ዓሳ ከውሃ ውስጥ ከወጣ በኋላ ያለው መጥፎ ጠረን ጭንቅላቱ ስለሆነ ተቆርጦ መጣል እንዳለበትና ያኔም ሌላው አካሉ ከመጥፎ ሽታ እንደሚፀዳ አመላካች ንግግር ነው፡፡
በኢትዮጵያ ስላለው ቅጥ ያጣ የሙስና ተግባርም ሆነ ብልሹ አሰራር መነሻው ገዥው ኢህአዴግና ቁንጮዎቹ እንደሆኑ የሰሞኑ መረጃ በራሱ በቂ ማሳያ ነው፡፡ ለዚህም ከሚኒስትር አቶ መላኩ ፈንታና ረዳታቸው የሙስና ተግባር መጠርጠር በተጨማሪ በወ/ሮ አዜብ መስፍን ‹‹ድሃ›› ስለመሆናቸው የተመሰከረላቸው ግን በዓለም 2ኛው ባለጠጋ ጠቅላይ ሚኒስትር(በ3 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር) እንደሆኑ የተነገረላቸው ሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ አለ የተባለው ሃብት ምንነት ካልተጣራና ካልተመለሰ የመንደር ሌቦችን ብቻ ማሳደድ ሙስናን ሊገታ አይችልም፡፡
ምንጭ፡- ኢቦኒ መፅሔት(ሰኔ በ2005ዓ.ም.)
የመከነው የአፍሪካ ራዕይ
ልክ የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ. በ1963 ዓ.ም የአፍሪካ ጥቁሮች ከባርነት ቅኝ ግዛት ለመውጣት የተወሰኑ መሪዎቿ ሽር ጉድ እያሉ ነበር፡፡ ሽርጉዱም የአፍሪካ ምድር በአውሮፓውያን ጨካኝ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ የወደቁትን ሀገሮች ነፃ ለማውጣት በጥቂት ጥቁር መሪዎች ምክክር ሊካሄድ ነው፡፡
ይሄን የሰሙት ገዥዎች በተለይም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ፖርቹጋልና፣ ጣሊያን ይበልጥ በጥቁሮች ላይ በደል መፈፀምን ተያያዙት፡፡ ይህን የተመለከቱት የአፍሪካ የአብራክ ልጆች በቁጭት በመንገብገብ ወገኖቻቸውን ከጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ መዘየድ ጀመሩ፡፡ ያኔ ግን የተለያዩ ሀገሮች በተለይም ጋና፣ ናይጄሪያና ደቡብ አፍሪካውያነ በየሀገሮቻቸው የተናጥል ትግል ያደርጉ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ትግሉ ፈቀቅ አላለም፡፡ ምክንያቱም ብቻቸውን ነበሩና፡፡
በወቅቱ ፈረንሳይ የሰሜን አፍሪካ ሀገሮችን በተለይም ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮን እንዲሁም በምዕራብ እንደ ማሊና ኮትዲቫርን በምስራቅ ጅቡቲን ይዛ ነበር፡፡ እንግሊዝ በበኩሏ በምስራቅ አፍሪካ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ሯንዳ፣ ክፊል ሱማሊያ በምዕራብ ናይጄሪያ፣ ጋና በደቡብ የቀድሞ ሮዴዥያ (ዙምባቤና ዛምቢያ)፣ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ይዛ ነበር፡፡ ፖርቹጋል ደግሞ በደቡብ ምዕራብ አንጐላን ስትቆጣጠር ጣሊያንም እንዳቅሟ ሊቢያንና ምስራቅ ሶማሊያን ተቆጣጥራ ነበር፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ለናሙና እንጂ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት የወደቁ ሌሎችም በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ነበሩ፡፡
ነፃ ሀገር
በተፈጥሮ የበለፀገችዋ እማማ አፍሪካ ምንም እንኳ በልጆቿ ስቃይ ማቅ ብትለብስም በወቅቱ እንደሀገር ሉዓላዊነት ያላቸው ሁለት ሀገሮች ነበሯት፡፡ እነኚህም በስተምስራቅ ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እና በምዕራብ የአልማዝ ምድር የሆነችው ላይቤሪያ ናቸው፡፡ በርግጥ ላይቤሪያ እንደሀገር ብትታይም ከነ ሰንደቅዓላማዋ ከአሜሪካ ቁጥጥር ስር ውጭ ነበረች ማለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እንደ ሀገር ከመመስረቷ በፊት የማንም ያልነበረች በኋላ ግን አሜሪካ በባርነት ከአፍሪካ ተወስደው በሀገሯ እየተባዙ የመጡትን የጥቁሮች ቁጥር ስጋት ላይ እንዳይጥላት በማሰብ ወደዛሬዋ ላይቤሪያ አብዛኞቹን ጭና በማራገፍ የዛሬዎቹ ላይበሪያውያን መኖሪያ አድርጋለች፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1888 እና በ1928 ዓ.ም በጣሊያን የቅኝ ግዛት ሙከራ ቢደረግም በጥቁር አናብስት ትግል ሳይሳካ በመቅረቱ ከአፍሪካ ብቸኛዋ ነፃ ሀገር ሆና ቆይታለች፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በዳግማዊ አጼ ምኒሊክ መሪነት የጥቁር አናብስት በጣሊያን ላይ በተቀዳጁት ድል ለሌሎችም ፋና ወጊ በመሆን የነፃነት ትግል እንዲቀጣጠል ፈር ቀዷል፡፡
የነፃነት ናፍቆት ህብር
አፍሪካውያን የነፃነት ናፍቆት ቢያንገበግባቸውም ትግሉ በተናጥል ስለሆነ በተፈለገው ፍጥነት ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለዚህም የናይጄሪያውን ኢቦ ኢቢቦ፣ የጋናው አሻንቲ እና የደቡብ አፍሪካውን የነ ባሱቶ ዙሉ ትግልን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ትግሉ እንዲሰምር በገዥዎች ሀገር ይኖሩ የነበሩ የጥቁሮች የአብራክ ክፋይ እነ ኩዋሜ ኑኩሩማ፣ ጆሞ ኬንያታ የመሳሰሉት በጋራ መታገሉ የተሻለ እንደሆነ በማሰብ በነፃይቱ የጥቁር አናብስት ምድር ንጉስ ከሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ጋር መከሩ፡፡
ምክክራቸውንም በማጧጧፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገሮች ገፉበት፡፡ በዚህም ጥቁሮች ሲነቃቁ ቅኝ ገዥ አውሮፓውያን ግን ድንጋጤ ወሯቸው ነበር፡፡ በተቃራኒው ጥቁሮች ደግሞ ከፍተኛ የአሸናፊነት ወኔን ተላብሰው ለልጆቻቸው ከጭቆና ነፃ የሆነ ምድር ለማውረሰና ለራሳቸውም ነፃነት ተግተው ተፋለሙ፡፡
ይሄን የተረዱት የትግሉ ውጤት ናፋቂዎች እነ አፄ ኃ/ስላሴና ኩዋሜ ኑኩርማን ጨምሮ ሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ይላቀቁ ዘንድ አፍሪካውያን በአንድ ስም ተጠርተው የሚጠለሉበትን ተቋም መመስረት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ የዚህም ተቋም ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከቅኝ ግዛት ነፃ ማውጣት ነበር፡፡
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት
አፍሪካውያንን የነፃነት ድል ለማቀዳጀት ሲባል የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ ግንቦት 1963 ዓ.ም በነፃይቱ ታሪካዊት ሀገር አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረትም ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ኢትዮጵያው ንጉስ አጼ ኃ/ስላሴ ነበሩ፡፡
በወቅቱ ተቋሙ ምንም እንኳ ቢመሰረትም ወዲያው የራሱን ቢሮና ለምክክር የሚሆን አዳራሽ መገንባት የማይቻል ቢሆንም ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃ/ስላሴ መንግስታቸውና መላው የሀገራቸው ህዝብ አፍሪካውያን ወገኖቹ ነፃ እንዲወጡ እንደሚሻ ተናገሩ፡፡ በዚህም ሳያበቁ በመንግስታቸውና በህዝባቸው ስም ዛሬ የህብረቱ አሮጌው ህንፃ ለፖሊስ ጽህፈት ቤት ተብሎ የተሰራውን ከነሙሉ ግቢው በነፃ ለድርጅቱ አስረከቡ፡፡ ድርጅቱም በነፃይቱ ምድር ያለማንም ከልካይ በነፃነት በመምከር የአፍሪካውያንን መፃኢ ተስፋ ብሩህ ለማድረግ ተግቶ ይሰራ ጀመር፡፡
በድርጅቱ ያላሰለሰ ጥረትም ጋና ቀድማ ከእንግሊዞች ቅኝ ግዛት ነፃ ስትወጣ ሌሎችም ተከታትለው ነፃ ወጥተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ግን ከአሰቃቂው የአፓርታይድ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ የወጣችው ዘግይታ ነበር፡፡
ያኔ በአዲስ አበባ የተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከባርነት ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት በተጨማሪ የአህጉሪቱ ሃብት በአውሮፓውያን ተወስደው ዜጐቿ እንዳይራቆቱ ነበር፡፡ የአፍሪካ አንጡራ ሃብት በቅኝ ገዥዎች ከልጆቿ ጉሮሮ ተነጥቆ እንዳይወሰድና ልጆቿ በእናት ምድራቸው በነፃነት እንዲቦርቁ ታስቦ በቀድሞው አባቶች መልካም ፈቃድ የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት /አ.አ.ድ/ ዛሬ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ይህም የሆነበት ምከንያት ድርጅቱ የተቋቋመለትን አፍሪካውያንን ከባርነትና ጭቆና ነፃ ማውጣት የሚለውን አሳክቶ ጨርሷል በሚል ነው፡፡
የጨነገፈው ፅንስ
የቀድሞ የአፍሪካ መሪዎች ያነገቡት ወገኖቻቸውን ነፃ የማውጣት መልካም ራዕይ በአሁኖቹ የአስተሳሰብ አድማስ እሳቤ ተሳክቷል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬ 12 ዓመት ግንቦት 2ዐዐ1 (እ.አ.አ) ደቡብ አፍሪካ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ወደ አፍሪካ ህብረት ተቀይሯል፡፡ እውነት ለመናገር ዛሬም ድረስ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፤ ነፃ የነበሩትም በአብራኮቻቸው ክፋይ ቅኝ ግዛት ውስጥ ገብተዋልና፡፡
በተለይ በዛሬዎቹ መሪዎች ድርጅቱ ዓላማውን አሳክቷል፤ ግቡን መቷል በሚል የአህጉሪቱን ልማት መሰረት በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ተቋቁሞ መቀመጫውንም እዚሁ አዲስ አበባ አድርጓል፡፡
ያኔ ቅኝ ገዥዎች ባላገሮቹን በግፍ ይጨቁኑ ነበር፣ ህዝቡ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ሲያቀርብ በጥይት እሩምታ በመረሸን የቀሩትን ወደ አሰቃቂ እስር ቤት ይከቱ ነበር፡፡ ይህ ግን ነፃዋን ኢትዮጵያን አይመለከትም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንጉሷም መሪዋም ባዕድ ሳይሆኑ ያው ያብራኳ ክፋይ አፄ ኃ/ስላሴና ኢትዮጵያውያን ናቸውና በመካከል የቅኝ ገዥነት እሳቤ የለም፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያውያን በንጉሱ ስርዓት ቅሬታ ሲሰማቸው በነፃነት ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ለዚህም እ.አ.አ በ197ዐ ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበረውን የነዳጅ ጭማሪ ዋጋ በመቃወም የነበረውን ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል፡፡ ከዛም በፊት ወጣቶች መሬት ላራሹ ተቃውሞን በነፃነት አሰምተዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ግን የማይቻል ነው፤ ቅኝ ገዥዎች ናቸውና፡፡
ዛሬ ግን ምናልባት አንፃራዊ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት አስተዳደር ያላቸው ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ካልሆነ በስተቀር አፍሪካውያን በራሳቸው ጥቁር ገዥዎች የጭቆና ቀንበር ስር ወድቀዋል፡፡ ለዚህም በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በኮትዲቫር፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና በአልጄሪያ ያሉትን ጨቋኝ አስተዳደሮች በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት ከቅኝ ገዥዎች በባሰ በአሽከሮቻቸው ታጣቂዎች በአደባባይ የጥይት እራት ሆነዋል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያም የተመለከትን እንደሆነ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ ህብረት ከተቀየረ በኋላ በቅኝ ያልተገዙት ኢትዮጵያውያን የመንግስት ገዥዎች በርካታ እኩይ ተግባራትን ለመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቢፈልጉም ለመጨረሻ ጊዜ በሚል ይመስላል እ.አ.አ በ2ዐዐ5 (በ1997 ዓ.ም) በምርጫ ወቅት ነበር የተደረገው፡፡ ከዚያም የምርጨውን ውጤት ተከትሎ በተፈጠረ ተቃውሞ አሁን በስልጣን ላይ ባለው ገዥው ቡድን መሪ በነበሩት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ ከ86ዐ በላይ ዜጐች የጥይት ናዳ አርፎባቸው እስከወዲያኛው አሸልበዋል፡፡
በኬንያና በሱዳንም ሆነ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገሮች በተመሳሳይ መልኩ ገዥዎችን ለመደገፍ ካልሆነ ለተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ለሞት ይዳርጋል፡፡ ይህንን ደግሞ ቅኝ ገዥዎች ያደርጉት የነበረው አስከፊ ድርጊት በጥቁር ቆዳ ካባ በለበሱ አምባገነን መሪዎች መደገፍ አፍሪካውያንም ሆኑ አፍሪካ ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የድጋፍ የድጋፍማ ቅኝ ገዥዎችም አሳምረው በመፍቀድ መፈክር እና ሌላ ወጭ በመሸፈን ይከናወን ነበር፤ ተቃውሞ ባይቻለም፡፡
ሌላው ያኔ በቅኝ ገዥዎች ወቅት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ተዝቆና ተሸጦ ወደ አውሮፓ ካዝና ይገባ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ በእራሳቸው በአፍሪካውያን መሪዎች ከአህጉሪቱ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቀው አንጡራ ሃብቷን ዝቀውና ሸጠው ወደ አውሮፓና እስያ ሀገሮች ካዝና ያስገባሉ፤ አፍሪካውያን ግን ዛሬም ይራባሉ፣ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ፣ ይጨቆናሉ፣ይሰደዳሉ፣ይገደላሉ፣ይዘረፋሉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመለትን ዜጐቿን ነፃ የማውጣት ራዕይ ግቡን ሳይመታና ሳያሳካ የነፃነት ፅንሱ በዚህ መልክ ጨንግፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእስያዎቹ ቻይና፣ ህንድና የአረብ ሀገራትን ጨምሮ አሜሪካና አውሮፓ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸውን አላወጡም፣ ዛሬም በዘመናዊው እጅ አዙር ቅኝ ጋዛት ቀፍድደው ይዘዋልና፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዓላማ ተጨናግፋል እንጂ ተሳክቷል ማለት አይቻልም፡፡
በትረ ከረባት ነዳያን
የቀድሞ ለነፃነት ቀናዒ የሆኑ የአባቶቻችንን ዓላማ ተሳክቷል በሚል ክህደት የዛሬዎቹ በትረ ከረባት ነዳያን የአፍሪካ ህብረትን አቋቁመዋል፡፡ የህብረቱም ዓላማ በአፍሪካ ልማትን ማምጣትና ማፋጠን እንዲሁም ማስተሳሰር የሚል ነው፡፡ በዚህም ስም በስልጣን ላይ ያሉት የአህጉሪቱ መሪዎች የራሳቸውን ሆድና ስልጣን ታሳቢ በማድረግ በአህጉሪቱ ህዝብ ስም ከረባት አስረው ለምነው የሚያመጡትን ገንዘብ በሌላ መንገድ በስማቸው ወደ ለጋሽ ሀገሮች ካዝና ይቋጥራሉ፡፡
ለዚህም የሊቢያ፣ የግብፅ፣ የቱኒዚያና የኢትዮጵያ መሪዎችን ጨምሮ አብዛኞቹ የዚህ ባለሟል ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መሪዎችም እጃቸው ከዜጐቻቸው የግፍ ደምና የህዝቡ አንጡራ ሃብት ዝርፍያ የፀዳ አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬም ድረስ ዜጐቻቸውን እጅግ ከቅኝ ገዥዎች በባሰ መልኩ በመጨቆን አንዳንዶቹ በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሌሎቹ ደግሞ በምርጫ ስም ህዝብን በማጭበርበር በትረስልጣናቸውን እያደላደሉ ይገኛሉ፡፡
አሁን በስልጣን ላይ ያሉት የአፍሪካ ማሪዎች የእነሱ የስልጣን ዕድሜ እስከረዘመና ዝርፊያውን እስኳጧጧፉ ድረስ የአህጉሪቱን አንጡራ ሃብት ጥቅም በማዘረፍ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ በዚህም ለዜጐቻቸው ያላቸው ቀናዒነትና ተቆርቋሪነት ከቀድሞዎቹ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መስራቾች ጋር ሲነፃፀር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ የበትረ ከረባት ነዳይ ሆነው የአህጉሪቱን ሃብት እያዘረፉ የዜጐቻቸውን ነፃ አስተሳሰብና ነፃ ሚዲያን በማፈን ከፍተኛ ጭቆና እያደረጉ ስለመሆኑ የህብረቱ ዋና መቀመጫ የሆነችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛው አፍሪካ ሀገሮችን ማየት በቂ ነው፡፡
በአጠቃላይ አሁን እ.አ.አ. በያዝነው ግንቦት 2ዐ13 የአፍሪካ ህብረት ምስረታ 5ዐኛ ዓመት ክብረ በዓል ለመሪዎቹ ብቻ ካልሆነ በቀር ለአህጉሪቱ ህዝብ ይሄ ነው የሚባል የፈየደው ነገር አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ምክንያቱም እየተሰሩ ያሉት መሰረተ ልማቶችና ሌሎች የህዝብ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ግንባታ ሰብዓዊ ልማትን ወደጐን በመተው እየተደረገ ያለው ቅኝ ገዥዎች በጊዜያቸው ሲያደርጉት ከነበረው እምብዛም የተለየ አይደለምና፡፡ በዚህም አፍሪካ ቀድሞ የነበራት ራዕይ በአሁኖቹ በትረ ከረባት ነዳይ መክኖ ቀርቷል ማለት ይቻላል፡፡ ያኔ ቅኝ ገዥዎች ሰብዓዊ መብትን በመርገጥ በቁሳዊ ልማት ህዝቡን ለመደለል ይሹ እንደነበረው ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡
እውን የሀገሪቱ ችግር እንዲህ በቀላሉ ይፈታ ይሆን?
ብስራት ወልደሚካኤል
የኢትዮጵያ ወቅታዊ ችግር ከዕለት ወደዕለት እየባሰበት በመሄዱ የችግሮቹን ውስብስብነት ከመባባሱ በስተቀር ለነዋሪው የፈየደ አንዳች የመፍትሄ ሐሳብም ሆነ ተግባር የለም፡፡ ችግሮቹ በገጠርም ሆነ በከተማ ተባብሰው በመቀጠላቸው ከብዛታቸው አንፃር በተናጥል መጥቀሱ አስቸጋሪ ነው፡፡ ቢሆንም ግን አሉ ከሚባሉት መካከል የተወሰኑትን ችግሮች እንኳ ለማየት እንሞክር፡፡
በአዲስ አበባ ያለው የመጓጓዣ እጥረት ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ በመምጣቱ እስካሁን መፍትሄም ሆነ ትኩረት ስላልተሰጠው የሀገሪቱ ሃበት ላይ የጊዜ፣ የገንዘብ፣ የጉልበትና የሞራል ኪሳራ ማድረሱ አይቀሬ ቢሆንም “እኛን ብቻ አድምጡን፣ ችግራችሁን ደብቁትና ቁጭ በሉ፣ ግዴታችሁን ተወጡ እንጂ መብታችሁን አትጠይቁ!” በሚል ግትር አቋሙ የፀናው የኢህአዴግ መንግስት ችግሩን የመፍታት አቅም እንደሌለው ያረጋገጠ ቢመስልም የስልጣን ጥሙ ግን ቀፍድዶ ይዞታል፡፡ በዚህም ምክንያት የታክሲ ሰልፉ፣ የከተማ አውቶቡስ፣ የሎንችንና የሃይገር ግፍያን ጨምሮ የመንገዶች መጨናነቅን ላየ እውን በሀገሪቱ መንግስት አለን? ያስብላል፡፡ ምክንያቱም ችግሩ ከዕለት ወደዕለት እየተባባሰ የመጣ እንጂ ቅፅበታዊ ክስተት አይደለም፡፡
ምናልባት አሁን እየተሰራ ያለው የከተማ ውስጥ ቀላል የባቡር ሃዲድ ግንባታና አገልግሎት እየተካሄደ ነው፣ ይሄ ሲጠናቀቅ ችግሩ ይፈታል የሚል መልስ ሊሰጡ የሚችሉ ሊኖሩ ቢችሉም የባቡር አገልግሎት ቢጀመርም የነዋሪው ቁጥር በየዓመቱ እየጨመረ በመምጣቱ ችግሩን ይፈታዋል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ችግሩን ሊፈታ የሚችለው ብቃት ያለው አመራር መኖርና ዴሞክራሲያዊ የመንግስት ስርዓት ሲሰፍን ብቻ ነው፡፡ አለበለዚያ ህዝብን ያላማከለና ያላሳተፈ ስራ ግልፀኝነት ስለሌለው ከሙስና እና ከብልሹ አሰራር ውጭ የሚፈይደው ነገር ስለሌለ ለመፍትሄው ከህዝብ ጋር በግልፅ መድረክ መወያየቱ ብቸኛው አማራጭ ነው፡፡
የኑሮ ውድነቱ አንዱ ዋነኛ ችግር ሲሆን ለዚህም መንግስት እንዳሻው የሚያደርገው የገበያ ጣልቃ ገብነትና የዋጋ ተመን ዕቃ እንዲጠፋና ጥራታቸው የጎደሉ ሸቀጦች ለህዝቡ ኢንዲደርሱ ከማድረጉ በተጨማሪ ወደፊት በውድድር ገበያ ዋጋቸው የሚወርዱ ዕቃዎች ባሉበት በመቀጠል ወደፊት በዛው ዋጋቸው እየጨመረ እንዲሄድ ያስገድዳል፡፡ ስለዚህ የፖሊሲ ለውጥ ማምጣትና መንግስት እጁን ከገበያ ማውጣት ካልቻለ ችግሮቹ ከአሁን በባሰ እንደሚቀጥሉ ጥርጥር የለውም፡፡
በክልል ከተሞችና በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ደግሞ ያለው የኢህአዴግ ቅጥ ያጣ አፋኝነት(በአዲስ አበባ የለም ማለቴ አይደለም) ህዝቡ የታዘዘውን ከማድረግ ውጭ መብቱን እንዳይጠይቅ በመደረጉ ችግሮች ሳይባባሱ በጊዜ እንዳይታረሙ በመደረጉ ከመቼውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ የሰቆቃ ህይወት እንዲመራ አድርጎታል፡፡ በተለይ ገበሬው ያልፍላጎቱና ያለ አቅሙ ለግብርና የሚያስፈልጉ ግብዓቶች( ማዳበሪያ፣ አረም ማጥፊያ፣ ዘር) ኢህአዴግ በተመነው ከፍተኛ ዋጋ እንዲገዙ በመደረጉ ምርቶቻቸውን ሙሉ ለሙሉ ሸጠው ለኢህአዴግ በመክፈል፤ መሬት እያላቸው እንደሌላቸው በመሆን የኢኮኖሚ ጥገኛ እንዲሆኑ ተደርጓል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ገበሬውም በንብረቱ የማዘዝ ስልጣኑ በመገፈፉ የእኔነት ስሜት ስለማይኖረው ውጤታማ ስራ ሊሰራ አልቻለም፤ አይችልምም፡፡ የዚህ ችግር ደግሞ ከባዶ የኢህአዴግ ፕሮፖጋንዳ በስተቀር በምግብ እራሷን እንዳትችል ያደረጋት ከመሆን ባለፈ ድሬ በምግብ እራሳቸውን የቻሉ ገበሬዎች ዛሬ ለልመና ወደ አዲስ አበባና ትላልቅ የክልል ከተሞች ጎዳና በመውጣት ለልመና ተዳርገዋል፡፡
በሀገሩቱ ትልቅ ተስፋ የተጣለባቸው ከፍተኛ አምራች ኃይል የሆኑት ወጣት ምሁራን ከዩንቨርስቲ ተመርቀው ወጥተው በሙያቸው እራሳቸውን፣ ቤተሰባቸውን፣ ማኀበረሰቡንና ሀገራቸውን ማገልገል ሲገባቸው አነስተኛ የትምህርት እድል ያላቸው ዜጎች ሊሰሩት የሚገባውን የድንጋይ ፈለጣ(ኮብልስቶን ስራ) ላይ እንዲሰማሩ በመደረጉ ለትምህርት ያወጡት፣ ጊዜ፣ ገንዘብ፣ ጉልበትና ሞራል በከንቱ እንዲባክን ተደርጓል፡፡ የዚህም ውጤት የሀገሪቱ ዜጎች ተስፈኛ ከመሆን ይልቅ ተስፋ ወደመቁረጥ በመዳረጋቸው ለተለያዩ ጎጂ ሱሶች ተጋልጠው በየመንገዱ ሲንቀዋለሉ ላየ “የየት ሀገር ቱሪስቶች ናቸው?” ሳያስብል አይቀርም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ህይወታቸውን ለአደጋ በማጋለጥ አስከፊ የስደት መንገዶችን ምርጫ በማድረግ የሚሞቱ ወጣት ዜጎች ቁጥር ከዕለት ወደዕለት እየጨመረ በመሄዱ “ሀገሪቱ እውን መንግስት አላትን?” ያስብላል፡፡ ለነዚህ ሁሉ ችግሮች ምክንያት ገዥው ኢህአዴግ የሚከተለው የተሳሳተ ፖሊሲና ግትር አቋም መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
በመላው ሀገሪቱ ያለው የሰብዓዊ መብት አያያዝን የተመለከትን እንደሆነ በዓለም ላይ እጅግ አምባገነንና ጨቋኝ መንግስት መኖሩን የሚያመላክቱ በርካታ ማስረጃዎች ማቅረብ ቢቻልም ይበልጥ ግን ለሁሉም ዜጋ በእኩልነት ሊያገለግሉ የሚገባቸው፣ ከየትኛውም የፖለቲካና የግለሰብ ተፅዕኖ ገለልተኛ ሊሆኑ የሚገባቸው የዴሞክራሲያዊ ተቋማት (የፍትህ አካል የሆኑ ፍርድ ቤቶች፣ ፖሊሶች፣ የደህንነት ኃይሎች፣…) በኢህአዴግ መዳፍ ወድቀው ወገንተኝነታቸው ለፍትህ፣ ለህግና ለህዝቡ ከመሆን ይልቅ ለአብዮታዊ ዴሞክራሲ ወገንተኛ በመሆናቸው የሀገሪቱን ችግር ይበልጥ ከድጡ ወደማጡ አድርጎታል፡፡ በዚህም በህግ የተሰጣቸውን መብት የተጠቀሙና መብቶቻቸው እንዲከበሩ የጠየቁ በርካቶች ወደ ወህኒ ቤት ተወርውረዋል፡፡ ከነዚህም መካከል ጋዜጠኞች(እስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት አለሙ፣ የሱፍ ጌታቸው፣…)፣ፖለቲከኞች(አንዱዓለም አራጌ፣ናትናኤል መኮንን፣በቀለ ገርባ፣ኦልባና ሌሊሳ፣…)፣ የኃይማኖት ነፃነት መብት እንዲከበር የጠየቁ (የሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፣ የዋልድባ መነኮሳት፣…) ይገኙበታል፡፡
ከላይ የተጠቀሱት ኢህአዴግ “ለስልጣኔ ያሰጉኛል” በሚል ብቻ በሀገር ስም ክስ ስለመሰረተ ሁሉም ተከሳሾች ወንጀለኛ የሚባሉ ሲሆን በአንፃሩ በኢህአዴግ ባለስልጣናትና አባላት በደል ተፈፅሞባቸው “የፍትህ ያለ” የሚሉ “ፍትህ በኪሴ ብይን” ተሰጥቷቸው በኋላ ወንጀለኛ እንባላለን በሚል በፍትህ ስርዓቱ ላይ እምነት በማጣታቸው “የማርያም ጠላት” የሚባሉ በርካቶች ናቸው፤እነኚህንም ቤት ይቁጠራቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በህገ መንግስቱ የተፈቀዱ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ፣ የፕሬስ ነፃነት፣ የመሰብሰብ፣ በሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞን የመግለፅ፣…በሙሉ ባልተፃፈና ባልታወቀ ህግ የተሻሩ ሲሆን ይበልጥ እነኚህ እንዳይተገበሩ ለገዥዎች ብቻ በሚመች ህገመንግስቱን በግልፅ የጣሱ በርካታ አንቀፆችን የያዘ የፀረ ሽብር አዋጅ በማውጣት ተጨማሪ የአፈና ገደቦች ተጠለዋል፡፡ የእነኚህ አፈናዎች ውጤት ችግሮች በጭሩና በቀላሉ እንዳይፈቱ ከማድረጋቸውም በተጨማሪ በአሁን ወቅት በሀገሪቱ እጅግ የታፈነ ቁጣ እንዲኖር አስችሎታል፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ ወደፊት በሀገሪቱ ላይ ምን ሊያስከትል እንደሚችል ግልፅ ቢሆንም ኢህአዴግ በያዘው ግትር አቋም ችግሮች እየተባባሱ ከመሄድ በስተቀር የሀገሪቱን ውስብስብ ችግር ሊፈታ አይችልም፤ምክንያቱም ኢህአዴግ አቅሙም ቁርጠኝነቱም የለውምና፡፡
ከላይ የተጠቀሱት የታፈኑ ጩኸቶች ድምር ውጤት ድንገት ከፈነዳ ሀገሪቱን ብቻ ሳይሆን ቀጠናውን(ምስራቅ አፍሪካን) ሊያናውጥ ስለሚችል ኢህአዴግና አመራሮቹ ከጭፍንና ግትር አቋም ወጥተው የህዝቡን ጥያቄ ማድመጥና ተገቢውን መልስ መስጠት፣ በጨለማ ክፍል ውስጥ የተቆለፈበትን ነፃ ፕሬስ በተግባር ላይ እንዲውል ከፍተኛ የሆነ የወረቀት ታክስን ከማስቀረት በተጨማሪ ህዝቢ መረጃ የማግኘት መብቱ ያለምንም ገደብ እንዲከበር ማድረግ፣ ለአፈና የዋሉ ህገወጥ ህጎችን ማሻሻል/መሻር፣1 ለ 5 እያሉ የሚጠቀሙባቸውን ህገወጥ የአፈና መዋቅር መበተንና ማቆም፣ በህገመንግስቱ የተቀመጡ ያወጧቸውን ህጎች በማክበር ለሌሎች አርዓያ በመሆን የፖለቲካ ቁርጠኝነት ሊያሳዩ ይገባል፡፡ አለበለዚያ በባዶ ሜዳ “በርካታ የልማት ፕሮጀክቶችን እየሰራሁ ነው…” በሚል የእንቁልልጭ ፈሊጥ የዜጎችን መብት ማዳፈን የዲያቢሎስ የህልም ሩጫ ካልሆነ ለፖለቲካ ፍጆታ ተጀምረው ከመቆም ያለፈ ተፈፃሚ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ከምንም ከማንም ቀድሞ መልማት ያለበት የዜጎች ነፃነት የተላበሰ የአስተሳሰብ አድማስ እንጂ ቁስ አይደለም፤ ቁሳዊ ልማቶች ሊሰሩ የሚችሉት በነፃና ጤናማ የዳበረ አስተሳሰብ ባለው የሰው ኃይል ነውና፡፡ ያኔ የምንመኘውና የሚዘመርለት ቁሳዊ ልማትም እውን ይሆናል፡፡
ተፎካካሪ የፖለቲካ ፐርቲዎችም ሆኑ ድርጅቶች ከእርስ በርስ መጠላለፍና ከፍርሃት ተላቀው ከቢሮ ፖለቲካ በመውጣት ሰላማዊ ትግል ምን እንደሆነ በተግባር ለማሳየት ወደህዝቡ መውረድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ አለበለዚያ በየቢሮው በሚደረግ የድርጊቶች መቃወሚያ ጋዜጣዊ መግለጫ ብቻ ለህዝብና ለሀገር ቆሜያለሁ ማለት ከቀን ቅዥት ባለፈ ጠብ የሚል ነገር ማምጣት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የፖለቲካ ትግል የተጠና ስልታዊ የተግባር ስራ እንጂ የወንበር ማድመቂያ አይደለምና፡፡ እዚህ ላይ ፖለቲከኞች አምነውበት እችላለሁ ብለው ወደፖለቲካው ትግል እስከገቡ ድረስ በሚከተሉት የትግል ስልት የሚታይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት መቻል አለባቸው፤ ካልሆነ ግን ከትግሉ እራሳቸውን ማግለልና ለሚሰራ ሰው መስጠቱ ለፖለቶከኞችም ሆነ ለሀገሪቱ እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ህዝቡም ቢሆን ወደባሰ ችግር ከመሄድ እራሱን ከፍርሃት ድባብ በማውጣት ብልሹ አሰራሮችን በግልፅ በመቃወም ከድርጊቱ ፈፃሚዎች ጋር ባለመተባበር የራሱን እርምጃ በመውሰድ ለመብቱ ሊሎች እንዲቆሙለት ከመጠየቅ ይልቅ ራሱ መታገል አለበት፡፡
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ያለውን ውስብስብ ችግር ለመፍታት እያንዳንዱ ሰው እገሌ ምን ሰራ ከማለት በተጨማሪ እኔ ምን ሰራሁ በሚል ሁሉም የድርሻውን ካልተወጣ የችግሩ ማዕበል ሁሉንም እንደሚያጠቃ እሙን ነው፡፡ አሁን ባለው የመጠባበቅና የማጉረምረም እንዲሁም የመፈራራት ሁኔታ ችግሮችን ከማባባስ ባለፈ የሀገሪቱ ችግር በቀላሉ ይፈታል ማለት የህልም እንጀራ ነው፡፡ ስለዚህ የሀገሪቱ ችግር ከድጡ ወደማጡ እየሆነ ስለሄደ ሁሉም ዜጋ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሊነጋገርና መፍትሄውን በማስቀመጥ ለተግባራዊነቱ ሊተጋ ይገባል፤አለበለዚያ የችግሮቹ መንስኤ ኢህአዴግም ሆነ ተጠቂው ህብረተሰብ ከሚመጣው አስከፊ የፖለቲካ፣ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ማምለጥ ስለማይቻል ስለሀገራችን ሁኔታ በግልፅ ሊመከርበትና መፍትሄ ሊበጅለት ይገባል፡፡
Black terror on freedom of expression
Bisrat Woldemichael
addismediab@gmail.com
Among the desperate times faced by Ethiopians in the 1970s are the socialist divisions among the citizens as groups of ‘white terror and red terror.’ At that time, military rules suppressed ideas. For this reason, some parties are established to face against the army while others are subjected to life in refuge.
The Derg regime did not allow the freedom to expressions and suppressed the press freedom amid its demise by the EPLF & EPRDF forces in 1991. The Derg opponents of that time split in to two as Ethiopia & Eritrea and repeating the same system they used to oppose.
Particularly, after controlling the Menlik II palace in Addis Ababa, under the leadership of Mr.Meles Zenawie, the EPRDF disclosed the right to free expressions, press freedom, multiparty, freedom of organization for professionals and political parties. Proclamation 34/93 for press freedom in accordance with the constitution Article 29(3) A & B, the right for press freedom for multimedia and copyright provisions are being respected. The press freedom particularly encompasses the following press rights:-
A. Any form of censorship is prohibited
B. Clearly indication of getting information for public interest but the above rights slightly worked only until May 2005 during the election. The main reason that the free press disclosed the bad operations and oppression of the press rights by the government and played major roles in the election by motivating the public at large. After the election, some journalists were jailed and others were subjected to refuge.
Consequently, the CPJ, HRW and other reputable international media indicate that more than 140 free press and about 48 government multimedia Journalists are subjected to refuge.
In fact, even during that time, the number of free press and government media are not proportional to the need of the people. Notwithstanding to the gaps in capacity of some free press & government media professionals, the number of such institutions remains lacking ; for this reason, information supply is limited to some towns and cities.
Notwithstanding to the provisions of the constitution, the press freedom proclamation No. 590/2007 article 4/1/ that attest ‘The freedom of multimedia is accredited by the constitution. Censorship is prohibited in any way.’ In this proclamation Article 2 attests that “any limitations to multimedia shall be enforced based up only on the provisions of the constitution and the laws.’ The fact presently is far beyond this truth.
For instance, the government owned ‘Berhanena Selam Printing Enterprise’ officially violated the constitution and the proclamation and drafted a new ‘printing Agreement.’ In this draft article 10/1/ is written ‘The printing press, up on findings that the script supplied by the client violates the law, has the right to reject the printing order.’ This shows that the firm is ready to censor the script before it is printed and as a result the newspapers that officially disclose human rights violations, non democratic operations, issues of good governance and inappropriate actions by EPRDF will be forced to diminish and the public remains thirsty of such information. This encourages dictatorship and the need to remain on power.
The other article 10/2 of this draft attests that ‘If the printing press finds a content that brings legal accountability is intentionally submitted for printing, it can terminate or dissolve the agreement.’ Besides implementing censorship, it articulates the Journalist or the press ethics as if it is not legally accountable and therefore leading to a conclusion that journalism is not a disciplinary profession. The amazing thing here is that it contradicts with the constitution regardless of the article 9/1/ that states any law or regulation that contradicts the constitution shall be nullified. Not only due to the fact that the printing press belongs to the government but also under the leadership of the EPRDF higher officials that it intended to censor scripts.
The socialist partisan philosophy divided parties as ‘white terror’ and ‘red terror’ and now indirectly imposed on the free press because of censorship. The White terror and red terror are direct signs for bloodshed but censorship is indirect way of violation of freedom of consciousness and that’s why we called it Black Terror. Thus any threat to the natural rights of human beings shall be cursed.
The EPRDF led Ethiopian Government appears saying ‘The right to free expression and press freedom are constitutionally approved’ to win the hearts of donors and fooling citizens but kept contrary in action. Writing on papers cannot guarantee the right of citizens nor does it have more value than the paper it is printed on. Freedom shall be shown in action not only by papers. Therefore, suppressing the free press and censorship is a black terror to the freedom of expressions. In this case now a day’s two independent newspapers Feteh and Finote Netasnet are blocked from publishing without legal ground.
In general, suppressing the free press is not only violation of the law but also threatening dignified humanity.
