መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ እስር ቤት በደረሰባቸው ችግር ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ
የህዳር 27 እና 28 ቀን 2007 ዓ.ም. የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የጠራው የአዳር ሰልፍ ወቅት ተይዘው በደረሰባቸው ከፍተኛ ድብደባ እና ለሶስት ቀን የስኳር በሽታ መድሃኒት እንዳይገባላቸው በመከልከላቸው ለህመም የተዳረጉት የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) ምክትል ፀኃፊ መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ ከእስር ከተፈቱበት ጊዜ ጀምሮ ለሁለት ወር ሆስፒታል ከቆዩ በኋላ በዛሬው ዕለት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡
መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ በአዳሩ ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ተይዘው ከፍተኛ ድብደባ የደረሰባቸው ሲሆን ለአምስት ቀናት ቀዝቃዛና ጨለማ ቤት ውስጥ ታስረው ቆይተዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ከታሰሩበት ጊዜ ጀምሮ ይዘውት የነበረውን የስኳር በሽታ መድሃኒታቸውን በመቀማታቸው፣ እንዳይገባላቸው በመከልከላቸውና በወቅቱም ህክምናም ባለማግኘታቸው ለከፍተኛ ህመም በመዳረጋቸው ለሁለት ወር ያህል ዘውዲቱ ሆስፒታል ቆይተዋል፡፡
መቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ እስር ቤት እያሉ በደረሰባቸው ችግር ምክንያት ዘውዲቱ ሆስፒታል ከገቡበት ታህሳስ 4 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ከፍተኛ ህመም እየተሰቃዩ እንደነበሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የመቶ አለቃ ተሰማ ወንድሙ የቀብር ስነስርዓት ዛሬ ጥር 27 ቀን 2007 ዓ.ም በቦሌ ሚካኤል እንደሚፈጸም ተጠቁሟል፡፡
ከዚህ በፊት ከኬንያ በህወሓት ደህንነት ታፍነው አዲስ አበባ ቃሊቲ በሚገኘው ወህኒ ቤት ታስረው በህወሓት ፖሊሶችና ደህንነቶች በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ድብደባ ኢንጂነር ተስፋሁን ጨመዳን ጨምሮ መገናኛ ብዙኃን ይፋ ያላወጣቸው የተለያዩ ኢትዮጵያውያን መሞታቸው ይታወቃል፡፡