Daily Archives: February 3rd, 2015

ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድ የፓርቲዎች ሚዲያ አጠቃቀም ድልድል ፍትሃዊ አለመሆኑን አስታወቀ

Semayawi-Party

ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድ ያወጣው ረቂቅ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ውድድር የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ሰዓት አጠቃቀም ድልድል ፍትሃዊና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ አለመሆኑን አስታወቀ፡፡

ጥር 25 ቀን 2007 ዓ.ም የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሀገር አቀፍ ፓርቲዎችን በረቂቅ የሰዓት ድልድሉ ላይ ጊዮን ሆቴል ጋብዞ ውይይት አድርጓል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ) ኃላፊዎች ረቂቁን ለውይይት ያቀረቡ ሲሆን፣ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ እና ሌሎች ኃላፊዎችም በውይይቱ ተገኝተዋል፡፡

የኢብኮ/ኢቴቪ ኃላፊዎች ባቀረቡት የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚዲያ አጠቃቀም ረቂቅ ድልድል መሰረት 55 ፐርሰንት በፓርላማ መቀመጫ ወንበር ላላቸው ፓርቲዎች፣ 20 ፐርሰንት ፓርቲዎቹ በሚያቀርቧቸው ዕጩዎች ብዛት እንዲሁም ቀሪ 25 ፐርሰንቱ ለሁሉም ፓርቲዎች በዕኩል የሚከፋፈል እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲን በመወከል በውይይቱ ላይ የተገኙት የፓርቲው የህግ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ይድነቃቸው ከበደ ለነገረ ኢትዮጵያ እንደገለጹት፣ ረቂቅ የሚዲያ አጠቃቀሙ ድልድል ሲወጣ እንደ መስፈርት የተጠቀሙባቸው ነጥቦች ችግር ያሉባቸው ናቸው፡፡
‹‹በእኛ እምነት መስፈርቱም ልክ አይደለም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የሚዲያ ሰዓት አጠቃቀም ድልድል ሲወጣ ሁለት መስፈርቶች በቂና ትክክለኛ ናቸው ብሎ ያምናል፡፡ እነዚህ ነጥቦች በሚቀርቡ እጩዎች ብዛት እና በእኩልነት የሚከፋፈል የድልድል መስፈርት መሆን አለባቸው›› ብለዋል አቶ ይድነቃቸው፡፡

በእርግጥ ረቂቁን ያቀረበው ኢብኮ እንደ መመዘኛ መስፈርት የተጠቀመው ‹‹እኩልነትና ፍትሃዊነት›› የሚሉ መርሆዎችን ነው፡፡ ‹‹ኢብኮ በቃላት ደረጃ የገለጻቸው ‹ፍትሃዊነትና እኩልነት› በተግባር ረቂቅ ድልድሉ ላይ አልታዩም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በእኩልነትና ፍትሃዊነት መርሆዎች ላይ ችግር የለበትም፡፡ መርሁን መሰረት አድርጎ ወጣ የተባለው የሚዲያ ድልድል መጠን ግን በትክክል መርሁን የተከተለ አይደለም፡፡ ስለሆነም ለውጥ ሊደረግበት ይገባል›› ብለዋል አቶ ይድነቃቸው፡፡

አቶ ይድነቃቸው የሰዓት አጠቃቀም ድልድሉ ላይ ስንወያይ ነጻ ሚዲያ በሌለበት፣ ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በተገደበበት፣ ጋዜጠኞች በታሰሩበትና በተሰደዱበት፣ አማራጭ የሚዲያ ተቋማት በሌሉበት በዚህ አጣብቂኝ ወቅት ላይ በህዝብ ሀብት በሚተዳደሩ ሚዲያዎች ላይ የፍትሃዊነት ችግር ይዘን መወያያታችን አሳዛኝ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ሳንሱር በህገ-መንግስቱ ተነስቷል፤ ይሁን እንጂ ኢብኮ የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለያዩ ጊዜያት ለህዝብ የሚያስተላልፏቸው አማራጭ ሀሳቦችና ፖሊሲዎቻቸውን በቆርጦ ቀጥል ሲያዛባ እናስተውላለን፤ ይህ ሁኔታ መወገድ ያለበት ነው፡፡››

በውይይቱ ላይ ኢህአዴግ የድልድሉ መስፈርት ላይ እንደሚስማማ በመግለጽ፣ በፐርሰንቱ የተቀመጠው መጠን ላይ ግን መሻሻል እንዲደረግ እንደሚፈልግ መግለጹ ታውቋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ አባላት በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን ተቀላቀሉ

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

ከግራ ወደ ቀኝ አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ አቶ አበበ አካሉ፣አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እና ወጣት ስንታየሁ ቸኮል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ በወሰኑብን ፖለቲካዊ ውሳኔ ምክንያት አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲን ተነጥቀናል ያሉ የአንድነት ፓርቲ አባላት› በይፋ ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስታወቁ፡፡

በእነ በላይ ፍቃዱ አመራርነት አንድነት ፓርቲን በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ሲመሩ የነበሩ አመራሮች ዛሬ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት ከቀድሞ ፓርቲያቸው አንድነት ጋር የፕሮግራምም ሆነ የስትራቴጂ ተመሳሳይነት ወዳለው ሰማያዊ ፓርቲ ተቀላቅለው ሰላማዊ ትግላቸውን ለመቀጠል መወሰናቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡

መግለጫውን የ”ቀድሞው አንድነት ፓርቲ” አፈ ጉባዔ የነበሩት አቶ አበበ አካሉ፣ ምክትል አፈ ጉባዔው አቶ ፀጋዬ አላምረው፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ነገሰ ተፈረደኝ እንዲሁም የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊው አቶ ስንታየሁ ቸኮል ሌሎችን በመወከል ሰጥተዋል፡፡

“የምናምነው በሰላማዊ ትግል ብቻ ነው፡፡ ይህን ሰላማዊ ትግል ለመምራት ደግሞ ሰማያዊ ፓርቲ ብቁ ነው ብለን በማመን ፓርቲውን ተቀላቅለናል” ብለዋል በመግለጫው ላይ የተወከሉት አዲሶቹ የሰማያዊ አባላት፡፡
በዚህ መሰረትም በርከት ያሉ አመራሮችና አባላት በይፋ የሰማያዊ ፓርቲ የአባልነት ፎርም ሞልተዋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአንድነት አባላት ሰማያዊ ፓርቲን መቀላቀላቸውን አስመልክቶ መግለጫ ለመስጠት ወደ ሰማያዊ ቢሮ ባቀኑበት ወቅት፤ፖሊስ ሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ ድረስ በመግባት “በሰማያዊ ስም መግለጫ የሚሰጡ አካላት እንዳሉ ሰለሰማን ነው” በሚል ለፓርቲው አመራሮች ጥያቄ ማቅረባቸውን ከስፍራው የደረሰን ዘገባ አመልክቷል፡፡

አይካ-አዲስ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ሰራተኞች የስራ ማቆም አድማ መቱ

ayeka-addis

በቱርክ ባለሃብቶች የተያዘው የአይካ አዲስ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ሰራተኞች ከጥር 23 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምረው የስራ ማቆም አድማ መምታታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ኩባንያው በየ አመቱ በሚያደርገው የደመወዝ ጭማሬ መሰረት በዘንድሮው አመት የተሻለ የደመወዝ ጭማሬ እንደሚያደረግ የገለጸበትን ወረቀት ለሰራተኞቹ በትኖ የነበር ቢሆንም ቅዳሜ ጥር 23 ቀን 2007 ዓ.ም ለሰራተኞቹ በተበተነው ሌላ ወረቀት የደመወዝ ጭማሬው ከተጠበቀው በታች ሆኖ በመገኘቱ ሰራተኞች ‹‹ስራ አንሰራም›› ብለው ፋብሪካው ግቢ ውስጥ ተቀምጠው ተቃውሟቸውን መግለጻቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ከሰኞ 25 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ኢትዮጵያውያን የድርጅቱ ሰራተኞች አድማውን አጠናክረው እንደቀጠሉ ታውቋል፡፡

ቅዳሜ ጥር 23/2007 ዓ.ም ሰራተኞቹ የደመወዝ ጭማሬውን ከሰሙ በኋላ “ስራ አንሰራም” በማለታቸው የፋብሪካው ኃላፊዎች “የአንድ ወር ገደብ ስጡንንና እናስተካክል” የሚል ጥያቄ ቢያቀርቡም ሰራተኞቹ በበኩላቸው “በሳምንት ጊዜ ውስጥ ይስተካከል” የሚል ሀሳብ አቅርበው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሆኖም በሁለቱ መካከል ስምምነት ላይ መድረስ አልተቻለም፡፡ የመስሪያ ቤቱ ኃላፊዎች ሰራተኞቹን እየነጠሉ ለማናገር ያደረጉት ሙከራም እንዳልተሳካላቸው ተገልጾአል፡፡

ቅዳሜ ጥር 23 ዓ.ም ዝቅተኛ ነው የተባለው የደመወዝ ጭማሬ ምክንያት ስራ ሳይገቡ መስሪያ ቤቱ ግቢ ውስጥ ተሰብስበው የዋሉት የአይካ አዲስ ሰራተኞች ከትናንት ሰኞ ጥር 25 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ማቆም አድማ መምታታውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

አይካ አዲስ ከ8 ሺህ በላይ ሰራተኞች እንዳሉት የገለጸችው አንዲት የድርጅቱ ሰራተኛ ድርጅቱ ተመሳሳይ ስራ ላይ በተሰማሩ ኢትዮጵያውያንና የውጭ ዜጎች መካከል ደመወዝን ጨምሮ ከፍተኛ ልዩነት እንዳለና በኢትዮጵያውያን ላይ መድሎ እንደሚፈጽም ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጻለች፡፡ ከዚህ በደል በተጨማሪ ፋብሪካው የገባውን ቃል አለመፈፀሙ ሰራተኞቹ ስራ እንዲያቆሙ ምክንያት እንደሆነም ሰራተኞቹ ገልፀዋል፡፡

የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደረገ

prisoners

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ውድቅ ተደረገባቸው፡፡ አመራሮቹ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ችሎት ቀርበዋል፡፡

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱት የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች መቃወሚያቸው በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡

ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የቀረቡባቸው የተለያዩ የክስ ይዘቶች ላይ መቃወሚያቸውን አቅርበው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ የተከሳሽ መቃወሚያ ውድቅ እንዲደረግለት የጠየቀውን በመቀበል ‹‹በመቃወሚያው ላይ የተነሱት ነጥቦች በአብዛኛው ማስረጃ በማሰማት ሂደት ወቅት ሊረጋገጡ የሚችሉ ስለሆኑ›› በሚል መቃወሚያቸው ውድቅ ተደርጓል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤት በቀረበው ክስ አግባብ የክስ ሂደቱ እንዲቀጥል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ በሚገኙበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ላይ ‹‹የመብት ጥሰት እየተፈጸመብን ነው›› በሚል አቤቱታ አቅርበው የነበር ሲሆን በአቤቱታው ላይ እስካሁን ከማረሚያ ቤቱ መልስ አለመሰጠቱ ታውቋል፡፡ አቤቱታው በጽሑፍ ተገልብጦ ለማረሚያ ቤቱ መላኩን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ ለአቤቱታው መልስ ከማረሚያ ቤቱ እየተጠበቀ እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

በመሆኑም ይህንኑ የማረሚያ ቤቱን መልስ ለመስማትና የክሱን ሂደት ለመቀጠል ፍርድ ቤቱ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ፡-ነገረ-ኢትዮጵያ

“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት

በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-

udj

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************

የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡

የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።

በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።

የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ጥር 26 ቀን 2007

%d bloggers like this: