ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ አረፉ
(አዲስ ሚዲያ) ለረጀም ጊዜ የኢትዮጵያ ረጅም ርቀት ሩጫ ውድድር አሰልጣኝ የነበሩት ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ69 ዓመታቸው ትናንት ሰኞ ግንቦት 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ዶ/ር ወልደመስቀል ኢትዮጵያ ከነ አበበ ቢቂላ፣ ማሞ ወልዴ እና ምሩፅ ይፍጠር በኋላ በጋራም ሆነ በግል በሚገኙ አትሌቶች የድል ውጤት ዋነኛ ተጠቃሽ አሰልጣኝ ናቸው፡፡

በተለይም አትሌት ኮሎኔል ደራርቱ ቱሉ፣ አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ፣ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ አትሌት ጠሩነሽ ዲባባ፣ አትሌት ብርሃኔ አደሬ፣ አትሌት ጌጤ ዋሚ፣ አትሌት ወርቁ ቢቂላ፣ አትሌት ፊጣ ባይሳ፣ አትሌት አሰፋ መዝገቡ፣ አትሌት ስልሺ ስህን፣…የመሳሰሉ ስመጥር አትሌቶችን ያፈሩ በማፍራት በርካታ የወርቅ፣ የብር እና የነሐስ ሜዳልያ ሽልማቶችን ከአትሌቶቹ በተጨማሪ ሀገሪቷም እንድታገኝ ያስቻሉ ታላቅ ሰው ነበሩ፡፡
ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ ከ1964 ዓ.ም. ጀምሮ ለ30 ዓመታት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ የረጅም ርቀት አሰልጣኝነት ላበረከቱት አስተዋፅዖ በሀገሪቱ መንግሥትም ሆነ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተሰጣቸው ዕውቅናም ሆነ ሽልማት ባይኖርም፤ የዓለም አቀፍ አትሌቲክ ማኀበር (IAAF) በ1998 ዓ.ም. (እ.አ.አ በ2006) ምርጥ አሰልጣኝ በሚል ተሸላሚ እንደነበሩ አይዘነጋም፡፡
በአርባምንጭ አካባቢ የመንግሥት ወታደሮች ላይ ጥቃት ተፈፀመ
(አዲስ ሚዲያ) በአርባ ምንጭ ነጭ ሳር አካባቢ ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች የመንሥት ወታደሮች ላይ ድንገተኛ ጥቃት አደረሱ፡፡ በጥቃቱ የአካባቢው ወታደራዊ አዛዥን ጨምሮ ከ20 ያላነሱ የመንግሥት ወታደሮች መገደላቸውን እና ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ወታደሮችም ጉዳት ደርሶባቸው በአርባምንጭና በአካባቢው ባሉ የጤና ተቋማት የህክምና ዕርዳት እየተደረገላቸው መሆኑን ከስፍራው የዓይን እማኞችን ጠቅሶ ኢሳት ዘግቧል፡፡ የተፈፀመውን ጥቃት በተመለከተ መንግሥት በመግለጫው እንዳተተው ከሆነ፤ ጥቃቱ የፈፀሙ አካላት ከኤርትራ ስልጠና ወስደው በዩጋንዳ፣ ኬንያ፣ ሞያሌ አድርገው ወደ አርባምንጭ አከባቢ እንደመጡ፤ ጥቃት አድራሾችም በፀጥታ ኃይሉ እንደተማረኩ አስታውቋል፡፡

መንግሥት ጥቃት አድራሾቹ እነማን እንደነበሩ እና ቁጥራቸው ምን ያህል እንደሆነ ከመግለፅ ተቆጥቧል፡፡
ይሁን እንጂ በስሩ ባሉ መገናና ብዙኃን እና በመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጽህፈት ቤት ገፅ ላይ ጥቃት አድራሾቹ ከነትጥቃቸው እንደተማረኩ በማስመሰል በአንድ ወቅት አሜሪካ በኢራቅ ከታጣቂዎች ማረኩት ብላ ያሰራጨው ምስል በማኀበራዊ ሚዲያ ከተጋለጠ በኋላ መንግሥት ማረኩት ያለውን የተሳሳተ መረጃ ምስልን ከአንድ ቀን በኋላ ከገፁ ላይ አንስቶታል፡፡
ማክሰኞ ግንቦት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. በዚህ በአርባ ምንጭ አካባቢ በመንግሥት ኃይሎች ላይ ለተፈፀመው ጥቃት ስርዓቱን በሁለገብ ትግል ለመጣል በይፋ የሚንቀሳቀሰው አርቦኞች ግንቦት 7 ለአንደነት እና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ (አርበኞች ግንቦት 7) ኃላፊነቱን ወስዷል፡፡ በተለይ የድርጅቱ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ እና ለኢሳት በሰጡት ቃለመጠይቅ ላይ አርበኞች ግንቦት 7 በመንግሥት ወታደሮች ላይ በአርባምንጭ አካባቢ ጥቃት መፈፀሙን አረጋግጠዋል፡፡
እንደ ፕሮፌሰሩ ገለፃ ከሆነ ድርጅቱ ሀገር ውስጥ ከሚንቀሳቀሰው እና በደቡብ ካለው አነስተኛ ቡድን የተሰነዘር ጥቃት መሆኑን እና የጦር መሳሪያውንም ቢሆን ያገኙት ከራሱ ከመንግሥት ኃይሎች መሆኑን በማረጋገጥ በሌሎች የአሀገሪቱ አካባቢዎችም ተመሳሳይ ጥቃት በመንግሥት ላይ እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡
ፕሮፌሰሩ አክለውም አርበኞች ግንቦት 7 የሚታገለው ኤርትራ ውስጥ ሳይሆን ሀገር ቤት ኢትዮጵያ ውስጥ መሆኑን እና በሁሉም የሀገሪቱ አቅጣጫ እየተንቀሳቀሰ ስለመሆኑ የአርባምንጩ ጥቂት ማሳያ እንደሆነ በመግለፅ የስርዓት ለውጥ እስካልመጣ ድረስ ወደፊትም ተመሳሳይ ጥቃቶች በመንግሥት ላይ የሚቀጥሉ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡ በጥቃቱም ከአርበኞች ግንቦት 7 በኩል በመንግሥት ወታደሮች በተወሰደ የፀፋ ርምጃ ምን ያህል ጉዳት እንደደረሰ ከመግለፅ ተቆጥበዋል፡፡
77 ቢሊዮን ብር የሚያንቀሳቅሰው ስኳር ኮርፖሬሽን የገጠመው ፈተና
‹‹ለስኳር ኮርፖሬሽን መውደቅ ሜቴክ ትልቅ ድርሻ አለው› ‹‹የስኳር ኮርፖሬሽን የቀድሞ አመራሮች መጠየቅ አለባቸው››

የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች
በዮሐንስ አንበርብር
በ2003 ዓ.ም. በተካሄደው የመጀመርያ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ትልቅ ትኩረት ከተሰጣቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል የስኳር ልማት አንደኛው ነው፡፡ አገሪቱ ለስኳር ልማት ያላትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም አሥር ግዙፍና አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎችን በመገንባት በዓመት 4.07 ሚሊዮን በላይ ስኳር በማምረትና ለውጭ ገበያ በማቅረብ፣ በ2007 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ 1.2 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት በዕቅድ ተይዞ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ይህ ዕቅድ በጣም የተለጠጠ መሆኑ በስተመጨረሻ ሲታወቅ፣ ሰባት ፋብሪካዎችን በመጀመርያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ማጠናቀቅ ተብሎ እንዲከለስ ተደርጓል፡፡
እነዚህ አዳዲስና ግዙፍ ፕሮጀክቶች በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገነቡት ኩራዝ አንድ፣ ኩራዝ ሁለት፣ ኩራዝ ሦስት፣ በለስ አንድ፣ በለስ ሁለት፣ ከሰም፣ ወልቃይት፣ አርጆ፣ ደዴሳና ተንዳሆ ናቸው፡፡
መንግሥት ፕሮጀክቶቹን አጠናቆ ስኳር ለውጭ ገበያ በማቅረብ በሚገኝ የውጭ ምንዛሪ ዕዳ መክፈል እንደሚችል በማሳመን ለስኳር ፋብሪካዎቹ መገንቢያ ከተለያዩ አበዳሪዎች ሁለት ቢሊዮን ዶላር ተበድሯል፡፡ ከአገር ውስጥ ባንኮችም ከፍተኛ ብድር አግኝቷል፡፡ በአጠቃላይ የስኳር ልማቱን የሚመራው የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን 77 ቢሊዮን ብር በላይ እያንቀሳቀሰ የሚገኝ ቢሆንም፣ አንድም ፋብሪካ እስካሁን ተጠናቆ ወደ ሥራ አልገባም፡፡ በሌሎች አገሮች አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ ግፋ ቢል አንድ ዓመት የሚፈጅ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ግን አንድ ዓመት ከስድስት ወራት (18 ወራት) አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ አቅዶ የውል ስምምነቶችን ቢያደርግም፣ አንድ ፋብሪካ ሥራ ሳይጀምር ስድስተኛ ዓመት ላይ ተደርሷል፡፡
የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የሥራ ኃላፊዎች በ2008 የበጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለማቅረብ ባለፈው ሰኞ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተገኝተዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ከተሾሙ የወራት ዕድሜን ያስቆጠሩት አቶ እንዳወቅ አብቴና ሌሎች ምክትል ሥራ አስፈጻሚዎች ያቀረቡት ሪፖርት ‹‹ተስፋ በመቁረጥና እያመመን ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት ግንባታው የተጀመረው ተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ በኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ስኳር ማምረት ቢጀምርም ጥራቱ የተጓደለ የእንፋሎት አቅርቦት፣ የፋብሪካውን ፊልተር በቆሻሻ በመዝጋቱና በተርባይን ላይ ጉዳት በማድረሱ እንዲቆም መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ጥገና ከተደረገ በኋላ በአገሪቱ በተከሰተው ድርቅ ለፋብሪካውና ለመስኖ የሚሆን የውኃ አቅርቦት ችግር ወደ ምርት እንዳይገባ እንዳደረገው ጠቁመዋል፡፡
የተንዳሆ ቁጥር ሁለት ፋብሪካ ግንባታም ገና 27 በመቶ ላይ ይገኛል፡፡ ኩራዝ አንድ የተባለው ፋብሪካ ኮንትራት ውል የተገባው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ የውል ማሻሻያ ሰኔ 2004 ዓ.ም. ላይ እንደተደረገ አቶ እንዳወቅ አስረድተዋል፡፡
በዚህ መሠረት ግንባታውን የሚያከናውነው አገር በቀሉ የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ፕሮጀክቱን በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. አጠናቆ ማስረከብ ይጠበቅበት ነበር፡፡
ፕሮጀክቱ በመጋቢት ወር 2008 ዓ.ም. ላይ የደረሰበት ደረጃ 83 በመቶ ሲሆን፣ ሜቴክ ግን 97 በመቶ ክፍያ እንደተፈጸመለት አቶ እንዳወቅ ተናግረዋል፡፡ ኩራዝ ሁለት የተባለውን ፋብሪካ ለማስገንበት ውል የተፈረመው እ.ኤ.አ. በሐምሌ ወር 2014 ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 58 በመቶ መድረሱን ይጠቅሳሉ፡፡ በውሉ መሠረት በመጪው ሐምሌ ወር ፕሮጀክቱ መጠናቀቅ የነበረበት ቢሆንም መዘግየቱን አስታውቀዋል፡፡ የፕሮጀክቱ ኮንትራክተር የፕሮጀክቱ ማጠናቀቂያ ጊዜ እንዲራዘምለት ጠይቆ እስከ መጪው ኅዳር ወር እንዲያጠናቅቅ መመርያ እንደተሰጠው አብራርተዋል፡፡
ኩራዝ ሦስት ግንባታው የተጀመረው እ.ኤ.አ. በፌብሯሪ 2015 ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 25 በመቶ ደርሷል፡፡ ይህም ቢሆን መሆን ከነበረበት ወደ ኋላ የቀረ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ኩራዝ አምስት ስኳር ፋብሪካን ለማስጀመር ከቻይና ኩባንያ ጋር ውል የተፈጸመ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ለመግባት ኩባንያው ዝግጅት ላይ መሆኑን አቶ እንዳወቅ ይገልጻሉ፡፡ በለስ አንድ ስኳር ፕሮጀክት ወደ ሥራ የገባው በየካቲት 2003 ዓ.ም. ነው፡፡ በሰኔ ወር 2004 ዓ.ም. የውል ማሻሻያ መደረጉንና በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. ኮንትራክተሩ ሜቴክ አጠናቆ ማስረከብ የነበረበት ቢሆንም፣ የፕሮጀክቱ አፈጻጸም በአሁኑ ወቅት ገና 60 በመቶ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ኮንትራክተሩ ግን 94 በመቶ የሚሆነውን ክፍያ መቀበሉን ገልጸዋል፡፡
በለስ ሦስት ፋብሪካን ለመገንባት ውል የተፈጸመው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ መጠናቀቅ የሚገባው በ2005 መጋቢት ላይ እንደነበረ ያስረዳሉ፡፡ ይሁን እንጂ ፕሮጀክቱ ገና 23 በመቶ ሲሆን፣ ኮንትራክተሩ ሜቴክ ግን 94 በመቶ ክፍያ እንደተከፈለው ያስረዳሉ፡፡
የከሰም ስኳር ፋብሪካ አፈጻጸም 96 በመቶ መድረሱን ነገር ግን ገና ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ እንዳልገባ አክለዋል፡፡ ወልቃይት ስኳር ፋብሪካም ግንባታው እንዳልተጀመረና በቅርቡ ግንባታው እንደሚጀመር ገልጸዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን ገንብቶና ምርት ኤክስፖርት በማድረግ ዕዳውን የመክፈል ኃላፊነት የተሰጠው ቢሆንም፣ ኤክስፖርት ማድረግ ይቅርና የአገሪቱን የስኳር ፍላጎት ማሟላት አለመቻሉን ገልጸዋል፡፡
ግንባታዎቹን ለማከናወን 77 ቢሊዮን ብር የውጭና የአገር ውስጥ ብድር የተበደረ በመሆኑ፣ አንድም ፋብሪካ ወደ ምርት ባልገባበት በአሁኑ ወቅት 13 ቢሊዮን ብር ዕዳ ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ የመክፈል ኃላፊነት ከፊቱ ተጋርጧል፡፡
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ይገዙና የኮሚቴው አባላት የኮርፖሬሽኑ ችግር ምን እንደሆነ፣ ሥራው ባልተሠራበት ሁኔታ ከ90 በመቶ በላይ ገንዘብ ለምን እንደተከፈለ ማብራሪያ ጠይቀዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ የኢንቨስትመንትና ልማት ዘርፍ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ አብርሃም ደምሴ በሰጡት አስተያየት፣ የአሥሩም አዳዲስ ፋብሪካዎች ኮንትራት የተሰጠው ለአገር በቀሉ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) መሆኑን አስታውሰው፣ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን መገንባት እንዳልቻለ ገልጸዋል፡፡ ይህ ቢሆንም የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን አመራሮች ከሜቴክ ጋር የነበራቸው ግንኙነት በቢዝነስ ኮንትራት ሕግ የማይመራ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡
‹‹አሥሩም ፋብሪካዎች በዚህ ኮንትራክተር እንዲሠሩ ነበር የተወሰነው፡፡ በኋላ ላይ የመፈጸም አቅሙ እየታየ ፕሮጀክቶቹ እየተነጠቁ አሁን እጁ ላይ ሦስት ፋብሪካዎች ናቸው የቀሩት፤›› ብለዋል፡፡
ከዚህ ኮንትራክተር (ሜቴክ) ተነጥቀው ፋይናንስ ተገኝቶላቸው ወደ ሥራ ከገቡት መካከል ከሰም ሥራ ለመጀመር ዝግጅት ላይ ሲሆን፣ ሌሎቹ ደግሞ እስከ ኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ይደርሳሉ ብለዋል፡፡ በሜቴክ እጅ የሚገኙት ግን መቼ እንደሚጠናቀቁ እንኳን ለማወቅ አስቸጋሪ እንደሆነባቸውና ከድርጅቱ ጋር ልቅ የሆነው ግንኙነት በውል ያልታሰረ በመሆኑ ዕርምጃ እንኳን ለመውሰድ እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡
ሜቴክ በእጁ የሚገኙትን ሦስት ፋብሪካዎች በተለይም ኩራዝ አንድ ፋብሪካን በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ለማጠናቀቅ ገንዘብ እንደሚያስፈልገው ገልጾ፣ በልዩ ሁኔታ ስኳር ኮርፖሬሽን የአገር ውስጥ ብድር እንዲያገኝ ተደርጎ ሊከፈለው መቻሉን አቶ አብርሃም አስረድተዋል፡፡
‹‹ይሁን እንጂ ይህ ፋብሪካ እስካሁን አልተጠናቀቀም፡፡ እኛ ግን ዕዳ የመክፈል አደጋ ከፊታችን ተጋርጧል፤›› ብለዋል፡፡ ፋብሪካዎቹ ባለመድረሳቸው ምክንያት አጠቃላይ የስኳር ኮርፖሬሽን ወጪ እየናረ መሆኑን የሚገልጹት የሥራ ኃላፊው፣ የሸንኮራ አገዳው ቢደርስም አገዳውን ከማስወገድ ሌላ አማራጭ አለመገኘቱን ገልጸዋል፡፡
‹‹ኩራዝ ላይ 870 ሔክታር አገዳ ለማስወገድ ተቃርበናል፡፡ 300 ሺሕ ሔክታር የሸንኮራ አገዳ በለስ ላይ አስወግደናል፡፡ ይህንን ለማስወገድ በሔክታር 50 ሺሕ ብር እያወጣን ነው፤›› በማለት በምሬት ተናግረዋል፡፡
‹‹በዚህ ኮንትራክተር ላይ እንደ ማንኛውም ኩባንያ ቅጣት መጣል እንደማንችል ሁላችሁም ታውቃላችሁ፡፡ የሚያስጠይቅ ነገር ካለ ባለቤቱ ተለይቶ መጠየቅ ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡
ሌላው የኮርፖሬሽኑ አመራርም የሜቴክ ችግር በመገንባት ላይ ባሉት ፋብሪካዎች ላይ ብቻ አለመሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ በማምረት ላይ ለሚገኙ ፋብሪካዎች መለዋወጫ የሚያቀርበው ሜቴክ መሆኑን በመጥቀስ፣ መለዋወጫ ባለማቅረቡ ምክንያት ፋብሪካዎች ለበርካታ ቀናት ምርት እንደማያመርቱ ገልጸዋል፡፡
‹‹የማይችሉትን ሁሉ እንችላለን እያሉ አገርን ዋጋ እያስከፈሉ ነው፡፡ ምክንያቱም ነባሮቹ ፋብሪካዎች ያለ ችግር ቢሠሩ ቢያንስ በውጭ ምንዛሪ ስኳር አናስገባም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ መለዋወጫ ከሜቴክ የመግዛት ግዴታ ለአገሪቱ አዋጭ አለመሆኑን፣ ምክንያቱ ደግሞ ሜቴክ ራሱ ከውጭ ከሚገባው በላይ እየሸጠ መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡ ‹‹ለምሳሌ ሮለር ከውጭ ስንገዛ ከ200 ሺሕ ብር አይበልጥም፡፡ ሜቴክ ግን 600 ሺሕ ብር ነው የሚሸጥልን፤›› ብለዋል፡፡
‹‹እንቢ ብለን እንኳን እንዳንታገል አመራሮች ያሸማቅቁናል፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው ከሌሎች አካላት ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለብቻ በሌላ መድረክ እንደሚያይ አስታውቆ አሁንም የኪራይ ሰብሳቢነት ችግር በኮርፖሬሽኑ ውስጥ መኖሩን በመጥቀስ ፋብሪካዎች ኦዲት እንዲደረጉ አዟል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ
ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ 5 ዓመት ከ4 ወር ቅጣት እስር ተበየነበት
( አዲስ ሚዲያ) የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ላይ 5 ዓመት ከ4 ወር የእስር ቅጣት ተበየነበት፡፡ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የደ ብርሃን ድረ-ገፅ ተባባሪ ብሎገር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ድህረ-ምረቃ ተማሪ የነበረ ሲሆን፤ በውጭ ሀገር የኢንተርኔት ደህንነት ስልጠና ለመውሰድ ማመልከቱ “ለሽብር ተግባር ተሰናድተዋል” በሚል በተመሰረተበት ክስ ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ሲል መበየኑ ታውቋል፡፡

በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ዘለዓለምን ጨምሮ 10 ተከሳሾች ከሰኔ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየታየ የነበረ ቢሆንም፤ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ሃታሙ አያሌው እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረው የሺዋስ አሰፋ፣ የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አባል አቶ አብርሃ ደስታ እንሁም መምህር አብርሃም ሰለሞን በተመሰረተባቸው ክስ በነፃ መሰናበታቸው ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ አቶ አብርሃ ደስታ ይህ ዜና እስከተዘገበበት ድሰር አሁንም በእስር ላይ ይገኛል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ከኦነግ ጋር ተያይዞ የሽብር ክስ ተመሰረተበት
የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና በምርጫ 2007 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ወረዳ 17 የፓርላማ እጩ ተወዳዳሪ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 የወጣውን አንቀጽ 4 ስር የተመለከተውን ተላልፏል በሚል ክስ ተመስርቶበታል፡፡

ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ክሱ በዳኞች ቢሮ በንባብ የተሰማበት አቶ ዮናታን ተስፋዬ፤ የአዲስ አበባ ከተማ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ሽፋን በማድረግ ከህዳር 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ተከሳሹ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ በተለይም ፌስቡክ አማካኝነት በኦሮሚያ ክልል የተነሳውን “አመፅና ብጥብጥ” ለማስቀጠል የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን ዓላማ ተቀብሎ ተንቀሳቅሷል ሲል አቃቤ ህግ ክስ መስርቶበታል፡፡ የክስ ፋይሉ ሌላ ተከሳሽ ውጭ ለአቶ ዮናታን ብቻ የቀረበበት የማስረጃ ዝርዝር በማኀበራዊ ሚዲያ የለጠፋቸው ፅሑፎች ናቸው፡፡
በዚህም ተከሳሹ የቡድን (ኦነግ) ዓላማን ለማሳካት አመፅና ብጥብጥ እንዲቀጥልና ሌሎችን ለማነሳሳት አስቦ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ (ፌስቡክ) ቀስቃሽ ፅሑፎችን በመፃፍ የሽብርተኝነት ድርጊት ለመፈፀም ማቀድ፣ ማዘጋጀት፣ ማሴር እና ማነሳሳት ወንጀል ክስ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት ታውቋል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ በተለያዩ ቀናት በግል የፌስቡክ ገጹ ላይ ያስነበባቸው ፅሑፎች ክሱ ላይ ተካተው በማስረጃነት ቀርቦበታል፡፡
ታህሣሥ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጭቆና መሳሪያነት የሚያገለግሉ ማናቸውንም ቁሳቁሶች ማቃጠልና ማውደም እንዲሁም መንገድ መዝጋትን በተመለከተ፣ ታህሣሥ 11 ቀን 2008 ዓ.ም. ኢህአዴግ ችግር ማዳፈን እንጂ ችግር መፍታት አይችልም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲጀመር ምንም ዓይነት መሪ ዕቅድ (ማስተር ፕላን) የለም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የተቃውሞ ትግሉ ቀጥሏል በሚል የፃፈው፣ ህዳር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. እነሆ 7 መልዕክት ብሎ በፃፈው እና በሌሎችም ፅሑፎች አማካኝነት ቅስቀሳ አድርጓል ሲል አቃቤ ህግ ክስ አቅርቦበታል፡፡
ዮናታን ተስፋዬ በነጠላ መዝገብ ብቻውን ክስ የተመሰረተበት ሲሆን፤ በዕለቱ ክሱ በንባብ በተሰማበት ወቅት ዳኛ አልተሟላም በሚል ምክንያት በዳኞች ቢሮ መታየቱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የክሱን ሂደት ዬናታን ቤተሰቦችም፣ ወዳጆችና ጋዜጠኞች በችሎት መታደም ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ አቶ ዮናታንም የክስ መቃወሚያውን ይዞ ለፊታችን ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዲቀርብ ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.