COINTELPRO: ተቃዋሚዎችን የመከፋፈያ ቀላል ዘዴ (ከአሜሪካ የተኮረጀ)

በፈቃዱ ኃይሉ
ይህንን ባለፈው በእንግሊዝኛ ጽፌው «በአማርኛ እና በኦሮምኛ ብትተረጉመው ጥሩ ነው» ተብዬ ነበር። በአማርኛ ይኸው፤ አፋን ኦሮሞ የምትችሉ ተርጉሙት።
ጋዜጠኛ #እስክንድር_ነጋ ነበር የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ልጠይቀው ቃሊቲ እስር ቤት ስሄድ ኮኢንቴልፕሮ (COINTELPRO) ስለሚባለው ነገር መጀመሪያ የነገረኝ። ቃሉ የአሜሪካ ፌዴራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ካውንተር ኢንተሊጀንስ ፕሮግራም ባጭሩ ሲጻፍ የተፈጠረ ነው። ፕሮግራሙ ድብቅ፣ አንዳንዴ ሕገ ወጥ፣ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ድርጅቶችን የመሰለል፣ ውስጣቸው ሰርጎ የመግባት፣ ተአማኒነት የማሳጣት እና የማስተጓጎል ተከታታይ ፕሮግራም ነው። ይህንን ጉዳይ አሁን ማንሳት ያስፈለገኝ ሰማያዊ ፓርቲ፣ እንደብዙዎቹ ከጨዋታ ውጪ እንደተደረጉ ፓርቲዎች በፈተና ውስጥ እያለፈ በመሆኑና ይህም የተቀናጀ ሴራ ውጤት ሊሆን ይችላል ብዬ መጠርጠሬ ነው።
«ማጋለጥ፣ ማስተጓጎል፣ ተአማኒነት ማሳጣት፣ ዝም ማሰኘት አሊያም ማጥፋት» ~ በወቅቱ የኤፍቢአይ ዳይሬክተር – ኤድጋር ሁቨር ለአንድ የኤፍቢአይ ኤጀንት የተሰጠ ትዕዛዝ ነው።
በዚህ መንገድ፣ ኤፍቢአይ በከፊልም ቢሆን የጥቁሮች የዕኩል መብት ጥያቄን፣ የፀረ-ቪየትናም ጦርነት እንቅስቃሴን እና ፀረ-ቅኝ ግዛት ድርጅቶችን አዳክሟል። በማልኮም ኤክስ እና በኤልያስ መሐመድ መካከል ያለውን አለመግባባት ኤፍቢአይ ማልኮም እንዲገደል በማድረግ ፕሮግራሙን ተጠቅሞበታል የሚሉ አሉ፤ ባይጠቀምበት እንኳ መረጃው እየደረሰው ዝም ብሏል።
በተመራማሪዎች እንደተሰበሰው ከሆነ፣ ኮኢንቴልፕሮ በመንግሥት ያልተፈለጉ እንቅስቃሴዎችን እና ድርጅቶችን የሚያስተጓጉልበት የተለያዩ ተግባራት (functions) እና ቅርፆች (forms) አሉት። ዴቪድ ካኒንንግሃም የዘረዘሩትን እነሆ፣
ተግባራት፣
1) መጥፎ ገፅታ መስጠት፤
2) ውስጣዊ አደረጃጀትን መሰባበር፤
3) በቡድኖች መካከል የርስበርስ ቅራኔ መፍጠር፤
4) ቡድኑ ለእንቅስቃሴው የሚረዱት ነገሮችን እንዳያገኝ መገደብ፤
5) የመቃወም አቅምን መገደብ፤
6) የተመረጡ ግለሰቦች እንቅስቃሴውን እንዳይቀላቀሉ ማድረግ፤
7) ግጭቶችን ማስቀየስ፤ እና
8) ስለላ ናቸው።
ቅርፆች
A) ምንጫቸው ያልታወቁ ደብዳቤዎች መላክ፤
B) በውሸት ማሕተም የተፈረመባቸውን ደብዳቤዎች መላክ፤
C) መጣጥፎችን ለብዙኃን መላክ፤
D) ለባለሥልጣናት መረጃ መስጠት፤
E) የውሸት ማስረጃ መቅበር፤
F) መረጃ ሰጪዎች መመልመል፤
G) ሚዲያዎችን መጠቀም፤
H) ኤፍቢአይ ያዘጋጃቸውን መረጃዎች ማሰራጨት፤
I) ለተመረጡ ሰዎች ቃለመጠይቅ ማድረግ፤
J) የተሳሳተ መረጃ መስጠት፤
K) የውሸት የስልክ ጥሪዎችን ማድረግ፤
L) ያለማቋረጥ ክትትልና ጥቃት ማድረግ፤
M) ለተቀናቃኞቻቸው ድጋፍ መስጠት፤ እና
N) ሥም አጥፊ መረጃዎችን መላክ።
(እነዚህ ሁሉ ተቃዋሚዎችን የማስተጓጎል ሙከራዎች በኢትዮጵያ ታይተዋል።)
የዚህ አጭር ማስታወሻ ዓላማ ዴሞክራሲያዊ የሆኑት አገሮች ሳይቀሩ ምን ያህል ተቀናቃኞቻቸውን ለማጥፋት እንደሚጓዙ ማስረዳት ነው። ኮኢንቴልፕሮ ከኤፕሪል 1971 ጀምሮ፣ በተግባር 15 ዓመት ከቆየ በኋላ፣ በይፋ ተዘግቷል። ነገር ግን፣ እንደኢትዮጵያ ላሉት ጨቋኝ መንግሥታት ትምህርት ሰጥቶ አልፏል። የፖለቲካ ፓርቲዎች እና አክቲቪስቶች መንግሥታቸው እነዚህን ሴራዎች እንደሚሸርብባቸው አውቀው ግብረመልስ ካዘጋጁ [ብቻ] በትግሉ ያሸንፋሉ።
ፓትርያርኩ፡- ለኢትዮጵያ የደኅንነት፣ ለምእመናን የድኅነት ሥጋት
ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

‹የክርስቶስ አንዲት በግ መከራን ስትቀበል ከማይ እኔ የበጉ እረኛ መከራ መቀበልን እመርጣለሁ›
ይህንን የተናገረው ዮሐንስ አፈወርቅ ነበር፡፡ የቁስጥንጥንያዋ ንግሥት አውዶቅስያ የአንዲት ክርስቲያን ምእመንን መሬት ወስዳ ባሰቃየቻት ጊዜ ለተግሣጽ የተናገረው ነው፡፡ እንዳለው አልቀረም አውዶቅስያ ባደረሰችበት መከራ ተግዞ በዚያው ሞትን ተቀብሏል፡፡ እውነተኛ አባት ስለ በጎቹ ራሱን አሳልፎ ይሰጣል እንጂ በጎቹን ለራሱ ክብርና ጥቅም ሲል አሳልፎ አይሰጥም፡፡ ፓትርያርክ ማለት በግሪክ ‹ታላቅ አባት› ማለት ነው፡፡ የታላቅ አባት ተግባር የልጆቹን ሥራ ማፍረስ አይደለም፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፤ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን መክሰስ አይደለም፤ ለዚህማ ሰይጣን እንጂ አባት አያስፈልግም፡፤ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን ጠርቶ መውቀስ እንጂ በር መዝጋት አይደለም፤ ለዚህማ አባት አያስፈልግም ሰይጣን እንጂ፡፡ የታላቅ አባት ሥራ ልጆቹን ማቀፍ እንጂ ማባረር አይደለም፤ ለዚህማ ሰይጣን አለ፡፡
ፓትርያርኩ እንጨት የሚሸጡ እናቶች ካወጡት የእንጦጦ ኪዳነ ምሕረት ገንዘብ ግማሽ ሚሊዮን ብር እንደዋዛ በአንድ ሙሰኛ ሲነጠቅ ተኝተዋል፤ በመሐል ከተማ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የተሠሩ ሕንጻዎች በጎጆ ቤት ዋጋ በሙስና ለዐሠርት ዓመታት ሲከራዩ ተኝተዋል፤ ከመንበረ ፕትርክናቸው ሥር ባለች አጥቢያ የቤተ ክርስቲንን ገንዘብ አናስበላም ያሉ ካህናትና ምእመናን ሲባረሩ ተኝተዋል፡፡ በሕዝብ ጥያቄ ሽፋን ጽንፈኛ አቋምን በሚያራምዱ ሰዎች አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ ይተኛሉ፤ የስልጤ ዞን ምእመናን በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ እየተቀበልን ነው ሲሉ ይተኛሉ፤ ቤተ ክህነቱ የኑፋቄ ማኅደር ሲሆን ይተኛሉ፤ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ሲዘጉ፣ ገዳማትና አድባራት ሲፈርሱ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች ሲበተኑ ይተኛሉ፤ በመሥዋዕትነት የተመሠረቱት የደቡብ አፍሪካ አብያት ክርስቲያናት በሙሰኛ አመራሮች አደጋ ላይ ሲወድቁ ይተኛሉ፣ ይሄ ሁሉ ዘለፋና ኑፋቄ በቤተ ክርስቲያን ላይ ሲዘንብ ይተኛሉ፡፡
መናፍቃንን የሚተች ጽሑፍ በኦርቶዶሳውያን ተጻፈ ሲሏቸው፤ ምእመናንን የሚያጸና ጉባኤ ሊዘጋጅ ነው ሲሏቸው፤ ሕዝቡ ወደ ቤተ ክርስቲያን እየመጣ ነው ሲሏቸው፤ ወጣቱ ትውልድ ቤተ ክርስቲያኑን ለማገልገል እየተጋ ነው ሲሏቸው፤ ዲያስጶራው ሕዝብ በእናት ቤተ ክርስቲያን ሥር ሆነ ሲሏቸው፤ ቤተ ክርስቲያንን የሚገልጥ ዐውደ ርእይ ሊዘጋጅ ነው ሲሏቸው፤ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን ፕሮግራም ሊቀርብ ነው ሲሏቸው ያን ጊዜ ብዕራቸውን ይዘው ለማገድና ለመክሰስ ይነቃሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ‹ድንግል ሆይ የአንቺን ምስጋና ለመጻፍ ምንጊዜም ብእሬ ቀለም እንደያዘ ነው› ነበር ያለው፡፡ የፓትርያርኩ ብእር ግን ምእመናንን የሚያጽናና ጦማር ለመጻፍ ወይም ድንግልን የሚያመሰግን ድርሳን ለመድረስ የሚጨበጥ አይደለም፡፡ እንደ ጠንቋይ ብዕር ለማፍዘዝና ለማደንገዝ እንጂ፡፡
የፓትርያርክ ዋናው ሥራው የሀገር ደኅንነት እንዲጠበቅ ‹ዕቀብ ሕዝባ ወሠራዊታ ለሀገሪትነ ኢትዮጵያ› እያለ መጸለይ፤ የምእመናን ድኅነት እንዲረጋገጥም ሃይማኖት ማስተማር፣ በጎችን መሠማራትና ቀኖናን መጠበቅ ነበረ፡፡ ለቅዱስ ጴጥሮስ ‹በጎቼን ጠብቅ፣ አሠማራ› ነበር የተባለው፡፡ መጠበቅ- ከክህደት፣ ከኑፋቄ፣ ከኃጢአት ከበደል፤ ማሠማራት – በትምህርት፣ በምግባር፣ በትሩፋት፣ በአገልግሎት፣ በጽድቅ መስክ ላይ፡፡

‹ባለሞያ ሴት የሠፋችውን ወራንታ፣ ጅል ትተረትረዋለች› እንደተባለው በደኅና ጊዜ ትጉኃን አበው የሰበሰቧቸውን ወጣቶች ካልበተንኩ ብሎ እንዴት አንድ ፓትርያርክ ይነሣል፡፡ ወጣቶቹ ሊሳሳቱ፣ ሊያጠፉም ይችላሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ግን ለዚህም መንገድ ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ የመንግሥት ባለ ሥልጣናት ሳይቀሩ የገዛ ልጆችዎን ያወያዩ ሲሏቸው በራቸውን ጠርቅመው የሚዘጉ ፓትርያርክ በታሪክ የሚጀመሪያው መሆን አለባቸው፡፡ በሱራፊ ነበልባል የተዘጋች ገነት ስትከፈት በፓትርያርክ የተዘጋች የቤተ ክህነት በር ልትከፈት አልቻለችም፡፡ ሰይጣንን ከእግዚአብሔር ጋር ለማነጋገር የደከሙ እነ ክርስቶስ ሠምራን የመሰሉ ቅዱሳን ባሉባት ቤተ ክርስቲያን እረኛው ከመንጋው ጋር መነጋገር አቃተው፡፡ ኢየሱሳውያንን በዐደባባይ ሳናነጋግራቸው መሄድ የለባቸውም ብለው የተሟገቱ እነ እጨጌ በትረ ጊዮርጊስ በነበሩባት ቤተ ክርስቲያን የገዛ ልጆቹን ለማነጋገር በር የሚዘጋ እጨጌ ተፈጠረ፡፡ የመካ ቁራይሾችን አሳልፈን ለጠላቶቻቸው አንሰጥም የሚሉ አበው በነበሩባት ቤተ ክርስቲያን የገዛ ልጆቹን አሳልፎ የሚሰጥ አባት መጣ፡፡
የኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናት በ1972 እኤአ ካይሮ ላይ ባደረጉት ጉባኤ ከተስማሙባቸው ነገሮች አንዱ የኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት ተልዕኮ ነበረ፡፡ እንዲህ ይላል ‹ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳት አምስት ተልዕኮ አላቸው፡፡ እነዚህም
1. ወንጌልን መስበክ(Preach the Gospel)
2. ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መፈጸም(Administer the Sacraments of the Gospel.)
3. የቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ አንድነትና ቀኖና መጠበቅ(Guard the faith, unity, and discipline of the church.)
4. ለካህናትና ለምእመናን የቅድስና ምሳሌ መሆን(Be a moral example of holiness and wholesomeness.)
5. በእረኛውና በበጎች መካከል ያለውን ክፍተት ማጠበብ(Diminish the distance between bishops and their flock.)
ለመሆኑ የእኛ አባት የቱን ነው እየፈጸሙ ያሉት? ወይስ ከኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር ውጭ ሆነናል?
ዐውደ ርእዩ የማይደረግበት በቂ ምክንያት ከነበረ ቢያንስ ከሳምንት በፊት መግለጥ ይቻል ነበር፡፡ ዓላማው ግን ማበሳጨት፣ ዐመጽ ማስነሣት፣ ተሥፋ ማስቆረጥና ምእመናንን ወደማይፈልጉት መሥመር መውሰድ ነው፡፡ ለዚህ ነው ፈያታዊ ዘየማን ገነት በገባባት ሰዓት ዐውደ ርእዩ እንዲዘጋ የተደረገው፡፡ የዚህች ሀገር ሰላም አይፈለገም? ምእመናን ሀገር እንደሌላቸውና መብት እንደሌላቸው ራሳቸውን እንዲቆጥሩ ይፈለጋል? ‹ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል› እንዲል ሀገሪቱ ያለባት ችግር አይበቃትም? ተጨማሪ ችግር ማምረት ይፈለጋል?
ችግሩ ሁሉ እየተፈጠረ ያለው በመንግሥት ስም ነው፡፡ ‹መንግሥት አዞናል፤ እገሌ የተባለ ባለ ሥልጣን ብሎናል፤ ፖሊስ እንጠራለን፤ ደኅንነት እናዛለን› ነው በቤተ ክህነቱ ዘንድ የሚባለው፡፡ እውነት መንግሥት በስሙ የሚሠራውን ያውቀዋል፤ ካወቀውስ ዝም ይላል? ቤተ ክህነቱ በሚያመጣው ዳፋ መከራ ለመቀበልስ ዝግጁ ነው? ይህ አካሄድስ ለሀገሪቱ ደኅንነት የሚበጅ ነው? ዐውደ ርእዩ እንዲዘጋ ያዘዘውስ የትኛው መንግሥት ነው? አንዱ የሚፈቅድ ሌላው የሚዘጋ ስንት መንግሥት ነው ያለው? ወይስ ‹ደብዳቤ መጻፉ አላዋጣምና ዝጋልኝ› ተብሎ እጅ የተሰነዘረለት አካል ያደረገው ነው? መጽሐፉ እንደሚል ‹የማይገለጥ የተሠወረ› አይኖርምና ዐውቀነዋልም፣ እናውቀዋለንም፡፡
የገዛ ፓትርያርካችን ለእኛ ለምእመናን ድኅነትን እንዳናገኝ ሥጋት ሆነውብናል፡፡ የታገሡትን ሁሉ ለክፋት በማነሣሣት ደግሞ ለሀገሪቱ ደኅንነት ሥጋት እየሆኑ ነው፡፡ የምእመናኑን ሥጋት ሲኖዶሱ፤ የሀገሪቱንም ሥጋት መንግሥቱ ሊያስቡበት ይገባል፡፡ ከቤተ መቅደስ የተነሣ ችግር መጀመሪያው እንጂ መጨረሻው አይታወቅምና፡፡ እንዲህ ያሉ ነገሮች የምእመኑን የአስተሳሰብ ቅርጽ ይቀይራሉ፡፡ የሐበሻን ሥነ ልቡና ለሚረዳ ደግሞ ሲረገጥ እንደሚጠክር ጭቃ ያጠነክራሉ፡፡ ሲሞረድ እንደሚሳል ቢላዋ፣ ሲቀረጽ እንደሚሾል እርሳስ ያደርጋሉ፡፡
በዐውደ ርእዩ የሚማሩት የሚያዩት ብቻ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ያላዩትም እንዲማሩ አድርገዋል፡፡ ሐሳብና ርእዮት ሊያስተባብረው የማይችለውን ተጠቂነት ያስተባብረዋል፡፡ ተጠቂነት ክርክርና ውይይት፣ ማስረጃና መረጃ አይጠይቅም፡፡ መጠቃቱን ያወቀ ሁሉ ራሱ ገብቶት ይተባበራልና፡፡ ምናልባትም ምእመናንን ከገድል ተራኪነት ወደ ገድል ሠሪነት ያሻግራቸው ይሆናል፡፡ ‹እዚያም ቤት እሳት አለ› አሉ አለቃ፡፡
እንደ ሶምሶን ከአንበሳ ሬሳ ማር ለማውጣት ግን በሳል አመራር ይጠይቃል፡፡ የማኅበሩ አመራርም ቢሆን ጊዜውን አይቶ የሚሣለጥ አመራር እንጂ የተቸከለ አመራር መሆን የለበትም፡፡ የፓትርያርክ ማትያስ ዘመን እንደ ፓትርያርክ ጳውሎስ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምም ዘመን እንደ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ አይደለም፡፡ አሁን የሆነው ነገር ሊሆን እንደሚችል ቀድሞ እየታወቀ ከግንቡ ጋር እስኪጋጩ ድረስ ቆሞ መጠበቅ ብልህነት አይደለም፡፡ አሁንም ‹እገሌ የተባለ ባለሥልጣንን አናግረናል፤ እገሌ የተባሉ አባት አይዟችሁ ብለውናል› እያሉ መጓዝ የሚያዋጣ አይደለም፡፡ ለጉባኤ ተሰብስቦ ‹ ለፓትርያርኩ የተጻፈው ደብዳቤ አንጀት አርስ ነው› ብሎ አጨብጭቦ የሚበተን አመራር ጊዜው ሊያልፍበት ይገባል፡፡ ከዲሚትሪ ሆቴል እስከ ፌዴራል ጉዳዮች የተደረጉትን ውይይቶች ገምግሞ አዲስ አቅጣጫ መያዝ ይገባ ነበር፡፡ የሚሰበሰብ ብቻ ሳይሆን የሚተነብይ አመራርም ያስፈልጋል፤ ካልሆነ ግን
‹ከክምር ድንጋይ ላይ ይበቅላል ደደኾ
የፈራሁት ነገር መጣ ድኾ ድኾ› የተባለው ይደርሳል፡፡
በኮንሶ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ሁለት ሰዎቸ ተገደሉ
በደቡብ ክልል ከዚህ ቀደም በልዩ ወረዳ አስተዳደር የነበረና በአሁን ወቅት የሰገን አካባቢ ዞን ስር ወደ ወረዳ አስተዳደርነት እንዲወረድ የተደረገው የኮንሶ ማኀበረሰብ አባላት የዞን አስተዳደር መዋቅር እንዲፈቀድላቸው መጠየካቸውን ተክትሎ በመንግሥት ተጣቂዎች በተወሰደ እርምጃ በግብርና የሚተዳደሩ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል፡፡
እሁድ መጋቢት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀትር ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት አቶ ሞሌ አዛዥ እና አቶ ፋንታዬ ጊዮርጊስ በግብርና ሙያ የሚተዳደሩ ጎልማሶች እንደሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከተገደሉት በተጨማሪ 3 ሰዎች በፀኑ የቆሰሉ ሲሆን፤ ማኀበረሰቡም የተገደሉ 2 አስከሬኖች ይዞ ወደ ካራት አደባባይ በመውጣት ከፍተኛ ተቃውሞ ማሰማቱ ታውቋል፡፡

የአዲስ ሚዲያ መረጃዎች እንዳረጋገጡት፤ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አሁንም በኮንሶ በርካታ የደቡብ ልዩ ፖሊስ ኃይል የደንብ ልብስ የለበሱ ፖሊሶች በኮንሶ ዋና ከተማ ካራት እና በተለያዩ የገጠር ቀበሌዎች ጭምር እንደሰፈሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የህዝባዊ ተቃውሞ ዋነኛ ምክንያት 55ሺህ የኮንሶ ማኀበረሰብ ስምና ፊርማ ያለበት ስምምነት ወደ ዞን አስተዳደር እንደግ የሚል ጥያቄ ከደቡብ ክልል እስከ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማስገባታቸውና መንግሥትም በሐረገ-መንግሥቱ መሰረት ተገቢውን መልስ ሳይሰጥ ከልዩ ወረዳነት ወደወረዳነት በማውረድ ጥያቄያቸው ምላሽ ባለማግኘቱ በተፈጠረ አለመግባባት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ተቃውሞንም ተከትሎ የኮንሶ ባህላዊ ንጉስ ካላ ገዛኸኝ ወልደ ዳዊትን ጨምሮ ከ200 ያላነሱ የአካባቢው ዜጎች መታሰራቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥት የሰጠው ይፋዊ ምላሽ ባይኖርም በአካባው ከፍተና ውጥረት መኖሩን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የደረሰውን የሰብዓዊ ጉዳት አስመልክቶ በ33 ወረዳዎች ብቻ 103 ዜጎች መገደላቸውን የሚገልፅ ገለልተኛ የምርመራ ሪፖርት ይፋ ሆነ

ከህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ተጀምሮ በነበረው እና መላው ኦሮሚያ ክልልን ያዳረሰው ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ የደረሰው ሰብዓዊ ጉዳት ልዩ የምርመራ ሪፖርት መግለጫ ይፋ ሆነ፡፡ ልዩ መግለጫው ይፋ የሆነው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሰመጉ ዋና ጽህፈት ቤት ሲሆን፤ መግለጫውም የ103 ዜጎች ህይወት መጥፋቱን አስታውቋል፡፡
ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ይባል የነበረውና በኋላም የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ(ሰመጉ) እየተባለ የሚጠራው ብቸኛው ሀገር በቀል መነግሥታዊ ያልሆነ ገለልተኛ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት ሲሆን፤ ባለፉት አራት ወራት በተጀመረውና እስካሁንም በቀጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ የሰብዓዊ ጉዳት ቀዳሚውን ልዩ መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡ ሰመጉ በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም ጠቁሟል፡፡

ሰመጉ 34 ገፅ ባለው ልዩ መግለጫው እንዳስታወቀው ከሆነ፤ የደረሰው የሰብዓዊ ጉዳት ምርመራ የሚያካትተው ከህዳር 2 ቀን እስከ የካቲት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሱ የሰብዓዊ ጉዳቶች ብቻ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በተለይ በምርመራ ወቅት ድርጅቱ የጋጠሙትን ችግሮችም የጠቀሰ ሲሆን በተለይም የገንዘብ ፣ የሰው ኃይልና የምርመራ መሳሪያ እጥረት፣ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ሁኔታ ውጥረት የተሞላበት በመሆኑ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተው ቀውስ እንደልብ ተዘዋውሮ ለመስራት አለመቻል፣የመንግሥት የደህንነት እና የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ጫና እና ክትትል ማድረጋቸው፣ ሕዝቡ ከፍተኛ ፍርሃት ውስጥ በመግባት ማንንም ሰው አለማመን እና መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆን ዋነኞቹ መሆናቸው ጠቅሷል፡፡
በክልሉ አሁንም በተለያዩ ቦታዎች ተቃውሞች መቀጠላቸውንም በመጥቀስ፣ ማንኛውም የሰብዓዊ መብት የሚመለከተው አካል የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን ሰብዓዊ መብት እንዲያከብር፣ እንዲያስከብርና እንዲያስጠበቅ ጫና እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡
ሙሉ መግለጫውን ከዚህ ቀጥሎ ያለውን መስፈንጠሪያ (ሊንክ) በመጠቀም ያገኙታል፡- http://ehrco.org/wp-content/uploads/2016/03/The-Human-Rights-Council-HRCO-140th-Special-Report-Amharic-Scanned-March-14-2016.pdf
የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ…
ከዚህ ቀደም በቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት የነበሩና ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የትግራይ ክልል ስር ያሉት የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ “እኛ አማራ ነን፣ ያለፈቃዳችን ተገደን ነው ወደ ትግራይ የተካለልነው፣ የአማራ ማንነት ጥያቄያችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አማራ እንጠቃለል” የሚል ጥያቄን ቢያነሱም፤ ከመንግሥት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ አባላት ተገደው ያለፈቃዳቸው ወደ ትግራይ እንድንጠቃለል ተደርገናል ከሚለው ጥያቄ በተጨማሪ አማራ በመሆናችን ብቻ በትግራይ ክልል አስተዳደር ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብና፤እየተፈፀመብንም ይገኛል በማለት የቀደመው የአማራ ማንነታችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አስተዳደር አማራ ክልል ለመጠቃለል አንዱ ምክንያታቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ይስተዋላል፡፡

እንደ ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴዎች አገላለፅ፤የነበረው የወልቃይት ጠገዴ አስተዳደር ወሰን ክልልም በሰሜን ተከዜ ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ ኤርትራ፣ በምስራቅ የቀድሞው ትግራይ ጠቅላይ ግዛት ፣ በምዕራብ ሱዳን በደቡብ የቀድሞው ቤጌምድር (የአሁኑ ጎንደር) አስተዳደር አካል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አካባቢውም በአሁን ወቅት በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በሚል አስተዳደር ስር በ3 ወረዳዎች የተዋቀሩት ቃፍታ ሁመራ፣ ወልቃይት እና ጠገዴ ወረዳዎች በቀድሞ ቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት ወልቃይት ጠገዴ አውራጃ አስተዳደር እንደነበርም ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ቀደምት የአስተዳደር ሰነዶችን እና የአማራ ማንነትን ያረጋግጣሉ የሚሏቸው መረጃዎችን አያይዘው በሕገ-መንግሥቱ መሰረት ጥያቄ ቢያቀርቡም ከሚመለከተው አካል እስካሁንም ምላሽ አለማግኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
በተለይ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ ተወካዮች የአማራ ማንነት ጥያቄ ይዘው ላለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ ጥያቄ ያቀርቡ እንደነበር እንደሚያውቁ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲአዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አስታውሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ይህን ያስታወሱት ባለፈው ከኦሮሚያ እና በሌሎች ሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ በተያያዘ መድረክ በዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ላይ ነበር፡፡
የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላቱም በተለያየ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ከሆነ፤ አማራ ሆነው ሳለ ሳይወዱ በግድ ወደ ትግራይ መጠቃለላቸውን፣ ልጆቻቸውም ከአፍ መፍቻ አማርኛ ውጭ ተገደው በትግርኛ እንዲማሩ መደረጉን፣ የአካባቢው ህዝብ ከአማርኛ በተጨማሪ አረብኛ እና ትግርኛም ባላቸው የድንበር ግንኙነት አማካኝነት መናገር ቢችሉም፤ ባህላቸውን እና ማንነታቸውን የሚገልፁበት ቋንቋ አማርኛ መሆኑን እና የማንነት ስነ ልቦናቸውም አማራ እንደሆነ፤ ይህንንም ላለፉት 25 ዓመታት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማት ጥያቄ ሲያነሱ ግድያ፣ እስራት፣ ድብደባ፣ ማስፈራራትና ስደት እንደደረሰባቸው፣ ከጥያቄው ጋር በተያያዘ የትግራይ ክልል መስተዳደር ግድያን ጨምሮ የተለያዩ በደሎችንም ይፈፅም እንደነበርና አሁንም እየፈፀመ እንደሆነ ሲያነሱ ይደመጣል፡፡
የአማራ ማንነት ፈቃዳችን ሳይጠየቅ ተገደን እንድንጠቃለል ተደርገናል ለሚሉት የትግራይ ክልል መስተደዳደርና በፌደራሉ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄን የሚያቀርቡ ተወካዮች በአዲስ አበባም ለተወሰኑ ቀናት በፖሊስና ደህንነት አባላት ታግተው መለቀቃቸው የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን ጨምሮ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን የተዘገበ ሲሆን፤ በተለይ የትግራይ ክልል አስተዳደርና እና የክልሉ ምዕራባዊ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎች አሁንም ከፍተኛ ማስፈራሪያ እና ዛቻ እየፈፀሙ መሆኑን የኮሚቴው አባላት ገልፀዋል፡፡ አዲሱን የአስተዳደር ክልል መዋቅር የመሰረተው ኢህአዴግ መንግሥት እና የትግራይ ክልል መስተዳደር ቀድሞ የነበረውን የአማራ ስነ ህዝብ ስብጥር፣ ባህል እና ማንነትን ለማጥፋትና መቀየር ላለፉት 25 ዓመታት ሙሉ ሲሰሩ ተቃውሞ ብናቀርብም ሰሚም አላገኘንም፣ እንደወንጀለኛም ተቆጥረናል ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ከዛ በተጨማሪ የእኛ የአማራ ማንነት እንደሌለ ተቆጥሮና ተክዶ ልጆቻችን በአማርኛ እንዳይማሩና እንዳይናገሩ፣ በአማራ ማንነታቸው እንዲያፍሩና የነበረውን የአማራ ማንነት ባህል እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ በግድም የትግርኛ ቋንቋ እንዲነገሩ፣ የትግራይ ማንነት ባህልን ብቻም እንዲያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ይህም ህገ-መንግሥቱን እንደሚፃረር ብናነገርም የከፉ በደሎች ተፈፅመውብናል ይላሉ፡፡
በተለይ አካባቢውን በተመለከተ በአጼ ኃይለስላሴ ዘመን የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩትና የአጼ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል መንገሻ ስዩም ወልቃይት ጠገዴ በሳቸው ዘመንም ሆነ ከዛ በፊት ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ አስተዳደር ስር እንዳልነበር እንደሚያውቁ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ገልፀው ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሃላፊ በኩላቸው ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ እንደሆነ እና ከዛ ጋ ተያይዞ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ የህዝቡ እንዳልሆነ ከመግለፃቸው በተጨማሪ የአማራ ማንነት ጥያቄ የሚያነሱ ተወካዮች የሚቃወም ሰልፍም በአካባቢው ተደርጎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአማራ ማንነት ጥያቄን ለሚያነሱ ማኀበረሰብ አባላትና ተወካዮች ጥያቄያቸው መፍትሄ አሊያም ህዝባዊ ውሳኔ ያገኝ ዘንድ ባሉበት ወልቃይት ጠገዴ ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፍ ቢጠይቁም በትግራይ ክልልም ሆነ በክልሉ ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሊፈቀድ ባለመቻሉ የማኀበረሰቡ ተወካዮች ህዝባዊ ስብሰባዎቻቸውን በአጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች ለማድረግ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለ ኦሮሚያው ተቃውሞ እና ስለ ጎንደር የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ቢገልፁም፤ ስለ ወልቃይ ጠገዴ አማራ ማንነት ጥቄን ግን ሳያነሱት ከማለፋቸው በተጨማሪ በጥቅሉ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንነት ጋር በተያያዘ ያልተመለሰ ጥያቄ የለም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ አዲስ ሚዲያ ባለው መረጃ መሰረት የብሔረሰብ ማንነት እና የራስ አስተዳደር ጋ በተያያዘ በትግራይ ወልቃይት ጠገዴን እና በኣማራ ክልል ምላሽ አግኝቷል ከተባለው የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጥያቄ በተጨማሪ በኦሮሚያ፣ በደቡብ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ከክልሎቹ እስከ አዲስ አበባው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ እስካሁንም ምላሽ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡