Category Archives: Social and Culture

ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸውን ታስረው ጨለማ ክፍል መታሰራቸው ተገለፀ

-ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ጠያቂ ተከልክሏል

የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ

የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ

የቀድሞው የጋንቤላ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸው ታስሮ ጨለማ ክፍል መታሰራቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡

አቶ ኦኬሎ ቂሊንጦ በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወስ ሲሆን፣ ሰውዬው ከሰሞኑ የርሃብ አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ በእስር በሚገኙበት እስር ቤት እጅና እግራቸውን ታስረው ብቻቸውን ጨለማ ክፍል እንዲገቡ እንደተደረጉ ምንጮች ተናግረዋል፡፡

ዛሬ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም ወደ ቂሊጦ ማረሚያ ቤት እስረኞችን ሊጠይቁ ሄደው እንደነበር የገለጹት ምንጮች፣ እዚያው በእስር ላይ ካሉ ሰዎች አቶ ኦኬሎ ያሉበትን ሁኔታ መረዳታቸውን አክለው ገልፀዋል፡፡

በሌላ በኩል የ18 አመት እስር ፍርደኛው ታዋቂው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ሌላ ሰው መጠየቅ እንደተከለከለ የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡

አንድነት ፓርቲ በአንድ ወር ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠራ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠራ፡፡ ፓርቲው ነገ እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ በድጋሚ እንዲጠራ የተገደደው ገለልተኛ እንዳልሆነ ተደጋጋሚ ቅሬታዎች የቀረቡበትና እየቀረቡበት ያለው ምርጫ ቦርድ ባደረገበት ጫና መሆኑን በመግለጫው አስታውቋል፡፡

በተለይ በአሁን ወቅት በርካታ አመራሮቹና አባሎች የታሰሩበት አንድነት ፓርቲ፤ የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ላይ ለመሳተፍ መወሰኑን እና በመላ ሀገሪቱም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን ማዘጋጀቱንና ምርጫውንም በአሸናፊነት ለመወጣት ህዝቡን “2007 ለለውጥ ተደራጅ” በሚል መርህ ሰፊ ሀገራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ አንድነት ፓርቲ፣ ከኢህአዴግና ከምርጫ ቦርድ ጋር ባለው የፖለቲካ እንቅስቃሴ ከቀድሞ በበለጠ እየተካረረ መሄዱን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ አውጥቷል፡፡ የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካዊ ደባ አንድነት ከመስመር አይወጣም!
*******************************************************************************

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
በየትኛውም የአለም ክፍል በተለያየ አጣራርና ስያሜ ቢሰጣቸውም ምርጫን ለማስፈፀም በሕግ የሚቋቋሙ ተቋማት ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ተቋማት በአንድ ሀገር ዘላቂ ለሆነ ሠላምና መረጋጋት ብሎም ለዴሞክራሲዊ ስርዓት ግንባታ ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ በአንባገነን ስርዓት ውስጥ ላሉ ሀገሮች ደግሞ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ያላቸው ሚና ከምንም በላይ ከፍተኛ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራው ምርጫ ቦርድ ይህን የመሰለ ግዙፍ ተግባር እንዲያከናውን፣ የሕዝብ እና የሀገር አደራ እንዲወጣ ኃላፊነት የተሰጠው ተቋም ነው፡፡ የዚህ ተቋም አሰራር በተቋቋመለት ዓላማ፣ ሕግ እና አለም አቀፍ መስፈርት መሠረት ነፃ፣ ገለልተኛ፣ ዴሞክራሲያዊ እና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀደሙት አሠራሮችና ውሳኔ አሰጣጦች በበርካታ ኢትዮጵያውያን እና አለም አቀፍ ታዛቢዎች በአሉታዊ ጎኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የ2ዐዐ7 ሀገር አቀፍ ምርጫን ‹‹የኢህአዴግ መጨረሻ›› እናደርገዋልን ብሎ ፖለቲካዊ አቋም ወስዶ እንቅስቃሴ ሲጀምር የምርጫ ቦርድን ቀደምት አሉታዊ ተግባሩን ዘንግቶ አይደለም፡፡ ይህ ተቋም መልካም ስም እንዲገነባ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በመሆን እድል ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህ ስትራቴጂ መሠረት ቦርዱን በተግባር ፈተና ላይ ጥለነዋል፣ ማንነቱንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ለዓለም ማህበረሰብ በማጋለጥ ላይ እንገኛለን፣ ዛሬ ለሁለም የሚዲያ አካላት ያካሄድናቸውን የደብዳቤ ልውውጦች በይፋ አንሰጣለን፣ ሁሉም ዜጋ እንዲደርሰውም እናደርጋለን፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከ2ዐዐ7 አጠቃላይ ምርጫ ገፍቶ ለማስወጣት ካልተሳካለትም በተዳከመ የአባላትና ደጋፊ ስሜት ውስጥ ገብተን እንድንጫወት የፈለገ ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የአንድነት ፓርቲ በ2ዐዐ7 ዓም ሀገራዊ ምርጫ ከጅምሩ በሁሉም ሂደቶች በንቁ ለመሳተፍ የያዘው አቋም እንዳስደነገጠው፤ ከዚያም አልፎ ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠውን ስልጣን አጣለሁ በሚል መሸበሩን የሚያጋልጥ ነው፡፡ ይህን ፍርሃቱን በህዝብ ፊት በሚደረግ ትግል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ የመረጠው ሜዳ በብሔራዊ ምርጫ ቦርደ በኩል እንዲሆን ነው፡፡ የቦርዱ ኃላፊዎች ተቋማዊ በሆነ መልክ ደብዳቤ ሲሰጣቸው፣ በደብዳቤ መልስ ከመስጠት ይልቅ በመገናኛ ብዙሃን ምላሻቸውን ቀድመው መናገር ጀምረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያው ታህሣሥ 27 ቀን 2ዐዐ7 ዓም የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዝአብሔር ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ ወጥተው ውሳኔ በመገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ቦርዱ እንደተቋም ሳይሆን በግለሰብ ውሳኔ የሚመራ መሆኑን ነው፡፡ ለዚህም መገለጫው በታህሳስ 30/2007 የደረሰን ደብዳቤ የቦርዱን ምክትል ስብሳቢ ከሚዲያ መግለጫ ጋር ተመሳሳይ መሆኑ ነው፡፡ ከምርጫ ቦርድ ባልተናነሰ ሁኔታ በኢትዮጵያ በህግ የተቋቋሙት እና በህዝብ ሀብት የሚንቀሳቀሱት የመገናኛ ብዙሃንም በፍጥነት ተቀብለው ማስተጋባታቸው በውዥንብር ፈጠራ ላይ ተሳታፊነታቸውን ያሳያል፡፡ ዓላማው በአባላት፣ በደጋፊና በህዝቡ ውስጥ ውዥንብር ለመፍጠር ታሰቦ የሚካሄድ ፖለቲካዊ ደባ ነው፡፡

በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እና ዘላቂነት ያለው ደህንነት የሚያረጋግጠው እንደ ምርጫ ቦርድ ያሉ ተቋሞች ነፃ፣ ገለልተኛ እና በህዝብ ዘንድ አመኔታ ሲጣልባቸው ነው፡፡ ይህ ተቋም አሁን በያዘው ሁኔታ ከቀጠለ ከታሪክ ተጠያቂነት አይድንም፡፡ ገዢው ፓርቲም ጧት ማታ የሚያባንነው ሕዝባዊ እምቢተኝነት መምጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ በመሆኑም አሁን ፓርቲያችንን ለመታደግ እና የቦርዱን የመጨረሻ ካርድ ለማስጣል አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለ2ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተናል፡፡ ይህ ማለት የትግሉ መጨረሻ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያደረሰብንን የሕግ ጥሰት ይዘን በፍርድ ቤት ክስ እንመሰርታለን፡፡ እስከ አሁን ያለውን ሂደት ስናየው የቦርዱ ፖለቲካዊ ደባ ቀጣይ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ስለሆነም መላው አባሎቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ለምንወስዳቸው ተከታታይ ፖለቲካው ውሳኔዎች እና እርምጃዎች ከጎናችን እንዲቆም ጥሪያችንን በአክብሮት እናስተላልፋለን፡፡

ድል የሕዝብ ነው
ጥር 1 ቀን 2ዐዐ7 ዓም
አዲስ አበባ

አባቶችና ምእመናን ‹‹ሸኚው ሸኚ ሲያጣ›› እስኪሉ ድረስ በመጣደፉ በእጅጉ ያዘኑበት የ106 ዓመት አረጋዊው የአቡነ አረጋዊ ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ

ዜና ሕይወቱ ወዕረፍቱ ለብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሊቀ ጳጳስ

ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ

ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ

ብፁዕ አቡነ አረጋዊ በ1901 ዓ.ም. በፀለምት (ሰሜን ጎንደር) ተወልደው ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ ትምህርት ቤት ገብተው ንባብና ዳዊት እንዲኹም ፀዋትወ ዜማ አጠናቅቀው ከብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ማዕርገ ዲቁናና ማዕርገ ቅስና ተቀብለዋል፡፡

በዋልድባ አብረንታንት ገዳም ገብተው ለዘጠኝ ዓመታት ያኽል (ከ1933 – 1942 ዓ.ም.) ሥርዓተ ገዳሙን ከአጠኑና በግብዝና ከአገለገሉ በኋላ በዚኹ ገዳም መዓርገ ምንኵስናን ተቀብለዋል፡፡ ትምህርታቸውን በመቀጠል በሰሜን ምዕራብ ትግራይ በሚገኘው በደብረ ዓባይ ገዳም የደብረ ዓባይ መዝገበ ቅዳሴ ዜማ ተምረው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡

በ1943 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ ፈቃድና ትእዛዝ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትን እንዲያገለግሉ ተልከው ለአራት ዓመታት ያኽል አገልግለዋል፡፡ አኹንም በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ ወደ ግብጽ ሔደው ለ16 ዓመታት ያኽል ነገረ መለኰትን በዓረብኛ ቋንቋ አጥንተው ተመርቀዋል፡፡

ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ለማገልገል ተልከው ለስድስት ዓመታት ያኽል በአስተዳዳሪነት ሠርተዋል፡፡ በዚኹ ሓላፊነት ሳሉም በ1968 ዓ.ም. ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ኹነው በተሾሙ ጊዜ በሱዳን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው በመምጣት ለበዓሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡

በ1972 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት በመኾን አገልግለዋል፡፡

በጥቅምት ወር 1983 ዓ.ም. በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ኾነው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ተሾመዋል፡፡

ከመጋቢት 1985 ዓ.ም. ጀምሮ የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው ለአንድ ዓመት ያኽል ሠርተዋል፡፡

ከየካቲት 1986 ዓ.ም. ጀምሮ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳምና ት/ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው አገልግለዋል፡፡

ከሐምሌ 1968 ዓ.ም. ጀምሮ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው አገልግለዋል፡፡

ከግንቦት 1992 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አዲስ አበባ ተዛውረው የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡

በመጨረሻም በዚኹ ሥራ ላይ ሳሉ ባደረባቸው ድንገተኛ ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በተወለዱ በ106 ዓመታቸው ከዚኽ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡

የሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ የቀብር ስነስርዓት

የሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ የቀብር ስነስርዓት

የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም በዚኹ ዕለት፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበትና የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱ ከተፈጸመ በኋላ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
ምንጭ፡- ሐራ ተዋህዶ

ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በህንድ ይገኛሉ – የተባበሩት መንገስታት

ethio indea

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባወጣው ሪፖርት ህንድ ባለፉት 6 ወራት ውስጥ 2 መቶ ሺህ ለሚደርሱ ስደተኞች መጠጊያ መሆኗን አስታውቋል፡፡

በህንድ እየታየ ያለው የስደተኞች መጨመር በፈረንጆቹ 2014 በዓለማችን አለመረጋጋት ከበረከተባቸው መካከለኛው ምስራቅ እና አፍሪካ የሚጎርፉ ስደተኞች ቁጥር መጨመር እንደምክንያት ተጠቅሷል፡፡

በተጠናቀቀው የፈረንጆቹ ዓመት 5.5 ሚሊዮን የሚደርሱ ዜጎች ተፈናቅለዋል፡፡
ታዲያ በህንድ በተለያየ ምክንያቶች በመግባት በስደት ላይ ከሚገኙ ህዝቦች መካከል ኢትዮጵያዊያንም እንደሚገኙበት የተጠቀሰ ሲሆን በህንድ የሚገኙ ስደተኛ ኢትዮያዊያን ቁጥር 580 ሺህ ይደርሳል ተብሏል፡፡

የሶርያ ስደተኞችም በህንድ ቁጥራቸው እጅጉን የበዛ ነው ተብሏል፡፡

የሶማሊያ ፣ የደቡብ ሱዳን ፣ የኬንያ ፣ የኮንጎ፣ ማይናማር እና ኢራቅም በህንድ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ስደተኛ ያስመዘገቡ ሀገራት ናቸው ሲል ድሬ ቲዩብ ዘግቧል፡፡

በየጊዜው ኢትዮጵያውያን ባህርና የብስ እንዲሁም አየር አቋርጠው ሀገራቸውን ጥለው የሚሰደዱ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ስደተኞች ቁጥር ከምንጊዜውም በላይ እየጨመረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ በአሁን ወቅት ግን ኢትዮጵያውያን በአፍሪካ፣ በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በመካከለኛው ምስራቅ ከሚያደርጉት ስደት በተጨማሪ እስካሁን ባልተለመደ ሁኔታ ህንድን ጨምሮ ወደ ተለያዩ የሩቅ ምስራቅ እስያ ሀገሮችም እየተሰደዱ እንደሆነ የተባበሩት መንግስታት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽን መረጃዎች ያስረዳል፡፡

የድሆች አባት ዶ/ር በርናርድ ተለየን!

ነብዩ ሲራክ

* የኢትዮጵያ አፈር የጠራው ጠቢብ

*” ክብር ሞቱ ለሰማዕት ”

ዶ/ር በርናንድ አንደርሰን

ዶ/ር በርናንድ አንደርሰን

ዛሬ የምናዘክረው ሰው የኢትዮጵያ አፈር ፍቅር ጠርቶት ለጉስቁል ተገፊው ደሃ የሀገሬ ሰው ህይዎት ትንሳኤ ተግቶ ለውጥ ስላመጣ ጠቢብ ነው። ዝካሬ ታሪኩ ቢያስተምረን ፣ አርአያ ሰብዕናው ግብአት፣ ተሞክሮ ቢሆነን ፣ ህይዎት ንብረቱን በእኛው ቀዬ ስላፈሱሰ ትጉት ሀኪም ነው ! ነፍሳቸውን ይማር ብለን ለሰሩት ስራ ክብር በመስጠት እናዘክራቸዋለን! ዶክተር በርናርድ አንደርሰን ይባላሉ ! በርናርድ ዛሬ አይሰሙም ፣ አያዩንም …

የዶር በርናርድን እረፍት ያረዳችኝ መነኩሴዋ እናቴ ሀዘኑ ጎድቷት ” ልጀዋ ዋርካችን ተገረሰሰ እኮ ፣ የድሆች አባትና ጠዋሪ መድሃኒታችን አጣንኮ … ” ነበር ያለችኝ … ያልጠበቅኩት ነበርና ድንጋጤው መላ አካሌን ወረረው ። የእንባ ሳግ እየተናነቃት ሃዘኗን ያጋራችን እናቴን ከማጽናናት ባለፈ ምንም ማለት አልተቻለኝም! እናም ስለ ጠቢቡን የድሆች አባት ዶር በርናርድ አንደርሰን ላዘክር በተጎዳ ስሜት ብዕሬን ሳነሳ ጠቢቡ በሰጡት የኑዛዜ ቃል መሰረት ቀብራቸው በሚወዷት ሀገረ ኢትዮጵያ ምድር ይሆን ዘንድ በተናዘዙት መሰረት ሊፈጸም ተቃርቧል ። ውድ ባለቤታቸው የአርበኛው ደራሲ ገሪማ ታፈረ ልጅ ከሲስተር እማዋይሽ ገሪማም ከምድረ አሜሪካ የዶር በርናርድን ቃል ለመፈጸም ዛሬ እኩለ ቀን አ.አ ይገባሉ ! ጥቂት ስለድሆች አባት በርናርድ አንደርሰን ላጫውታችሁ …

ዶ/ር በርናርድን ሳውቃቸው

ከአራት አመት በፊት ጠቢቡ ወንድም አግኝቻቸዋለሁ ። ስለሚሰሩት በጎ አድታጎት በቅርብ የሚያውቋቸው ስለደግነት ቸርነታቸው አውርተው የማይጠግቡ ወገኖችን አግኝቸ ብዙ ተነግሮኛል። ከዚህም ተነስቸ ጠቡቡን ወንድም በአንድ የራዲዮ ዝግጅት ከአንጋፋው የረጅም ጊዜ የጀርመን ራዲዮ ጋዜጠኛ ከተክሌ የኋላ ጋር በመሆን በአንድ ዝግጅት ለማቅረብ ጠይቄያቸው ነበር ። ዶር በርናርድ ግን ” ምኑን ሰርቸ ታሪኬ ይነገራል ! ” በማለት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ፋና ወጊና አርአያ ተግባራቸውን ለማስተዋወቅ አልተሳካልኝም ! ያም ሆኖ ጠቢቡ በርናርድ እና ባለቤታቸው ሲስተር እማዋይሽ ገሪማን በኢትዮጵያ ባህል በተሽቆጠቆጠው ቪላቸውን ሲያስጎበኙኝ እዚህ ስላደረሳቸው መንገድ አውግተናል ። “አጴ ቴዊድሮስ በተወለዱበት እና ባቀኑት ሃገር የአህያ ግንባር የምታክል ማስታወሻና መዘከሪያ ቦታ እንዴት አይኖራቸውም? ” በሚል ለቴዎድሮስ መታሰቢያ ሙዝየም ለማስፈቀድ ሲከላተሙ ያገኘኋቸው ከእውቋ ሀገር ወዳድ ከወ/ሮ እማዋይሽ ገሪማ ጋር በመሆን የምድረ አሜሪካ የተደላደለ ኑሮ ስላፈናቀላቸው የእናት ኢትዮጵያ ፍቅር ፣ በታሪካዊዋ የጎንደር ከተማ ስላሰሩት የአዛውኖቶች መጠለያ ፣ ለህሙማን መርጃ ባቋቋመው የህክምና እርዳታ መስጫ ቦታና ያኔ ጅምር ስለነበረው የሆስፒታል ግንባታ መሰረት በሚጣልበት ማሳ ላይ ቆሜ ህልማቸውን አውገተውኛል ፣ ሃሳባቸውን ተጋርቻለሁ!

ለመሆኑ ዶ/ር በርናርድ አንደርሰን ማናቸው?

በሃገረ ጃማይካ ካትሪን ደብር ተብላ በምትታዎቅ አንዲት መንደር እ.ጎ.አ መስከረም 21 ቀን 1944 ዓም ህጻን በርናንድ አንደርሰን ከአርሶ አደር ወላጆቹ ተወለደ። የበርናንድ ህይዎት በጃማይካዋ የካትሪን ትንሽ የገጠር መንደር መጀመሩ እንጅ ከዘር ማንዘሩ ርቆ በሌላ የአለም ጫፍ ካለችው ኢትዮጵያ ጋር በፍቅር ተቆላልፎ ህይወቱን ያሳልፋል ብሎ የሚገምት አልነበረም ። ገና ከልጅነት ህይዎቱ ጀምሮ ብሩህ አዕምሮ የታደለው በርናንድ በካሪቪያን ውስጥ አንጋፋ በሆነው የዎልማር የወንዶች ት/ቤት ተግቶ በመመማር ወደ ተሻለ ደረጃ መሸጋገር ጀመረ ፣ ከዚያም ጉዞውን ቀጠለ … የተሻለ እውቀት ጥም እያንገበገበው ወደ አደገችው ምድረ አሜሪካ አቀና ፣ በትምህርቱ በመግፋት እ.ጎ. አ 1960 ዎቹ መጀመሪያ በዋንሽን ግተን ዲሲ የሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ በህክምና ሳይንስ የመጀመሪያውን የባችለር ዲግሪ ሲቀዳጅ በከፍተኛ ማዕረግ ነበር ። ለጎልማሳው በርናንድ በከፍተኛ የህክምና ተቋማት የላቀ ውጤት ማምጣት ተራ ትምክህት ሆኖ ሳይገታው የተሻለና የላቀ ፣ ከፍ ያለ ትምህርት የመቅሰም ህልምን ሰንቆ የማታ ትምህትቱን በመከታተሉን ገፋበት ። ይህንንም ህልም በአጭር ጊዜ ታጥቆ ለስኬት አደረሰው ። እ.ጎ. አ በ1970 ዎቹ በርናንድ በከፍተኛ ማዕረግ የዶክትሬት ማዕረግ ተመረቀ፡፡

የዚያ ደርባባ ጎልማሳ ዶር ማንነት የተገነባው ከመደበ ኛው እውቀት ባለፈ አብሮት ከተቆራኘ ሰብዕና እንደነበር የሚያውቁት ምስክርነታቸውን ይሰጣሉ ። ዶር በርናርድ አንደርሰን በሙያው ያጡ የነጡ፣ ጉስቁል ፣ምንዱባንን ለመርዳትና ለመደገፍ ቆርጦ ተነሳ ፣ ከምንም በላይ ደግሞ እንደ ቃል ኪዳን አድርጎ የያዘውን ተተኪ ፍለጋና ተተኪን ማፍራት ነበርና ድሎት ሳያታልለው ያደገ የተመነደገችውን ምድረ አሜሪካ ለቆ ወደሚያውቀው የድሆች ምድር አቀና ! ወደ ጃማይካ ኪንግስተን …

ጃማይካ ኪንግስተን …

ህልሙን ለማሳካት ወደ ትውልድ ሃገሩ ጃማይካ ተመልሶ በወቅቱ ታዋቂ ከነበረው የኪንግስተን የህዝብ ሆስፒታል ስራውን ጀመረ ። የቀዶ ጥገና ጥበብ ባለሙያው ጎልማሳ ሃኪም ቅድሚያ የሰጠው በድህነት የሚማቅቁ ወገኖቹን መታደግ ነበር ፣ በህክምና ድጋፉ ፣ በተጓዳኝ ጥናትና ምርምሩ አንቱ በሚያሰኘውን ተመክሮ ራሱን እያጎለበተ ጉዞ የጀመረው ሃኪም በህክምና ድጋፍ ከመስጠት ርቆ ሔዶ በመምህርነት ሙያው ተተኪ ትውልድን የማነጽ ህልሙን አሳካ ። በዚህም ጉዞው ዶር በርናርድ አንደርሰን ለሃገሩና ለወገኑ ይህ ነው የማይባል አመርቂ ውጤት ማስመዝገብ ቻለ !

ከጃማይካ መልስ በዋሽንግተን

የጃማይካ ኪንግስተን ተልዕኮውን በሚገባ ከውኖ አቅፋ ደግፋ እውቀት ወደ መገበችው ሀገረ አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ ተመለሰ ። ዶር በርናርድ ለዚህ ላበቃው ዩኒቨርሲቲ ከእለትጉርሱ ያጠራቀመውን ከ100 ሽህ የአሜሪካ ዶላር የለገሰ ፣ ለሚሰረሰው በጎ ስረሰ ከመደሰተረ ውጭ ፣ መወደስ የማይሻ ሰብአዊም ነበር ።
ዶ/ር በርናርድ ከጃማይካ መልስ እንደ አቻ የሙያው ባልደረቦቹ ሃብት ንብረት የሚያካብትባቸው ሆስፒታሎ ች በከፍተ ኛ ገንዘብ ሊቀጥሩት ሲሻሙ አሻፈረኝ አለ። ጥቅም ፍለጋ መማሰኑን ” ወዲያልኝ ” ብሎ ፣ የጤና ከለላና ሽፋን የሌላቸው ፣ በድንገተኛ አደጋ ተጎድተው ህይዎታቸው አጣብቂኝ የገቡትን የስልጡኑ ሀገር ተገፊ ምንዱባን መታደግ ወደ ሚችልበት በዲሲ ጄኔራል ሆስፒታል በአነስተኛ ደመወዝ ተቀጥሮ መስራት ጀመረ ። በሙያው ተግቶ ፣ በሰብዕናው ጸንቶ ፣ ባሳየው ስኬትም በአጭር ጊዜ አንቱታን በማግኘቱ የሆስፒታሉ ሊቀመንበርና የቀዶ ጥገናው ክፍል ዋና ዳይሬክተር ለመሆን በቃ ! በአስተዳደር እና በሙያው ክህሎት የዲሲ ጀኔራል ሆስፒታል ከፍ ወዳለ ደረጃ ያደገው በዶር በርናርድ አንድሰን አመራር እንደነበር ዝክረ ታሪኩ ያስረዳል። ዶር በርናንድ ሆስፒታሉን ከማስተዳደር ጎን ለጎን የግል ክሊኒክ በድሆቹ መኖሪያ አቅራቢያ በዲሲ ሮድ አይላንድ መንገድ በመክፈት ፣ ለቻሉት በአነስተኛ ክፍያ ፣ ያልቻሉትን በነጻ በማከም ግልጋሎት ይሰጥም ነበር ።

የዶር በርናርድ አፍሪካና ኢትዮጵያ ትስስር

በቀጣይ ዝካሬ ዶር በርናርድ ስነሳ እንደ አባት አቅርቤ ፣ እንደ ታላቅ ትጉህ ጠቢብ አንቱ እያልኩ መተረኬ ይገባኛል ፣ መልዕክቴ ከገባችሁ ለእኔ ያ በቂ ነው! ብቻ ያገሬ ሰው ዶር በርናርድን “የድሆች አባት ” ስላለበት አንድምታ ዘልቀን እናወጋለን …

ታህሳስ 24, 2007 ዓም ይህችን አለም የተለዩን ያልተጨበጨበላቸው ፣ ያልተነገረላቸው የኢትዮጵያ ወዳጅ ጃማይካዊ አሜሪካዊ ዶር በርናርድ የምናዘክረው በታላቅ ክብር ነው ! “ዶር በርናርድ ጉስቁል ምንዱባን ን ስትደግፍ ኖረሃልና ሞትህ የክብር ሞት ነው ! ” ክብር ሞቱ ለሰማዕት ” በሚል ትናንት እኩለ ሌሊት በዋሽንግ ተን ዲሲ በተደረገ ሰፊ የጸሎትና የዝክር ስነ ስርአት ቤተ ሰብ ፣ ወዳጅ ዘመድና አድናቂዎቻቸው በተገኙበት የክብር ስንብት አድርገው በርናንድ በድናቸው እንዲያ ርፍ ወደ ፈቀዱባት ቅድስት ሀገረ ኢትዮጵያ በክብር ተሸኝተዋል ! በዚሁ ፕሮግራም ከተሰራጨው ዝክረ ህይዎት ያገኘሁትን መረጃ በቀጣይ እንደሚሆን አድርጌ የምናየው ይሆናል !

ለመላ ቤተሰብ ለወዳጆቻቸውና ለአድናቂዎቻቸው መጽናናትን እመኛለሁ ! ለሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪው የድሆችን አባት ፈጣሪ በቀኙ ያሰቀምጣቸው ዘንድ የዘወትር ጸሎቴ ነው ! ነፍስ ይማር !

ታህሳስ 30 ቀን 2007 ዓ.ም