“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት
በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************
የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡
የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።
በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።
የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡
ድል የህዝብ ነው!!!
አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 26 ቀን 2007
አንድነት ፓርቲ የጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ሲጠናቀቅ፤በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል
-“የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!”- አንድነት
-በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞችም ተከታታይ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች እንዲቀጥሉ ተወስኗል
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዛሬ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ አራት የክልል ከተሞች የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ተጠናቀቀ፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻውን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ጽህፈት ቤት በማድረግ መዳረሻውን ጥቁር አንበሳ አካባቢ በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰልፍ በፅህፈት ቤቱ አካባቢ በተፈፀመ የፖሊስ ድብደባና እገታ ሊቋረጥ ችሏል፡፡
የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማም ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አንድነት ወደ ምርጫው መግባቱን በመወሰን በመላ ሀገሪቱ ከ450 በላይ ዕጩዎቹን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተክትሎ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ፓርቲው ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በሚል ፓርቲውን ከምርጫ ውድድር ለማስወጣት የሚደረገውን ተግባር ለመቃወም መሆኑን ቀደም ሲል ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡ ከተጠቀሰው ዓላመ በተጨማሪ በዜጎች ላይ የሚደርስ ህገወጥ እና የግፍ እስር እንዲቆም፣ የታሰሩ የህሊና እስረኞች እንዲፈጡ፣ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ እንዲኖር፣…የሚሉ ጥያቄዎች ይገኙበታል፡፡
መረጃዎች ከስፍራው እንደጠቆሙት ከሆነ፤ የተቃውሞ ሰልፉ ቀበና ከሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት የተነሳው ከ 150 በላይ የሚሆን ሰልፈኛ ከጽህፈት ቤቱ 100 ሜትር ርቀት ላይ ከሚጠብቁ ከ500 በላይ ሰልፈኞች ጋር ከመቀላቀላቀላቸው አስቀድሞ ፖሊሶች ቆርጠው በመግባት ከባድ ድብደባ አድርሰዋል፡፡ አራት ኪሎ፣ በፒያሳና የሰልፉ ማጠናቀቂያ በሆነው ኢቲዮ -ኩባ አደባባይ ይጠባበቅ የነበረው ሰልፈኛ ሊበተን መቻሉንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በተፈፀመው የፖሊስ ድብደባም ከ26 በላይ የፓርቲው አባላትና አመራሮች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፤ ከሰልፉ ጋር ምንም ንክኪ ያልነበራቸውና ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የነበሩ የ70 ዓመት አዛውንትም ከፍተና ጉዳት ደርሶባቸው በአቅራቢያው በሚገኝ የጤና ተቋም የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት በክልል ከተደረጉት የተቃውሞ ሰልፎች መካከል ፓርቲው በደብረማርቆስ፣ በሸዋሮቢት እና በጋሞጎፋ ከምባ የተሳካ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ተጠቁሟል፡፡
በአዲስ አበባው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጉዳት ከደረሰባቸው የአንድነት አባላት መካከል የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ስለሺ ሐጎስና የፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን ኃላፊ ዳግማዊ ተሰማ ከፍተኛ ጉዳት ስለደረሰባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበርና ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደነበር የዓይን እማኞች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይም ……የተባሉ ነፍሰጡር በፖሊስ ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤በፖሊስ ድብደባ ከተፈፀመባቸውና ጉዳት ከደረሰባቸው የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና አባላት መካከል፡-
- አቶ አስራት አብርሃም (የህዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሃላፊ)
2. አቶ ዳንኤል ተፈራ (የውጭ ጉዳይ ሃላፊ)
3. አቶ ብሩ ብርመጅ (የፖለቲካ ጉዳይ ሃላፊ)
4. አቶ ፀጋየ አላምረው (ምክትል አፈ-ጉባኤ)
5. አቶ አሻግሬ መሸሻ (የሰሜን ቀጠና ሃላፊ)
6. አቶ ሰለሞን ስዩም (የኤዲቶሪያል ቦርድ ሰብሳቢ)
7. ወ/ት ልዕልና ጉግሳ (የም/ቤት አባል)
8. አቶ ዳግማዊ ተሰማ (የም/ቤት አባል)
9. ጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ (የም/ቤት አባል)
10. አቶ ስንታየሁ ቸኮል (የአዲስ አበባ የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ)
11. አቶ አሸናፊ አሳምረው (የወረዳ አመራር)
12. አቶ ኢሳያስ ቱሉ (አባል)
13. ወ/ት መስከረም ያረጋል (አባል)
14. አቶ ሃይሉ ግዛው (የወረዳ ሰብሳቢ)
15. አቶ አዲሱ መኮንን (የወረዳ ሰብሳቢ)
16. አቶ ሲሳይ ካሴ (አባል)
17. አቶ ወጋየሁ አድማሴ (አባል)
18. አቶ ክብረት ሃይሉ (የም/ቤት አባል)
19. አቶ ስለሺ ደቻሳ (አባል)
20. አቶ ማሩ አካሉ (አባል)
21. አቶ ክፍሉ በዳኔ (አባል)
22. አቶ ፋሲካ አዱኛ (የወረዳ አመራር)
23. ወ/ሮ ገነት ሞገስ (የወረዳ አመራር)
24. ተስፋየ ብዙነህ (አባል)
25. ሙሉጌታ ተፈራ
26.ኤፍሬም ሰለሞን(የአዲስ አበባ ስራ አስፈፃሚ)
በተቃውሞ ሰልፉ ፖሊሶች ያደረሱትን ጉዳት በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩት የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች የአንድነት አመራሮችን እና ጉዳት ደርሶባቸው በየሆስፒታሉ የሚገኙ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አነጋግረዋል፡፡ የፓርቲው አመራሮች ከአባላትና ከደጋፊዎች ጋር ውይይት ያደረጉ ሲሆን አንድነት በአዲስ አበባ ተከታታይ የተቃውሞ ሰልፎችን እንደሚያደርግ ይፋ ተደርጓል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ ያወጣ ሲሆን፤ ሙሉ መግለጫውን ከዚህ በታች ይመልከቱ፡-
የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
ፓርቲያችን አንድነት ገዥው ፓርቲ፣ ምርጫ ቦርድና የገዥው ፓርቲ ልሳን በመሆን እያገለገሉ ያሉ ሚዲያዎች በመተባበር ከምርጫ ለማስወጣትና ተለጣፊ አንድነት ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ መጥራቱ የሚታወቅ ነው፡፡
የተቃውሞ ሰልፉን ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም እንደምናከናውን ለአዲስ አበባ መስተዳድር ብናሳውቅም መስተዳድሩ በ12 ሰዓት ውስጥ በፅሁፍ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ ሰልፉ እውቅና አለው፡፡ መስተዳድሩ ግን የተጣለበትን ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ወደ ጎን በመግፋት የተወሰኑና የማይታወቁ ግለሰቦች ፔቲሽን ተፈራርመው አምጥተዋል በማለት ብዥታ ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ፓርቲያችን ህጉን ጠብቆ ህጋዊ የሆነ ሰልፍ ለማካሄድ ቢሞክርም አሁንም ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ጭካኔ በተመላበት ሁኔታ ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በተደጋጋሚ እንዳየነው ፖሊስ ደንብ ማስከበር ሲገባው አድሎ ለፈፀመው አካል በመወገን ድብደባ መፈፀሙ ከወገንተኝነት ያልፀዳ መሆኑን እንድናረጋግጥ አድርጎናል፡፡
ጥያቄያችን አሁንም የፍትህ፣ የእኩልነትና ህግ እንዲጠበቅ የማድረግ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የመንግስትነት ስልጣኑን በመጠቀም የስልጣን ዘመኑን ለማስረዘም እየከወነ ያለውን ሴራ ማስቆም ነው፡፡ ጥያቄያችን የነፃነትና ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ይረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ጥቄያችን ምርጫ ቦርድ የገዥው ፓርቲ አጋር መሆኑ ቀርቶ ገለልተኛ ሚናውን ይወጣ የሚል ነው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎቻችን ደግሞ ደም በማሰስ፤ በድብደባም ሆነ በእስር ፈፅሞ አይቆሙም፡፡
በሚቀጥለው ሳምንትም በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የሰላማዊ ተቃውሞ ድምፃችንን ከፍ አድርገን እናሰማለን፡፡ ትግሉ ይቀጥላል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ
የመኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረት ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ፓርቲው ገለፀ
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የፓርቲያቸው ምክትል ፕሬዝደንት እና የሰሜን ቀጠና ኃላፊ የሆኑት አቶ ዘመነ ምህረት እጅግ ዘግናኝ ድብደባ ደርሶባቸው ሲል ፓርቲው ጥር 15 ቀን 2007 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ አስታወቀ፡፡ አቶ ዘመነ የመኢአድን ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ወደ መኖሪያቸው ጎንደር ከተማ ከተመለሱ በኋላ ከፍተኛ የደህንነት ክትትልና ጫና ይደረግባቸው እንደነበር ለፓርቲያቸው አሳውቀው ነበር ያለው ፓርቲው ጥር 10 ቀን 2007 ዓ.ም ጎንደር ከሚገኘው መኖሪያው ቤታቸው ከባቤታቸውና ከህፃን ልጃቸው ፊት የፖሊስ ልብስ በለበሱ አካላት ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸው ወዳልታወቀ ቦታ መወሰዳቸውን ግልጾአል፡፡ በአሁኑ ወቅት የፓርቲው አባላት ባደረጉት ክትትል አቶ ዘመነ አዘዞ የሚገኘው የመከላከያ ካምፕ ውስጥ እንደሚኙ አረጋግጠናል ያለው መግለጫው የሰው ልጅ ላይ ይፈጸማል ተብሎ የማይገመት ከፍተኛ ስቃይና ሰቆቃ ደርሶባቸዋል ብሏል፡፡
ከአቶ ዘመነ በተጨማሪ ጠቅላላ ጉባኤውን ተሳትፈው የተመለሱት የፓርቲው የማህበራዊ ጉዳይ ኃላፊ አቶ እያሱ ሁሴን 3 አመት ተፈርዶባቸው እስር ቤት እንደሚገኙ፣ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ፣ መ/አ ጌታቸው መኮንን፣ አቶ ጥላሁን አድማሴ የተባሉትን ጨምሮ ሌሎችም የፓርቲው አመራሮች ለእስር መዳረጋቸውን ያወሳው መግለጫው በአመራርና አባላቶቻቸው ላይ የሚደረገው እስር መኢአድ ምርጫውን ተጠቅሞ በገዥው ፓርቲ ላይ ጫና ማሳደር ስለሚችል እንደሆነ ተገልጾአል፡፡
በሌላ በኩል በአባላቶቻቸው ላይ በሚደርሰው በደልና ጫና ባሻገር ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን ከምርጫ 2007 እንዳይሳተፍ የኢህአዴግ ቀኝ እጅ ሆኖ በመስራት ላይ እንዳለ ያወሳው መግለጫው ፓርቲው በምርጫው እንዳይሳተፍ ከተደረገ ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብሏል፡፡ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ በፓርቲው ላይ የሚፈጽመውን በደል ተከትሎ ፓርቲው በሚደርገው ትግልም ህዝቡ ከጎኑ እንዲቆም ጥሪ ማቅረቡን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
አንድነት ፓርቲ እሁድ “የነፃነት ቀን ቀርባለችና ወደ አደባባይ ውጡ” በሚል ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ጠርቷል
-የሰልፉን ቅስቀሳ ተከትሎ የፓርቲው ወጣት አመራሮች ታስረዋል
.አንድነት ፓርቲ የጠራው የነገው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ተጠናክሮ ቀጥሏል
አንድነት ፓርቲ ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢህአዴግና በምርጫ ቦርድ በኩል ፓርቲው ወደ ምርጫ ውድድር እንዳይገባ የሚደረገውን እንቅስቃሴና ድርጊት በመቃወም የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ በፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ ዛሬ ጥር 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም፣ ምክትል ኃላፊው አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ኃላፊው አቶ ሰለሞን ስዩም እና የፓርቲው የአዲስ አበባ ወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ቸኮል እና ሌሎች አመራሮች አቶ ያሬድ አለማየሁ፣ አቶ ሲሳይ ጌትነት፣ አቶ ማቲያስ ሐረጉ በፀጥታ ይሎች መታሰራቸውና ወዳልታወቀ ስፍራ የተወሰዱ ሲሆን፤ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት አቶ አስራት አብርሃም፣ አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ አቶ ሰለሞን ስዩም እና አቶ ስንታየሁ ቸኮል መፈታታቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ፓርቲው ሰልፉን እንዲጠራ ያስገደደው ምርጫ ቦርድ ከሀገሪቱ የምርጫ አዋጅ ህግ አግባብ ውጭ በአንድ ወር ውስጥ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በመወሰኑ ሲሆን፤ ቅሬታ ነበረን በሚል ጥያቄ ካቀረቡት ዋነኞቹ አቶ አየለ ስሜነህ እና አቶ ኢሳይያስ ቱሉ ምርጫ ቦርድ እና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲውን ለሁለት ለመክፈል በመሞከሩ፣እኛ ደግሞ አንድነት አንድ ነው እንዲከፈልም ስለማንፈልግ ተመልሰን ወደ ዋናው ፓርቲያችን ቢሮ ተመልሰናል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም አንድነት ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በጠራው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንዲታዘብ ጥሪ ሲደረግለት እነ አቶ አየለ ስሜነህ ሌላ ጠቅላላ ጉባኤ ለማድረግ ደብዳቤ ስላስገቡ ቦርዱ ሁለት ቦታ ለመታዘብ ወኪል መላክ እንደማይችል በጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ደብዳቤ መፃፉ ታውቋል፡፡
አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣ የነበርነው የአንድነት ፓርቲ አባላት ከ15 አንበልጥም፤ ነገር ግን የፓርቲው አባላት ያልሆኑ ከ60 በላይ ሰዎች በስብሰባችን ላይ ተገኝተዋል፣የሆቴል አዳራሽ ኪራይ ማን እንደከፈለ አናውቅም፣ ተከፍሎላችኋል እዛ ሆቴል ሂዱ እንባላለን፣ይሄ ሁሉ ስላላማረን እና ፓርቲያችን አንድነት አንድ ስለሆነ ወደ ፓርቲያችን ተመልሰናል ሲሉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲታዘብ ለቀረበለት ጥሪ እነ አቶ አየለ ስሜነህም ጠርተውናል ሲል በፃፈው ደብዳቤ ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ምንም ዓይነት ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣በመካከላችን የነበረው ጥቂት አለመግባባት እንዲፈታ ስንል እንጂ ከፓርቲው ህልውናም ሆነ አሰራር ጋር ቅሬታም ሆነ ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ የሚል ጥያቄ አላቀረብንም ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
በአሁን ወቅት ጥያቄ ነበረን ያሉት አቶ አየለ፣ ያለንን ጥያቄ በፓርቲያችን ውስጥ ሆነን እንፈተዋለን፣ ወደ ውጪ ይዘን መውጣታችን ትክክል እንዳልነበረና እኛ ባላሰብናውና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲው ላይ በእኛ ስም አደጋ ለመፍጠር እየተሰራ እንዳለ ስንገዘነብ ተመልሰናል፣ መጀመሪያም ቢሆን ፓርቲው አልተከፈለም፣ እኛም ጥያቄ አቀረብን እንጂ ከፓርቲው አልወጣንም ሲሉ አክለዋል፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ ለጋዜጠኞች የሰጡትን መግለጫ ለራሱ ለምርጫ ቦርድ ግልባጭ ማድረጋቸውንም አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ጥያቄ አቅርበው የነበሩት አቶ አየለ ስሜነህ ወደ ፓርቲው መመለሳቸውን ቢያሳውቁም፤ ምርጫ ቦርድ ግን በነ አቶ አየለ ስሜነህ ስም ሌላ አካል እያደራጀ መሆኑን በመጥቀስ ፓርቲው ድርጊቱን ለማውገዝ የሰልፍ መጥራቱን ይፋ አድርጓል፡፡ ፓርቲው ድርጊቱን የኢትዮጵያ ህዝብም እንዲረዳውና እንዲያወግዘው ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ኣ.ም. የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን መጥራቱን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ከዚህ በኋላ ፓርቲው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በመላ ሀገሪቱ ማካሄድና ነውጥ አልባ የነፃነት ትግሉን አጠናክሮ ከመቀጠል ውጭ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማይጠራ ማሳወቁ አይዘነጋም፡፡ ወደ ፓርቲያቸው ስለተመለሱት አቶ አየለ ስሜነህ እስካሁን ባይዘግብም ፓርቲው እንደተከፈለ አድርገው ከሬዲዮ ፋና እና ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በተደጋጋሚ ከሚያቀርቡት በስተቀር ምርጫ ቦርድ እስካሁን የሰጠው ምላሽ የለም፡፡
የነገው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መነሻ አዲስ አበባ ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ፊትለፊት ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት ሲሆን፤ የሰላማዊ ሰልፉ መነሻ ሰዓት ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት መሆኑንም ታውቋል፡፡
የሰልፉ መዳረሻ ቦታ አዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ጀርባ እና ዋናው ፖስታ ቤት ፊትለፊት በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ መሆኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት (እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.) የተቃውሞ ሰልፉ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በደብረ ማርቆስ፣ በአርባምንጭ አካባቢ ከምባ ወረዳ፣በጂንካ እና በሸዋ ሮቢት እንደሚደረግ በፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በመወሰኑ በክልሎችም የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ቀጥሏል፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ቀኑ እንዲራዘም የመንግስት አካላትና ዲፕሎማቶች ጥረት ቢያደርጉም፤የአንድነት ፓርቲ ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ መብታችንን ከእንግዲህ ለምነን አናገኝም፣ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉም በታቀደለት መሰረት ይቀጥል ሲል መወሰኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
ፓርቲው ከላይ ከተጠቀሱት 5 ከተሞች በተጨማሪ በተከታታይ በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞችም የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ እንደሚቀጥል ይፋ አድርጓል፡፡
ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸውን ታስረው ጨለማ ክፍል መታሰራቸው ተገለፀ
-ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ጠያቂ ተከልክሏል
የቀድሞው የጋንቤላ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸው ታስሮ ጨለማ ክፍል መታሰራቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡
አቶ ኦኬሎ ቂሊንጦ በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወስ ሲሆን፣ ሰውዬው ከሰሞኑ የርሃብ አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ በእስር በሚገኙበት እስር ቤት እጅና እግራቸውን ታስረው ብቻቸውን ጨለማ ክፍል እንዲገቡ እንደተደረጉ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ዛሬ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም ወደ ቂሊጦ ማረሚያ ቤት እስረኞችን ሊጠይቁ ሄደው እንደነበር የገለጹት ምንጮች፣ እዚያው በእስር ላይ ካሉ ሰዎች አቶ ኦኬሎ ያሉበትን ሁኔታ መረዳታቸውን አክለው ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል የ18 አመት እስር ፍርደኛው ታዋቂው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ሌላ ሰው መጠየቅ እንደተከለከለ የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡












