Tag Archives: Ethiopia

አቶ ማሙሸት አማረ ለውሳኔ ተቀጠሩ

“ምስክርነቱ የሐሰትና የተጠና ነው!” ጠበቃቸው

Mamushet Amare

አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም መንግስት ከጠራው ሰልፍ አንድ ቀን ቀድሞ ከለቅሶ ቤት ወደ ቤተ መንግስት ለተደረገውና ለዋናው (ለሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም) ሰልፍ አነሳስቷል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው የቀድሞው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዘዳንት አቶ ማሙሸት አማረ ዛሬ ነሃሴ 20 ቀን 2007 ዓ.ም አራዳ ምድብ ችሎት ቀርቦ ለነሃሴ 22 ቀን 2007 ዓ.ም ለውሳኔ ተቀጠሯል፡፡ አቶ ማሙሸት አማረ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በተካሄደው ሰልፍ ላይ ሁከትና ብጥብጥ ፈጥሯል በሚል ተከሶ የነበር ቢሆንም በወቅቱ ከምርጫ ቦርድ ጋር በነበረው ክርክር ሰልፉ ላይ አለመገኘቱን የሚያጋግጥ መረጃ በማቅረቡ በነፃ እንዲለቀቅ ተወስኖ ነበር፡፡ ነገር ግን ክሱ ወደማነሳሳት ተቀይሮ እስር ቤት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡

አቶ ማሙሸት በአዲሱ ክስ የአቃቤ ህግን ምስክሮች ለመስማት ከ5 ጊዜ በላይ ፍርድ ቤት እንደተመላለሰ የተገለፀ ሲሆን በተለይ አንዱ ምስክር በፖሊስ ተይዞ እንዲመጣ ቢጠየቅም ፖሊስ ሳያስፈፅም ቀርቷል፡፡ ከአራቱ ምስክሮች መካከል ሶስቱ ዛሬ የመሰከሩ ሲሆን “አቶ ማሙሸት አማረ 300 ብር ከፍሎ ሰልፍ እንድንወጣ አድርጎናል” ሲሉ መስክረዋል፡፡

ይሁንና ምስክሮቹ ከማሙሸት ጋር በተገናኙበት ወቅት እንዲሁም ገንዘቡ ሲሰጣቸው፣ ሰልፉ ያለፈባቸውን ቦታዎችና ስለ ሌሎችም ጉዳዮች ሲጠየቁ ‹‹አላስታውሰውም›› ከማለት ባለፈ ዝርዝር የምስክርነት ቃል ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ከምስክሮቹ መካከል ሁለቱ አቶ ማሙሸትን ያስያዙ ደህንነቶች መሆናቸውን አቶ ማሙሸትና ጠበቃው በችሎቱ የገለፁ ሲሆን ምስክሮቹ በበኩላቸው ስራቸውን ሲጠየቁ ‹‹የግል›› እያሉ ከመመለስ ውጭ የመንግስት ስራ እንደማይሰሩ ተናግረዋል፡፡ ሆኖም የመንግስት ሰራተኛ መሆናቸውን የሚያሳይ መታወቂያ ሲጠየቁ ሊያሳዩ አልቻሉም፡፡ ከሶስቱ ምስክሮች መካከል አንደኛው ስራውን ሲጠየቅ “የግል” ብሎ የነበር ቢሆንም በመስቀለኛ ጥያቄ የቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ጥቃቅንና አነስተኛ አመራር መሆኑን አምኗል፡፡

ከምስክሮቹ መካከል ሁለቱ የመኢአድ ደጋፊዎች መሆናቸውን ሲጠቅሱ አንደኛው አቶ ማሙሸት ባቀረቡበት የመስቀለኛ ጥያቄ ከምርጫ በኋላ የወጣቶች ሊግና የኢህአዴግ አባል መሆኑን አምኗል፡፡ የኢህአዴግ አባል ሆኖም ቢሆን መኢአድን እንደሚደግፍም ገልጾአል፡፡ ዳኛው “በሁለት ወር ውስጥ እንዴት ብለህ የወጣቶች ሊግ አባል መሆን ቻልክ?” ሲሉት መልስ ሳይሰጥ አልፎታል፡፡

የአቶ ማሙሸት አማረ ጠበቃ ሶስቱም ምስክሮች አብዛኛዎቹን ጉዳዮች እንደማያስታውሱ በመግለፃቸው የተጠና የምስክርነት ቃል መሆኑን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡ በተጨማሪም ከ7 አመት በላይ አዲስ አበባ ውስጥ ኖረው መስቀል አደባባይን ጨምሮ ሰልፉ አመራባቸው የተባሉትን ቦታዎች አናውቃቸውም ማለታቸው፣ መተዳደሪያ ስራቸውን መደበቃቸውና መታወቂያ ለማሳየትም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ምስክርነቱ የሀሰት እንደሆነ ስለሚያረጋግጥ ደንበኛቸው በነፃ እንዲለቀቁ መጠየቃቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
አቶ ማሙሸት አማረ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. አይ ኤ አይ ኤልን ለመቃወም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተጠራው ሰልፍ ላይ ረብሻ አንስተዋል በሚል በተመሰረተባቸው ክስ ሰዓትና ቀን፤ ፓርቲያቸው መኢአድ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሌላ እንዲሰጥ መወሰኑን በመቃወም ፍርድ ቤት ክስ መስርተው ለክርክር በተጠቀሰው ሰዓትና ዕለት ችሎት ላይ እንደነበሩ የሚያስረዳ ደብዳቤ ፍርድ ቤቱ መፃፉ ይታወሳል፡፡

ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሚ የሰማያዊ ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ

አንደኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ለሁለት ቀናት በአዲስ አበባ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲ ኢ/ር ይልቃል ጌትነትን በድጋሜ የፓርቲው ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል፡፡
ትናንት ነሀሴ 16/2007 ዓ.ም ጉባኤውን የጀመረው ፓርቲው በዛሬው ሁለተኛና የማጠቃለያ ውሎው የፓርቲውን ሊቀመንበር፣ የብሄራዊ ምክር ቤት አባላት እንዲሁም የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላት ምርጫን አድርጓል፡፡
ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሜ ለቀጣዩ ሦስት አመታት ፓርቲውን እንዲመሩ የተመረጡ ሲሆን፣ አምስት የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላትም በጉባኤው ተመርጠዋል፡፡ ጉባኤው የፓርቲውን የብሄራዊ ምክር ቤት አባላትንም መርጧል፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ የ2007 ዓ.ም. 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ

የሰማያዊ ፓርቲ የ2007 ዓ.ም. 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ

ለፓርቲው ሊቀመንበርነት ቀደም ብለው ፓርቲውን ለሁለተኛ ዙር ለመምራት ራሳቸውን በእጩነት ያቀረቡት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ብቻ ሲሆኑ፣ ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን ለመቀበል ባቀረበው ሀሳብ መሰረት ራሱን በእጩነት የሚያቀርብ ይኖራል ተብሎ ቢጠበቅም በእጩነት ራሱን ያቀረበ አልነበረም፡፡
በመሆኑም በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን በጥቆማ ለማወዳደር ተገድዷል፡፡ በዚህም ጉባኤው ስድስት እጩዎችን የጠቆመ ቢሆንም አምስቱ ‹‹አንወዳደርም›› በማለታቸው ከተጠቆሙት መካከል አቶ ዮናታን ተስፋዬ ብቻ ለመወዳደር ፍላጎታቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ፓርቲውን በህዝብ ግንኙነት ማገልገላቸው የሚታወስ ሲሆን ዛሬ ደግሞ ለሊቀመንበርነት መወዳደር ችለዋል፡፡
ለሊቀመንበርነት እጩ ሆነው የቀረቡት ሁለቱ እጩዎች በጉባኤው ፊት በተመደበላቸው ጊዜ ገደብ ውስጥ ራሳቸውን ካስተዋወቁና የምረጡኝ ቅስቀሳ ካደረጉ በኋላ ወደ ድምጽ መስጠት መግባት ተችሏል፡፡ በተሰጠው ድምጽ መሰረትም ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲን ለቀጣይ ሦስት አመታት እንዲመሩ በአብላጫ ድምጽ ተመርጠዋል፤ በዚህም ኢ/ር ይልቃል ከተሰጠው ድምጽ 136 ድምጽ አግኝተው ሲያሸንፉ፣ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በበኩላቸው 60 ድምጽ በማግኘት ፉክክር አድርገዋል፡፡

ይልቃል ጌትነት ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

ይልቃል ጌትነት ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

የምርጫ ውጤቱ ይፋ መሆኑን ተከትሎ ንግግር ያደረጉት ተመራጩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲ በሁለቱ ቀናት ጉባኤው ያነሳቸውን ችግሮች ለመፍታት እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ጠቅላላ ጉባኤ በዛሬው ውሎው ቀጣይ የፓርቲውን እንቅስቃሴ አስመልክቶም በጉባኤው አባላት አጠቃላይ ውይይት አድርጓል፡፡ በዚህም ፓርቲው ወደፊት ማደራጀት ላይ አተኩሮ መስራት እንደሚገባው ጉባኤው አጽንኦት ሰጥቶበታል፡፡
ጠቅላላ ጉባኤው የብሄራዊ ምክር ቤትና የፓርቲው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ያቀረቡት ሪፖርት ላይ ተወያይቶ ሪፖርቶቹ የፓርቲው ሰነድ ሆነው እንዲፀድቁ በአብላጫ ድምፅ ወስኗል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ያካሄደውን ጉባኤ ዛሬ ነሐሴ 17 ቀን 2007 ዓ.ም ማጠናቀቁን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ሰበር ዜና፤ በእስር ላይ የነበሩት የቀድሞ የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲ አመራሮች እና አንድ ሌላ ተከሳሽ በነፃ እንዲሰናበቱ ተወሰነ

የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት፤ ዛሬ ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ በፌደራሉ አቃቤ ህግ በሽብርተኝነት ከአንድ ዓመት ከአንድ ወር አካባቢ ታስረው ከነበሩት መካከል አራት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና አንድ መምህር በነፃ እንዲሰናበቱ ወሰነ፡፡

Politicians
ከተመሰረተባቸው ክስ በነፃ እንዲሰናበቱ የተወሰነላቸው የአንድነት ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋና የቤተል ትምህርት ቤት መምህርና የሀገር አቀፍ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሀገር አቀፍ አሸናፊ የነበረው መምህር አብርሃም ሰለሞን በነፃ የተሰናበቱት፣ የቀረበባቸው የሽብርተኝነት ክስ ከጥርጣሬ ባለፈ ተሳትፎአቸውን ማረጋገጥ ባለመቻሉ መሆኑን ፍርድ ቤቱ በውሳኔው አስታውቋል፡፡
በውሳኔው መሠረት አቶ ሀብታሙ የሚጠየቁበት ወይም ሌላ የሚፈለጉበት ጉዳይ ከሌለ በዛሬው ዕለት እንዲፈቱ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺና አቶ የሺዋስ አሰፋ ከዚህ ቀደም ችሎት በመድፈር የተፈረደባቸውን ቅጣት እንዳጠናቀቁ እንዲፈቱ ሲል መወሰኑ ታውቋል፡፡

አብርሃም ሰለሞን

አብርሃም ሰለሞን

በዚሁ ክስ መዝገብ በተመሳሳይ ተከሰው ከነበሩት 10ሩ መካከል ከላይ የተጠቀሱት 5ቱ እንዲፈቱ ሲወሰን፤ ቀሪዎቹ 5ቱ እንዲከላከሉ እንተበየነባቸው ተጠቁሟል፡፡
በአሁን ወቅት በርካታ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች እና የኃይማኖት ነፃነት ጠያቂዎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወቅ ሲሆን፤ ባለፈው ሶስት ጋዜጠኞች፤ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ እና ኤዶም ካሳዬ እንዲሁም የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ሁለቱ ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን ከተመሰረተባቸው ክስ በነፃ ሲሰናበቱ፤ የተፈረደባቸውን ፍርድ ከጨረሱት መካከል ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ እና የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባ ከእስር መፈታታቸው አይዘነጋም፡፡

ሰበር ዜና፤ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ተፈረደባቸው

አዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ በሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ምድብ ችሎት፤ ዛሬ ሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. በ አቡበከር አህመድ የክስ መዝገብ ክስ ተመስርቶባቸው ከ3 ዓመታ በላይ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የነበረው የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ላይ የቅጣት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡ የኮሚቴው አባላትም ከ7 ዓመት እስከ 22 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ለ5 ዓመታት ከማኀበራዊ መብቶቻቸውም እንዲታገዱ የቅጣት ውሳኔ መተላለፉ ተጠቁሟል፡፡

 የኢትዮጵያ ሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት


የኢትዮጵያ ሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት

ዛሬ በተላለፈባቸው የቅጣት ውሳኔ የተላለፈባቸው 18ቱ የኮሚቴው አባላት፡-
አቡበከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ እና ካሚል ሸምሱ እያንዳንዳቸው 22 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
በድሩ ሁሴን፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሃመድ አባተ፣ አቡበከር አለሙ እና ሙኒር ሁሴን እያንዳንዳቸው 18 ዓመት እስር ሲፈረድባቸው፤
ሼህ መከተ ሙሄ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ሼህ ሰኢድ አሊ ጁሃር፣ ሙባረክ አደም እና ካሊድ ኢብራሂም እያንዳንዳቸው 15 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
ቀሪዎቹ ሙራድ ሽኩር፣ ኑሩ ቱርኪ፣ ሼህ ባህሩ ኡመር እና ጋዜጠኛ ዩሱፍ ጌታቸው እያንዳንዳቸው 7 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡
የዛሬውን ፍርድ በተመለከተም ድምፃችን ይሰማ ተቃውሞውን በመግለፅ፤ የሚከተለውን የትግል ስልት አጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለፅ 6 ነጥቦች ያሉት የአቋም መግለጫ ማውጣቱን ቢቢ ኤንን ጨምሮ የተለያዩ ዘገባዎች አመልክተዋል፡፡
የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ከመቋቋሙ በፊት በጥር 2004 ዓ.ም. ይፋ ጥያቄ መነሳት የጀመረው በአዲስ አበባ አወሊያ ትምህርት ቤት ጋር ተያይዞ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፤ የተጠ የቁ 3 መሰረታዊ ጥያቄዎች በወቅቱ ምላሽ ባለማግኘታቸው አሁን የተፈረደበት ኮሚቴ ሊቋቋም መቻሉንና ኮሚቴው አባላት ከመታሰራቸው በፊት በመፍትሄው ዙሪያ ከሚመለከታቸው የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ጋር በይፋ ውይይት ሲደረግ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

ሚኒስትሩ ስለ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት ላይ ጥርጣሬ አለኝ!

ብስራት ወልደሚካኤል

ትናንት ረቡዕ ሐምሌ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት የአማርኛው ፕሮግራም ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ስለ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት ላይ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ጥርጣሬም የመኘጨው ከኢህአዴግ ባህርይ እና ሴራ በመነሳት ሲሆን፤ይህም አስቂኝ እና ምናልባትም እጅግ አጠራጣሪ እና ሊሆን የማይችል ንግግር ሚኒስትሩ በመናገራቸው ነው፡፡ ጥርጣሬየንም እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡

አንዳርጋቸው ጽጌ

አንዳርጋቸው ጽጌ

1ኛ. የግንቦት 7 ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ሰኔ 2006 ዓ.ም. በየመን የፀጥታ ኃይሎች ትብብር ታፍነው ለህወሓት መንግሥት ተላልፈው ከተሰጡ ጀምሮ በኢትዮጵያ እስር ቤት ከመገኘታቸው ውጭ የት እንደታሰሩ፣ በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንዳሉ….እንዳይታወቅና ማንም ቤተሰብ እንዳይጎበኛቸው ተደርጓል፡፡ በብዙ ዲፕሎማሲያዊ ጫና በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ አምባሳደር ግሪጎሪ ዶሪ ብቻ ሁለት ጊዜ እንደጎበኟቸው ይታወቃል፡፡ ይሄንንም በተመለከተ አምባሳደሩ ስለ አቶ አንዳርጋቸው ደህንነት ሁኔታ ስጋት እንዳደረባቸው መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ነገር ግን ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም በቤተሰብም፣ በወዳጅ ዘመድም ሆነ በኃይማኖት አባት እንዳይጎበኙ የተከለከሉትን እና እስካሁንም የትኛው ወህኒ ቤት እንዳሉ ያልታወቁትን አቶ አንዳርጋቸውን የሀገሪቱን ልማት በተለይም ከአዲስ አበባ አዳማ ያለውን እንዲጎበኙ ተደርገው መደነቃቸውን እንዲሁም በሚሰቃዩበት ወህኒ ቤት ላፕ ቶፕ ኮምፒዩተር ተፈቅዶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ወደ መጨረሱ እንደደረሱ ነግረውናል፡፡ ዘይገርም ነው፡፡ ቢሆን ደስ ይላል፤ ግን ሊሆን የማይችልና የማይታመን ነው፡፡

ከህወሓት/ኢህአዴግ ባህርይ አንፃር በቤተሰብ ያውም በወላጆቻቸውና በእህቶቻቸው እና ወንድሞቻቸው እንኳ እንዲጎበኙ ያልተፈቀደላቸው ግለሰብ፤ ላፕ ቶፕ እንዲገባላቸውና መፅሐፍ እንዲፅፉ ሊፈቀድ አይችልም፡፡ ይህ የሚሆን ከሆነ ለምን እነ እስክንድር ነጋ፣ አንዱዓለም አራጌ፣ በቀለ ገርባ (ወህኒ ቤት ሳሉ)፣….ወዘተ በእጅ ፅሑፍ እንኳ የፃፉት ተራ ማስታወሻ እንኳ በየጊዜው እየተበረበረ ሲወሰድ እና ድጋሚም ምንም ዓይነት ነገር እንዳይፅፉ፤ እንደውም ለረጅም ጊዜ ማንኛውም መፅሐፍ እንኳ እንዳይገባላቸው ይከለከሉ እንደነበር እናውቃለን፡፡ በአሁን ሰዓት ራሱ በተለያዩ የሀገሪቱ ወህኒ ቤቶች እንኳን ላፕ ቶፕ ኮምፒዩተር ሊፈቀድ ይቅርና ሊያነቡት የጠየቁት መፅሐፍ እንኳ በማረሚያ ቤቱ አስተዳደር የዕውቀትና አስተሳሰብ ደረጃ ተመዝኖ ካልተፈቀደ እንደማይቻል ይታወቃል፡፡

ታዲያ ለአቶ አንዳርጋቸው ምን ያህል ቢራሩ ነው ላፕ ቶፕ የፈቀዱት? እውነት ከራሩ ለምን በቤተሰብና በአድናቂዎቻቸው እንዲጎበኙ አልተፈቀደም; ከዶ/ሩ እና አመራሮቻቸው መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ይህንን ቀላል ጥያቄ የVOA ጋዜጠኛዋ ለሚኒስትሩ ሳታቀርብ እንዴት እንዳለፈችው ገርሞኛል፤ ደንቆኛልም፡፡ ምናልባት የትናንቱ ላይ ተንተርሳ ድጋሚ ተዘጋጅታበት ልታነሳው ካሰበችም እንጠብቃለን፡፡
2ኛ. ከህወሓት/ኢህአዴግ ልምድና ባህርይ አንፃር ሌለው አስገራሚ ነገር፤ አቶ አንዳርጋቸው እየፃፉ ነው የተባለው መፅሐፍ በማን አማካኝነት ከወህኒ ቤት ወጥቶ ለንባብ ሊበቃ ነው? ይሄ ደግሞ ሌላ መልዕክት አለው፡፡

ከዚህ በፊት በስልጣን የቁም እስረኛ የሆኑት ክቡር አቶ አባዱላ ገመዳ ሳይወዱ በግድ ስማቸውን በማዋስ በስማቸው መፅሐፍ መፃፉን ስንቶቻችን እንደምናውቅ አላውቅም፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ ለህወሓት በተለይም ለራሳቸው የስልጣን መደላደል ይሆን ዘንድራሳቸው በመሰላቸውና በሚፈልጉት መንገድ ስለ ኦሮሞ ትግል መፅሐፍ ፃፉ፡፡ ከዚያም በህወሓት ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት መርህ መሰረት አቶ አባዱላ ገመዳ ፈቃዳቸው ሳይጠየቅና የመፅሐፉን ረቂቅ ሳያዩት በስማቸው ለገበያ እንዲበቃ ተደርጎ ራሳቸውም ከአንባቢው እኩል አነበቡት፡፡ በስልጣን የቁም እስረኛም ስለሆኑ ቅሬታም ሆነ አስተያየት መስጠት አልቻሉም፤ በመለስ ዜናዊ ተፅፎ በአባዱላ ገመዳ ስም ግን ገበያ ላይ ውሎ ተነቧል፡፡

አሁን ደግሞ ምንም ዓይነት አካላዊም ሆነ አዕምሯዊ ነፃነት እንዳይኖራቸው በማይታወቅ ወህኒ ቤት የሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስም፤ አቶ በረከት ስምዖን እና ሌሎች ተባባሪዎቻቸው በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ስም መፅሐፍ ለንባብ ሊያበቁ እያዘጋጁ መሆኑን ሚኒስትሩ አምልጧቸው የነገሩን ይመስለኛል፡፡ የመፅሐፉም ይዘት የኢህአዴግን “ልማት በማድነቅ” ፣ የተቃዋሚዎችን ስህተት፣ በተለይ የትጥቅ ትግል እያደረጉ ያሉትን እነ አርበኞች ግንቦት 7፣ ኦነግ፣ ትህዴን፣ አዴኃን፣ ኦብነግ፣ሲአግ፣አርዱፍ፣ … ወዘተ ድርጅቶችን በማብጠልጠል ላይ ተንተርሶ፤ አቶ አንዳርጋቸው ራሳቸውን ተሳስተው እንደነበርና በመፅሐፉ ይቅርታ ጠየቁ የሚል አዝማሚያ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህም የተወሰነ የፖለቲካ ድል ለማግኘትና ተቃዋሚዎችንም ለመምታት እንደ አንድ መንገድም ሊጠቀሙበት ያሰቡም ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ጨወታው የዓለም አቀፉን በተለይም የአውሮፕንና የእንግሊዝን ዲፕሎማሲያዊ ጫና ለማርገብና ኢትዮያውያንን ለማታለል የታሰበ እንጂ፤ አካላዊና አዕምሯዊ ነፃነት ተነፍገው ባሉበት ሁኔታ አቶ አንዳጋቸው መፅሐፍ ይፅፋሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እውነት ህወሓት/ኢህአዴግ ርህራሄ ተሰምቶት አቶ አንዳርጋቸውንም ሆነ አሁንም በጅምላ እየታሰሩ ያሉትንና የታሰሩትን የፖለቲካ እስረኞች ለምን በነፃ አያሰናብትም?
በተለይ ለአቶ አንዳርጋቸው ላፕቶፕ ኮምፒዩተር ተፈቅዶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ወደማገባደዱ ላይ ናቸው ሲሉ ሚኒስትሩ አይደለም አቶ አንዳርጋቸው አንድ ተራ ደራሲም ሆነ ፀሐፊ በግፍ ላሰረውና እያሰቃየው ላለ ዘረኛ፣ ጨካኝና አረመኔ አገዛዝ በምን ሂሳብ፣ በምን የዋህነት ነው መፅሐፍ ፅፈው እየጨረሱ መሆናቸውን ሚናገሩት? ሌላው ቀርቶ የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሩ የነበሩት አቶ ተፈራ ዋልዋ ባለቤትና የአቶ አንዳጋቸው ጽጌ እህት ወ/ሮ አይኔ ጽጌ እንኳ እንዲገበኟቸው ባልተፈቀደበት፣ አዲስ አበባ ከሞላ ቤተሰብና ወዳጆቻቸው እንኳ አንድ ሰው እንዲገበኝ ባልተፈቀደበት፤ ላፕቶፕ ተፈቅዶ መፅሐፍ እየፃፉ ነው መባሉ፤ አቶ አንዳርጋቸው ላይ ሌላ ሴራ እየተሰራ ነው ወይም ተሰርቶ አልቆ አደባባይ ሊያበቁት ተዘጋጅተዋል ማለት ነው፡፡

ቴድሮስ አድሃኖም

ቴድሮስ አድሃኖም

3ኛው ጥርጣሬ፤ አይበለውና* በአሁን ሰዓት ኢህአዴግ አቶ አንዳርጋቸው ላይ እጅግ ጭካኔ የተሞላበት ምርመራ በሚያደርግበት ወቅትም ይሁን ሆን ብለው ህይወታቸው ላይ ከባድ አደጋ አድርሰው በስማቸው እጅግ የረከሰና ለኢህአዴግ አመራሮች የሚመጥን አስተሳሰብ ለገበያ ካቀረቡ በኋላ፤ አቶ አንዳርጋቸው በህመም ምክንያት አሊያም ራሳቸው ላይ በወሰዱት ርምጃ እንደተጎዱ ተደርጎ ድራማ ሊሰራ አሊያም ተሰርቶ አልቆም ሊሆን ይችላል ብሎ መገመት እንደ ሟርት ሊቆጠር አይችልም፡፡ ምክንያቱም አቶ አንዳርጋቸውን ለመግደል አስመራ ድረስ ትልቅ ተልዕኮ ተሰንቆ መክሸፉ የአደባባይ ምስጢር በሆነበት እና እጅግ ለሚፈሩትና አጥብቀው ለሚፈልጉት አንዳርጋቸው እውነትም ራርተው ከሆነ ይልቀቋቸውና ርህራሄያቸውን እንመን፡፡ ካልሆነም ቤተሰብና ወዳጅ ዘመድ እንዲሁም አድናቂዎቻቸው እንዲጎበኗቸው በይፋ ይፍቀዱና እንያቸው፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ላፕ ቶፕ ገብቶላቸው መፅሐፍ እየፃፉ ነው፣ ሊጨርሱ ነው…ማለት ከኋላው የተሰራና የተጠናቀቀ አሊያም ሊሰራ የታሰብ ሴራ መኖሩን ከማረጋገጥ ውጭ እውነት ነው ብሎ መቀበል በ24 ዓመታት ውስጥ ኢህአዴግን ካለማወቅ በሚመነጭ የዋህነት ካልሆነ መረጃውን ትክክል ነው ማለት ሞኝነት ይመስለኛል፡፡

በአጠቃላይ ጥርጣሬዬ ህወሓት/ኢህአዴግ እንደለመደው ስንኩል ፖለቲካዊ ሴራ ድራማውን ለማጠናቀር ይረዳው ዘንድ በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስም መፅሐፍ እያዘጋጀ መሆኑን አሊያም አዘጋጅቶ መጨረሱን በጓዳ ርስ በርስ ሹክ የተባባሉትን አምልጧቸው እንደተናገሩት እቆጥረዋለሁ፡፡ ቢቻል በአሁን ወቅት የእንግሊዝ መንግሥት ስለ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ወቅታዊ ሁኔታ በአካል ሄዶ ማረጋገጥ እንዳለበትም መጠቆሙ የሚከፋ አይመስለኝም፡፡
ሌላው ሚኒስትሩ ጥሩ ናቸው በሚል ባይሆንም ስለ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በተናገሩት “መረጃ” ዙሪያ ማመስገኑ የሚከፋ አይመስለኝም፡፡ ለነገ የሚሆን መረጃ ጀባ ብለውናል ብዬ ስለማምን፡፡
በተረፈ አቶ አንዳርጋቸው ባሉበት ፈጣሪ ጠብቆ በሙሉ ጤንናትና ሰላም እናያቸው ዘንድ ተመኘሁ፡፡