እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ 28 ቀን ቀጠሮ ተጠየቀባቸው
የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ትናንት መጋቢት 21 አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ እነ ብርሃኑ ተክለያሬድን ‹‹ለግንቦት 7 አባላትን መልምለው ወደ ኤርትራ በመላክና ቡድኑን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ተይዘዋል›› ብሏል፡፡
ጠበቃው እነ ብርሃኑ ተ/ክለያሬድ ለግንቦት ሰባት ሲመለምሉም ሆነ አባል ሲሆኑ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ እንደሌለ በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምመረምራቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ሌሎች የምንይዛቸው ግብረ አበሮችም አሉ፡፡ መረጃ ያጠፉብናል፡፡›› በሚል ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆ 28 ቀን ተፈቅዶለታል፡፡ ሚያዚያ 19 ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡
ፖሊስ ሌሎች ሰዎች ይዘውት የተነሱትን መሳሪያ በማሳየትም እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ እንደነበር ለማሳየት በመረጃነት አቅርቧል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹የማህበራዊ ሚዲያ ላይ ምርመራ ለማድረግና መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተጠርጣዎቹን ማሰር ተገቢ አልነበረም፡፡ ሌሎች ሰዎች የያዙትን መረጃ እነሱን ለመክሰስ መጠቀም ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ ተቃውመዋል፡፡
በሌላ በኩል ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ የታሰረበት ቤት መብራት ስለማይጠፋ አይኑ ላይ ለከፍተኛ ችግር እንዳደረሰበት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ለ15 ደቂቃ ፀኃይ እንዲሞቁ ከሚፈቀድላቸው ውጭ ወደ ከታሰሩበት ቤት ውጭ መውጣት እንደማይፈቀድላቸውና ቤተሰቦቻቸውም እንዲጠይቋቸው እየተደረገ አለመሆኑን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡
የዞን9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ቃል
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡
ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ ተሰሙት ምስክሮች
7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡
8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡
9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡
10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)
11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡
12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡
በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡
ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡
ምንጭ፡- ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ
ፍትህ መረገጡን በአደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል!
ለኔ እዉነተኛው የአንድነት ፓርቲ ትናንት መጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም. በፍርድ ቤት ውሳኔ ተቀብሯል፡፡ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል እንደሆነ ቀድም ሲል አውቀናል፡፡ ዳኛ ብርቱኳንም፣ ፍርህይወትም ዳግም አልተከሰቱም፡፡ እንደ ኢህአዴግ የምርጫ ውጤት 99.6 ከመቶ አመራሩና አባላቱ በምርጫ ቦርድ እንዲበተኑ የተበየነበት እንዲሁም በደጋፊዎች የተገዛ ንብረት ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ በመንግስት ታጣቂ ፖሊሶች የተዘረፈበት አንድነት የፍትህ ተቋሙን ለመፈተሸ ምርጫ ቦርዱን መክሰሱ ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድን መክሰሳችን አግባብ እንዳልሆነ አንቀጽ ተጠቅሶ ከማስፈራሪያ ጋር ክሱ ዉድቅ ተደርጓል፡፡ በዚህም ፍትህ መረገጡን ባደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል፡፡ ቀጣዩን በቀጣይ ሂደት የምናየዉ ይሆናል፤እንደሚፈልጉት ተበትነን አንቀርም፡፡ አንድነቶች በያለንበት እንረጋጋ!!
ታላቋ ምዕራብ አፍሪካዊት ሃገር ናይጀሪያ እዚህ የደረሰችዉ ዉድ ዋጋ ከፍላ ነዉ፡፡ ከናይጀሪያም በላይ ዋጋ ብንከፈልም በልተዉ በማይጠግቡ በሎች ትግሉ እየተነጠቀ ዛሬም እዛዉ ላይ ነን፡፡ ታላቅዋ የምስራቅ አፍሪካ ኮከብ ሀገረ ኢትዮጵያ በልማት ስም ክብሯ እንዲወርድ እየተደረገች ትገኛለች፡፡ እናም በዲፕሎማሲ፤በዲሞክራሲ፤በኢኮኖሚም ይሁን በሁለንተናዊ ልማት የአለም ማህበረሰብ በአፍሪካ ትኩረት ናይጀሪያ ሆናለች፡፡ ኢትዮጵያ የምትፈለገዉ ለክፍለ አሁጉሩ የደህንነት አጋርነት ብቻ ነዉ፡፡
የናይጀሪያ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና(የተቀናቃኝ ፓርቲዎች ትብብርና ዉህደት ያስከተለዉን ዉጤትም ልብ ይሏል) የተወዳዳሪ ግለሰቦች ሚና ቀላል ባይሆንም ለናይጀሪያ ተስፋ የሆናት ግን ህዝቡ ነዉ፡፡ የኢትዮጵያችንም የለዉጥ ተስፋ ህዝቡ ነዉ፡፡ በዚህ ወቅት የተቃዋሚ የፖለቲካ ሃይሎች አሰላለፍም የጎላ ድርሻ ይኖረዋል፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ‘ሰጡ’
“ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ህወሓት/ኢህአዴግ ነው” አብርሃ ደስታ
“የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” የሺዋስ አሰፋ
በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገቡ የተካተቱ ተከሳሾች በተከሰሱበት ድርጊት ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ፡፡
የሰማያዊ፣ የአንድነት እና የዓረና ትግራይ ፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ 10 ተከሳሾች መጋቢት 10 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡ ሲሆን ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ በዚህ መሰረት ከአንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ጀምሮ፣ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም?” የሚል ተመሳሳይ ጥያቄ ለእያንዳንዳቸው የቀረበላቸው ሲሆን ብዙዎቹ ተከሳሾች ምላሻቸውን በቀጥታ ለመስጠት አለመፈለጋቸውን አሳይተዋል፡፡
1ኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ለቀረበለት ጥያቄ፣ “በአቃቤ ህግ እና በፖሊስ ተቀነባብሮ የቀረበብኝን ክስ በተመለከተ ለክሱ እውቅና ላለመስጠት ምንም አልልም፡፡ በክሱ ላይ አስተያየት በመስጠት ለጸረ-ሽብር አዋጁ እውቅና መስጠት አልፈልግም” የሚል መልስ በመስጠቱ ፍርድ ቤቱ ክሱን ክዶ ቃል እንደሰጠ አድርጎ መዝግቦታል፡፡
2ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት እንዳልፈጸምኩ እንኳን እኔ ከሳሾቼም በደንብ ያውቃሉ፡፡ ከሳሾቼ እኔ ድርጊቱን የመፈፀም ፍላጎቱም ሀሳቡም እንደሌለኝ ያውቃሉ” ብሏል፡፡
3ኛ ተከሳሽ ዳንኤል ሺበሽ ደግሞ፣ “እኔ ስለ ሽብር የሰማሁት ከአልቃይዳው መሪ ኦሳማ ቢላደን እና መለስ ዜናዊ ነው፡፡ እኔ አሸባሪ አይደለሁም፤ ሀሳቡም ሆነ ፍላጎቱም የለኝም፡፡ ባህሌና እምነቴም አይፈቅድልኝም” ሲል ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡
4ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታ “አሸባሪ ማለት የፖለቲካም ሆነ ሌላ ዓላማውን ሰላማዊ ዜጎችን በማሸበር ለማስፈፀም የሚሰራ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ድርጅት ህወሓት/ኢህአዴግ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የዚህ አሸባሪ ድርጅት ተቃዋሚ ነኝ” ብሏል፡፡
5ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ በበኩሉ፣ “በመጀመሪያ ለመጨረሻ ጊዜ ስለሆነ የምናገረው እንዳታቋርጡኝ አደራ እላለሁ፡፡ ክሱ ቅንብር ነው፡፡ ዳኞችም ህጉ የሰጣቸው ነጻነት አይታይባቸውም፡፡ ይህ 19ኛ ወንጀል ችሎት የጦር ችሎት ነው የሚመስለኝ፡፡ ስለሆነም የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” ሲል ተናግሯል፡፡ የሺዋስ በዳኞች በተደጋጋሚ ንግግሩ እንዲቅረጥ ተደርጓል፡፡ በመጨረሻም ክሱን ክዶ ቃል ሰጥቷል በሚል ተመዝገቦለታል፡፡
6ኛ ተከሳሽ ዮናታን ወልዴ፣ “የተዘጋጀብኝን ክስ ያለፍቃዴ እንድተውን እየተገደድኩ ነው” ብሏል፡፡
7ኛ ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞን ደግሞ፣ “የተቀነባበረ ክስ ላይ ምንም ማለት አይቻልም” ብሏል፡፡
8ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማ፣ “ነፃ ሰው ነኝ፡፡”
9ኛ ተከሳሽ ባህሩ ደጉ “ባህሉንና ፈጣሪውን ከሚያከብር ማህበረሰብ ወጥቼ አሸባሪ ልሆን አልችልም” ሲል አስረድቷል፡፡
10ኛ ተከሳሽ ተስፋዬ ተፈሪ ደግሞ፣ “ድርጊቱን አልፈጸምኩም” ብሏል፡፡
በአጠቃላይ ተከሳሾች ክሱ ላይ የተጠቀሰውን ድርጊት ክደው ቃል በመስጠታቸው አቃቤ ህግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ለግንቦት 13፣ 14፣ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ለተከታታይ 3 ቀናት ምስክር እንዲሰማ ቀጠሮ መሰጠቱን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክታል፡፡
የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
በአብዛኛዎቻችን ኢትዮጵያዉያን አንድ ጥሩ ባህል አለን፡፡የምንወደዉንና የሚመቻንን ሰዉ በሞት ስናጣ እርም የማዉጣት ባህል፤ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሆኖ አገኘሁት፡፡ሠዉና የፖለቲካ ድርጅ ባይገናኙም በጉልበተኛ ሃይል እንዲገናኙ ሲደረግ ከማገናኘት ዉጪ ምርጫ የለንምና እናገናኛቸዋልን፡፡
አቅምና ሁኔታዎች በፈቀዱት መጠን የወቅቱን ያገራችን ችግር በመፍታት በኩል የራሱን አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት፤ የኢህአዴግ ሰዎችን ጨምሮ ያብዛኛዉ ተራማጅ ኢትዮጵያዊ ቤት እንዲሆን አድርገን ስንገነባዉ(ሲፈጥሩትም ለዚህ ኣላማ ነበር ተብሎ ይታመናል) የነበረዉን አንድነት ፓርቲን በፖለቲካዊ ዉሳኔ የሆነዉ እንዲደርስበት ተደርጓል፡፡አማራጭ እንዲኖር የማይፈልጉት በከፍተኛ የመንግስት ሃላፊነት የተመደቡቱ ጥቂት የህወሓት ቡድኖች የማይጠቅማቸዉን ዉሳኔ እንደወሰኑ ይታወቃል፡፡ ተዉኔቱ በማን ተዘጋጅቶ እነማን እንደተጫወቱትና እነማን ደግሞ ለህዝቡ እንዳደረሱት በተደጋጋሚ ገልጸነዋል፡፡
ፓርቲዉን በተለያዩ ስሞች ሲከሱና ሲፈርጁ ቆይተዉ አመራሩንም በእስርና ድብደባ እያሹ እንዳልተንበረከከና ይበልጥ መጠናከሩን ሲያረጋግጡ ለዚህ ዉሳኔ በቅተዋል፡፡ በ40 ዓመታት ታሪኩ ፓርቲዎችን በመብላትና ከዉስጥና ከዉጭ የሚነሳ ልዩነትን በማቻቻል ሳይሆን በማጥፋት የሚታቀወቀዉ ጥቂት የህወሓት ቡድን አንድነት ፓርቲን ከማጥፋት አሁን ወደ መረጠዉ ደረጃ እንዲወርድ አድርጓል፡፡ታሪክ ሁሉን ይፈርዳል፡፡በጨለማዉ ዘመን ግፍ የተፈፀሞባቸዉ ቡድኖችና የፈሰሰዉ ደምም ተደብቆ ኣልቀረም፡፡ፖለቲካችንን ለማዘመንና ያለፈዉ ግፍ ሁሉ ባይረሳም በይቅር መታለፍ አለበት ብለን ለተነሳን ሃይሎችም እድሉን (በጉልበት በህዝብ ሃብትና በያዙት ስልጣን ተጠቅመዉ) ዘግተዉብናል፡፡ በደም መጨማለቅ በዚህ ያበቃ ዘንድ አሁንም እንታገላለን፡፡የፖለቲካ ትግሉ ሂደትም አይቆምም፡፡ያዉም ይብልጥ የመጠናከር እድል አግኝቷል ተብሎ ይታመናል፡፡የሚያቆመዉ ሃይል የለም፤መጪዉ ግዜ የለዉጥ ነዉ፡፡ለዉጡ እንደይሰረቅና ለሁሉም ይመች ዘንድ የጋራ ትስስርን እንደሚጠይቅ እሙን ነዉ፡፡
ለግዜዉ ከጀርባ ያለዉን ፖለቲካዊ ግፊት ለሌላ ፖለቲካዊ ትግል ትተን የምርጫ ቦርድ ዉሳኔን በመቃወም ክስ መስርተን ወደ ፍርድ ቤት ተብየዉ ወስደንዋል፡፡ ወደ ህግ ለመዉሰድ ስንወስን የፓርቲ ስምና አርማ አስጨንቆን አይደለም፡፡ የደጋፊዎችና አባላት ንብረት ለይምሰልም ቢሆን ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ፖለቲካዊ ዉሳኔ እንግበዉ በመጡ ከህዝብ ግብር በተሰበሰበ ደሞዝ የሚተዳደሩ የክፍለ ከተማ ፖሊስ ሃይሎች ( ህዝባዊ ሃለፊነትን የተሸከመ ተቋም በፖለቲካ እዝና ዉሳኔ የፓርቲን ንብረት ይዘርፋል የሚል እምነት አልነበረንም) ስለተዘረፈብን ሃላፊነታችንን ለመወጣትና ታሪካዊ እልባት እንዲኖረዉ ለማስቻል ነዉ፡፡እንጂማ ራእያችን በእያነዳንዳችን ዉስጥ ቢሆንም የወቅቱ ትግል ግን የነፃነት መሆኑን አጥተነዉ አይደለም፡፡
በወቅቱ የብሔራዊ ስራ አስፈፃሚዉ የወሰነዉ ዉሰኔ የመድብለ ፓርቲ ስርኣቱ ከምን ግዜዉም በላይ ፈተና ላይ መዉደቁና አዲስ ፓርቲ መመስረት ችኮላና ህዝቡን ስርአቱ ለመድብለ ፓርቲ አሁንም ይመቻል፤ጥፋቱ የኛ ነዉ ብሎ መዋሸት መሆኑ፤እስኪያጠፋቸዉ ድረስ ሌሎች ፓርቲዎች ጋ መቀላቀል በተላይም ከምርጫዉ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ተስፋ ያላቸዉ አባላት የግል ምርጫቸዉ መሆኑንና አመራሩም ይህን እንደማይቃወም፤የፓርቲዉ አባላት ጉዳዩ በፍ/ቤት እስኪቋጭ ድረስ አመራሩን እንዲጠብቁ ይሀም ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ከሰዓት እንዲቀርብና ተወያይቶ ዉሰኔ እንዲሰጥበት የተስማማ ሲሆን በወቅቱ ሁለት አባላት ብቻ አልተገኙም፡፡ከሰኣት ቢሮዉ የፖሊስ ደንብ በለበሱ የመንግስት አካላት ተዘረፈ፡፡ይህ ደግሞ አእላፍ ወንድሞቻችን ላለፉት 40-50 አመታት በተለያየ ጉራ ተሰልፈዉ በተሰዉለት በተላይም በትግረዋይ ደም/ የትግል ዉጢት ሌላዉ ቀልድ እንደመሆኑ ጉዳዩ አብዛሃዉ የአንድነት ደጋፊና አባል በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንወስደዋለን ባልነዉ መሰረትእየታየ ይገኛል፡፡በመሆኑም ጉዳዩን መከታተል የእያነዳንዱ የአንድነት አባልና ደጋፊ የህሊና እዳ ይመስለኛል፡፡በአንድነት ቀብር ላይ አሁንም አንድነታችንን በማረጋገጥ ባብዛሃ ዉሳኔ ቀጣዩን መንድ መጓዝ እንጂ ልንለያይ የሚጋብዝን መንገድ መከተል ያለብን አይምስለኝም፡፡ካለፉት የተቃዉሞ ጎራ በጎዉን ትምህርት መቅሰም የሚኖርብን እንዳለ ይሰማኛል፡፡በችኮላ ፓርቲ ለመመስረት የሚደረግ ሩጫ የስልጣን ሀይልነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለህዝባችን ፋይዳ አለዉ ብየ አልገምትም፡፡ ምርጫቸዉ ላደረጉት ጓዶቼ ግን ስህተት ቢሆን ምርጫቸዉን አከብራለሁ፡፡
ጉዳያችንን ወደ ፍርድ ቤት ስንወስደዉ በፍትህ ተቋማቱ ምናልባትም በሰላማዊ ትግል ስልት ስርኣቱን ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች መካከል ከቀድሞዉ ቅንጅት ቀጥሎ የግፍ ፍርድ ሲበየንበት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት እንደሆነ ስተነዉም አይደለም፡፡ ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል የሚለዉ ብሂል እንዳለ ሆኖ ብርቱኳን መደቅሳ፤ዳኛ ፍረህይወት እና ሌሎች (ለህሊናቸዉ የተገዙ ዳኞች አልፎ አልፎም ቢሆን) የተገኙት በዚህ አፋኝ ስርኣት በዘረጋዉ መዋቅርና በህዝባችን ዘንድ እምነት በታጣባቸዉት የፍትህ ተቀዋማት ውስጥ ነዉ፡፡ታድያ እየተፈተኑ የሚወድቁትን ተቋማት ሳይሆን ግለሰብ ዳኞችንም ለመፈተን ይህን ታሪካዊ ክስ ስናቀርብ የግለሰቦችን የህሊና ዳኝነትንም ተስፋ ባለመቁረጥ ጭምር ይሆናል፡፡ ሁሌም እንደምንለዉ ፓርላማ ተቀምጦ የተከበሩ እየተባሉ ለመጠራት ሳይሆን ትግላችን ለለዉጥ ነዉና ድንክየዉን አንድነት ቢመለሱልንም ባይመሉሱልንም፤ የህዝብ ከሆነዉ ትግል መሃል ሆነን ፖለቲካዉን ከመስራት አንታቀብም፡፡ዉሳኔዉም በሁሉም የለዉጥ ሃይሎች ቀጣይ እንቅስቃሴ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡የአንድነት ልጆች ህወሓት ለመደዉ የጥባጥቤ ጨዋታዉ ቦታ ይኖረናል ተብሎ አይታሰብም፡፡አንድነታቸንን እንደ ጠበቅን የሚቀብሩት ከሆነ የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
ላለፉት አምስት አመታት ብዙዎቹ በእስር የሚማቅቁበት የተሰደዱለትና የቆሰሉ፤ የደሙለት ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የብዙ ወገኖችን እና ተቋማትን የፍትህ ጥያቄ በማዉሳት ባደባባይ የጮኸዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡በኢትዮጵያዊነት ማእቀፍ ዉስጥ የብሄረሰቦችን እና የቡድኖችን መሰረታዊ የፖለቲካ ጥያቄ ለመመለስ ቁርጠኝነት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ የህዝብን ጥያቄዎች በጠራ መልኩ በማዉሳት ድምጻቸዉን ከሚያሰሙ ፓርቲዎች ዉስጥ ተጠቃሹ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የቅርርብ፤የመደማመጥና የመከባበር ፖለቲካ እንዲኖር ባሳለፋቸዉ አጭር አመታት ጥረት ያደረገ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ በዚህም ከህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሃገራቸዉ በጎዉን ለዉጥ የሚሹ በርካታ የኢህኣዴግ ተራ አባላትና አንድንድ ባለስልጣናትም ጭምር በበጎ አይን ይመለከቱት እንደነበር ገምግመናል፡፡ በዚህ ወቅት አወንታዊ ተፅእኖ ያመጣል ተብሎ በመፈራቱ ግን ከ40 አመት በኃላም ትቂቱ የህወሓት ቡድን በለመደዉ ስልቱ በልቶታል፡፡
ይህን ድርጊት ለዉጥ ፈላጊ ሃይሎች በጥሞና ይከታተሉታል ተብሎ ይገመታል፡፡የምትችሉ ሁሉ ፍርድ ቤት በመገኘት እስከ ታሪካዊዉ ዉሳኔ እለት ድረስ ሂደቱን ለመዘገብና ለታሪክ ምስክር ለመሆን፤ እንዲሁም አጋርነታችሁን ለመግለፅ ትገኙ ዘንድ የክብር ጥሪ ተላልፏል፡፡እዉነተኛ አንድነት ነባር አመራር፤አባለትና ደጋፊዎች ጉዳዩን በአንድነት እንቋጭኛ እንደስማቸን በአንድነት ቦይ እንፈስ ዘንድ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡
አቶ ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)





