Tag Archives: Ethiopian Justice

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና አቶ አንዱዓለም አራጌ 5 ዓመት እስር እንደዋዛ

ጋዜጠኛና ጦማሪ እስክንድር ነጋ እና የሰላማዊ ትግል አቀንቃኝ ፖለቲከኛ አቶ አንዱአለም አራጌ በሽብር እና በሃገር ክህደት ወንጀል ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው እስር ቤት ከገቡ መስከረም 3 ቀን 2009 ዓ.ም ድፍን አምስት ዓመት ሆናቸው፡

እስክንድር “ንፁህ ስለሆንኩኝ፣ የቀረበብኝ ማስረጃ የሌለ በመሆኑ እንዲሁም ፍርድቤቶችን የሚያህሉ የተከበሩ ተቋማት የበቀል የአፈናና የጭቆና መድረክ መሆን ስለሌለባቸው በነፃ እንድለቀቅ የተከበረውን ፍርድቤት እጠይቃለሁ” ብሎ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድቤት ይግባኙን በነሐሴ 2004 ዓ.ም ያቀረበ ቢሆንም የከፍተኛው ፍርድቤት የፈረደበትን የአስራ ስምንት ዓመት ፅኑ እስራት እና አምስት አመታት ህዝባዊ መብቶች እግድ ጠቅላይ ፍርድቤቱም አፅንቶበት የፍርዱን ሩብ አመታት በእስራት አሳልፏል፡፡

በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር አዲስ አበባ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት አምስት አመታትን በእስር ሲያሳልፍ ዘንድሮ የ48 አመት ጎልማሳ የሚሆነው ጦማሪው እስክንድር ነጋ በየኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ መንግስት ለሰባተኛ ጊዜ ሲታሰር በበርካታ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብተ ተሟጋች ድርጅቶች እስራቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሆን ደምፃቸውን ከፍ አድርገው አምስቱንም አመታት ለኢትዮጵያ መንግስት ውትወታቸውን አስምተዋል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፍርድቤት የችሎት ሂደቱን በመከታተል ላይ እያለ በግንቦት ወር 2004ዓ.ም ፔን አሜሪካ ከተባለ አለማቀፍ ድርጅት በአደገኛ የመገናኛ ብዙሐን ድባብ ውስጥ ሆኖ በመፃፍ ላደረገው አስታዋፅኦዖ “የመፃፍ ነፃነት ሽልማትን” አግኝቷል፡፡ በዚሁ አመት አለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተማጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል እስክንድር ነጋ የህሊና እስረኛ ስለመሆኑ አውጇል፡፡

ለሰባተኛ ጊዜ ለእስር በተዳረገ በአንድ አመት ከአራት ወራት ጊዜ ውስጥ በታህሳስ 2005ዓ.ም ደግሞ የሂውማን ራይትስ ዎች የነፃ ንግግር ሽልማት አሸናፊ ከመሆኑ በተጨማሪ በ36ተኛው አለማቀፍ የፀሃፊዎች ፌስቲቫል ላይ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ “የአንድ ስብዓዊነት ሽልማት” አሸናፊ ሆኗል፡፡

በጋዜጠኝነት ሙያው በሚሰራው ስራ የኢትዮጵያ የፀረ ሽብር አዋጅ ቀደምት ሰለባ የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር በ1997 ዓ.ም የተደረገውን አገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ መንግስት በአገር ክህደት፣ አመፅ በመቀስቀስ፣ህገ መንግስት እና ህግ መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል በመናድ ወንጀል ተከሶ ፍርድ ቤት የፈረደበት ቢሆንም አንድ አመት ከአምስት ወራት እሰራት በኃላ ክሱ ተቋርጦ መለቀቁ ይታወሳል፡፡

የኢንተርናሽናል ወመንስ ሚዲያ አሶሴሽን “የብርቱ ጋዜጠኛ” ሽልማት አሸናፊ የጋዜጠኛ እስክንድር ባለቤት ጋዜጠኛ ሰርክዓለም ፋሲልም የ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ ከባለቤቷ ጋር በተመሳሳይ ክስ በአንድነት ታስራ በቃሊቲ እስር ቤት ሳለች የመጀመሪያ እና ብቸኛ ልጃቸውን ናፍቆት እስክንድርን ተገላገላለች፡፡

የያኔው ስድስተ አመት ህፃን ልጁን ከትምህርትቤት ወደ ቤት እያመጣ ሳለ በድንገት ያለምንም ማስጠንቀቂያ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው እስክንድር ነጋ እነሆ ዛሬ አብረውት ከተከሰሱት 23 አባሪዎቹ ጋር አምስት አመትን ሲደፍን የቀደሞ የአንድነት ፓርቲ ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበርና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አንዷለም አራጌም የእድሜ ልክ እስራቱን በቃሊቲ ማረሚቤት እየገፋ ይገኛል፡፡

‹ምርጫ 97ን›› ተከትሎ ወህኒ ከወረደው የቅንጅት አመራር አንዱ የነበረው የያኔው ወጣት የአሁኑ ጎልማሳ፣ በብዙዋች ዘንድ የሰላማዊ ትግል አርበኛ ተበሎ የሚወደሰውአንዷለም አራጌ የቅጥት ማቅለያ እንዲያቀርብ በፍርድቤት ሲጠየቅ አንዷለም አራጌ እንዲህ ብሎ ነበር ማቅለያውን ያቀረበው፡፡ “እኔም ለልጆቼ፣ ለወገኖቼ፣ ለአገሬ እና ለራሴ በመረጥኩት ሰላማዊ ትግል ስታገል ቆይቻለሁ፡፡ የበደልኩት ህዝብ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ወንጀል ሰርቻለሁ ብዬ አላሰብም፡፡ ውስጤ ፍፁም ሠላማዊ ነው ከሳሾቼ የሚስጡኝን የግፍ ፅዋ ለመጠጣት ዝግጁ ነኝ፡፡”

አቶ አንዷለም አራጌ “ያልተሄደበት መንገድ” የሚል የመጀመሪያ መጸሐፉን በእስር ላይ ሆኖ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለአንባቢያን አደርሷል፡፡ በ2007 ዓ.ም ሰኔ ወር ደግሞ “የሀገር ፍቅር እዳ” የተሰኘው ሁለተኛ መጽሐፋ ዳግም ለህትመት በቅቷል፡፡

እስካሁንም ድረስ በእስር ላይ የሚገኙት እነዚህ የሰላማዊ ትግል አርበኞ አዲሱን አመት 2009 ዓ.ም የተቀበሉት አምስተኛ አመታቸውን በማሰብ ነው፡፡

እስክንድር ነጋ እና አንዷዓለም አራጌ በፍትህ እጦት አመታትን በእስር እንዲያሳልፉ ሲገደዱ እስራቸው አገሪቷ በዓለም አቀፍ ህግ መደረክ ተገዢ እሆናለሁ ብላ ቃል የገባችባቸውን የቃልኪዳን ሰነዶች ሁሉ የናደ ሰለመሆኑ የሰበዓዊ መብት ተሟጋቾች በተደጋጋሚ ሲሞግቱ አምስት አመታት አልፈዋል፡፡

ዛሬም አስራቸው ህገ መንግስቱን የጣሰ፣ አላግባብ፣ ኢፍታዊ እና የሰብዓዊ መብቶቻቸውን ያላከበረ ነው ፡፡ አንዱአለም በተለምዶው ቅጣት ቤት ተብሎ የሚጠራው ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግበት ክፍል ውስጥ ታስሮ ሲገኝ እስክንድር በቃሊቲ የተለያዩ ዞኖች ታስሯል፡፡ ሁለቱም እስረኞች ከቅርብ ቤተሰብ ውጪ ማንም እንዳይጠይቃቸው የተከለከሉ ሲሆን ከእስራቸው እስከ አያያዛቸው ኢሰብአዊነትን እያስተናገዱ አምስት አመት አስቆጥረዋል፡፡
ምንጭ፡- EHRP

በደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ

በባህር ዳር በአበባ እርሻዎችና በሌሎች ንብረቶች ውድመት ደርሷል

– የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ አሳስቦኛል አለ

በአማራ ክልል በደቡብ ጎንደር ዞን ዋና ከተማ ደብረ ታቦር ማረሚያ ቤት በደረሰ ቃጠሎ በእስረኞች ላይ ጉዳት ደረሰ፡፡ የመከላከያ ሠራዊት እስረኞች እንዳያመልጡ ዙሪያውን ከቦ እንደነበርና ሊያመልጡ የነበሩ በርካታ እስረኞች መሞታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የእሳት አደጋው የተከሰተው ሐሙስ ነሐሴ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ እስረኞቹ ከአደጋው ለማምለጥ መሞከራቸውን አስረድተዋል፡፡ ይሁን እንጂ አካባቢውን በፍጥነት የከበበው የመከላከያ ሠራዊት እስረኞቹ እንዳያመልጡ ሲተኩስ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

debre-tabor-prison-fire

በእሳት አደጋው ሳቢያ ከፍተኛ ጉዳት በማረሚያ ቤቱ ላይ መድረሱንና ሊያመልጡ በነበሩ እስረኞች ላይም ጉዳት እንደደረሰ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የደቡብ ጎንደር ማረሚያ ቤቶች መምርያ ኃላፊ ምክትል ኮማንደር መንጌ ከበደ ቃጠሎው የተነሳው በኤሌክትሪክ መስመሮች መገናኘት መሆኑን ገልጸው፣ ሊያመልጡ የነበሩ ሁለት እስረኞች መገደላቸውንና ከእስረኞች ደግሞ ሁለት መቁሰላቸውን አስረድተዋል፡፡
በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተስፋፋ የሚገኘው አመፅ፣ ከመንግሥት ጋር ቁርኝት አላቸው በተባሉ የግል ባለሀብቶች ንብረቶችና የሕዝብ አገልግሎት መስጫ ተቋማት ላይ ያነጣጠረ ጉዳት እያደረሰ መሆኑም ተገልጿል፡፡

ኢስመራልዳ (Esmeralda Farms) የተባለው በባህር ዳር የሚገኘው የኔዘርላንድ ባለሀብቶች የአበባ እርሻ በእሳት ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡
መቀመጫውን በኔዘርላንድ ያደረገው የአበባ ኩባንያው ዋና ቢሮ ባወጣው መግለጫ፣ በፖለቲካ ተቃውሞው ምክንያት በባህር ዳር የሚገኘው የአበባ እርሻ (ኮንዶር ፋርም) በእሳት ሙሉ በሙሉ መውደሙንና የኩባንያው አጠቃላይ ኢንቨስትመንት አሥር ሚሊዮን ዩሮ እንደሆነም አስታውሷል፡፡

በኢትዮጵያ ከሚገኘው ቢሮ ጋር መገናኘት አለመቻሉን የሚገልጸው መግለጫው፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጃችን በቀውሱ ምክንያት ከአካባቢው በመልቀቃቸው መረጃዎችን ማግኘት አልተቻለም፤›› ብሏል፡፡

በመንግሥት ላይ የተነሳው ተቃውሞ በአካባቢው በሚገኙ የአበባ እርሻዎች ላይ ጉዳት ማድረስ መቀጠሉንና አሥር ያህል የአበባ እርሻዎች መቃጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ኮንዶር ፋርም የተባለው የአበባ እርሻ ሲቃጠል በአካባቢው የመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች የነበሩ ቢሆንም፣ ጉዳቱን ያደረሱት ከፀጥታ ኃይሎች ቁጥር በብዛት የሚበልጡ በመሆናቸው ማዳን አለመቻሉን ኩባንያው ገልጿል፡፡
መጋዘኖች፣ የማቀዝቀዣ ክፍሎች፣ ትራክተሮች፣ የጭነት ተሽከርካሪዎች፣ ኮንቴይነሮችና ማሸጊያዎች በሙሉ በእሳት መውደማቸውን አስታውቋል፡፡

‹‹ሁሉም ጠፍቷል፡፡ የአሥር ሚሊዮን ዩሮ ኢንቨስትመንትና የረጅም ዓመታት ጥረት በአንድ ቀን ወድሟል፤›› ሲል በመግለጫው የደረሰውን ጉዳት አመልክቷል፡፡

ሌላው በየመኑ ባለሀብት መሐመድ አልካሚን የተቋቋመውና ከ500 በላይ ሠራተኞች የነበረው የአበባ እርሻ ይገኝበታል፡፡
ለባህር ዳር ከተማ የውኃ አቅርቦት ምንጭ የሆነው እንፍራንዝ ከተማ አካባቢ የሚገኘው የጥቁር ውኃ የውኃ ማጠራቀሚያ ጋንም ቃጠሎ ደርሶበታል፡፡ ይህም በከተማዋና በአካባቢዋ የውኃ አቅርቦት ላይ እጥረት እንደሚያስከትል እየተነገረ ነው፡፡
በተያያዘ ዜና በክልሉ ውስጥ ያለው ተቃውሞ እየተባባሰና በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ የሚደርሰው ጉዳት እየጨመረ መምጣቱን መረጃዎች እያሳዩ ነው፡፡

በተለይም ማክሰኞ ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትሩ በክልሉ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ ለማስቆም የፀጥታ ኃይሉ ሕግ እንዲያስከብር ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውን ከገለጹ ጀምሮ ሰዎች መሞታቸውን፣ የዘር ጥቃት ተፈጸመባቸው የተባሉ ደግሞ ወደ ጎረቤት አገር እየተሰደዱ መሆናቸው እየተገለጸ ነው፡፡

በተለይ በአምባ ጊዮርጊስ፣ በደብረ ታቦር፣ በመተማ ዮሐንስና በአጎራባች አካባቢዎች የሰው ሕይወት መጥፋቱን የሚገልጹ ቁጥሮችም እየጨመሩ ስለመውጣታቸው መረጃዎች እየጠቆሙ ይገኛል፡፡ ነገር ግን በመንግሥት በኩል እስካሁን ምንም ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ አልተሰጠም፡፡

ሪፖርተር ከምንጮች ማረጋገጥ እንደቻለው በክልሉ የተለያዩ ከተሞች የመከላከያ ሠራዊት እየገባ ሲሆን፣ የከባድ መሣሪያ ተሽከርካሪዎች መታየታቸውን ለማወቅ ችሏል፡፡

የአማራ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን፣ በክልሉ ምዕራባዊ አካባቢዎች ሁከት መከሰቱን ተናግረዋል፡፡ በአንዳንድ ፀረ ሰላም ኃይሎች የተነዛ መረጃ ሕዝቡን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ መምራቱንና በተፈጠረው ሁከትም በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ እየተከሰተ ያለው ግጭት እያሳሰበው መምጣቱን ጠቁሞ፣ ሁሉም ወገኖች ከማንኛውም ግጭት እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡

የኮሚሽኑ ዋና ሊቀመንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ ዓርብ ነሐሴ 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ ‹‹በአገሪቱ የማኅበራዊ ፖለቲካው የሰው ሕይወት ማጥፋት፣ በንብረቶች ላይ ውድመት ማስከተል፣ እንዲሁም የቴሌኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት እስከማቋረጥ ደረጃ መድረሱ አሳሳቢ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ሊቀመንበሯ አክለው ሁሉም ወገኖች ወደ ሰላማዊ ሁኔታ በማመዘን ለሕግ መከበር እንዲተጉ፣ ሰላማዊ ሠልፍ የማድረግ መብትና የዴሞክራሲ ባህልና መርሆችን እንዲያከብሩ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

በአዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ እስረኞች ህይወት አለፈ

(አዲስ ሚዲያ)ዛሬ ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት ቃጠሎ ከ25 ያላነሱ እስረኞች መሞታቸው ተጠቆመ፡፡ በጥበቃ ላይ የነበሩ ወታደሮችም ከእሳቱ ለማለጥ የሞከሩ እስረኞች ላይ ሲተኩሱ እንደነበር ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ከቃጠሎው በፊት በነበረው ተኩስ ምን ያህል እስረኞች ላይ ጉዳት እንደደረሰ እስካሁን ማረጋገጥ ባይቻልም፤ በነጋታው ጠዋት በነበረው የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ ሰዎች መሞታቸውን ከቅዱስ ጳውሎስ፣ ሜክሲኮ በሚገኘው ፖሊስ ፣ ጥሩነሽ ቤጂንግ እና የካቲት 12 ሆስፒታል ምንጮች ለማወቅ ተችሏል፡፡ በቃጠሎው ጉዳት የደረሰባቸውና በህይወት የተረፉትም አብዛኞቹ ፖሊስ ሆስፒታልና የካቲት 12 ሆስፒታል በጥበቃ ስር ሆነው ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡

Addis Ababa Akaki Kilinto Prison

በወህኒ ቤቱ ታስረው ከሚገኙት መካከል ስመጥር እና ህዝባዊ ተቀባይነት ያላቸው በርካታ የፖለቲካ እስረኞች ያሉበት ሲሆን በተለይም፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ፖለቲከኞች፣ የመብት አራማጆች እና ጋዜጠኞች እንደሚገኙበት ይታወቃል፡፡

በያዝነው 2008 ዓ.ም. ብቻ ከአዲስ አበባ አቃቂ ከሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በተጨማሪ በርካታ የፖለቲካ እስረኞች የሚገኙባቸው ጎንደር፣ አምቦና ደብረ ታቦር ወህኒ ቤት በተመሳሳይ መልኩ የእሳት አደጋ ሰለባ መሆናቸው አይዘነጋም፡፡ በነበሩ አደጋዎች መንስኤ እና ጉዳትን በተመለከተ የሚመለከተው የመንግሥት አካልም ከመግለፅ መቆጠቡ ይታወቃል፡፡

በተለይ የአቃቂ ቂሊንጦውን እሳት ቃጠሎ ተከትሎ በርካታ የታሳሪ ቤተሰቦች፣ ወዳጆች እና ደጋፊዎች ስጋት እንዳደረባቸው በተለያየ መድረክ ከመግለፅ በተጨማሪ በአዲስ አበባና አጎራባች አካባቢ ያሉ ሰዎች የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለማጣራት ሙከራ ቢያደርጉም በወህኒ ቤቱ አስተዳደር እንዳልተፈቀደ ተረጋግጧል፡፡ በወህኒ ቤቱ የታሰሩ ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ ከተለያዩ የክልል ከተሞች የመጡ ሰዎችም ወደ እስር ቤቱ ግቢም ሆነ ከግቢ ውጭ በቅርብ ርቀት እንዳይጠጉ በመከልከላቸው ወደየመጡበት መመለሳቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

በአደጋው የደረሰውን ጉዳትና ምክንያት በተመለከተ የወህኒ ቤቱ አስተዳደርም ሆነ መንግሥት እስካሁን የሰጡት መረጃ የለም፡፡ ይሁን እንጂ የተለያዩ ሰዎች አደጋው በመንግሥት ሆን ተብሎ የተቀነባበረና የፖለቲካ እስረኞችን ለመጉዳት የታሰበ የገዥው ስርዓት የተለመደ ስልት እንደሆነ የሚገልፁ ቢኖሩም፤ ስለ አደጋውና አጠቃላይ መረጃ ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት ለማወቅ አልተቻለም፡፡

የሪዮ ኦሎምፒክ እና የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና

ብስራት ወልደሚካኤል

ኢትዮጵያ ከሐምሌ 29 እስከ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በተካሄደው የ2016ቱ የብራዚሉ የበጋ ሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ 35 ስፖርተኞችን በ3 ዘርፍ በማሳተፍ 8 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም ተወዳዳሪዎች 44ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች፡፡ በበርካታ ዓለም አቀፍና የኦሎምፒክ ውድድሮች ኢትዮጵያ በምታገኛቸው ድሎች ትበልጣት የነበረችውና በአፍሪካ የቅርብ ተቀናቃኟ ኬንያ በበኩሏ 13 ሜዳሊያ በማግኘት 15ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች፡፡

ኢትዮጵያ ለ13ኛ ጊዜ የበጋ በሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር የተሳተፈችው በሶስት የውድድር ዘርፍ በተለይም በአትሌቲክስ ሩጫ፣ ዋና እና ብስክሌት ውድድር ሲሆን፤ ሜዳሊያ ያገኘችው በሩጫው የአትሌትክስ ዘርፍ ብቻ ነው፡፡ በዚህም 1 ወርቅ፣ 2 ብር እና 5 ነሐስ ያገኘች ሲሆን በአጠቃላይ 8 ሜዳሊያ አግኝታ ተመልሳለች፡፡ ባለፈው የለንደኑ 2012ቱ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ በ2 ስፖርት ዘርፍ 35 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 3 ወርቅ፣ 2 ብር እና 2 ነሐስ በአጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት በዓለም 23ኛ ደረጃን በመያዝ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በቤጂንጉ የ2008 ኦሎምፒክ በ1 ስፖርት ዘርፍ 27 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 4 ወርቅ፣ 1 ብር እና 2 ነሐስ አጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት 18ኛ ደረጃን ይዛ ነበር ያጠናቀቀችው፡፡ ይህም የኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ውድድር፣ ተሳትፎ፣ ብቃት እና ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እጅግ እየቀነስ መሄዱን ቢያሳይም፤ በተለይ በአትሌቲክስና በሌሎች ፌዴሬሽኞች እንዲሁም በኦሎምፒክ ኮሚቴና በስፖርት ፌዴሬሽን በኩል ከመገናኛ ብዙኃኝ ፍጆታ ባለፈ ለስፖርቱ መሻሻል ትኩረት እንዳልተሰጠው ያሳያል፡፡

ኬንያ በ2012 የለንደኑ ኦሎምፒክ በ4 ስፖርት ዘርፍ 47 ተወዳዳሪዎችን አሳትፋ 2 ወርቅ፣ 4 ብር እና 6 ነሐስ በአጠቃላይ 12 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም 28ኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በ2008ቱ የቤጂንግ ኦሎምፒክ በ5 ስፖርት ዘርፍ 48 ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ 6 ወርቅ፣ 4 ብር እና 4 ነሐስ በአጠቃላይ 14 ሜዳሊያ 13ኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋይታወሳል፡፡ በርግጥ አብዛኞች የኢትዮጵያ ድሎች በአትሌቶች የግል ጥረት እንጂ በፌዴሬሽነች ስራ ጥረት እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ቅሬታን መፍጠሩ የሚታወቅ ሲሆን፤ በሪዮ ኦሎምፒክም በተለይ በስመ ጥር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሳይቀር ባልተለመደ መልኩ ከፍተኛ ተቃውሞና ቅሬታ መሰማቱ ይታወሳል፡፡

ኢትዮጵያ በ3 የውድድር መስክ በአጠቃላይ 38 ተወዳዳሪዎችን ለኦሎምፒክ ውድድሩ ብታስመዘግብም፤ እስካሁን ለምን እንደሆነ በይፋ የታወቀ ነገር ባይኖርም ውድድሩ ላይ ለመሳተፍ የጠጓዙት ግን 35 ተወዳዳሪዎች ብቻ ነበሩ፡፡ ተወዳዳሪዎችን አስቀርቶ በምትካቸው ከስፖርቱ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን ልዑካን ይዞ መሄድ እና ስፖርቱን በፖለቲካዊ ዝምድና እና ማዕቀፍ ውስጥ መውደቁ አዲስ ባይሆንም፤ የሪዮ ኦሎምፒክ በሀገር ቤት የተገደበውን ፖለቲካዊ ፈር የለቀቀ ሙስና ለአደባባይ የበቃበት ክስተት አሳዛኝ ትዝታን አስፍሮ አልፏል፡፡ ይህ ክስተት ምንም እንኳ በሪዮ ኦሎምፒክ አዲስ ባይሆንም ከምን ጊዜውም ይበልጥ በተለይ ገዥውን ስርዓት በዓለም አደባባይ ያጋለጠ ነበር፡፡

የሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር ውጤት ለኢትዮጵያ አስደሳች ባይሆንም፤ በዓለም የኦሎምፒክ መድረክ አሳዛኝ፣ አስደሳችና አሳፋሪ አዳዲስ ክስተቶች በኢትዮጵያውያን ተወዳዳሪዎች ለዓለም አደባባይ በቅቷል፡፡ በተለይ ስፖርታዊ ቅርፅም ሆነ ብቃት የሌለው ሮቤል ኪሮስ፣ አባቱ የውሃ ዋና ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት በመሆናቸው፣ የኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነማርያምና የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ ወ/ሮ ዳግማዊት ግርማይ አማካኝነት ብቃት ያላቸውን ተወዳዳሪዎችና የዋና አሰልጣኑ አበበ ቢቂላን ሀገር ቤት ጥለው ባላቸው የስጋና ፖለቲካዊ ዝምድና ብቻ በዓለም መድረክ ሀገርን ወክሎ እንዲወዳደር በማድረግ ሀገሪቱንም ልጁንም የዓለም መሳቂያ ማድረግ ችለዋል፡፡ በአትሌቲክ ፌሬሽንም ተመሳሳይ ቅሬታ ያለ ሲሆን፤ በተለይ የማራቶን አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ በጀት የለንም በሚል ከሪዮ ኦሎምፒክ እንዲቀሩ ተደርጉ፤ ከስፖርቱ ጋ ምንም ግንኙነት የሌላቸው እንደነ ሚሚ ስብሃቱ ያሉ የስርዓቱ ደጋፊ ሰዎች በኦሎምፒክ ኮሚቴ ወጪ እንዲጓዙ መደረጉም ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ አትሌቶቹ በውድድሩ ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ ለማገዝ በራሱ ሙሉ ወጪ ብራዚል ሪዮ ኦሎምፒክ እንደሄደ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተለይ ሮቤል ኪሮስን የተለያዩ የስፖርት ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንም ስፖርታዊ ብቃትና ቅርፅ አልባ መሆኑን በመታዘብ ሮቤል ዓሳ ነባሪው የሚል ስም በመስጠት ግርምታቸውን ለዓለም ህዝብ አሰራጭተው ነበር፡፡ በተለይ በሀገር ቤት በዋና ውድድር ለኦሎምፒክ ማጣሪያ በጥሩ ብቃትና ተክለ ቁመና አንደኛ ሆኖ ያለፈው የአዲስ አበባው አብዱልመሊክ በዋና ፌዴሬሽኑ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው አማካኝነት ያለምንም ምክንያት በሪዮ ኦሎምፒክ እንዳይሳተፍ ሲደረግ፤ በምትኩ ብቃትና ቅርፅ አልባው ሮቤል ኪሮስ፤ በአባቱና በኦሎምፒክ ኮሜቴው አማካኝነት እንዲሄድ መደረጉ እጅግ አሳዛኝና አሳፋሪ ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

ወደ ኦሎምፒኩ ውድድር መሄድ ያለበት ተወዳዳሪ እንዲቀር ከመደረጉ በተጨማሪ የውሃ ዋና አሰልጣኙ ዋናተኞች እንዲያሰለጥኑ በሪዮ ኦሎምፒክም ዋናተኞች ይዘው በዛውም ልምድ ቀስመው ለቀጣይ ዓለም አቀፍ በቃት ያላቸው ተወዳዳሪዎችን ማፍራት እንዲችሉ በሚል አሰልጣን አበበ ቢቂላ በማስታወቂያ በተደረገ ውድድ አልፈው ከሚሰሩበት ጋምቤላ ተጠርተው፣ የሪዮ ኦሎምፒክ ግብዣ ቢመጣላቸውም፤ የውሃ ዋና ፌሬሽን ፕሬዘዳንት በሆኑት የሮቤል አባት አቶ ኪሮስ ሃብቴ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነ ማርያም አማካኝነት አዲስ አበባ እንዲቀሩ ተደርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ያለ ብቃት ኦሎምፒክ ላይ እንዲሳተፍ የተደረገው ሮቤል ኪሮስ አሰልጣን አበበ ቢቂላ የኦሎምፒክ ጉዞውን እንዲሰርዝና አዲስ አበባ እንዲቀር የ10 ሺህ ብር ቼክ ጉቦ መስጠቱን፣ አሰልጣኙም ጉዳዩን ለዋና ፌሬሽን፣ ለኦሎምፒክ ኮሜቴ፣ ለስፖርት ኮሚሽን እና ለወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር ድረስ ቢያሳውቁም ምላሽ ሳያገኙ መቅረታቸው ሌላ ጥያቄን የሚያስነሳ ጉዳይ ነው፡፡

በውድድሩ በሮቤ፣ በአባቱ አቶ ኪሮስና በኦሎምፒክ ፖለቲካው ና ስጋዊ ዝምድና ምክንያት ሀፍረት ውስጥ የወደቀችው ሀገር፤ በአልማዝ አያና የሴቶች 10 ሺህ ሜትር ውድድር በአዲስ ክብረወሰን አንደኛ ሆና የወርቅ ሜዳሊያ ማምጣቷ ብዙዎችን አስደስቷል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አትሌቷ በ5 ሺህ ሜትርም ተወዳድሯ ለሀገሯ የነሐስ ሜዳሊያንም በማምጣት ከማስደሰቷ በተጨማሪ ሁለት ወርቅ ባለማምጣቴ ህዝቡን ይቅርታ እጠይቃለሁ ያለችው ንግግር ይበልጥ የብዙዎችን ልብ ሰብሯል፡፡

አትሌት አልማዝ አያና ብቃት ብቻ ሳይሆን ትህትና እና ብሔራዊ ፍቅርን አንድ ላይ አንግባ በግሏ በአንድ የኦሎምፒክ ውድድር ብቻዋን ሁለት ሜዳሊያ ማምጣቷ ከኢትዮጵያውያን አልፎ ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብም ከፍተኛ አድናቆትና ክብርንም አጎናፅፏታል፡፡ በርግጥ በአንድ ኦሎምፒክ ሁለት ሜዳሊያ ስታመጣ ለኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ባትሆንም፤የሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያውያን በብዙ የሀዘን እና የመከፋት እንዲሁም በውጤት ላይ ስጋት ውስጥ በነበሩበት ወቅት መሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡

ሌላው በኢትዮጵያዊው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ አማካኝነት ከስፖርቱ በተጨማሪ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንን ትኩረት የሳበነ፣ የተከፉና የተገፉ ኢትዮጵያውያንን በሁለት ነገሮች ያስደሰተ፤ ግን ደግሞ ለኢትዮጵያ እንዲሁም ለአፍሪካ ታሪክ አዲስ የሆነ፤ በኦሎምፒክ ታሪክ ደግሞ ሁለተኛ የሆነ አሳዛኝ ክስተት በሪዮ ኦሎምፒክ አደባባይ ታይቷል፡፡ አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ የኦሎምፒኩ መዝጊያ በሆነው በወንዶች ማራቶን ውድድር ሁለተኛ ሆኖ በማሸነፍ ለሀገሩ የብር ሜዳሊያ ቢያስገኝም፤ በሀገር ቤት መንግሥት በዜጎች ላይ እያደረሰ ያለውን ግድያ፣ እስር፣ ስቃይና እንግልት በመቃወም ለዓለም አደባባይ አሳይቷል፡፡ ተበድለናል የሚለውን ገላጭ ምልክቱን በፕሬስ መግለጫ እና በሽልማት ስነ ስርዓቱም ላይ ደግሞታል፡፡

የአትሌት ፈይሳ ያልተጠበቀው የተቃውሞ ክስተት ገዥውን ስርዓት ሀፍረት ውስጥ ቢከተውም፣ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውንን በተለይም በገዥው ስርዓት ግፍና በደል የተፈፀመባቸውን እንዲሁም ለዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብት የቆሙትን በሙሉ አስደስቷል፡፡ በመጨረሻም አትሌቱ ውድድሩን ሁለተኛ ሆኖ በሚያጠናቅቅበት ወቅት እጁን በመስቀለኛ አጣምሮ በተለይም ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ተቃውሞ በኋላም የኦሮሞ ተቃውሞ አሁን ደግሞ በአማራ ተቃውሞም ታስረናል፣ ተጨቁነናል፣ ተበድለናል፣ ነፃነት እንፈልጋለን የሚል መልዕክት ያለውን ምልክት እያሳየ ውድድሩ ሲያሸንፍ ታይቷል፡፡ ድርጊቱ ባለስልጣናቱን እና የስርዓቱን ደጋፊዎች እጅግ አስደንግጧል፡፡

አትሌት ፈይሳም በኦሎምፒኩ መድረክ የተገኙ የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ለምን ያንን ምልክት እንደተጠቀመ ሲጠየቅ፤ ሀገር ቤት በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ በርካቶችን እየገደለ፣ እያሰረ ያለውን ድርጊት መቃወሙን ለመግለፅ እንደሆነ፣ ያቀረበውን ተቃውሞ ተከትሎ ሀገር ቤት ቢመለስ መንግሥት እንደሚገድለው፣ ምናልባት ባይገድለው እንኳ እንደሚያስረው አሊያም ከሀገር እንዳይወጣ ሊያደርገው እንደሚችል ስለሚሰጋ ወደ ሀገር ቤት እንደማይመለስ በማስታወቅ ለጊዜው ብራዚል ቀርቷል፡፡ ሌሎች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እና የልዑካን ቡድን አባላቱ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸው ታውቋል፡፡

በውጭ የሚገኙ የተለያዩ የኢትዮጵያውያን መገናኛ ብዙኃንም ቃለመጠይቅ ያደረጉለት ሲሆን፤ አትሌቱም የቅርብ ጓደኞቹና አብረውት የተማሩ ሳይቀሩ በባሌ፣ በአርሲ፣ እንዲሁም በተለያየ የኦሮሚያና አማራ ክልል ሰዎች እየተገደሉ እና እየታሰሩ መሆኑን በመግለፅ፤ ድርጊቱንም በመቃወም ምልክቱን እንዳሳየና ህዝቡም በአንድነት ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት እምነቱን ሲገልፅ ተሰምቷል፡፡ በተለይም ህዝቡ በዘር ከመከፋፈል ይልቅ ሁሉም ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት በአፅንዖት ሲናገር ተሰምቷል፡፡

በተለይ የመንግሥት ባለስልጣናት እና ደጋፊዎች የአትሌት ፈይሳ የኦሎምፒክ ማራቶን ድል የብር ሜዳሊያ እንዲሰረዝ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ላይ ጫና ለማድረግ ቢሞክሩም፤ ዓለም አቀፉ የኦሎምፒክ በበኩሉ የአትሌቱን ሜዳሊያ ሊነጥቅም ሆነ ምንም ዓይነት ርምጃ እንደማይወስድ ይፋ አድርጓል፡፡ በመጨረሻም የኢትዮጵያ መንግሥት አትሌቱ ወደ ሀገሩ መመለስ እንደሚችል እና ላሳየው ተቃውሞ ምምልክት በማሳየቱ ምንም እንደማይደርስበት ቢያሳውቅም፤ አትሌቱ ግን ወደ ሀገር ቤት መመለስ ለደህንነቱ አደጋ እንዳለው በመግለፅ ለጊዜ ብራዚል ሪዮ ዲ ጄኔሪዮ መቅረቱ ተረጋግጧል፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ የኢትዮጵያ ውጤት:

ውጤት የተወዳዳሪ ስም        የውድድር ዓይነት እና ርቀት      የተገኘው ሜዳሊያ
1ኛ. አልማዝ አያና                 በሴቶች 10,000 ሜትር           ወርቅ
2ኛ. ገንዘቤ ዲባባ                  በሴቶች 1,500 ሜትር               ብር
2ኛ. ፈይሳ ሌሊሳ                    በወንዶች ማራቶን                     ብር
3ኛ. ጥሩነሽ ዲባባ                   በሴቶች 10,000 ሜትር           ነሐስ
3ኛ. ታምራት ቶላ                   በወንዶች 10,000 ሜትር          ነሐስ
3ኛ. ማሬ ዲባባ                      በሴቶች ማራቶን                       ነሐስ
3ኛ. አልማዝ አያና                  በሴቶች 5,000 ሜትር               ነሐስ
3ኛ. ሐጎስ ገብረህይወት            በወንዶች 5,000 ሜትር            ነሐስ
አጠቃላይ ድምር                     8    ሜዳሊያ

በተለይ በኦሎምፒክ ውድድር ዘርፍ ኢትዮጵያ ካሏት በርካታ የወድድር መስክ ዕድሎች ውስጥ አብዛኛውን ለምን መጠቀም እንደማትፈልግ እስካሁን ግልፅ ባይሆንም፤ በውጤትም ሆነ በውድድር ዘርፍ እንዲሁም ውጤት ማነስ ብዙ ጥያቄ የሚያስነሱ ጉዳዮች አሉ፡፡ ይሁን እንጂ ስፖርቱ አጠቃላይ በፖለቲካ መዋቅር የተሳሰረ በመሆኑ እና በብቃት ሳይሆን በፖለቲካ ሹመት ከየክልሉ በሚመጡ ሹመኞች እና ለፖለቲካ ስርዓቱ ታማኝ የተባሉ ብቻ ከፌዴሬሽን፣ ኦሎምፒክ ኮሜቴ እና ስፖርት ኮሚሽን ስለሚሞሉ ስርዓቱ እስካለ ስፖርቱ ላይ የተለየ አዎንታዊ ለውጥ ሊመጣ እንደማይችል እሙን ነው፡፡ ምክንያቱም ከወረዳ እስከ ፌደራል ድረስ ባሉ የስፖርት ፌዴሬሽን እና ስፖርት ኮሚሽን የሚመለከታቸው ሰዎች ባላቸው የትምህርት ዝግጅት፣ ዕውቀት፣ ብቃት፣ ልምድና ተነሳሽነት ኃላፊነት የሚቀመጡ ሳይሆን ባላቸው የፖለቲካ ወገንተኝነት ብቻ የሚሾሙ አንዳንዶቹ ስለ ስፖርት ስራና አስፈላጊነት ምን እንደሆነ እንኳ የማያውቁ የፖለቲካ ሹመኞች የኃላፊነት ቦታውን ይዘው እንዳሉ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡

ብቃቱ ያላቸው የስፖርት አመራር ባለሙያዎች ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችም ነፃ የወድድር ተሳትፎ ሊያገኙ የሚችሉባቸው ዕድሎችም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየመነመኑ መጥተዋል፡፡ ስለዚህ ሀገሪቱ ኦሎምፒክን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዘርፎች ውጤታማ እንድትሆን በአጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ካልመጣ አሁን ባለው አሰራር የሚሾሙ ሰዎች ቢቀያየሩ እንኳ የተለየ ውጤት መጠበቅ አስቸጋሪ ነው፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ አጠቃላይ ውጤት አሜሪካ 121 ሚዳሊያ (46 ወርቅ፣ 37 ብር እና 38 ነሐስ)፣ እንግሊዝ 67 ሜዳሊያ (27 ወርቅ፣ 23 ብር እና 17 ነሐስ)፣ ቻይና 70 ሜዳሊያ (26 ወርቅ፣ 18 ብር፣ 26 ነሐስ)፣ ራሽያ 56 ሜዳሊያ (19 ወርቅ፣ 18 ብር እና 19 ነሐስ) እንዲሁም ጀርመን 42 ሜዳሊያ (17 ወርቅ፣ 10 ብር እና 15 ነሐስ) በማግኘት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል፡፡

የበጋው የሪዮ ኦሎምፒክ 207 የዓለም ሀገሮች የተውጣጡ 11,303 ተወዳዳሪዎች የተሳተፉበት ዓለም አቀፍ ዝግጅት ባለፈው እሁድ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በመዝጊያው የማራቶን ውድድር በሰላም ተጠናቋል፡፡ በቀጣይም በ2018 የክረምት ኦሎምፒክ በደቡብ ኮሪያዋ ፓዮንቻን የሚካሄድ ሲሆን፤ የ2020ው የበጋው ኦሎምፒክ ውድድር ደግሞ በጃፓኗ መዲና ቶክዮ እንደሚዘጋጅ ይጠበቃል፡፡

በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል፤ በኦሮሚያ ኢኮኖሚ ተኮር ተቃውሞ እንደሚጀመር ይፋ ተደረገ

ብስራት ወልደሚካኤል

(አዲስ ሚዲያ)የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ አድርጎ በጎንደር ፋሲል ከተማ የተጀመረው ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የተለያዩ የሰሜን እና ደቡብ ጎንደር ወረዳና ከተሞችን ጨምሮ ወደ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም እንዲሁም ወደ ሰሜን ወሎ መቄት እና ሸዋ ሮቢት መስፋፋቱን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡

በተለይ ነሐሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ጎጃም ፍኖተ ሰላም ከተማ፣ ነሐሴ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ቡሬ ወምበራ ወረዳ ቡሬ ከተማ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር በተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ተቃውሞዎች እና የመንግሥት የኃይል ርምጃዎችም የቀጠሉ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡

በጎንደር፣ ባህርዳር እና ደብረማርቆስ ከተሞች ከቤት ያለመውጣት ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች የተደረጉ ሲሆን ከነሐሴ 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ በተመሳሳይ ምልኩ በደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር ከተማ ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ እንደሚደረግ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

በአማራ ክልል ባሉ ሰሞንኛ ተቃውሞች በተለይ በማክሰኝት፡በገደብዬ፡በእንፍራንዝ፣ በአብደራፊ፣ በአርማጭሆ፣ በፍኖተ ሰላም፡ቡሬ፡ ጅጋ እና ማንኩሳ በተባሉ ወረዳዎች ህዝባዊ ተቃውሞዎች የበረቱባቸው መሆኑን ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡ በነኚህ ስፍራዎች የነበሩ ተቃውሞች መካከልም የተወሰኑ በማኀበራዊ ሚዲያዎች ሲሰራጩ መዋላቸውን ለመታዘብ ተችሏል፡፡

በነበሩ የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞች ሁለት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት መገደላቸው የተጠቆሙ ሲሆን፤ በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች በነበሩ ተቃውሞች ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገምቷል፡፡

በኦሮሚያ ክልልም ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞች የቀጠሉ ሲሆን፤ በዚህም በምዕራብ ሐረርጌ መሰላ ወረዳ በሚገኙ ዋልተሲስ እና ጎሮ በተባሉ መንደሮች በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ አራት ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ መገደላቸው ታውቋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በሀገሪቱ ያለውን የመንግሥትን ግድያ፣ እስርና እና አፋና በመቃወማቸው በአዲስ አበባ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች በተለይም እነ አቶ በቀለ ገርባ በሀገሪቱ ከነሐሴ 19-21 ቀን 2008 ዓ.ም. ብሔራዊ የሀዘን ቀን በሚል ታስቦ እንዲውል ያደረጉት ጥሪ ከወዲሁ በተለያዩ ደጋፊዎቻቸው ተግባራዊ መደረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡

የመንግሥት የኃይል ርምጅና ግፍ በመቃወም በሚደረግ ብሔራዊ የሀዘን ቀንም ፀጉር መላጨት፣ ጥቁር ልብስ መልበስ፣ ጥቁር ባንድራ(ጨርቅ) ማውለብለብ፣ ሻማ ማብራት፣ በተቃውሞ ትግሉ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቤተሰቦችን መጎብኘት እና ተሰብስቦ ህዝባዊ ውይይት በማካሄድ እንዲተገበር ጥሪ ማስተላለፋቸውን ተከትሎ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ባሉ ዜጎች ከወዲሁ ተግባራዊ መደሩ የሚያመለክቱ የተለያዩ ምስሎች በማኀበራዊ ሚዲያዎች ላይ መሰራጨታቸውን ማየት ተችሏል፡፡

በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ ካለው የፖለቲካና ማኀበራዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ከጳጉሜ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞችም እንደሚተገበሩ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች እና የመብት አራማጆች ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞው ምን ላይ እንደሚያተኩር በዝርዝር የተቀመጠ ነገር ባይኖርም፤ ወደፊት ይፋ እንደሚደረግ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡

በታቀደው መሰረት በኦሮሚያ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ መንግሥት በክፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪ እጥረትና አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ይጠበቃል፡፡ በተለይም መንግሥት ከክልሉ በከፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪና የሀገሪቱ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የሆኑት እንደ ቡና፣ የጫት፣ የአበባ፣ የቁም እንሰሳትና፣ የቆዳና ሌጦ እንዲሁም የምግብ ነክ የሆኑ የብግርና ምርቶች እንዲሁም ወርቅና የመሳሰሉ የማዕድን ሃብቶች ከክልሉ እንዳይወጡና ወደ ማዕከላዊም ሆነ የክልሉ ገበያ ንግድ ላይ የማይውሉ ከሆነ ምን አልባትም በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ፈተና በመንግሥት ላይ ሊደርስ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡

የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ በቀጣይ ወደሌሎች ክልሎች በተለይም አማራ እና ደቡብ ክልል የሚዛመት ከሆነ ደግሞ የመንግሥት 90% የገቢ ምንጭ በማድረቅ ስርዓቱን ሙሉ ለሙሉ አደጋ ላይ እንደሚጥለው ይገመታል፡፡ በተለይ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ብቻ የሀገሪቱን 54% የሆነውን ህዝብ ቁጥር እንደሚሸፍኑ እና ከ65% የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪና የገቢ ምንጭም መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ከባለፈው ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ የተቀጣጠለው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መላው ኦሮሚያ ክልልን በማዳረስ፤ ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አማራ ክልል ተዛምቷል፡፡ በሁለቱም ክልሎች ዘገባው እስከተጠናቀረበት ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞዎቹ በተለያዩ ወረዳዎችና ከተሞች ቀጥሏል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በሁለቱም ክልሎች ባሉ የተለያዩ ቦታዎች መደበኛ የመንግሥት ስራን ጨምሮ የተለያዩ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋቶች እየታዩ ነው፡፡

አስረኛ ወሩን ባስቀጠረው ህዝባዊ ተቃውሞ በሁለቱም ክልሎች ከ650 በላይ ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ ሲገደሉ፣ ከ 1,250 ያላነሱ ዜጎች ቆስለው በግምት ከ35,000 በላይ ሰዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉ እና የቆሰሉ ሰዎች በተለያየ ጊዜ ስማቸውና ምስላቸው በሰፊው በማኀበራዊ ሚዲያ እየተገለፀ ይገኛል፡፡ በሁለቱም የኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የወጣው ህዝብ አንዱ ለሌላው በተለያዩ ጊዜና ቦታ ያሳዩት የርስ በርስ አጋርነት፤ መንግሥትን ከፍተኛ ድንጋጤ ላይ እንደጣለው ባለስልጣናቱ በስራቸው ባሉ መገናኛ ብዙኃን ሲናገሩ የተደመጡ ሲሆን፤ በዚህም ስጋት እንዳደረባቸው ባለስልጣናቱና ደጋፊዎቻቸው በይፋ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎችና ከሚሰነዝሯቸው አስተያየቶች መረዳት ተችሏል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ፤የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ”የጋራ ልማት የተቀናጀ ማስተር ፕላን” በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ገበሬዎች የሚያፈናቅልና ለጎዳና ህይወት የሚዳርግ ነው በሚል ቀደም ሲል የነበረውን ተቃው ከዓመት በኋላ በማገርሸት በምዕራብ ሸዋ ጊንጪ ከተማ መጀመሩ ይታወቃል፡፡ በአማራ ክልል ደግሞ የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ ህዝባዊ ወኪሌ ኮሚቴ አባላት ላይ መንግሥት በሌሊት በመኖሪያቸው አካባቢ የፀጥታ ኃይሎችን በመላክ የኃይል ርምጃ መውሰዱን ተከትሎ በጎንደር ከተማ መጀመሩ ይታወሳል፡፡

መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ ስለደረሱ አጠቃላይ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶች በተመለከተ በመንግሥት ጉዳዩን ለመሸፋፈን ከመሞከር በዘለለ ትክክለኛውን ቁጥርና የጉዳት መጠለን ለመናገር አልደፈረም፡፡ ቀደም ሲል ሀገር በቀል በሆነው የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ) እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች በሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች (HRW) አማካኝነት በተወሰኑ ወረዳዎችና አካባቢዎች የተደረጉ ምርመራዎች ይፋ ከመደረጋቸው በስተቀር አጠቃላይ በደረሱ የሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጉዳቶች የተደረገ ምርመራም ሆነ ሪፖርት የለም፡፡ ይህን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ምት ኮሚሽን ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ እንዲደረግ በይፋ ጥያቄ ቢያቀርብም በስልጣን ላይ ያለው መንግሥት በበኩሉ የመንግሥታቱን ድርጅት ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ምላሽ መስጠቱ ይታወሳል፡፡