Tag Archives: Ethiopian Justice

የእነ ኦሞት አግዋ ላይ ዛሬም የአቃቤ ህግ ምስክር ሳይሰማ ተቀጠረ

ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡

Omot Agua

አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡

በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡

ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡

የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP

በእነ በቀለ ገርባ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላለፈ

*ወህኒ ቤት ለአቶ በቀለ ገርባ የታዘዘውን መድሃኒት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል

Bekele Gerba

በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኙት እነ በቀለ ገርባ (22 ሰዎች) የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሰባቸው መሆኑን ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤት ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ችሎቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት (ጉዳያቸውን ያይ የነበረው 19ኛ ወንጀል ችሎት እንደነበር ይታወሳል 19ኛ ችሎት ለሁለት ተከፍሎ አዲስ 4ተኛ ችሎት የሽብር ጉዳዮችን ማየት ጀምሯል) በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሰኔ ቀን 2008 ዓ.ም የሰጠውን መልስ ተመልክቶ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾች ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ ድብደባ እንደደረሰባቸው፣ ልብሶቻቸው እንደተወሰዱባቸው፣ በጨለማ ቤት ስለመታሰራቸው፣ በህክምና የታዘዘን መድሃኒት እንዳያገኙ ስለመደረጋቸው፣ ቤተ መጽሐፍት እንዳልተሟላላቸው፣ በቤተሰቦቻቸው እንዳይጎበኙ ገደብ እንደተጣለባቸው፣ ገንዘብ እንደተወሰደባቸው እና ሌሎች የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንደደረሱባቸው አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር በበኩሉ አቤቱታቸውን ‹‹የተቋሙን ስም ለማጥፋት›› የቀረበ ነው ሲል አጣጥሎ መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡

በዚህ ላይ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ውሳኔውን አሳውቋል፡፡ በዚህ መሰረት በሀኪም የታዘዘን መድሃኒት ማግኘት አልቻልንም በሚል ተከሳሾች ላቀረቡት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የእስር ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣሪዎቹ መድሃኒቱን እንዲያገኙ እንዲፈቅድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ድብደባ ደርሶብናል፣ ገንዘብም ተወስዶብናል በሚል ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ድርጊቱ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀል ስለሆነ አስፈላጊውን ማጣራት አድርገው ተከሳሾች በህግ ሊጠይቁ የሚገባቸው ስለሚሆን በዚህ የክስ መዝገብ ውሳኔ ሊሰጥበት አይችልም ብሏል፡፡
ተከሳሾች በጨለማ ክፍል መታሰራቸው ህግን ያልተከተለና የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በተመለከተ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ‹‹በማረሚያ ቤቱ በኩል ጨለማ ቤት የለም ተብሏል፤ ተከሳሾች ደግሞ ጨለማ ክፍል ታስረናል ብለዋል፡፡ ይህ ጉዳይ ማጣራትን የሚጠይቅ ስለሆነ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ጉዳዩን አጣርቶ ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም አስተያየቱን ይስጥበት›› የሚል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

የቤተ መጽሐፍትና የቴሌቪዥን አለመሟላትን እና የቤተሰብ ጥየቃ ሰዓትን በተመለከተ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ‹የማረሚያ ቤቱን አስተዳደራዊ አሰራር የሚመለከት ስለሆነ ውሳኔ አንሰጥበትም› በሚል አልፎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አቶ ደጀኔ ጣፋ በቤተሰብ መጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታችን እንጂ የአስተዳደር ጉዳይ ነው ተብሎ የሚታለፍ እንዳልነበር በመጥቀስ በውሳኔው ላይ ቅሬታቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡

ሌላ የተሰሙ አቤቱታዎች

ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ በተከሳሾች ለቀረቡት አቤቱታዎች ውሳኔ ቢያሳልፍም ዛሬም ሌሎች አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡ በዋናነት አቶ በቀለ ገርባ የታዘዘላቸውን መድሃኒት አለማግኘታቸውን በተመለከተ የቀረበ አቤቱታ ሲሆን፣ አቶ በቀለ መድሃኒት ከታዘዘላቸው ሁለት ወራት ቢቆጠርም መድሃኒቱን ማግኘት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ዋና ኦፊሰር የሆኑት ተሾመ ስዩም በጽሁፍና በቃል በሰጡት መልስ እንደተመለከተው ለአቶ በቀለ ገርባ በሀኪም የታዘዘላቸው መድሃኒት በአስተዳደሩ ባለሙያዎች በመንግስትና በከነማ መድሃኒት ቤቶች ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ‹‹መድሃኒቱ ተፈልጎ አለመገኘቱንና የሚችሉ ከሆነ በቤተሰብ በኩል እንዲሞክሩ ለአቶ በቀለ ነግሬያቸዋለሁ›› ብለዋል ዋና ኦፊሰሩ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው በኦፊሰሩ የተሰጠው መልስ ስህተት ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ፍርድ ቤት እንደምቀርብ አውቀው የተዘጋጁበት መልስ ነው፡፡ ለእኔ የነገሩኝ ነገር የለም›› ብለዋል አቶ በቀለ፡፡ ፍርድ ቤቱ ይህን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ በቤተሰብ በኩል መድሃኒቱ ተገዝቶ እንዲገባ እንዲፈቅድ ማሳሰቢያ በመስጠት አልፎታል፡፡

ሌላው አቶ በቀለን ከሚኖሩበት አዳማ ከተማ ተመላልሰው ከሚጠይቋቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ልጃቸው ቦንቱ በቀለ ባለተገለጸ ምክንያት አባቷን በእስር ቤት እንዳትጠይቅና ምግብ እንዳታደርስላቸው መከልከሏን የአቶ በቀለ ጠበቃ ለችሎት በመግለጽ፣ ልጃቸው አባቷን እንድትጠይቅና ስንቅ እንድታቀብላቸው እንዲፈቀድላት ችሎቱን ጠይቀዋል፡፡ ችሎቱ ዋና ኦፊሰር ተሾምን ስለጉዳዩ ቢጠይቅም፣ ኦፊሰሩ ‹የማውቀው ነገር የለም፣ ግን ለሚመለከታቸው አካላት አሳውቃለሁ› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡

በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ የስዋህሊኛ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በተደጋጋሚ አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ስዋህሊኛ አስተርጓሚ ኬንያ ኤምባሲ ጭምር ተፈልጎ ማግኘት እንዳልተቻለ ተገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሹ በመጠኑ እግሊዝኛ ቋንቋ ስለሚረዱ የእንግሊዝኛ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በጠበቃቸው በኩል አሳስበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የመቃወሚያ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

ምንጭ፡- EHRP

እነ በቀለ ገርባ ላቀረቡት የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ምላሽ ለመስጠት ዳግም ቀጠሮ ሰጠ

– አቶ ደጀኔ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መገናኘት እንዲችሉ ፍርድቤቱ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
– አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አቤት ብለዋል፡፡
– አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ሰለታመሙ ህክምና እንዲያገኙ ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
– ተከሳሾች ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀው፡ ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሏል፡፡

Bekele-June-27-court-150x150

ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ጉርሜሳ አያኖ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች አመራሮች(22 ተከሳሾች) ዛሬ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ችሎቱን ከሚመሩት ሶስት ዳኞች መካከል ዳኛ ታደለ ተገኝ ስልጠና ላይ በመሆናቸው የተከሳሾችን አቤቱታ እና የማረሚያ ቤቱን ምላሽ መርምረው ብይን መስራት እንዳልቻሉ ዳኛ ሳሙኤል ታደሰ ለተከሳሾች አስረደተዋል፡፡

ፍርድቤቱ ብይኑን ለመሰጠት ማክሰኞ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም ከሰዓት በኃላ ቀጥሯል፡፡
የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት አዲስ አበባ ድረስ መጥተው በጡረታ መታወቂያ ልጃቸውን ለማየት እንደተከለከሉ ያሰረዱት የተከሳሽ ጠበቃ ፍርድቤቱ መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀው ፍርድቤቱ በተለየ ሁናቴ የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት ስም ከነአባት በዝርዘር ጠይቆ ለማረሚያ ቤቱ ጉብኝት እንደፈቀድላቸው ትዕዛዝ እንደሚሰጥ ገልጿል፡፡

አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አመልክተዋል ፤በሌላ በኩል አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ታመው ህክምና ቢጠይቁ ከህመም ማስታገሻ ውጪ ምንም እርዳታ እንዳልተሰጣቸው እና ለከፍተኛ ህመም መጋለጣቸውን አስርድተዋል፡፡ ፍርድቤቱ ህክምናን በተመለከተ ተከሳሾቹ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ ትዕዛዝ ለማረሚያ ቤቱ ስጥቷል፡፡

በተያያዘ የተከሳሾችን አቤቱታ ሲሰማ የዋለው ችሎት ተከሳሾች ክስ ተመስርቶባቸው ከማዕከላዊ ፖሊስ ምርመራ ወደ ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተከሳሾች ብራቸውን ቆጥረው ለማረሚያ ቤቱ እንዳስረከቡ ምስክሮች አሉን ቢሉም ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሎ ለፍርድቤቱ ደብዳቤ ልኮ አስታውቋል፡፡

ምንጭ፡-የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እንቅስቃሴን የተመለከተ መረጃ ለኤርትራ መንግስት ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በእስራት ተቀጡ

በታሪክ አዱኛ

በኢትዮጵያ ድንበር ስለሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና ኤርትራውያን ስደተኞች እንቅስቃሴ ለኤርትራ መንግስት መረጃ ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በፅኑ እስራት ተቀጡ።

Ethiopian federal high court

ተከሳሾቹ 1ኛ ካሃሳ መስፍን፣ 2ኛ አብደላ ኢብራሂም፣ 3ኛ ልኡል መሃሪ፣ 4ኛ ፍስሃይ ተክለገብረስላሴ፣ 5ኛ ጎይቶም ይደጎ ተስፋይ፣ 6ኛ ጎበዘይ ገብረስላሴ፣ 7ኛ ገብረሚካኤል ገብረማርያም፣ 8ኛ ብርሃኔ ምረጽ ይልማ እና 9ኛ ትኩህ ንጉሴ ገብረ መድን ይባላሉ።

ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያሉ ተከሳሾች የኤርትራ ዜግነት ያላቸው ሲሆኑ ከ6ኛ እስከ 9ኛ ያሉ ተከሳሾች ደግሞ ኢትዮጵያውያን ናቸው።

ተከሳሾቹ ከጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም እስከ 2006 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ከኤርትራ መንግስት የመረጃ ሰራተኞች ጋር ሚስጥራዊ ግንኙነት በመፍጠር በኢትዮጵያ ድንበር የሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና የኤርትራ ስደተኞች እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ስለ ኢትዮጵያ ሚስጥራዊ መረጃዎችን ለኤርትራ መንግስት አቀብለዋል ይላል የአቃቤ ህግ ክስ።

በተጨማሪም 2ኛ ተከሳሽ በግንቦት ወር 2006 ዓ.ም አራት ኤፍዋን ቦምቦችን በአካባቢው ለሚገኙ ግለሰቦች ለመሸጥ ሲዘጋጅ በቁጥጥር ስር ውሏል።

በተመሳሳይ 8ኛ ተከሳሽም የመሳሪያ ጥይቶችን እና አምስት ቦምቦችን ሸሽጎ መያዙንም ክሱ ያስረዳል።

በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ የሃገሪቱን ሚስጥራዊ መረጃ በማቀበል እና ስለላ ወንጀል ክስ መስረቶባቸዋል።

ተከሳሾቹ ድርጊቱን ክደው የተከራከሩ ቢሆንም አቃቤ ህግ የብሄራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎት ኤጀንሲ የሰነድ ማስረጃና የሰው ምስክር አቅርቦ አሰምቷል።

የግራ ቀኙን ክርክር የተከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎትም ተከሳሾቹን ጥፋተኛ ብሏቸዋል።

ችሎቱ ከ7ኛ እና ከ8ኛ ተከሳሾች ውጪ ያሉትን ተከሳሾች በ3 አመት ከ4 ወር እስራት እንዲቀጡ ወስኗል።

7ኛ ተከሳሽ የደም ግፊት ህመምተኛ መሆኑን በማስረጃ በማቅረቡ አንድ ማቅለያ ተይዞለት በሶስት አመት ጽኑ እስራት ሲቀጣ፥ 8ኛ ተከሳሸ ደግሞ በአራት አመት ከስድስት ወር እስራትና በ500 ብር እንዲቀጣ ተወስኖበታል።

በተከሳሾቹ እጅ ላይ የተያዙ ቦምቦች ለመንግስት ገቢ እንዲሆኑ ፍርድ ቤቱ አዟል።

በአጠቃላይ ሁሉም ተከሳሾች ለአምስት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብታችው እንዲታገዱ ችሎቱ ወስኗል።
ምንጭ፡- ፋናቢሲ (የሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘገባ), http://www.fanabc.com/index.php/news/item/17450

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል

*ጌታቸው ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል

Getachew Shiferaw

ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የእምነት ክህደት ቃሉን ለፍርድ ቤት ሰጥቷል፡፡

አርብ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያ ውድቅ መሆኑን ተከትሎ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ በችሎቱ ተጠይቆ ‹‹የቀረበብኝን የወንጀል ድርጊት አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛም አይደለሁም›› ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡

መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሹ ቀደም ሲል ያቀረበው የክስ መቃወሚያን መርምሮ ብይን ለመስጠት ሲሆን፣ ጉዳዩን የሚያየው 14ኛ ወንጀል ችሎት የተከሳሹን መቃወሚያ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡ ችሎቱ የመቃወሚያ ብይኑን በንባብ ከማሰማት ይልቅ በጥቅሉ “የቀረበውን መቃወሚያ ውድቅ አድርገነዋል” ሲል ለተከሳሹ ገልጹዋል፡፡

”በአጭሩ የክስ አቀራረቡ ከተጠቀሰው የወንጀሉ ክፍል አለመጣጣምን በተመለከተ የቀረበው መቃወሚያ አልተቀበልነውም፤ ዝርዘሩን ማስረጃ ስንመዝን እናየዋለን፡፡ የቀረበው ክስ ግልጽ አይደለም የተባለውን በተመለከተም፣ ክሱን ስንመለከተው በተብራራ መልኩ የቀረበ መሆኑን ስለተገነዘብን ውድቅ አድርገነዋል” በማለት የመቃወሚያው ውድቅ መሆንን ችሎቱ በቃል ለተከሳሹ አስረድቷል፡፡

ችሎቱ ተከሳሹ የእምነት ክህደት ቃሉን ሲሰጥ ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ጥፋተኛም አይደለሁም ማለቱን ተከትሎ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህጉ በበኩሉ ከክስ ማመልከቻ ጋር ያያያዘው የሰነድ ማስረጃ ተመርምሮ ብይን እንዲሰጥለት አመልክቷል፡፡
ፍርድ ቤቱም የሰነድ ማስረጃውን መርምሮ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ ከሳሽ ያቀረበበት የሰው ማስረጃ እንደሌለ በችሎቱ ተገልጹዋል፡፡

ምንጭ፡- EHRP